ዘ-ሀበሻ በቴሌግራም ገጹ “ ሽብርተኛው ትህነግ የማረካቸውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት ሲያሰቃይና ግፍ ሲፈጽም የሚያሳይ ቪዲዮ ደርሶናል። ከደቂቃዎች በኋላ ‘በረብል’ አካውንታችን የምንለቀው ሲሆን የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና ቡድኑን የምታጋልጡ አካላት እንድትመለከቱት እንመክራለን። “የሚለውን የዜና ፍንጭ*
/newsflash/አይነት ነገር ስመለከት፤ ወዲያው የጥቅምት 24 ፣ 2013 ዓ.ም የሰሜን ዕዝ ክህደትና ጭፍጨፋ ፤ በአፋርና በአማራ ክልሎች የተፈጸሙ ሰቆቃዎችንና ግፎችን ሳስታውስ ሆዴ ይታወክና ይታመም ጀመር። ወደ መጸዳጃ ክፍል መሔድ አስፈለገኝ። ወዲያው ያቺ ክፉ ሌሊት ወደ አእምሮዬ ከች አለች ። በወገኔ መሐል ነኝ ብሎ ትጥቁን ፈትቶ በተኛበት በውድቅ ሌሊት ለማየት የሚዘገንን ፣ ለመስማት የሚሰቀጥጥ ጭፍጨፋ የተፈጸመባት ጽልመተ ሌሊት ጥርሷን አግጥጣና ጥፍሯን አሹላ መጣችብኝ ። ሴት የመከላከያና የፌደራል ፖሊስ አባላት ላይ ለዛው የሰው ልጅ በ21 ኛው መክዘ በገዛ ዜጋውና መከታው ላይ ይፈጽመዋል ተብሎ የማይታሰብ ዘግናኝ ግፍ ተፈጸመ ። ይሄ ከሀዲና አረመኔ የተወለደበትን መሀጸን በስለት ወጋ ፤ የጠባውን ጡት በሳንጃው ቆረጠ ። ሁለት ዓመታት ወደኋላ በሀሳብ ሄጀ ይሄን አስታውሸ ነው የዘ-ሐበሻ ኒውስፍላሽ ያውከኝ የያዘው ።
ሰሞኑን በማህበራዊ ሚዲያዎች በስፋት እየተዘዋወረ ብዙዎች በተቀባበሉት/viral/በሆነ በዚህ ቪዲዮ በጥላቻና በጭካኔ የታወሩ የሽብርተኛው ታጣቂዎች በሰደፍ እያዳፉና በዱላ እየከተከቱ ፤ ከምርኮኛ አያያዝ አለማቀፍ ሕግ ባፈነገጠና ፍጹም ኢሰብዓዊ በሆነ አግባብ እንደ ከብት ከሚነዷቸው የመከላከያ የደንብ ልብስ ከለበሱና ምርኮኛ ከሚመስሉ መካከል (ያው በእርግጥ የመከላከያ አባላት መሆናቸው በሚመለከተው አካል ስላልተረጋገጠ ነው የሚመስሉ ያልሁት፤) በሴቷ ላይ በተፈጸመ ድብደባ አፍንጫዋ ደምቶ ፣ አካሏ ተጎሳቁሎና ተዳክሞ የምትታይን ፤ ምን አልባትም ለበርካታ ቀናት በባዶ እግሯ በርሀብና በውሃ ጥም የተዳከመች ሴት ላይ የሚያዘንቡት ዱላና ጸያፍ ስድብ በእርግጥ እነዚህ አረመኔዎች ከሴት የተፈጠሩ ፣ እህት ያላቸው ፣ ሴት ያገቡና ሴት የወለዱ ናቸው !? ።
“የልጅ እናት ነኝ ፣”እያለች እንዲያ ስትማጸናቸው ቅንጣት ታህል ርህራሄ የማያሳዩት ምን ያህል በጭካኔና በጥላቻ ቢታወሩ ነው ፤ መልሱን ለማግኘት ገና ብዙ ስራ ይጠብቀናል ። እንግዲህ እነዚህ ግፈኞች ናቸው ሲማረኩ ተገደን ነው የሚሉን ፤ አፈግፍገው እንደ ሰላማዊ ሰው ማህበረሰቡ ውስጥ መልሰው የሚቀላቀሉት ። ይሄን ባሰብሁ ቁጥር ጦርነቱን በድል ከመቋጨት ወይም በድርድር ከመደምደም በላይ ገና ብዙ ስራ እንዳለብን ይሰማኛል ። በዚህ ጉዳይ አንድ ቀን በሌላ መጣጥፍ የምመለስበት ሆኖ ፤ በቪዲዮው የተመለከትኋት እህቴ ግን ለአገሬ ሉዓላዊነትና ቀጣይነት ፤ ለእኔ ነጻነት ዋጋ የከፈለች ወታደር ብቻ ሳትሆን ፤ የተፈጸመባት ግፍ በአገሬ ፣ በእናቴ ፣ በሚስቴ ፣ በእህቴና በሴት ልጄ ላይ የሆነ ነው ።
እዚህ በቅጡ ሊጤን የሚገባው ነገር ግፈኞች ሲፈጽሙት ያላፈሩበትን እኛ ሰለባዎች ልናፍርበትና ልንሸፋፍነው አይገባም ። የሩዋንዳውንና የደቡብ አፍሪካውን ጭፍጨፋዎችና ግፎችን የሚዘክሩ ሙዚየሞችን ከአህጉራችን የናዚን ግፎች ማስታወሻዎችን ከአውሮፓና ከአሜሪካ መመልከት በቂ ነው ። መደበኛው ሚዲያ ባላየና ባልሰማ ማለፉም ተገቢ አይደለም ። ፍርጥርጥ አርገን ልናወግዘውና ልንነጋገርበት ይገባል ። በዚህ ዘግናኝ ቪዲዮ ላይ ይሄን ያህል ካልሁ ፤ ነገርን ነገርን ያነሳዋልና በነካው ብዕሬ ከሚዘገንነውና ሞልቶ ከፈሰሰው የሽብርተኛው ትህነግ የጭካኔ ጥግ መለስ ብለን በስሱ እንቃኝ ።
የካቲት 11 ቀን ፣ 1967 ዓ ም በ11 ሰዎች በምዕራብ ትግራይ ቆላ በሽሬ አውራጃ ልዩ ስሙ ደደቢት በተባለ ስፍራ የተመሰረተው እና የቀዳማይ ወያኔ ቅርሻ የሆነው “ ተጋድሎ ሓርነት ህዝቢ ትግራይ “ / ተሓህት / ወደ አማርኛ ሲመለስ የትግራይ ሕዝብ አርነት ግንባር ፤ የዛሬው አሸባሪው ትህነግ ስንክሳር ሲገለጥ ደምቀው ከሚታዩት አሪዎስነት ፣ ክህደት ፣ ሴረኝነትና እስስታዊነት ይገኙበታል ። ስለከሀዲነቱ፣ ሴረኝነቱ ፣ መርህ አልባነቱ ስለሚገለጥበት እስስታዊነቱ በዚሁ ጋዜጣ በተደጋጋሚ ስለጻፍሁበት የዛሬው መጣጥፌ ትኩረት በአሪዎስነቱ ፣ በአረመኔነቱ ፣ በጨካኝነቱ ፣ በጭራቅነቱ/በቡልቡልነቱ/ላይ ነው ።
አሸባሪው ትህነግ ርህራሄና ሰብዓዊነት የሚባል ነገር ያልፈጠረበት ጨካኝ አረመኔ ነው ። የጭካኔው ጥግ የሰው ልጅ ይፈጽመዋል ተብሎ የማይታመን ነው ። በተለይ በአቦይ ስብሀትና በመለስ የሚዘወረው ቡድን የፖለቲካና የወታደራዊ ትርፍ እስካስገኘለት ድረስ ምንም ከማድረግ አይመለስም ። ይህ በላኤ ሰዕብነቱ ዛሬ ወይም ትላንት የተጀመረ ሳይሆን አብሮት ያደገና ጥርሱን የነቀለበት ነው ። የጋዜጠኛ አርዓያ ተስፋማርያም ፣ “ከሕወሓት ጓዳ”መጽሐፍ ይሄን ማንነቱን ፍንትው አርጎ ያሳያል ።
አሸባሪው ትህነግ ገና ከጅምሩ በአቋምና በአመለ ካከት የተለዩትን ፤ ለስልጣኔ ያሰጉኛል ያላቸውን እንደ ድመት እየበላ ያደገ ጨካኝ አረመኔ ነው ። እነ ገሠሠው አየለ/ስሁል/ ፣ ዮሐንስ ገብረመድህን/ዋልታ/ ፣ ዘርኡ ገሰሰ/አግአዚ/ እና ሌሎች በሴራ ገድሎ በመቃብራቸው የተረማመደ አሪዎስ ነው ። በተለይ በትግራይ ክልል ፊውዳል ብሎ የፈረጃቸውን ከ40ሺህ በላይ ትግራዋይን ደመ ከልብ አድርጎ ያስቀረ ጭራቅ ነው ። አምነውት ለድርድርና ለእርቅ የቀረቡትን በውድቅት ሌሊት በተኙበት የጨፈጨፈ አውሬ ነው ። በትግራይና በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ባቋቋማቸው ዘግናኝ ከምድር በታች እስር ቤቶች “ሀለዋ ወያኔ” ወይም “ባዶ ስድስት” ያለቁ ኢትዮጵያውያንን ብዛትማ ቤቱ ይቁጠረው ። ከ1971/72 አንስቶ በወልቃይት ፣ በጠገዴና በጸለምት አማሮች ላይ የተፈጸመ ግፍ ለመስማት ይሰቀጥጣል ፤ ለማየት ይዘገንናል ።
ማንነታችን የአባቶቻችን አገር ርዕስት ይከበር ባሉ በግፍ ተገድለዋል ። ተሰቃይተዋል ። በጅምላ ተግዘዋል ። ተሰደዋል ። ጭው ባለ በርሀ በተሰሩ የምድር ቤት እስር ቤቶች ወገን በወገኑ ላይ ይፈጽመዋል ተብሎ ለማሰብ በሚከብድ ህልቆ መሳፍርት የሌለው ግፍ ተፈጽሞባቸዋል። በቁማቸው ተቀብረው ከብት ተነድቶባቸዋል። እስከ አንገታቸው ተቀብረው ራሳቸው ላይ ጨው ተነስንሶ ከብት እንዲልሳቸው ተደርጓል። እነሱን ገለውና አስረው ሚስቶቻቸውን ልጅ በማስወለዶ ዘር ለማጽዳት ጥረዋል። በማንነቱ እንዲሸማቀቅ በገዛ አገሩ ሁለተኛ ዜጋ እንዲሆን ተደርጓል። ዜጎችን ኦነግ በሚል የፈጠራ ክስ ፈርጆ ለማሰር የደህንነት መዋቅሩን ተጠቅሞ በፒያሳው ትግራይ ሆቴል፣ በሚኒባስና ሕዝብ በሚሰበሰብበት አደባባይ ፈንጂ የሚያፈነዳና ንጹሐንን የሚፈጅ እፉኝት ነው።
የቀድሞ የሕወሓት ነባር ታጋይ አይተ ገብረመድህን አርአያ በአንድ ወቅት ከ” ኢትዮጲስ “ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ስለ ጌታቸው አሰፋ ተጠይቀው “…ጌታቸው ስለ ፈፀመው ግፍና ያጠፋው የንፁሀን ነፍስ ላይ በግልፅ ጥናት ቢደረግ ፤ …ከሂትለር ባለሟሎች ተርታ የሚሰለፍ ነው።በአንድ ወቅት ከፍየል ውሃ ሁለት ገበሬዎችን አፍኖ ወደ ሀዋላ ወያኔ አስገባቸዋለሁ ብሎ መንገድ ላይ ገሎ ጥሏቸው አስከሬናቸው በጅብ ተበልቶ የራስ ቅላቸው ወድቆ ተገኝቷል ፡፡
የጌታቸው አሰፋ ደስታ የሚመነጨው ከሰው ልጆች ስቃይና መከራ ነው ። በጭካኔያዊ ድርጊት የሚደሰት SADIST ነው ።ከቀድሞው የወያኔ የደህንነት ኃላፊ ጋር በመሆን ብዙ ሰላማዊ ሰዎችን የጨረሰ ወንጀለኛ ነው ። ከመነሻው አንስቶ እጁ በንፁሀን ደም የጨቀየ ነው ። የትግራይ መሪዎች በትግራይ ሕዝብ መካከል የበቀሉ አረሞች እንጅ ከትግራይ ሕዝብ አብራክ የወጡ አይደለም።አሸባራ ትህነግ ፀረ ኢትዮጵያዊ ብቻ ሳይሆን ፤ ፀረ ትግራይም ነው ፡፡… ይላሉ ። ዛሬ አሸባሪው ትህነግ ሸለቆ ለሸለቆ እየተሽሎከለከ የሚፈጽመው ግፍ አብሮት ያደገ እንጂ ዛሬ የተጀመረ አይደለም ። ስለጌታቸው አሰፋ አረመኔያዊ ማንነት የተገለጸው የአሸባሪው ትህነግ መገለጫ ነው ።
አሸባሪው ትህነግ አገዛዝ ላይ እያለም ሆነ በመማጸኛ ከተማው መቐሌ መሽጎ ያልጣሰው የሰብዓዊ መብት ጥሰት የለም ። ገልብጦ ገርፏል ። አካል አጉድሏል ። ዘር እንዳይተኩ አድርጓል ። ወንድ ልጅ ሳይቀር እንዲደፈር አድርጓል ። ጥፍር ነቅሏል ። በወንድ ልጅ ብልት የሁለትና የሶስት ሌትር የላስቲክ ውሀ አንጠልጥሏል ። በደረሰባቸው ስቃይ ብዙዎቹ ለአእምሮ ህመም ተዳርገዋል ። ሽባ ሆነዋል ። እግራቸው ተቆርጧል ። በማዕከላዊ ፣ በቃሊቲ ፣ በቅሊንጦ ፣ በሽዋ ሮቢትና በሌሎች “ማረሚያ” ቤቶችና ስውር ማሰቃያ ቦታዎች ህልቆ መሳፍርት የሌለው ግፍ ፈጽሟል ። አስፈጽሟል ።
በእስክንድር ነጋ ፣ በአንዷለም አራጌ ፣ በሀብታሙ አያሌው ፣ በከፍያለው ፣ በዳባ ገሬ ፣ በወልቃይት ሕዝብ ፣ በዋልድባ አባቶች እና በሙስሊም ወንድሞቻችን ለይ ለመስማት የሚሰቀጥጥና ለማየት የሚዘገንን ግፍ ፈጽሟል። ለሶስት ዓመታት በፊት”የፍትሕ ሰቆቃ”በሚል በኢቲቪና በሌሎች ቴሌቪዥኖች የተላለፈው ዘጋቢ ፊልም ፤ የጌታቸው ሽፈራው”የሰቆቃ ድምጾች”፤ የአንዳርጋቸው ጽጌ”የታፋኙ ማስታወሻ”፤ የአንዷለም አራጌ ፤ የሀብታሙ አያሌው ፤ ወዘተረፈ ግለ ማስታዎሻዎች ዛሬም ህያው እማኝ ናቸው ።
ከስቃዩ ሰለባዎች አንዱ የሆነው ዳባ ገሬ በዚሁ ዘጋቢ ፊልም ፤ በዜጎች ላይ ይፈፀም የነበረው ግፍ ወገን በወገኑ ላይ ይፈፅመዋል ተብሎ የማይታመንና ልጅ ሆነን ወላጆቻችን ያስፈራሩበት በነበረው ጭራቅ/ቡልቡል/የሚፈፅም ይመስለኝ ነበር ያለው ይሄን ያረጋግጣል። የትህነግ መራሹን ግፍ በ”የፍትሕ ሰቆቃ”የተመለከትሁ እለት ማንባቴን አስታውሳለሁ ። ለእራሴ እውን እነዚያ አረመኔዎች ፣ አውሬዎች ከሰው ዘር የተፈጠሩ ናቸው ? ብያለሁ ። መልሱ የስቃዩ ሰለባ ዳባ እንዳለው ጭራቆች ናቸው ። ሕገ መንግስቱን ለሽንት ቤት ተጠቀምበት እያሉ ይሄን ዘግናኝ ስቃይ በወገናቸው ለፈፀሙ አረመኔዎች ነው እንግዲህ እነ አንቶኒዎ ጉተሬዝ ፣ ሱዛን ራይስና አንቶኒ ብሊከን ጠበቃ ሆነው ብቅ ያሉት !? በዛ ዘጋቢ ፊልም የስቃዩ ሰለባ ሆነው የቀረቡ እህት ወንድሞቼን ባሰብሁ ቁጥር አለማቀፉ ማህበረሰብና ምዕራባውያን በሀሰተኛና ሆን ተብሎ በተዛባ መረጃ ዛሬም ከትህነግ ጭፍራና ርዝራዥ ጎን መቆማቸውን ስመለከት በእነሱ ቁስል ላይ እንጨት እየሰደዱ እንደሆነ ስለሚሰማኝ ህመማቸው ያመኛል ።
በሮማውያን ዘመን የነበሩ ገዥዎች ሰውን ከአንበሳ ፣ ከነብር ጋር እያታገሉ በሰው ልጅ ስቃይ ይዝናኑ እንደነበር ከታሪክ ድርሳናት አንብበን እንዳልተደነቅን ፤ በአገራችን አብዲሌ በሶማሊያ ክልል ጅግጅጋ በ” ጄል ኦጋዴን “ ! ዜጎች ከአንበሳ ፣ ከነብር ፣ ከጅብ ጋር ይታሰሩበት የነበረ ምን አልባት በአለማችን በ21ኛው ክ /ዘ የመጀመሪያም ፣ የመጨረሻም የሆነ ማሰቃያ አዘጋጅቶ ህልቁ መሳፍርት የሌለው ግፍ ይፈጸም የነበረው በአሸባሪው ትህነግ ቡራኬ መሆኑን ያስተዋለ በዜጎች ይፈጸም የነበረ ግፍ ተቋማዊ እንደነበር ያረጋግጣል ። ሆኖም ከሀዲውና እፉኝቱ አሸባሪው ትህነግ የጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም የሰሜን ዕዝ ጥቃት እና የጥቅምት 30ን የማይካድራን ፣ የጭናን ፣ የአጋምሳን ፣ የአንጾኪያ ገምዛን ፣ የደባርቅን ፣ የጋሊኮማን ፣ ወዘተረፈ ትውልድና ታሪክ ይቅር የማይለውን የክፍለ ዘመኑን ታላቅ ክህደትና ጭፍጨፋ ለመፈጸም ዝግጅቱንና ልምምዱን የጀመረው ከደደቢት ውልደቱ ከየካቲት 11 ቀን 1967 ዓ.ም አንስቶ ነው ። ለግማሽ ክፍለ ዘመን በዝግ የተዶለተበት የክህደት ደባ ። የጭካኔ ልምምድና ዝግጅት ውጤት ነው ።
እንደ መውጫ
አዎ አሸባሪው ሕወሓት ጭራቅ ፣ ቡልቡል ወይም ዙምቢ እንጂ በፈጣሪ አምሳል የተፈጠሩ ሰዎች ስብስብ አይደለም ። ዙምቢ ሲመለከቱት አስፈሪ ፤ ባህሪው ደግሞ ጨካኝ አረመኔ ነው ። በላዔ ሰብዕና ደም መጣጭ ነው ። የአሸባሪው ሕወሓት በገዛ ዜጎቹ ላይ ለ27 ዓመታት ይፈፅመው በነበረ ግፍና ስቃይ የተነሳ እንደ ዙምቢና ጭራቅ መፈራት ጀምሮ ነበር ።በገዛ እህት ወንድሞቹ ላይ የፈፀማቸው ለመስማት የሚሰቀጥጡ ፣ ለማየት የሚዘገንኑ ግፎችን መለስ ብለን ባሰብን ቁጥር በአምላክ አምሳል የተፈጠረ የሰዎች ስብስብ ያደረጋቸው ሳይሆን የሰውነትና የኢትዮጵያዊነት ባህሪ ባልነበረው ዙምቢ ቡድን የተፈጸሙ ነበሩ ። በገዛ ወገኑ ስቃይ ፣ ግፍ ፣ በደል ፣ ርሀብ ፣ እርዛት ፣ ቸነፈር፣ እልቂት ፣ ግጭት ፣ ወዘተረፈ እንጀራውን የሚያሰፋና የሚደሰት የአሸባሪው ትህነግ ዙምቢ ብቻ ነው ።
አንዱን ብሔር ከሌላው ብሔር ፤ አንዱን ሀይማኖት ከሌላው ሀይማኖት በማጋጨት የደም ምሱን የሚያገኝ ። ዛሬም ለዚህ የደም ምሱ ርዝራዡ ቀን ከሌት እዚህም እዚያም እየዛከረና እየተንቀዠቀዠ ነው። በአጠቃላይ የአሸባሪው ትህነግ ባህሪም ሆነ መልክ ከኢትዮጵያውያን የስነ ልቦና ውቅርና ማንነት ያፈነገጠ መሆኑን የሴራ ፣ የደባ ፣ የጭካኔና የግፍ ጥጉ ጥሩ ማሳያ ነው። ባለፈው በሰሜን እዝ ላይ የፈጸመው ትውልድም ሆነ ታሪክ ይቅር የማይለው ክህደትም ሆነ እስከዛሬ የቀጠሉት ኅልቆ መሳፍርት የሌላቸው ግፎች ፤ በአገሪቱ የዘመናዊ ፖለቲካ ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ እንደማያውቅ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። ወደፊትም በኢትዮጵያ ሰማይ ስር ይፈጠራል ተብሎ አይታሰብም፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ በሀቀኛና ጀግኖች ልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር !
አሜን ።
አዲስ ዘመን ጥቅምት 13 ቀን 2015 ዓ.ም
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com