ባለፈው ሐሙስ ጥቅምት 10 ቀን 2015 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በተገኙበት በቡራዩ ከተማ የልዩ ተሰጥዖ ኢንስቲትዩት ተመርቋል።የኢንስቲትዩቱ ምረቃ እንደ ቀላል መታየት ያለበት አይደለም።በአንድ አካባቢ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም (ዩኒቨርሲቲ) ተገንብቶ ተማሪዎችን መቀበል ሲጀምር ትልቅ ዜና እንደሚሆን ሁሉ ግንባታው ከዚያም በላይ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደገለጹት ዕውቀት ወደ ተግባር የሚቀየርበት ተቋም ነው።
አስታውሳለሁ! በዘመነ ኢህአዴግ በየትኛውም ምሁር እና የፓርቲ አመራሮች በሥርዓተ ትምህርቱ ላይ ይነሳ የነበረው ቅሬታ፤ የተግባር ተማሪዎችን መፍጠር አልተቻለም የሚል ነበር።ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎቻቸውን ባስመረቁ ቁጥር ይሰጥ የነበረው አስተያየት ‹‹የአውሮፓ ቲዎሪ ብቻ ተምሮ መመረቅ ምን ዋጋ አለው!›› የሚል ነበር።መንግሥት በአፉ ‹‹ተግባር ተኮር›› ቢልም መሬት ላይ ግን የታየ የተግባር ትምህርት አልነበረም፡፡
እነሆ አሁን እነዚያ ይነሱ የነበሩ ቅሬታዎች መልስ ሊያገኙ ይመስላል።የልዩ ተሰጥዖ ትምህርት ቤቱ እጅግ ሊደነቅና ሊመሰገን የሚገባ ሥራ ነው።ምክንያቱም ለብዙ ተማሪዎች እና በተለያየ ሙያ ውስጥ ላሉ ሰዎች መነሳሳትን ይፈጥራል።ባክነው የሚቀሩ የፈጠራ ሀሳቦች ዕውቅና እንዲያገኙ ያደርጋል፡፡
ከምንም በላይ ደግሞ የዚህ የልዩ ተሰጥዖ ኢንስቲትዩት ዋና ጠቀሜታው አገር በቀል ዕውቀት እንዲስፋፋ ያደርጋል።በተደጋጋሚ እንደሚባለው ኢትዮጵያ የብዙ ሥልጣኔዎች መነሻ ናት።በብዙ ዘርፍ ተሰጥዖ ያላቸው ሰዎች ያሉባት ናት፡፡
ዳሩ ግን በቅድመ አያቶቻችን ጥበብ በመፎከር ነበር የምንኖር።አክሱምና ላሊበላን በሰሩ አባቶቻችን ከመፎከር፤ ልክ እንደ እነርሱ አይነት የፈጠራ ሰዎች የሚወጡበትን ዕድል መስጠት ነው ታሪክ መሥራት ማለት።ሞፈርና ቀንበር ከእንጨት አዘጋጅተው እርሻ ባስጀመሩ አያቶቻችን እነሆ ሦስት ሺህ ዘመናት ተጠቀምን።ዛሬ ደግሞ እርሻን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የሚያስጀምሩ ሰዎች ያስፈልጉናል፤ ስለዚህ ይህ የሚጀመርበትን ዕድል መፍጠር ታሪክ መሥራት ነው።
ይህን የልዩ ተሰጥዖ ኢንስቲትዩት ማሰብ በራሱ ልዩ ተሰጥዖ ነው፤ ፈጠራ ነው።ምክንያቱም እስከዛሬ ያልነበረ ነው።ትኩረት ሳይሰጠው የኖረ ጉዳይ ነው።አገር በቀል ዕውቀቶችና ሀሳቦች ተዳፍነው ነበር የኖሩ፤ የእንዲህ አይነት የተቋም ግንባታ መጀመሩ መነቃቃትን ይፈጥራል።አዲስ የአስተሳሰብ አብዮት ያመጣል ነው፡፡
ተሰጥዖን በተመለከተ በየዘርፉ ካሉ ባለሙያዎች የምንሰማው አንድ ተደጋጋሚ ቅሬታ ነበር።ይሄውም ኢትዮጵያ ውስጥ ለልዩ ተሰጥዖ ትኩረት አይሰጥም የሚል ነበር።አንድ ተማሪ የተለመደውን የክፍል ውስጥ ትምህርት ማለፊያ ነጥብ አምጥቶ፣ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ተመርቆ እስካልወጣ ድረስ እንደ ባለሙያ አይቆጠርም ነበር ፡፡
ለምሳሌ፤ ሰዓሊ ቢሆን እንደ ሰነፍ ተማሪ ነው የሚቆጠር።የሥዕል ሙያ ሳይንስም ጥበብም መሆኑ ልብ አይባልም።ሙዚቀኛ ቢሆን እንደ ሰነፍ ተማሪ ነው የሚቆጠር።ድምጽ እንደ ተሰጥዖ (እንደ መታደል) አይቆጠርም።የሙዚቃ መሳሪያዎችን መሥራት እንደ ችሎታ (ጥበብ) አይታይም።በአካባቢው የሚያስተውላቸውን ነገሮች (የመገልገያ ዕቃዎች፣ የጦር መሳሪያዎች፣ የባህል ቤቶች…) አስመስሎ የሚሰራ ተማሪ ትኩረት አይሰጠውም ነበር።
አሁን ግን የዚህ የልዩ ተሰጥዖ ኢንስቲትዩት መጀመር ለእነዚህ ሁሉ ትኩረት እንዲሰጥ ያደርጋል።አንድ ሰው በአንድ ነገር ደካማ ቢሆን ሌላ የሆነ ተሰጥዖ ይኖረዋል።የማህበራዊ ሳይንስ ትምህርቶች የማይገቡት ተማሪ ጎበዝ የሒሳብ ወይም የኬሚስትሪ ሊቅ ሊሆን ይችላል።ዳሩ ግን በእነዚያ ትምህርቶች ምክንያት ውጤት ካልመጣለት ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ወይም ወደ መሰናዶ ትምህርት ቤት ላይገባ ይችላል።እንዲህ አይነት የልዩ ተሰጥዖ ተቋማት ካሉ ግን ይህ ልጅ የሚሰራቸው የጂኦሜትሪ ሙያዎች አስተዋይ ያገኛሉ ማለት ነው፡፡
የተፈጥሮ ሳይንስ (ሒሳብ፣ ኬሚስትሪ፣ ፊዚክስ…) የማይችል ተማሪ የተዋጣለት ደራሲ፣ ድምጻዊ፣ ሠዓሊ፣ ተዋናይ… ሊሆን ይችላል።ዳሩ ግን በተፈጥሮ ሳይንሶች ምክንያት ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚያደርስ ውጤት ላያመጣ ይችላል።እንዲህ አይነት የልዩ ተሰጥዖ ተቋማት መኖራቸው ግን የዚህ ልጅ ተሰጥዖ ተዳፍኖ እንዳይቀር ያደርጋል ማለት ነው።
በቡራዩ የተጀመረው የልዩ ተሰጥዖ ኢንስቲትዩት ለጊዜው ጅማሮ ነው።በውስን የተሰጥዖ አይነቶች ላይ ይሁን በሁሉም የተሰጥዖ አይነቶች ለጊዜው ወሰኑ አልታወቀም።አንድ ሺህ ባለ ልዩ ተሰጥዖ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር እንደሚችል ነው በዜናው የተገለጸው።ያም ሆነ ይህ ዋናው ቁም ነገሩ ግን ሰርቶ ማሳያ ሆኖ መጀመሩ ነው።ሌሎች አካባቢዎችም እንዲህ አይነት ተቋማ ሊገነቡ ይገባል፡፡
ተሰጥዖ በብዙ ሰዎች ውስጥ አለ።ምናልባት ብዙ የተለመደው በትምህርት ቤቶች ስለሆነ (የመታየት ዕድል ስላለው) ተማሪ ብቻ ይመስለናል እንጂ የትምህርት ዕድል ያላገኙ ብዙ ባለተሰጥዖዎች አሉ።መንግሥት ተቋማትን ሲገነባ እኛ ደግሞ ሕብረተሰቡ ውስጥ ያሉ ባለተሰጥዖዎች ይህን ዕድል እንዲያገኙ መንገር አለብን።
በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች እንደየ አካባቢው ባህልና ልማድ የተለያየ ተሰጥዖ ያላቸው ሰዎች አሉ።ባህላዊ የመገልገያ ዕቃዎች የሚሰሩት በአካባቢው ጥበበኞች ነው።እነዚህ የመገልገያ ዕቃዎች በባህላዊ መንገድ ስለሚሰሩ ሳይንሳዊ ይዘት ያላቸው አይመስለንም።ብዙ ጊዜ የሳይንስ ውጤት የሚመስለን በማሽን የሚሰራ የፋብሪካ ዕቃ ብቻ ነው።
በባህላዊ መንገድ የሚሰሩ መኖሪያ ቤቶች የፊዚክስ ሳይንስ የተተገበረባቸው ናቸው።በባህላዊ መንገድ የሚሰሩ አልባሳት የቴክስታይል ውጤት ናቸው።በባህላዊ መንገድ የሚሰሩ ምግቦች ሰሪዎቹ አስበውት ባይሆንም የኬሚስትሪ ዕውቀት የተተገበረባቸው ናቸው።የባህል መጠጦች የኬሚስትሪ ውጤት ናቸው።
እነዚህን ነገሮች ወደ ሳይንሱ ማምጣት ነው ቴክኖሎጂ ማለት።መንግሥት እነዚህ የተሰጥዖ ባለቤቶች ከሳይንስና ቴክኖሎጂ ጋር እንዲገናኙ የሚያደርግ ማዕከል መፍጠሩ ትልቅ ታሪካዊ አሻራ ነው።አገር በቀል ዕውቀቶች ወደ ሥርዓተ ትምህርቱ እንዲመጡ ያደርጋል።
ለሳይንስና ቴክኖሎጂው ግብዓት የሚሆኑ የፈጠራ ሥራዎች እንዳሉ ሁሉ ለማህበራዊ ሕይወት ግብዓት የሚሆኑ ብዙ የፈጠራ ጥበቦችም አሉ።የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የእርስበርስ መተዋወቅ እና አንዱ ሌላውን እንዴት እንደሚያከብር የሚያሳዩ የባህል እና የጥበብ ሥራዎች አሉ።እነዚህም በእንዲህ አይነት የተሰጥዖ ማዕከላት ቦታ ትኩረት ያገኛሉ ማለት ነው፡፡
ይህ የልዩ ተሰጥዖ ትምህርት ቤት በተለይም የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ተደራሽ ላልሆኑ የገጠር ተማሪዎች ጥሩ ዕድል ነው።‹‹የእጅ ሥራ›› የሚባል የትምህርት ክፍለ ጊዜ በነበረበት ወቅት (አሁን ይኑር አይኑር አላውቅም) ብዙ የፈጠራ ሥራዎች ባክነው ይቀሩ ነበር።ምንም እንኳን እኔ የእጅ ጥበበኛ ባልሆንም ብዙ የትምህርት ቤት ልጆች ግን አስገራሚ የሆኑ የእጅ ሥራዎችን ሰርተው እዚያው የትምህርት ቤቱ ማጠራቀሚያ ማዕከል ውስጥ ይቀመጥ ነበር፡፡
እንዲህ አይነት የተሰጥዖ ተቋማት ከተመሰረቱ ግን ባክኖ የሚቀር ተሰጥዖ አይኖርም ማለት ነው።መንግሥት ለሰራው ሥራ እያመሰገንን ተማሪዎች የዕድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ሁላችንም የድርሻችንን እንወጣ።
ሚሊዮን ሺበሺ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 13 ቀን 2015 ዓ.ም