ፈረስና ጋሪ ለአሁናዊው የአገራችን ሁኔታ ጥሩ ማሳያ ሆነው አግኝቻቸዋለው።ፈረስና ጋሪ ታሪክ የሚኖራቸው ቅደም ተከተላቸውን ሲጠብቁ ነው።ፈረስ ከኋላ ሆኖ ጋሪው ከፊት ከቀደመ የአገሬ ህዝብ እንደሚለው ከፈረሱ ጋሪው ይሆንና ውጥንቅጡ ይወጣል።እኛም እንዲህ ነን..ማስቀደም ያለብንን ሳናስቀድም ለዘመናት ከህዝብ በቀደመ የፖለቲካ ፊተኝነት ውጥንቅጣችን ወጥቶ ከርመናል።ባለማወቅ ሳይሆን በቸልተኝነት ፊትና ኋላነትን ባልጠበቀ ቅደም ተከተል ተፋልሰን ኖረናል።
አሁን የሚጠበቅብን የቦታ ለውጥ ነው።የቦታ ለውጥ የአስተሳሰብ ለውጥ ነው።ያለ ምንም ተግባር ከፈረሱ የቀደመውን ጋሪ ወደ ቦታው መልሶ የሳትናቸውን ቅደም ተከተሎች ማስተካከል ይኖርብናል። እኚህ የተፋለሱ ቅደም ተከተሎች ደግሞ ቦታቸውን የሚይዙት በእርቅና በምክክር ነው።በእርቅና በምክክር ችግሮቻችንን ፈልገን እንድናገኝ አገራዊ ምክክር ያስፈለገበት ዋና አላማም ለዚህ ነው።አሁን ጊዜው ከጋሪው ፈረሱ ቀድሞ በአንድ ልብ ወደ ፊት የምንሄድበት እንጂ ከፈረሱ ጋሪው እየቀደመ ስህተቶቻችንን እየደጋገምን የምንደነቃቀፍበት አይደለም፡፡
አገር የልዕልና ጥግ ናት።ይህ የእኔና የእናንተ፣ ያንቺም የእሱም የሁላችንም እውነት ነው።አገር መከበሪያ ናት፣ በትላንት በዛሬና ነጋችን ውስጥ የተሳለች ምስል ናት። አገር የእያንዳንዳችን የማንነት ማህተማችን ናት።ስለ አገር ሲነሳ ጥላሁን ገሰሰ ትዝ ይለኛል።ስለ አገር ሲነሳ በባንዲራዋ ፊት ያነባው ኃይሌ ገብረ ስላሴ ይታወሰኛል። አገር ይቺ ናት..በልባችን በነፍሳችንም ውስጥ ያለች፣ የትም ይዘናት የምንዞር። ስሟን በሰማን ቁጥር፣ ባንዲራዋን ባየን ቁጥር እንባችን የሚመጣ፣ ስለ ደግ ህዝብ ሲወራ ባር ባር የሚለን ይቺ ናት አገር። ይቺን ነው ኢትዮጵያ የምላችሁ፡፡
ስለ አገራቸው ክብር ደማቸውን ያፈሰሱ፣ አጥንታቸውን የከሰከሱ፣ ከአገሬ በፊት እኔን ያሉ በርካታ ኢትዮጵያዊያን እዛም እዚም ሞልተዋል።እነ በላይ ዘለቀ፣ እነ አብዲሳ አጋ፣ እነ ዘርዐይ ደረስ የአገር ፍቅርን ጥግ ድረስ ያሳዩን ምልክቶቻችን ናቸው።እነሱ በዘመን ውስጥ ሳይደበዝዙ ያበሩት ቅደም ተከተላቸውን ሳይስቱ ፈረስና ጋሪ ሆነው ነው። እኛም ሳንደበዝዝ እንድናበራ የእይታ መነጽራችንን ማስተካከል ይኖርብናል። ከዘነጋነው ወይም ደግሞ አውቀን ከሰወርነው የዝባዝንኬ ጨዋታ ወጥተን አገርና ህዝብን በሚጠቅም እውነት በሆነ ስፍራ ላይ መቆም ይጠበቅብናል፡፡
አገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ እስኪጠፋን ድረስ መጉደል የለብንም።ሩጫው ሁሉ ወደአልተፈለገ አቅጣጫ ከማድረግ ወጥተን መስተካከል አለብን። ከእውቀት ማነስና ከኃላፊነት መጉደል አሁን ላይ ጭራሽ የምናየው፣ የምንሰማው ሁሉ ከኢትዮጵያዊነት ባህልና ስርዐት ያፈነገጠ የጭካኔ የመጨረሻው ማሳያ እየሆነ የመጣበት ጊዜ ላይ ነን።ወጣቱ በምክንያት ከመኖር ይልቅ በስሜት መመራትን የመረጠበት ጊዜ፣ የተማረው በእውቀቱ አገር ከመጥቀም ይልቅ የውሸት ተረት እየፈጠረ በህዝቦች መካከል የጠብ ቁርሾ መንዛትን የተካነበት ዘመን ላይ ነን።
በየቦታው በየአገሩ የምንሰማው አንድ አይነት ሆኗል።ሀዘን፣ ሞት፣ ስደት ያልሰማንበት ጊዜ የለም።በየቀኑ በየሚዲያው የምንሰማው ክፉ ወሬ ብቻ ነው።በጣም የሚገርመው ነገር ደግሞ ይሄ ሁሉ በደልና ጭቆና እየደረሰ ያለው ተማርን በሚሉ ራስ ወዳዶች መሆኑ ነው። ከአገርና ህዝብ ሀብት ላይ ቀለብ እየተሰፈረላቸው ተምረው መፍትሄ እንደመሆን ተመልሰው አገር የሚያፈርሱ ተበራክተዋል። ያጎረሳቸውን የእናታቸውን እጅ የሚነክሱ ወጪት ሰባሪ ትውልድ የበዛበት አስከፊ ዘመን ላይ ደርሰናል። የእስካሁኗ ኢትዮጵያ ባልተማሩ ልጆቿ የተሰራች ናት። የእስካሁኗ ኢትዮጵያ የፍቅርና የአንድነት የደም ፍሬ ናት። ይሄ ሁሉ ገናናነታችን በነሱ የመጣ ነው።ለዚች አገር እኛ የዋልነው ውለታ የለም።እኛ የተሰራ ከማፍረስ፣ አንድ ሆኖ የቆመን ህዝብ ከመለያየት ባለፈ አሁን ላለችው ኢትዮጵያ ምንም አይነት ጥቅም እየሰጠን አይደለም፡፡
እኛ የአገር ጠባቂ እንጂ ጠላት አይደለንም።የአገራችንን ህመም ስናስብ ህመሟ ሁሉ በእኛ የመጣ እንደሆነ እንደርስበታለን።ዛሬም እያሳመምናት ያለነው እኛ ልጆቿ ነን።አገራችን በሌሎች ታማ አታውቅም።ህመሞቿ እኛ ነን።እኛው እንዳንገላት እፈራለው።ይሄ እንዳይሆን ከፈረሱ ጋሪው የሆነ ፖለቲካና ፖለቲካዊ አስተሳሰባችን መጽዳትና መስተካከል አለበት።በብዙ ችግር፣ በብዙ ድህነት፣ በብዙ ማጣትም ተተብትባ የምትኖር አገር ተስፋዋን በሰነቀችብን በእኛ መጎሳቆሏ እንደ አንድ ወጣት ሳስበው ያመኛል።ወጣቱ ከጦርነት ወጥቶ ለልማት የሚታጠቅበት፣ አዛውንቶች ከስደት ወጥተው ለእርቅ የሚቀመጡባት ኢትዮጵያ ናፍቃኛለች።ህጻናት ከርሀብ ወጥተው ለነገ ተስፋ የሚሆኑባት፣ የተማሩት ከነውጥ ወጥተው ለወገን አለኝታ የሚሆኑባት ጦብያ ናፍቃኛለች።
ከፈረሱ ጋሪው በሆነ የራስ ወዳድነት ልክፍት ወጣቱን ለልማት ከመጠቀም ይልቅ ጦርና መሳሪያ አስታጥቀው ለእኩይ አላማ የሚያሰለጥኑ፣ መብቱን በሰለጠነ መንገድ ከመጠየቅ ይልቅ በረብሻ እንዲጠይቅ በማድረግ የግል ጥቅማቸውን ለማስፈጸም የሚለፉ ባንዳዎች እየተፈጠሩ ነው።አሁን ላይ በየቦታው በሰው ህይወትና በንብረት ላይ የሚደርሱ ውድመቶች ሁሉ ስሜታዊውን ወጣት መጠቀሚያ በማድረግ የተከሰቱ ናቸው።እነሱ በሞቀ ቤታቸው ጮማ እየቆረጡ፣ ውስኪ እየተጎነጩ ተቀምጠው ወጣቱን በጊዜአዊ ጥቅም በመደለል ወደ እሳት የሚማግዱ እኩዮች አሉ፡፡
ቆይ መማራችን ለአገርና ወገን ካልሆነ ጥቅሙ ምን ላይ ነው? እኔ ካልተጠቀምኩ፣ የእኛ ሀሳብ ካልሆነ በሚል አጉል አስተሳሰብ የነገውን ተስፈኛ ወጣት ለጥፋት ማነሳሳት ተገቢ ነው ብዬ አላስብም። በአገራችን ውስጧ በርካታ ዩኒቨርሲቲዎችን ገንብታ እያስተማረች የተማረ የታጣባት አገር ሆነናል።አለም በስልጣኔ መጥቃ ጨረቃ ላይ ቤቷን በሰራችበት በዚህ ስልጡን ዘመን ላይ እየኖርን ለአለም ስልጣኔ ፈር ቀዳጅ የሆነን ቀደምት ህዝቦች እኛ እርስ በርስ መግባባት አለመቻላችን የምንጊዜም ጥያቄዬ ሆኖ ጭንቅላቴ ውስጥ አለ።
እስኪ እንግባባ።አንተ ትብስ አንተ የሚለውን የጥንቱን ባህል ዛሬ ላይ መልሰን ከፈረሱ ጋሪው የሆነች አገራችን እንታደግበት። ኢትዮጵያዊነት ስርዐት እኮ ነው። ሀበሻነት ራሮት እኮ ነው።ፈርሰን መሰራት አለብን። ራስ ወዳድነት የወለደው ፖለቲካችን ህዝብን ከፊት አስቀድሞ እንደ አዲስ ነፍስ መዝራት አለበት። ወጣቱ በቤተሰቡ መሰራት አለበት።ፈርሀ እግዚአብሄር እንዲኖረው ሆኖ ማደግ አለበት።የተባረከ ሆኖ ስለ አገር ፍቅር እየተነገረው ማደግ ነገ ለሚኖረው ህይወት ወሳኝነት አለው፡፡
አሁን ላይ ነውጥ የሚፈጥሩ፣ ለአገር ስጋት ሆነው የምናያቸው ሰዎች በስርዐት ያላደጉ የነውረኛ ቤተሰብ ልጆች ናቸው። ሀገር..ሀገር ሆና እንድትቀጥል ታላላቆቹን የሚያከብር፣ የአባቶቹን ስርዐት ያልናቀ ትውልድ ያስፈልጋል። ከሰሞኑ ለሆነ ጉዳይ ወደ አንድ ቦታ እየሄድኩ ታክሲ ውስጥ ተቀምጫለው። ታክሲ ቆሞላቸው አንድ አዛውንት እናት መንገድ ላይ ይሳፈራሉ።ከፊት ለፊት ቦታ ስላልነበረ ኋላ ወንበር መቀመጥ ግድ ነበረባቸውና በዛ እርጅና ኋላ ወንበር ላይ መጉላላቱን ስላልፈለጉት ከፊት የተቀመጠውን ወጣት ‹የኔ ልጅ ቦታ አትቀይረኝም..› አሉት፡፡
ወጣቱም ‹ኋላ መቀመጥ አልወድም› ሲል መለሰላቸው፡ ይሄ መልስ ታክሲ ውስጥ የተሳፈርነውን ሁላችንንም ያሳዘነ መልስ ነበር። በሚቀጥለው ወንበር ላይ የተቀመጡ አንድ አባት በወጣቱ ንግግር እያዘኑ ‹ምናለበት ብትነሳላት? መታዘዝክ እኮ ትልቅነትክን ነው የሚያሳየው› ሲሉት፡፡
‹እኔን ከሚሉ ለምን እርሶ አይነሱም? ሲል ትዕቢታዊ ምላሽ ሰጣቸው።መልስ አልሰጡትም..በልባቸው ግን ትውልዱን የሚረግሙ ይመስለኛል።‹አምላኬ ሆይ ምነው እዚህ ዘመን ላይ ጣልከኝ? የሚሉ።ለባልቴቷ ቦታቸውን ለቀው ኋላ ወንበር ተቀምጠው ሲተክዙ ነበር፡፡
ብዙ የአለም አገሮች ልጆቻቸውን የሚያስጠኑት አንድ አባባል አለ..‹አገሬ ለኔ ምን አደረገችልኝ ሳይሆን እኔ ለአገሬ ምን አደረኩላት› የሚል።ይህ አባባል የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበረው የጆን ኦፍ ኬኔዲ ይሁን እንጂ ብዙ አገራት የሚጋሩት እውነት ነው።ብዙ ኢትዮጵያዊያን ከአገር መውሰድ እንጂ ለአገር መስጠትን አያውቁበትም። የሁልጊዜ ጥያቄያቸው አገሬ ለኔ ምን አደረገችልኝ የሚል ነው። እንዲህ አይነት እኩይ አመለካከት አገር ከመጉዳት ባለፈ ጥቅም የለውም፡፡
ይሄ አስተሳሰብ ነው ዛሬ ላይ አገር እየጎዳ ያለው። ለሙስናና ስልጣንን ያላግባብ ለሚጠቀሙ ህገ ወጦች በር የከፈተው።ወጣቱ ለአገሩ ተስፋና የብልጽግና ምንጭ እንጂ የጥፋት ምክንያት መሆን የለበትም።በመልካም ሀሳብ ተሞልቶ ለወገኑ አለኝታ እንጂ ስጋት የመሆኑ ነገር ማክተም አለበት።አባቶቻችን ታላቅ አገርና ታላቅ ህዝብ እንዳስረከቡን ሁሉ እኛም ለነገ ልጆቻችን የምናስረክባት መልካምና በሁሉ ነገሯ የምትደነቅ አገር ልንፈጥር ይገባናል።ይሄ የመንግስት ወይም የተወሰኑ ሰዎች ኃላፊነት ሳይሆን የሁላችንም ኃላፊነት ነው፡፡
መማር ማለት መፍትሄ መሆን ማለት ነው።እኛ ግን እውቀታችንን ጥበባችንን ሁሉ አገር ለማፍረስና ለዘመናት ተዋዶና ተከባብሮ ተቻችሎም የሚኖርን ህዝብ ለመከፋፈል እየተጠቀምንበት እንገኛለን። ከአገርና ከህዝብ ጥቅም ይልቅ ራስ ተኮር ሆነን ብዙ የሆነችልንን አገርና ህዝብ ስንጎዳ ስናስጎዳም ቆይተናል። መማራችን ምኑ ላይ እንደሆነ አልገባኝም። የድሮ አባቶቻችን ባልሰለጠነ ዘመን አክሱምና ላሊበላን የመሰለ ለዘመናዊው አለም ትንግርት የሆነ ታላቅ የስልጣኔ ምልክትን ትተውልን ከማለፋቸውም ባሻገር በአንድነቷ የምትደነቅን አገር ሰርተውልን አልፈዋል።
እኛ ተማርን የምንለውና እጅግ በሰለጠነው ዘመን ላይ ያለነው የዛሬዎቹ ግን ያልተማሩ አባቶቻችን ያወረሱንን ታላቅ አገር በማፍረስ ደፋ ቀና እንላለን። በህዝቦች መካከል ጥላቻና መለያየት እንዲኖር፣ በፍቅር ፈንታ ጥላቻን፣ በአንድነት ፈንታ መለያየትን በመስበክ ለአገራችንም ለህዝባችንም ነቀርሳ ሆነን እየኖርን ነው። የአገራችን መከራ ፊደል በቆጠሩና ከስማቸው በፊት ማዕረግ በቀጠሉ ግለሰቦችና ቡድኖች የተፈበረከ ነው፡፡
እስኪ ምን ያህሉ የተማረ ዜጋ ነው ለዚች አገር መድህን ሲሆን ያያችሁት? ጎኗ ላይ ተጣብቀው እንደ መዥገር ደሟን ከመምጠጥ ባለፈ የፈየዱት መላ አለ ብዬ አላስብም። አስተምራ ለቁም ነገር አብቅታቸው ነበር፣ ካላት ላይ ከሌላት ላይም ቀንሳ ቀን አውጥታቸው ነበር፣ በድህነት ጎኗ ብዙ ብዙ ሆናላቸው ነበር ዛሬ ላይ ለክብሯ ፊታውራሪ ከመሆን ይልቅ ውርደቷን ናፍቀው ከፊት ቆመው በለው ይላሉ።
ድህነት ለዘመናት ተብትቦ በያዛት አገር ላይ እንዲህ አይነት ጭካኔ ስርየት የሌለው በደል ሆኖ ነው የሚታየኝ። በፖለቲካው በኢኮኖሚው በማህበራዊው በሁሉም ውስጥ የክፋት እጃቸው አለ። በእውቀታቸው ውስጥ እውነት የለም።በልባቸው ውስጥ አምላክ የለም። ትላንት ራስ ወዳድ ነበሩ ዛሬም ራስ ወዳድ ሆነው ይኖራሉ። ይበቃናል..አሁን ደግሞ ቀና እንበል። ከፈረሱ ጋሪው ቀድሞ ሲያሰቃየን ከነበረው የፖለቲካ አስተሳሰብ እንውጣ።በእርቅና በምክክር የፈረሱን ቦታ ለጋሪው፣ የጋሪውን ለፈረሱ ሰጥተን ልክ በሆነ ቅደም ተከተል አገር እንስራ፡፡
የእርቅና የመቻቻል ባህል ያስፈልገናል።የአንድነት የፍቅር አለም መገንባት ግድ ይለናል።ተምረን የተገነባ ከማፍረስ፣ መኪና ከማቃጠል፣ ህዝብ ከማፈናቀል የዘለለ ለዚች ድሀ አገር ውለታ መዋል አለብን። አሁን ላይ ህዝብ የጦርነት ወሬ መስማት ሰልችቶታል።አሁን ላይ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደ ሰላም፣ እንደ አንድነት የናፈቀው ምንም የለም።እስኪ ለአፍታ እናስብ..ከፈረሱ ጋሪው በሆነ የፖለቲካ ስርዐት ተራምደን ግራ የተጋባች አገር ፈጥረናል፡፡
እስኪ አሁን ደግሞ በፍቅርና በእርቅ ከጋሪው ፈረሱ የሚቀድምባትን ኢትዮጵያ እንፍጠር።ፈረሱ እኮ ህዝብ ነው..ጋሪው ደግሞ ፖለቲካ።እስከዛሬ ፖለቲካው ቀድሞ ህዝብ እየተከተለ ከማንወጣው ማጥ ውስጥ ገብተናል። እስኪ ደግሞ ህዝብ ይቅደምና ፖለቲካ ይከተል።ከጥያቄ በቀር መልስ በሌላት አገር ላይ ነን።በቀን ሶስቴ መብላት ባቃተው ድሀ ህዝብ መካከል፤ በስራ ማጣት መሄጃ ባጣ ወጣት መካከል ነን፣ የውስጥና የውጪ አገራዊ አጀንዳ የበረከተበት ሰሞን ላይ ነን።ለመፍትሄ እናምጥ እንጂ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ አንሁን።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)