በኢትዮጵያ የማስታወቂያ ኢንዱስትሪ ውስጥ ከመሪዎቹ ዋነኛው እሱ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፤ ሰማያዊ ፈረስ በተሰኘ ፊልሙም የዓባይን እጣ ፈንታ እና ሰው ሰራሽ ደመናን ቀድሞ ተንብዩአል ፤ አብዬ ዘርጋው የተሰኘው ገጸ ባህሪውም በኢትዮጵያ የሬዲዮ ድራማ ታሪክ ውስጥ የማይረሳ ስም ተክሏል።
የዛሬው እንግዳችን ተዋናይ ፤ የማስታወቂያ ባለሙያ እና ስራ ፈጣሪ የሆነው አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ ነው። የተወለደው መሀል ካዛንቺስ ላይ ነው። ለቤተሰቡ የበኩር ልጅ ነው። አባቱ አቶ ፍቅሬ ምህርካ የማዘጋጃ ቤት ሰራተኛ እና በማህበራዊ ኑሮአቸው በነበራቸው ንቁ ተሳትፎ ታዋቂ የሰፈሩ አድባር ነበሩ። እናቱ ወ/ሮ በለጥሻቸው ማመጫም እንዲሁ የቤት እመቤት እና የሴቶች አውራ የነበሩ እናት ናቸው። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በአስፋው ወሰን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሁለተኛ ደረጃውን ደግሞ ምስራቅ አጠቃላይ ተምሯል።
በትምህርቱ በጣም ጎበዝ ከሚባሉት ባይሆንም ለክፉ የምሰጥ ተማሪ አልነበርኩም ይላል። እንደማንኛውም ተማሪም በኋላ ላይ ፓይለት ለመሆን እቅዶ ነው ይማር የነበረው። የፓይለት ምኞቱ እንዳለ ቢሆንም፣ የነፍሱ ጥሪ ግን ለጥበብ ሆነ። እሳት የላሰ ተማሪ፣ እንደ ጓደኞቹም ለስፖርት የሚሆን አይነት ተክለ ሰውነት አልነበረውም። አፈጣጠሩ ለጥበብ ነበር። በተለይም እንደ ብጤዎቹ ወንድ ወጣቶች ስፖርታዊ ነገር ላይ የተቀላጠፈ አለመሆኑ ቀስ በቀስ ወደ ጥበብ እንዲሳብ አደረገው። በወቅቱ እሱ እና ጓደኞቹ የመሰረቱት ሀራምቤ የሚባል ቡድን ነበራቸው። አፍላው ሰራዊትም የቡድኑ መስራች አባል ነበር።
ስለዚህም ቋሚ ተሰላፊ ሆኖ ወደ ሜዳ ይገባል። ነገር ግን ኳሱ እንደታሰበው አልሆነም። አጥቂ ሆኖ የገባው ሰራዊት ሲገፋ የትኛውም የሜዳው ክፍል ላይ ለመጫወት አስተማማኝ ባለመሆኑ ምደባው በረኝነት ላይ ደረሰ፤ እሱም አልሆነም። ከእግር ኳስ ጋር የቀረው የመጨረሻ እድል ተጫዋች ወይም በረኛ መሆን ሳይሆን የስፖርት ዘጋቢ መሆን ነበር፤ ሆነ፤ ተሳካለት። ይህ ትንሽዬ ስኬት ለቀጣይ የሕይወት አቅጣጫው ጠቋሚ ሆነ። የሰራዊት አባት የመንግስት ሰራተኛ ቢሆኑም አጎቶቹ ግን የሰራዊቱ አባል እና ከፍ ያለ ማእረግ ላይ የደረሱ የጦር መሪዎች ነበሩ።
ወደ እነሱ ቤት ሲመጡ በወታደራዊ የማእረግ ልብሳቸው ተውበው ነበር። ይህ አለባበሳቸው በሰራዊት ልቦና ላይ የውትድርናን ፍቅር ማሳደር ያዘ። ለሰራዊቱ ያለው ፍቅር ሰንብቶ ሰራዊትን በብሄራዊ ውትድርና ተቀላቅሎ ለ2 አመት ከ9 ወር አገሩን እንዲገለግል አደረገው።
እዚያም እያለ ከመሰረታዊ የውትድርና ልምምድ ጎን ለጎን ኪነጥበባዊ ስራዎችን የሚሰራበት እድል አገኘ። ከብሄራዊ ውትድርና ሲመለስ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ በቋንቋና ስነ ጽሁፍ ተመረቀ። ወደ ሕይወት እጣ ፈንታው መጓዝ የጀመረው ሰራዊት ቀጣዩ እርምጃው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ያስተዋወቀውን የአብዬ ዘርጋውን ገጸ ባህሪ መተወን ሆነ። የአብዬ ዘርጋው ታሪክ ለየት ያለ ነው። ሰራዊት እና ጓደኞቹ በኢትዮጵያ ቤተሰብ መምሪያ ስር የተቋቋመ አፍለኛ የቴአትር ቡድን የተባለ ስብስብ ነበራቸው።
የድራማው ደራሲ ሰለሞን አለሙ ነው። የድራማው ስምም ሸምጋይ የተባለ ነው። ድራማው ለመጀመሪያ ጊዜ ሲተላለፍም 5 ክፍሎች ብቻ ነበሩት። ሰራዊት እና ጓደኞቹ ያን አምስት ክፍል ድራማ ለሬዲዮ ጣቢያው ካስረከቡ በኋላ ወደ ጣቢያው አልሄዱም። አምስቱ ክፍል ተላልፎ ከተጠናቀቀ በኋላ ሰራዊት እና ጓደኛው ከረሜላ የተባለ ሌላ የሬዲዮ ድራማ ለጣቢያው ለማሳየት ሲሄዱ ሬዲዮ ጣቢያው በአንድ እግሩ ቆመ። ለካስ የጣቢያው ሀላፊዎች በአምስት ክፍል ብቻ የተጠናቀቀውን ድራማ ባለቤቶች እየፈለጉ ማግኛውን መንገድ አጥተው ተቸግረው ነበር። ተፈላጊ እና ፈላጊ ተገናኙ። በሉ ይሄን ድራማ ቀጥሉ ተባለ፤ ተቀጠለ።
34 ክፍል ተጨመረበት። 39ኛው ክፍል ላይ አብዬ ዘርጋውን ውሀ ወሰዳቸውና ድራማው ተጠናቀቀ። የድራማው አጨራረስ ሕዝቡን ስላናደደ ድራማው አሁንም እንዲቀጥል ተደረገ። ሌላ 40 ክፍል ተጨመረ።
ታሪካዊው የሬዲዮ ድራማ በሰራዊት ፍቅሬ መሪ ተዋናይነት ለ79 እሁዶች የሕዝብን ቀልብ ሰቅዞ እንደያዘ ዘለቀ። ሰራዊት ፍቅሬም ታሪካዊ የሆነ ስምን በሕዝብ አእምሮ ውስጥ ጻፈ። ሁለተኛው የሰራዊት ታላቅ ሙያዊ እመርታ ሰማያዊ ፈረስ ፊልም ነው። ሰማያዊ ፈረስ በዓባይ ወንዝ ዙሪያ የታየ አስገራሚ ርእይ ነበር። ፊልሙ ዛሬ ላይ እውን ሆነው የምናያቸውን በዓባይ ወንዝ ላይ የሚደረግ ልማትን እንዲሁም ሰው ሰራሽ ዝናብ ማዝነብ አንድ ላይ አዳቅሎ የሚያወሳ ጥበባዊ ርእይ ነው።
በወቅቱ የፊልሙን ሀሳብ የሰሙት ጓደኞቹ እንዲያው ይሄ ነገር ቢቀርብህ እና የተለመደውን የፍቅር ወይም የኮሜዲ ዠነር ብትከተልስ ብለውት ነበር። እሱ ግን በሀሳቡ ጸና። እንዲያውም እያካሄደ የነበረውን መኖሪያ ቤት ግንባታ አቁሞ ፊልሙን ለመስራት የገዛ ገንዘቡን ሲያውል ይህን የሰሙት ወላጅ አባቱ በንዴት ጡፈው አባታዊ ግሳጼያቸውን አሰምተውት ነበር። ነገር ግን በሀሳቡ ገፍቶ ፊልሙን ሰራ። ፊልሙ በወቅቱ ከፍተኛ ተወዳጅነት እና ገቢ ያገኘ ፊልም ሆነ። ነገር ግን ሰማያዊ ፈረስ የአንድ ሰሞን ኪነ ጥበባዊ ብልጭታ ሆኖ አልቀረም።
ታኅሳስ 1997 የተሰራው ፊልም ከ6 አመታት በኋላ በ2003 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን የመሰረት ድንጋይ ሲጥሉ ከምናብነት ወደ እውነታነት ተሻገረ። ሰው ሰራሽ ዝናብ የማዝነቡም ሀሳብ በ2013 ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ባሉበት በተግባር ሲፈጸም ታየ። ዛሬ ላይ ሰራዊት ያን ጥበባዊ ርእዩን መሬት ላይ ያለ ሀቅ ሆኖ ሲያየው እንደሚደሰት ይናገራል።
ያኔ ፊልሙ ከሲኒማ ከወረደ በኋላ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እንዲታይለት ጥያቄ ቢያቀርብም ተቀባይነት ያላገኘው ሰራዊት በ2003 የህዳሴ ግድብ የመሰረት ድንጋይ ሲጣል ግን ጣቢያው ፊልምህን እናሳይ ብሎ እንደመጣበት ያስታውሳል። ያስገረመው ነገር ግን ያኔ እሱ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ፊልሙን እንዲያሳይለት በሚጠይቅበት
ሰዓት የኤርትራ ቴሌቪዥን ያሳየው ነበር። አሁን ላይ ሰራዊት ቢሳካ እንኳ በልጅ ልጆቼ ዘመን ነው ብሎ ይገምት የነበረው የሰማያዊ ፈረስ ሀሳብ እውን ሆኖ ሲያየው የተሰማው ደስታ ከሚገልጸው በላይ እንደሆነ ይናገራል። የሰራዊት ሌላኛው ከፍታ በማስታወቂያው ዘርፍ ከአርቲስት ሙሉአለም ታደሰ ጋር ያኖረው ግዙፍ አሻራ ነው። አጋጣሚው የተፈጠረው በአዋሽ ባንክ ማስታወቂያ ነው። ከዚያ ማስታወቂያ በፊት ሰራዊት እና ሙሉአለም በዝና ካልሆነ በቀር በአካል የሚተዋወቁ ሰዎች አልነበሩም።
እሱ ማዘጋጃ ቤት እሷ ብሄራዊ ቴአትር ነበር የሚሰሩት። አብርሃም ጸጋዬ እና ጥላሁን ታፈረ የሚባሉ ፕሮዲውሰሮች ነበሩ ሁለቱን ተዋናዮች የመረጡት። የተመረጡት ተዋንያን እና ፕሮዲውሰሮቹ የቀጠሮ ቦታቸው ካዛንቺስ ሆነ፤ ተገናኙ ፤ ተነጋገሩ። ስክሪፕቱ ተሰጣቸው። ስክሪፕቱ ገንዘባቸውን በማሰሮ ቤት ውስጥ ቀብረው የተኙ አባወራ እና እማወራ በህልም ገንዘባቸውን ሲዘረፉ የሚያሳይ አጭር ትእይንት ነበር። የመጀመሪያ ስራቸውም በዚያ መልኩ ተሰራ።
ከፍተኛ ተወዳጅነት አገኘ። የባንኩን ማስታወቂያ ተከትሎ አዋሽ ኢንሹራንስም ቀጠለ። ከዚያ በኋላ ወደ 3ሺ አምስት መቶ ገደማ የሬዲዮና ቴሌቪዥን ማስታወቂያዎችን በመስራት የኢትዮጵያ የማስታወቂያ ኢንዱስትሪ ንጉስ እና ንግስት መሆናቸውን አወጁ። ሰራዊት ባለትዳር እና የሁለት ልጆች አባት ነው።
ባለቤቱን ያገኛት ደግሞ በአንድ ጓደኛው ሰርግ ላይ ሚዜ ሆነው ነው። ለትውውቃቸው መንስኤ የሆነው ግን ሚዜ መሆናቸው ሳይሆን በሰርጉ ላይ የተፈጠረ ጠብ ነው። ነገሩ እንዲህ ነው። የሰርጉ ቀን ሙሽራው ወደ ሙሽሪት ቤት ሄዶ ሙሽሪትን ከያዘ በኋላ ጉዞው ወደ መናፈሻ እንዲሆን ነበር። ነገር ግን ወደ መናፈሻ ሲኬድ ከሴት ቤት መያዝ ያለበት የአገልግል ምግብ ነበር። ያን የመያዝ ግዴታም የሴት ሚዜዎች ነው። እንደ አጋጣሚ ሆኖ አገልግሉ ተረሳ። የሙሽሪት ቤት ኦሎምፒያ ሲሆን መናፈሻው ደግሞ ኮተቤ ነበር። ነገሩ እንደዛሬው ቀላል አልነበረምና በመኪና ላጥ ብሎ ሄዶ ምግቡን ማምጣት አልተቻለም።
በወንድ ሚዜዎች እና በሴት ሚዜዎች መካከል የጦፈ ጠብ ተነሳ። ወንድ ሚዜዎች ሴቶቹን ተቹ። ይህ ትችት እና ዘለፋ ግን ከሚዜዎቹ አንዷን ክፉኛ ስሜቷን ጎድቷት ወደጓሮ ሄዳ እያለቀሰች ነበር።
ሚዜዎቹን ሲቆጥር አንዲት ሚዜ የጎደለችበት ሰራዊት ዞር ዞር ብሎ ሲያይ ያቺ ሚዜ ወዲያ እልፍ ብላ እንባዋን እያፈሰሰች ተመለከታት። ጠጋ ብሎ አባበላት። እሷን ማንም እንዳይነገራትም አዘዘ።
በጠብ ውስጥ ፍቅር ተወለደ። ከዚያ ወዲያ ያለው ነገር ታሪክ ነው። እነሆ በዚያች ቀን የተመሰረተ ግንኙነት 9 አመት በወዳጅነት 20 አመት በትዳር በጠቅላላው 29 አመት ዘልቋል ፤ ሁለት ልጆችንም አፍርቷል። የመጀመሪያ ልጁ ልዑል አሁን በአሜሪካ አገር በትምህርት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ ከአንድ በላይ ዲግሪዎችን በከፍተኛ ውጤት እየተመረቀ የያዘ እሳት የላሰ ጎበዝ ተማሪ እንደሆነ ሰራዊት በኩራት ይናገራል። በቅርቡም አባት እና እናት አሜሪካ ሄደው ልጃቸውን አስመርቀው መጥተዋል። ትንሹ ሚካኤል የሚባል ሲሆን እዚሁ ተማሪ ነው።
ትልቁ ልጁ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ አገሩን ማገልገል እንደሚፈልግ የሚናገረው ሰራዊት፣ በየቀኑ በሚኖራቸው የስልክ ውይይትም አብዛኛውን የውይይታቸው ክፍል ስለ ኢትዮጵያ በማውራት እንደሚያሳልፍ ይናገራል። በሙያዊም ሆነ በቤተሰባዊ ሕይወቱ እንደተሳካለት በግልጽ የሚታየው ሰራዊት አሁን ላይም ቢሆን ስራውን በትጋት እንደሚሰራ ይናገራል። ከሰራተኛነት በተጨማሪም ስራ ፈጣሪ ነው። በአንድ የሬዲዮ ጣቢያ ላይ ባለድርሻ መሆንን ጨምሮ የተለያዩ ከኪነ ጥበብ ውጭ የሆኑ የግል ስራዎችን ይሰራል።
የኪነ ጥበብ ባለሙያው አሁንም በቸገረው ቁጥር ሕዝብን መለመኑ መጥፎ ልማድ እንደሆነ የሚገልጸው ሰራዊት፣ በተለይ ከምእራቡ ዓለም የኪነ ጥበብ ሰዎች ልምድ በመቅሰም ከኪነ ጥበብ ስራው በተጨማሪ የግል ስራዎችን መስራት አለበት ብሎ እንደሚያምን ይናገራል።
እሱ በግሉ ከኪነ ጥበባዊ ስራው በተጨማሪ የግል ስራዎችን እንደሚሰራ ጠቅሶ፣ በተለያዩ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ውስጥ በቦርድ አባልነት እና በሌሎች መልኮች እንደሚሳተፍ ይናገራል። ራሱን ግን ባለሀብት ሳልሆን ባለጸጋ ነኝ ብዬ አምናለሁ በማለት ይገልጻል።
አሁን ላይ ያሉ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የሆኑ ወጣቶች በብዙ ተሰጥኦ የታደሉ እና ብዙ ቴክኖሎጂያዊ ድጋፍ ያላቸው እንደሆነ የሚናገረው ሰራዊት፣ በስራዎቻቸው ይዘት ላይ ስጋት እንዳለው ግን ይናገራል። ትውልድን የሚያንጽ እና ዘመን ተሻጋሪ ስራዎችን መስራት ላይ መሻሻል እንደሚስፈልግ ይናገራል።
ለዚህም እሱን ጨምሮ ሁሉም አንጋፋ አርቲስቶች ድጋፍ ማድረግ እንዳለባቸው ይናገራል። የአገሩ ጉዳይ እንደሚያሳስበው የሚናገረው ሰራዊት ኢትዮጵያ ሁሌም ቢሆን የጸሎቱ ዋነኛ ርእስ እንደሆነች ያወሳል።
”አንዳንዴ በአገር ደረጃ ነገሮች ደብለቅለቅ ሲሉ ሊነጋ ሲል ይጨልማል ብዬ አምናለሁ”ም በማለት አሁን ካለው አስቸጋሪ ሁኔታ የሚሻገር ተስፋ እንደሚታየው ይናገራል። በውትድርና ከማገልገል አንስቶ በሙያውም ሆነ በሌሎች መልኮች አገሩን እንዳገለገለ እና ለአገሩ ያለው ፍቅር ከአፍ ባለፈ በተግባር የሚገለጽ መሆኑንም ይገልጻል። ሰራዊት የእረፍት ቀኑን በመዝናናት እንደሚያሳልፍ ይገልጻል።”ወጣ ብዬ እዝናናለሁ።
አንዳንዴ ከልጃችን እና ከጓደኞቹ ጋር አንዳንዴ ደግሞ እኔና ባለቤቴ ለብቻችን ወጣ ብለን የራሳችንን ቫለንታይ ደይ እናከብራለን። ያው ወጣቶቹ የሚገኙባቸው ቦታዎች ላይ ድሮ ስለሄድን አሁን ተለቅ ተለቅ ያሉ ሰዎች ያሉባቸው የመዝናኛ ቦታዎች ላይ እየሄድኩ እዝናናለሁ።
ከዚያ ውጭ አባል የሆንኩባቸው የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ስብሰባዎች እና ሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮችም በእረፍት ቀን የሚከናወኑ በመሆናቸው የእረፍት ቀኔን በነዚህ አይነት ስራዎች ነው የማሳልፈው” ብሎናል። በቀጣይ ዶግ አመድ የተሰኘ ትልቅ ፊልም እያዘጋጀ መሆኑን እንዲሁም የራሱን ቶክሾው የመፍጠር እቅድ እንዳለው የሚናገረው ሰራዊት ለከርሞውም ከግል ታሪኬ ይልቅ ሌሎች የማስባቸውን ሀሳቦች የያዘ መጽሐፍ የመጻፍ ፍላጎትም አለኝ ብሏል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን የካቲት 20 /2014