የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሦስተኛው ዙር ውሃ ሙሌት በስኬት መጠናቀቅን አስመልክቶ ትናንት ያስተላለፉት የእንኳን ደስ አለን መልዕክት!
ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ እንዲሁም በዚህ ስፍራ በዚህ ታሪካዊ ፕሮጀክት ውስጥ በእውቀት፣ በጉልበት የተሳተፋችሁ የኢትዮጵያ ድንቅ ልጆች፤ ከዚህም ባሻገር የዚህን ፕሮጀክት ጠቃሚነት ተገንዝባችሁ ኢትዮጵያን በሀሳብና በተለያየ መንገድ ስትረዱ የቆያችሁ የኢትዮጵያ ወዳጆች በሙሉ፤ ዛሬ በዚህ ስፍራ ሦስተኛው ዙር የውሃ ሙሌት መጠናቀቁን ሳበስርላችሁ በታላቅ ደስታ ነው:: ዛሬ ከጀርባዬ የምትመለከቱት (የውሃው ፍሰት ከጀርባቸው እያስመለከቱ ስለሚናገሩ የተጠቀሙት ቃል ነው) የሦስተኛው ሙሌት የውሃ በላይ መፍሰስ (ኦቨር ቶፕ ማድረግ) እየተከናወነ ይገኛል::
ይህ ክንውን አምና ከነበረው ጋር ለማነጻጸር ብንሞክር፤ አምና በመሃከል ውሃ የሚፈስስበት ቦታ 575 ሜትር ነበር:: ዘንድሮ ተጨማሪ 25 ሜትር ከፍ በማድረግ 600 ሜትር ላይ የውሃው ፍሰት ይታያል:: ግራና ቀኝ አምና 585 ሜትር ነበር:: ዘንድሮ 611 ሜትር በመድረስ በከፍተኛ ደረጃ ውሃ የመያዝ አቅምችንንና ኃይል የማመንጨት(ኢነርጂ ጀነሬት የማድረግ) አቅማችንን ከፍ አድርጎታል:: ይህ በዚህ ስራ ለተሳተፉ ሰዎች ሁሉ እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ ደስታን የሚፈጥር ታላቅ ድል ስለሆነ እንኳን ደስ ያላችሁ፤ እንኳን ደስ ያለን ማለት እፈልጋለሁ::
ሁላችሁም እንደምትገነዘቡት፣ ዓባይ የእኛ የፈጠራ ውጤት አይደለም:: ዓባይ የፈጣሪ ስጦታ ነው:: ይህ የፈጣሪ ስጦታ በአግባቡ እንድንጠቀምበት፣ በአግባቡ እንድንገለገልበት ታስቦ የተሰጠን ነው:: ፈጣሪ እጅ ሰጥቶናል፤ እጃችንን በአግባቡ መጠቀም ማረስ፣ መዝራት፣ መነገድ፣ መገንባት፣ የእያንዳንዱ በነጻ እጅ የተሰጠው ሰው ኃላፊነት ይሆናል:: ዓይን በነጻ ተሰጥቶናል:: ዓይናችንን በአግባቡ መጠቀምና መገልገል የእያንዳንዱ በነጻ የተሰጠው ሰው ኃላፊነት ይሆናል:: ከተሰጠው በኋላ የማይጠቀም ሰው ቢኖር ተወቃሹ እሱ እንጂ ሰጪው ሊሆን አይችልም:: በዚሁ አግባብ ዓባይ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ተሰጥቷል::
ለዓለም የተሰጠበት መንገድ የዓለም ሕዝቦች አስፈላጊ ነው ብለው በሚያምኑበት በማንኛውም ጊዜ በዚህ ስፍራ መጥተው ሊዝናኑ፣ ሊያዩ፣ ጊዜያቸውን በደስታ እንዲያሳልፉ የሚያስችል ከፍተኛ ብቃት አለው:: በዚህ ግድብ ምክንያት ከኋላ በምናየው ቦታ(ውሃው የተኛበትን ቦታ) 70 ገደማ ደሴቶች (ሃይ ላንዶች) አሉ:: እነዚህ ደሴቶች ከ40 በላይ የሚሆነው ደሴት እያንዳንዱ ከ10 ሄክታር በላይ ቦታ ይዟል:: አንዳንዶቹ 800 ሄክታር፣ ከ2ሺህ ሄክታር በላይም ደሴት የሆነ ቦታ ይገኛል:: ዝቅተኛው ደሴት(ሃይ ላንድ) አምስት ሄክታር የሚይዝ ነው:: እያንዳንዱን ሃይላንድ(ደሴት) አንዳንድ ሪዞርት ብናደርግ፣ በመሃል ከውሃ ጋር የሚደረጉ ጫወታዎችን ብንጨምር ከፍተኛ የሆነ የዓሣ ምርት በዚህ ቦታ አለ:: እስከ 70ና 80 ኪሎ የሚመዝኑ ዓሣዎች አሉ:: እናም ዓሣን በማጥመድ ደስታን የሚያገኙ ሰዎች ቢኖሩ መጥተው ሊዝናኑበት ይችላሉ::
አካባቢውን እንደምታዩት እጅግ ተራራማ እና በጣም ሲበዛ አረንጓዴ(ግሬን) ቦታ ነው:: ተራራውን ለሃይ ኪንግ፣ እንዲሁም አረንጓዴ ስፍራውን ለተለያየ መዝናኛ መጠቀም ይቻላል:: ከዚህ አንጻር ዓለም መጥቶ በዚህ ቦታ ላይ ለመዝናናት የሚያስችለው ትልቅ ስጦታ ነው:: ነገር ግን ግድቡ ከመገደቡ በፊት እንደዚህ አይነት ደስታ በዚህ ቦታ ማግኘት አይቻልም ነበረ:: ሙቀቱ ብቻ ሳይሆን የውሃው መቆየት በራሱ ደሴት ፈጥሯል፤ ዓሣ ፈጥሯል፤ በጣም በርካታ የተፈጥሮ ሃብቶቻችንን አጉልተን የምናይበትን እድል ፈጥሮልናል:: እናም ዓለም ከዚህ አንጻር መገልገል የሚችልበት ቦታ መሆኑን ተገንዝቦ ለመጠቀም ዝግጁ መሆን፤ ኢንቨስት ለማድረግ ዝግጁ መሆን ይኖርበታል::
ሁለተኛው በነጻ ተቀባይ አፍሪካ ነው:: አፍሪካ የኢኮኖሚ ትስስር ብሎ ካፀደቀ ዓመታት ተቆጥረዋል:: እናም የኢኮኖሚያዊ ትስስር አንዱ መንገድ ኢነርጂ(ኃይል)ን ለጎረቤት አገሮች መሸጥ ነው:: ይህ ኃይል ሙሉ በሙሉ ሲመነጭ ለእኛ ጎረቤቶች ብቻም ሳይሆን ከዛም ተሻግሮ ሊጠቅም የሚችል ነው:: ለዜጎቻችን ይጠቅማል፤ እኛም ለጎረቤት ሕዝቦች ኃይል በመሸጥ እንዲገለገሉ ለማድረግ ያስችላል:: ያስተሳስራል፤ በጋራ እንድንለማ፤ በጋራ እንድናድግ እድል ይከፍታል::
ሦስተኛው በነጻ የተሰጣቸው አገራት፣ ሦስቱ አገራት ናቸው፤ ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ:: እነዚህ ሶስቱ በነጻ ይሄን ውሃ የመጠቀም እድል የተሰጣቸው አገራት፤ የሚገባቸውን ድርሻ በአግባቡ መጠቀም ከቻሉ ለእነሱ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የአፍሪካ ወንድምና እህቶችም ጭምር መጥቀም የሚችሉ በርካታ ስራዎች ሊሰሩ ይችላሉ:: እነዚህ ሶስት አገሮች የተሰጣቸውን መገንዘብ፣ በተሰጣቸው ልክ መተባበር እና በጋራ መቆም ከእነሱ ይጠበቃል:: ነገር ግን ዓባይ ለሶስቱ አገራት እንደተሰጠ፣ ሶስቱም በሚገባቸው ድርሻ መጠቀም እንዳለባቸው የማያምኑ ኃይሎች ካሉ የተፈጥሮን ሕግ ያዛባሉ::
ዓባይ ለእኛ ብቻ የተሰጠ ቢሆን ኖሮ ልክ እንደ አዋሽ እዚሁ በቀረ ነበር:: ወይም ወደ ደቡብ፣ ወደ ምስራቅ በፈሰሰ ነበር:: ዓባይ በተፈጥሮ ይሄንን ኮርስ(የፍሰት መስመር) ሲይዝ እኛ የሚገባንን ተጠቅመን የሱዳንና የግብጽ ወንድሞቻችንም እንዲጠቀሙበት ሰጪው በነጻ የሰጠን ስፍራ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል:: ለዚህም ኢትዮጵያ ለሺህ ዓመታት ዓባይን ሳትጠቀም በመቆየቷ ከፍተኛ ቁጭትና ሃዘን ይሰማታል:: ለሺህ ዓመታት የተሰጣትን ዓይን አላየችበትም ማለት ነው:: የተሰጣትን እጅ አልሰራችበትም ማለት ነው:: ዛሬ ግን እጅግ ደስታ የሚሰጥ ኩልል ያለ ውሃ በዚህ ስፍራ ማየት ይቻላል:: በርካታ ዓሣዎች እያጠመዱ መመገብ ይቻላል:: አጠቃላይ አካባቢውን ለቱሪዝም ምቹ አድርጎ መጠቀም የሚያስችል እጅግ ከፍተኛ የሆነ ሃብት፤ ወይም አንዳንዶች እንደሚሉት ብሉ ጎልድ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል::
ሰው እና አገር የሚመሳሰል ባህሪ አላቸው:: አንድ ሰው ምንም እንኳን በተፈጥሮው የሚያምር ቁመና ቢኖረውም በቂ ምግብ ካላገኘ፣ ቆንጆ ልብስ ካልለበሰ፣ ካልታጠበ ያ ሰው የቆሸሸ ነውና መልካም ስፍራ ላይ የማይኖር ስለሆነ ሰዎች በቀላሉ ደሃ መሆኑን፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚኖር ሰው መሆኑን ተገንዝበው ናቅ አድርገው ሊያዩት ይችላሉ:: ሰው በተፈጥሮ የተሰጠው ቁመና ብቻ ሳይሆን በምግብ፣ በንጽህና፣ በአለባበስም ጭምር የሚቀየር ስለሆነ:: አገርም እንደዚሁ ናት:: ምንም እንኳን በተፈጥሮ እጅግ ያማረ ፀጋ የተሰጣት አገር ብትሆንም፤ ያንን አልምታ ተጠቅማ፣ ከልመና ወጥታ ለሌሎች ማሳየት ካልቻለች፤ ልክ በጎዳና በቆሸሸ ባደፈ ልብስ እንደሚታየው ሰው ዝቅ ተደርጋ ልትታይ ትችላለች::
ኢትዮጵያን ደሃ ያሰኛት፣ ኢትዮጵያን ለማኝ ያሰኛት ስላልተሰጣት አይደለም:: እጅግ አስደማሚ የሆኑ የተፈጥሮ ፀጋዎች አሏት:: ነገር ግን ወንድ እና ሴት ልጆቿ በተባበረ መንፈስ በጋራ ቆመው፣ የአገርን ጥቅም አስቀድመው ለልማት ቅድሚያ ሰጥተው መስራት ባለመቻላቸው ነው እንጂ፤ በአንድ ግድብ 70 ደሴት(አይላንድ) አለን ማለት ቀላል ሃብት አይደለም:: ግራና ቀኝ ያለውን መልክዓ ምድር ብታዩት እጅግ አስደማሚ የሆነ ተራራማ፣ ከተራራም በላይ በጣም ግሪን ቦታ ይታያል:: ሁላችሁም እንደምታውቁት፣ በአፍሪካ ውስጥ ያሉ ተራራዎች ከግማሽ በላይ ኢትዮጵያ ውስጥ አለ ይባላል:: ይሄንን መጠቀም ብንችል ኖሮ ምን ያክል ተለውጠን በጽዱ ልብስ፣ በጽዱ ቁመና፣ በጽዱ ሁኔታ ደሃ ከመባል የተላቀቅን መሆን እንደምንችል መገንዘብ ይቻላል::
መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ 85 በመቶውን የዓባይ ውሃ ስናበረክት ቆይተን ላለፉት ዘመናት አለመጠቀማችን የሚያስቆጭ ቢሆንም፤ አሁን መልካም ጅምር በመታየቱ የሚገባንን ተጠቅመን፣ የሚገባቸውን ለወንድሞቻችን ሰጥተን በጋራ ለማደግ በእኛ በኩል ዝግጁ መሆናችንን በድጋሚ እየገለጽኩ፤ ዓባይ የኢትዮጵያ ኩራት፣ ዓባይ የኢትዮጵያ የብልጽግና ጅማሮ መነሻ፣ ዓባይ ኢትዮጵያዊነትና የኢትዮጵያ ከፍታ የሚለመልምበት ቦታ መሆኑን ተገንዝበን፤ እስላም ክርስቲያን፣ ጉራጌ ስልጤ፣ ኦሮሞ አማራ፣ ሶማሌ አፋር፣… ሳንል ኢትዮጵያዊ ሁሉ በጋራ በመደመር አንድ ላይ በመቆም ብልጽግናችንን እውን እንድናደርግ እና ከእርዳታ ከልመና ራሳችንን እንድንገላግል በዚሁ አጋጣሚ ጥሪዬን አቀርባለሁ::
መላው የአፍሪካ ወንድሞቻችን እንኳን ደስ ያላችሁ፤ ዓባይ እንደተለመደው በድል የሚገባውን አስቀርቶ የሚገባቸውን እየሰጠ መጓዝ ጀምሯል:: መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ በዚህ የተሳተፋችሁ፣ ገንዘብ ያዋጣችሁ፣ በሙያ የደገፋችሁ፣ በዲፕሎማሲው መስክ የጮኻችሁ ሁሉ ልፋታችሁ ፍሬ ስላፈራ እንኳን ደስ ያላችሁ ልል እፈልጋለሁ:: ከሁሉ በላይ የጀመርነው የእጅ ስራ እንዲከናወን የረዳን፤ የተናገርነው እንዲፈጸም ያገዘን፤ በድካም በፈተና ሁሉ በጥንካሬና በስኬት እንድንወጣ ያደረገን መልካሙ አምላክ፣ የኢትዮጵያ ፈጣሪ የተመሰገነ ይሁን::
አሁንም ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን አብዝቶ ይባርክ፤ ብልጽግናችንን እውን ያድርግ፤ የእጃችንን ስራ ይባርክ፤ የተጀመረው ድል ይቀጥላል፤ የተጀመረው የብልጽግና ጉዞ ይቀጥላል፤ እያንዳንዱ ፈተና ግን የሚያጠነክረን ይሆናልና የምንሸማቀቅበት ሳይሆን የምንማርበት እንዲሆን አደራ እያልኩ፤ እንኳን ደስ ያላችሁ፣ እንኳን ደስ ያለን ማለት እፈልጋለሁ፤ እጅግ አድርጌ አመሰግናለሁ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 7 /2014