ቀጠሮአችን መኖሪያ ቤቱ ነበር።ስንደርስ አንዲት ክፍል ውስጥ ከአንድ የሥራ ባልደረባው ጋር ሆነው የቀረጹትን ማስታወቂያ አርትኦት እየሠሩ ነው። የቤቱ መገኛ ፈረንሳይ ለጋሲዮን 41 ኢየሱስ ተብሎ የሚጠራ አካባቢ ነው። ተራራማ የሆነ ቦታ ላይ የተሠራው ቤቱ አካባቢውን እና የአዲስ አበባን የተወሰነ ክፍል ማሳየት ይችላል።ለእይታ ምቹ ሆኖ የተሠራ ቦታ ላይ ወንበር ይዘን ተቀመጥን።ወግ አዋቂ ነው።አንደበቱ ለዛ አለው።የዛሬው እንግዳችን ለሦስት አስርተ ዓመታት ገደማ በኢትዮጵያ ሕዝብ አይን ውስጥ የኖረው ተዋናይ እና የማስታወቂያ ባለሙያ አርቲስት ጥላሁን ዘውገ ነው።
የተወለደው የዛሬ 55 አመት ታህሳስ 1 ቀን 1959 አ.ም አዲስ አበባ ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ነው።አባቱ መቶ አለቃ ዘውገ ወልደሩፋኤል ወታደር ነበሩ።በጃንሆይም በደርግም ዘመን አገራቸውን በውትድርና አገልግለዋል።እናቱ የቤት እመቤት የሆኑት ወ/ሮ ለገሴ ጸጋዬ ይባላሉ።ሁለቱ ሰዎች ከወለዷቸው ስድስት ልጆች መሐከል ጥላሁን ሁለተኛ ልጅ ነው። ቤተሰቡ ውስጥ ከሱ ቀድሞ የኪነ ጥበብ ዝንባሌ ያለው ሰው አልነበረም።ነገር ግን የተወለደበት እና እትብቱ የተቀበረበት ፈረንሳይ ለጋሲዮን አርቲስቶችን በማፍራት የታወቀ ነው።ስለዚህም በቤቱ ውስጥ የኪነ ጥበብ ዝንባሌ ባይኖርም የአካባቢው የጥበብ መንፈስ ጥላሁንም ዳብሶት ነበር።እነ ጥላሁን ገሰሰ ፤ እነ ሙናዬ መንበሩ ፤ እነ ተፈራ ካሳ ፤ እነ ሳህሌ ደጋጎ ፤ እነ ለማ ገብረ ህይወት ፤ እና ሌሎችም እውቅ አርቲስቶች የኖሩበት ሰፈር በጥላሁን ላይም ጥላ ቢጥል አይገርምም።
ጥላሁን እና ኪነ ጥበብ የተገናኙበት መንገድ አስገራሚ ነው።የሚማርበት ትምህርት ቤት ራስ ስዩም (በኋላ ሕዝባዊ ሠራዊት ትምህርት ቤት የተባለ) የ6ኛ ክፍል ተማሪ እያለ በክፍላቸው በደረጃ ከአንድ እስከ ስድስት የወጡ እና የደህና ቤተሰብ ልጅ በመሆናቸው ለድራማ የተመረጡ ተማሪዎች ስለ ቀድሞው የባሪያ አሳዳሪ ሥርዓተ ማኅበር ችግር የሚያወራ ድራማ እንዲሠሩ ተመርጠው ነበር።ድራማውን የሚለማመዱት ደግሞ ከትምህርት ክፍል ጊዜዎች በአንዱ ከክፍል ወጥተው ሌላ ባዶ ክፍል ሄደው ነው።ስለዚህም አንድ የትምህርት ክፍለ ጊዜ መዝለል ነበረባቸው።የተዘለለው ክፍል ጊዜ የእንግሊዝኛ ክፍለ ጊዜ ነው።
የእንግሊዝኛ መምህሩ ቁጡ ናቸው። ለመግረፍ ይበረታሉ።ጥላሁን ደግሞ የቤት ሥራ መሥራት አይሆንለትም። ደግሞም የዚያን ቀን የቤት ሥራ አልሠራም።ስለዚህም የዚያን ቀንም ዱላ ይጠብቀዋል። ያን ዱላ ለማምለጥ ያለው ብቸኛ አማራጭ ድራማ ሠሪ ባይሆንም ድራማ ሠሪዎቹን ተከትሎ መውጣት ነው። ወጣ። ድራማ ሠሪዎቹ ልምምድ ወደሚያደርጉበት ክፍል ሲሄዱ ጥላሁን አውላላ ሜዳ ላይ ቀረ። ደጅ መገኘት ሌላ ቅጣት ያስከትላል።ወደ ሽንት ቤት መሄድ ጀመረ።ወደዚያ ሲሄድ ደግሞ ሌላ ችግር ተፈጠረ። ዩኒት መሪው ወደዚያ እየመጡ ነው።ከተያዘ ሌላ ቅጣት ይከተለዋል።ግራ ገባው።ድራማ ሠሪዎቹ ጋር እንዳይገባ አይፈልጉትም።ክፍል እንዳይመለስ ዱላ ይጠብቀዋል።ደጅ እንዳያውደለድል ዩኒት መሪው አሉ።
ግራ ገብቶት ሲቁለጨለጭ አንድ አጋጣሚ ተከሰተ።ድራማ ሠሪዎቹ ጭቅጭቅ ጀመሩ።የጭቅጭቁ መንስኤ ደግሞ ድራማው ላይ ሁሉም ሰው ዘበኛ ሆኖ ለመሥራት አለመፈለጉ ነው።ጥላሁን ይሄን አጋጣሚ ማባከን አልፈለገም።እኔ ዘበኛ ልሁንላችሁ አላቸው ፤ ተስማሙ ፤ ተዋናዮቹን ተቀላቀለ ፤ ዱላውን አመለጠ። ድራማው ተሠርቶ ለተማሪዎች ሲቀርብ ተወዳጅነትን አገኘና ከአራቱ የስድስተኛ ክፍል ንዑስ ክፍሎች የነ ጥላሁን ክፍል አሸናፊ ሆነ።ለማሸነፉ ደግሞ ዋነኛው መንስኤ የዘበኛው አስቂኝ ገጸ ባህሪ ሆነ።ጥላሁን ዝነኛ ሆነ።እኒያ የሚፈራቸው መምህር እንኳን ጥላሁንን ወደዱት።ከዚያ ወዲያ ገርፈውትም አያውቁ።ጥበብ ጥላሁንን ከተገራፊነት አውጥታ የራሷ አደረገችው።
ቀጠለ።በተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያለ ሌላ ክስተት ተከሰተ።አማርኛ መምህሩ ዓርብ እለት ሁሉም ሰው 10 መስመር ድርሰት ጽፎ እንዲመጣ አዘዙ።የቤት ሥራው የሚቀርበው ሰኞ ነው።ቅዳሜና እሁድ በጨዋታ ታልፎ ጥላሁንም የቤት ሥራውን ሥራ ሳይሠራ ሰኞ ደረሰ።ሰኞ ጠዋት መምህሩ ክፍል እንደገቡ የቤት ሥራውን አውጡና ጠረጴዛ ላይ እንዲያስቀምጥ አዘዙ።ጥላሁን የቤት ሥራውን እንዳልሠራ ሲያውቅ ክው አለ።ነገር ግን ላለመገረፍ የአቅሙን መላ ዘየደ። ቀጭን እና ረዥም እንደመሆኑ እሱ ከኋላ ነው የሚቀመጠው።ስለዚህም መምህሩ ከፊት ጀምረው የእያንዳንዱን ተማሪ የቤት ሥራ እያዩ ያልሠራውን ለዱላ ሲያስወጡ ጥላሁን መጻፍ ጀመረ።
ከዱላው ስለማምለጥ እንጂ ስለ ድርሰቱ ጥራት አላሳሰበውም፤ጻፈ።እሱ ጋር ሲደርሱ በደመነፍስ የሞነጫጨራትን ድርሰት አቀረበ።አነበቡት።ያዝና ውጣ አሉት።ዱላው እንዳልቀረለት ሲያውቅ ደብተሩን ይዞ ወጥቶ ከሌሎች ተገራፊዎች ጋር ተንበረከከ።ተነስ ተነስ አሉ መምህሩ።የጻፈውን እንዲያነብ ተነገረው። ድርሰቱ ጥሩ ስለሆነ ሳይሆን ድርሰት እንዴት እንደማይጻፍ ለተማሪዎች ሊያሳዩበት እንደሆነ በማሰብ በጭንቀት የጻፈውን አነበበ።አጨብጭቡለት ተባለ።ያኔ መምህሩ ድርሰቱን እንደወደዱት አወቀ።በኩራት ልቡ ተሞልቶ ተገራፊ ጓደኞቹን ወደኋላ እየገረመመ ወደቦታው ተመለሰ።
ተፈሪ መኮንን ከነጥላሁን ሰፈር ትንሽ ራቅ ይላል።ያኔ ፈረንሳይ ለጋሲዮን ላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ስለሌለ ሁሉም ሁለተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ ተማሪ ተፈሪ መኮንን ሄዶ መማር ግዴታው ነበር።ከዚያ ግን ፈረንሳይ ለጋሲዮን ላይ ከፍተኛ 12 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተገንብቶ ሲጠናቀቅ ጥላሁን ወደ አዲሱ ትምህርት ቤት ገብቶ ትምህርቱን ቀጠለ።ጓደኞቹ የነበሩት እነ አለምነህ ዋሴ ፤ ጋዜጠኛ ሰለሞን ጥኡመ ልሳን እና ሌሎች ግን አንመለስም ብለው እዚያው ተፈሪ መኮንን ቀሩ።እሱ ወደ ከፍተኛ 12 ከተመለሰ በኋላ ተፈሪ መኮንን የቀሩት ጓደኞቹ እነሱ ትምህርት ቤት ሚኒ ሚዲያ የሚባል ነገር መጀመሩን አዳንቀው ነገሩት።ሚኒ ሚዲያ ምን እንደሆነ የማያውቀው ጥላሁን ተፈሪ መኮንን ጊቢ በአጥር እየገባ ስለሚኒ ሚዲያ ምንነት ከጓደኞቹ ተረዳ።
ስለ ሚኒሚዲያ ያየውን በልቡ ያኖረው ጥላሁን ወደ አዲሱ ትምህርት ቤት ጓደኞቹ መጥቶ ስለ ሚኒ ሚዲያ ምንነት አስረዳቸው ፤ እነሱም እንዲጀምሩ አነሳሳቸው።ተጀመረ።ያኔ ነው እንግዲህ የብዙ ዘመን የሥራ አጋሩ እና የረዥም ዘመን ጓደኛው ከሆነው አለልኝ መኳንንት ጋር የተገናኙት።እርግጥ ጥላሁን እና አለልኝ አባቶቻቸው ጓደኛ ሲሆኑ እነሱም ቢተዋወቁም ሚኒ ሚዲያ ግን የበለጠ አወዳጃቸው።ሚኒ ሚዲያው ተጀመረ።ሥራቸውም እየተወደደ መጣ።ያኔ ደግሞ ሌላ ታሪክ ተከሰተ።ወቅቱ ኤች አይ ቪ የጀመረበት ጊዜ ነበር።እናም ትምህርቱ ሁሉ ኤች አይ ቪ ምን ያህል ገዳይ እንደሆነ እና መድኃኒት እንደሌለው የሚሰበክበት ወቅት ነበር።በአንድ የተማሪዎች ግንዛቤ ማስጨበጫ ዝግጅት ላይም ተመሳሳይ መልዕክት ከተላለፈ በኋላ እነ ጥላሁን ድራማ እንዲያቀርቡ ተጋበዙ።
ድራማው መቅረብ ጀመረ።መልዕክታቸውም ኤድስ መድኃኒት አለው የሚል ነበር።መልዕክቱ በቦታው የነበረውን ሰው በሙሉ ክው አደረገ።በኋላ በድራማው መጨረሻ ላይ ግን መድኃኒቱ አንድ ለአንድ መወሰን መሆኑን ሲናገሩ ተመልካቹም መምህራኑም ሌሎችም እነ ጥላሁን መልዕክቱን ያስተላለፉበትን መንገድ አድንቀው እጅግ ሞቅ ያለ ጭብጨባ እና ፉጨት አሰሙ። ይሄኔ የአካባቢው ሕዝብ ሁሉ ልጆቻችንን ምን ሆኑብን ብሎ በድንጋጤ ወደ ትምህርት ቤቱ ጎረፈ።የነጥላሁን ዝናም መናኘቱን ቀጠለ።
እነ ጥላሁን ዘውገ ፤ አለልኝ መኳንንት ፤ አለባቸው ጽጌ እና ሌሎችን የያዘው ስብስብ በኪነት በኩል አልፎ ቀስ በቀስ ወደ ዋና መድረኮች መጓዙን ጀመረ።1985 ላይም የእነ ጥላሁን ተራ ደርሶ እነሱም በኢትዮጵያ ቴሌቪዢን የመታየት እድሉን አገኙ።ወቅቱ እነ አለባቸው እና ልመንህ ፤ ደረጄ እና ሀብቴ ፤ እንግዳ ዘርን እና አበበ በለው ፤አስረስ በቀለ እና ሌሎችም ከዋክብት መድረኩን ሁሉ የተቆጣጠሩበት ወቅት ነበር።ስለዚህም ጥላሁን እና አለልኝ በኮሜዲ ዘርፍ ቢመጡ እነዚህን ከዋክብት መብለጥ እንደሚያስቸግራቸው ስላወቁ ጠንከር ያሉ ይዘት ያላቸውን ድራማዎች ይዘው መጡ።ሕዝብ ወደዳቸው።ከዚያ በኋላ ለሁለት አስርተ ዓመታት ገደማ ከሺ በላይ ድራማዎችን ሠሩ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ጥላሁን 1992 ዓ.ም ላይ ትዳር የመሠረተ ሲሆን በአሁኑ ወቅትም የ4 ልጆች አባት ነው።ልጆቹ የጥበብ ዝንባሌ እንዳላቸው የሚናገረው ጥላሁን ነገር ግን እሱ ለትምህርት ሥራ ቅድሚያ እንደሚሰጥ ይናገራል።”ልጆቼ እኔን መብለጥ አለባቸው።ልጆቼ እኔን ከበለጡ አገሪቱ ታተርፋለች።እኔ ከበለጥኳቸው ግን አገሪቱ ቆማለች ማለት ነው” ይላል።
ጥላሁን አሁንም በሥራ ላይ ነው።ከመድረክ አልራቀም።የኛ ሰፈር የተሰኘ ቴአትር ላይ ይተውናል።የ5 ወር ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ አዘጋጅቶ እንደጨረሰም ነግሮናል።ከሥራ የተረፈውን ሰት በምን እንደሚያሳልፍ ጠየቅነው።”አሁን አሁን ተውኩ እንጂ ዋና መዋኘት እና ኳስ መጫወት እወዳለሁ።ከዚያ በተጨማሪ ከጓደኞቼ ጋር አብረን ጊዜ እናሳልፋለን።ለቤተሰቤም ጊዜ እሰጣለሁ” ይላል።
ለሕዝብ የሚያስተላልፈው መልእክት
”ለሁሉም ነገር ሰላም ነው የሚያስፈልገው።እዚሁ ሰፈር ላይ ቀይ ሽብር እየተባለ ሰው ሲገደል አይቻለሁ። ከዚያም በኋላ ብዙ ነገር አይቻለሁ።እኔ ያየሁትን ልጆቼ ባያዩት ደስ ይለኛል።እስካሁንም አገሪቱ እዚህ የደረሰችው በእግዚአብሄር እርዳታ ነው።አሁንም እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይጠብቃት” ብሎናል።እኛም አሜን ብለን ከአንጋፋው አርቲስት ጋር የነበረንን ቆይታ በዚሁ ቋጨን።ቸር እንሰንብት።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን መጋቢት 25 ቀን 2014 ዓ.ም