በኦሮምኛ ቋንቋ ድምጻዊ ነው፡፡ ነገር ግን የሚዘፍነው ለኦሮሞ ብቻ አይደለም፡፡ ሙዚቃ የዓለም ቋንቋ ናት የሚለውን ብሂል በሚያሳይ መልኩ ሙዚቃዎቹ ኦሮምኛን ፈጽመው በማያውቁ ሰዎች ዘንድ ሁሉ የተወደዱ ናቸው፡፡
እስካሁን ከ260 በላይ ዘፈኖችን ተጫውቷል፤ ስድስት አልበሞችንም ለህዝብ አድርሷል፡፡ ይህ ሰው አሊ ቢራ ይባላል፡፡ ሰሞኑን የጤና እክል አጋጥሞት በሆስፒታል የሚገኝ ሲሆን፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና በኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ሽመልስ አብዲሳ ተጎብኝቷል፤ በርካታ አድናቂዎቹም እየጎበኙት ይገኛሉ። ከህመሙ እያገገመ እንደሆነም ተነግሯል፡፡ በቅርቡ በትክክለኛ ቦታው ማለትም በመድረክ እንደሚታይም እየተጠበቀ ነው፡፡
አሊ ቢራ የተወለደው በ1940 ዓመተ ምህረት በድሬዳዋ ከተማ ነው፡፡ እናት እና አባቱ ያወጡለት ሥም አሊ መሐመድ ሙሳ ይባላል። ይሁንና ገና የ14 አመት ታዳጊ እያለ የኦሮሞን ሙዚቃ ለማሳድግ በተቃቋቋመው አፍረን ቀሎ የሙዚቃ ቡድን ውስጥ ሲገባ በቡድኑ ውስጥ ሌላ አሊ የሚባል ልጅ በመኖሩ ሁለቱን ለመለየት መጀመሪያ ከሚያዜመው “ቢራ ዳ ባሬ” ዘፈን ወስደው “አሊ ቢራ” የሚለው ሰም ተሰጠው።
አሊ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በመድረስ ጅዲዳ እና በልዑል መኮንን ትምህርት ቤት እንዲሁም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ወደ አዲስ አበባ በመሄድ በካቴድራል ትምህርት ቤት ተከታትሏል። አሜሪካን አገር በሚገኘው የሳንታ ሞኒካ ኮሌጅም የሙዚቃ ትምህርት እንደተከታተለ ይነገራል።
አሊ ቢራ ለመጀመሪያ ጊዜ መድረክ ላይ መዝፈን የጀመረው በ15 አመቱ ማለትም በ1955 ድሬዳዋ ውስጥ በአፍረን ቀሎ ባንድ በአጃቢ ድምጻዊነት ነው፡፡ ከዚያም በክቡር ዘበኛ ኦርኬስትራ ተቀጥሮ ለሶስት ዓመታት ተጫውቷል። ችሎታው እየጎለበተ ሲሄድም አይቤክስ ባንድን በመቀላቀል ለስምንት አመታት የሙዚቃ ሥራውን በዲ-አፍሪክ አቅርቧል።
በአሊ ዙሪያ የተጻፈው የምስራቁ ዋርካ የተሰኘ መጽሐፍ ስለወቅቱ ሁኔታ እንዲህ ሲል ያብራራዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ1977 መጀመሪያ አካባቢ አሊ ከአይቤክስ ባንድ ጋር ኮንትራት መፈራረሙን ተከትሎ የዛምቤዚ ክለብንና የዲ-አፍሪክ ሆቴልን ለቆ በራስ ሆቴል ስራ ጀመረ፡፡ በወቅቱ የደንበኞች ቁጥር በመቀነሱ ምክንያት የአይቤክስ ባንድ በራስ ሆቴል የሚያቀርበውን ዝግጅት ቅዳሜ ማታ ብቻ ለማድረግ ተገዶ ነበር፡፡
ማህሙድ አህመድንና ሌሎች ስመ-ጥር ሙዚቀኞችን ያቀፈው አይቤክስ ባንድ አሊን ማግኘቱ የተቀዛቀዘውን የሆቴሉን ደንበኛ በማነቃቃት ገቢው ከፍ እንዲል ማድረግ እንደሚችል በማመን ነበር 1000 ብር የወር ደመወዝ ሊከፍሉት የተስማሙት፤ አሊ የስራ ስምምነቱን ከመቀበል ባለፈ በአጭር ጊዜ ውስጥ በ2000 ብር የአይቤክስ ሙዚቃ መሳሪያዎችን አክሲዮን መግዛት ቻለ፡፡
እ.ኤ.አ በ1979 የአሊና የአይቤክስ ባንድ ወዳጅነት ጠንክሮ “አማሌሌ” የሚል መጠሪያ የተሰጠውን ለእርሱ አራተኛ ከባንዱ ጋር የመጀመሪያ የሆነውን አልበም ለገበያ አበቃ፡፡ የአልበሙ መጠሪያ የሆነው “አማሌሌ” ዘፈን አሊ ባደገበት በምሥራቁ የአገሪቱ ክፍል የሚዘወተር ባህላዊ ዘፈን ሲሆን፤ አሊና ማህሙድ አህመድ በኦሮምኛና በአማርኛ እየተቀባበሉ በዘመናዊ መልኩ ተጫውተውታል፡፡
አይቤክስ ሙዚቃ ቤት የአልበሙ አሳታሚና አከፋፋይ ሲሆን በወቅቱ ኦሮሞዎች ስራውን የተቀበሉበት የደስታ ስሜት ዛሬ ድረስ በህይወት ያሉ እማኞች በመገረም ያስታውሳሉ። “የሰዉ አቀባበልና ከአልበሙ ሽያጭ የተገኘው ትርፍ ከጠበቅነው በላይ ነበር” ይላል የሙዚቃ ቤቱ ባለቤት አቶ ጣሃ አህመድ (የማህሙድ አህመድ ወንድም) ስለ አልበሙ ሲያስታውስ፡፡
የአልበሙ ሽያጭ አስጨንቆት የነበረው ሙዚቃ ቤት የካሴቱን ዋጋ ከተለመደው 15 ብር ወደ 12 ብር እንዲወርድ አድርጎ የነበረ ሲሆን ፣ ከዚህ በፊት ባልተለመደ ሁኔታ ቁጥሩ እጅግ የበዛ ህዝብ አልበሙን በእጁ ለማስገባት በመፈለጉ ማዳረስ እንኳን አልተቻለም፡፡ የመግዛት አቅምና አጋጣሚውን ያገኘ አልበሙን ተረባርቦ ገዛ። ያልቻለው ደግሞ አንዱ ከአንዱ እየተዋዋሰ አልበሙን ይኮመኩም ያዘ፡፡ “አማሌሌ” አልበም በወቅቱ የነበረውን ፖለቲካዊ ውጥንቅጥ ከፍቅርና ከባህል ጋር ደባልቆ ለአደባባይ ቢያቀርበው የብዙዎችን ጆሮ አጠመደ፤ ከብዙዎች አንደበት አልጠፋ አለ፡፡
…እ.ኤ.አ 1979 የአይቤክስ፣ ዳህላክ እና ዋቢ ሸበሌ ባንዶች ያለፈ ታሪክ ከል የለበሰበት ዓመት ነበር፡፡ ሱዳኖች የባንዶቹን መሳሪያ ተጫዋቶች አገራቸው ወስደው እንዲጫወቱ ስላግባቧቸውና ስምምነት ላይ ስለደረሱ ሶስቱም የሙዚቃ ቡድኖች ነፋስ እንዳየው ገላባ ብትንትን ብለው ፈረሱ።
ይህን ተከትሎም አንዳንድ የአይቤክስና የዳህላክ ባንድ አባላት ተሰባስበው ዋልያስ ባንድ በሚል ስያሜ በሂልተን ሆቴል መስራት ጀመሩ። ማህሙድ አህመድም ባንዱን ተቀላቀለ፡፡ ለአሊ ግልፅ ባልሆነ ምክንያት የአይቤክስ ባንድ አባላት ወደ ሂልተን ሄደው ስራ እንደጀመሩ በእሱ ምትክ ተክሌ ተክለእግዚ ቡድኑን እንዲቀላቀል አደረጉ።
ከእነዚህ የሙዚቃ ቡድኖች የተረፉት ሌሎች ሙዚቀኞች በመሰባሰብ ሌላ ባንድ መስርተው በራስ ሆቴል ለመስራት ሀሳብ አቀረቡ፡፡ የራስ ሆቴልም አሊን የሚቀላቅሉት ከሆነ ብቻ ሀሳባቸውን እንደሚቀበል አስታወቀ፡፡ ሙዚቀኞቹም በመስማማታቸው ሙሉቀን መለሰ /ከዳህላክ ባንድ/፣ ዳዊት ሰንበታ /ቤዝ ጊታር ተጫዋች/፣ ግርማ ወልደሚካኤል /ሳክስፎን ተጫዋች/፣ ሽመልስ በየነ /ትራምፔት ተጫዋች በጋራ ሆነው ኢትዮ-ስታር ባንድን መሰረቱ፡፡
ኢትዮ-ስታር ባንድ ከራስ ሆቴል ኩኩ ሰብስቤ፣ ግርማ ጭብሳና ሌሎች ዘፋኞችን ጨምሮ በመያዝ ጅቡቲ፣ የመንና የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ በመዘዋወር የሙዚቃ ስራውን ማሳየት ችሏል። በጥቅሉ አሊ በራስ ሆቴል ለ7 ዓመታት የሰራ ሲሆን ከዚህም ውስጥ 3ቱን ዓመት ከአይቤክስ ባንድና ቀሪውን 4 ዓመት ደግሞ ከኢትዮ-ስታር ባንድ ጋር አሳልፏል፡፡
አሊ ከዚያ በኋላ ከአገር በመውጣት በተከታታይ ወደ ሳወዲ አረቢያ ፣ ስዊድን እና አሜሪካ በመሄድ የኖረ ሲሆን በርከት ላሉ ዓመታትም ከአገር ርቆ ነበር፡፡ አሊ ቢራ ከመዝፈንም ባሻገር ፒያኖ ፣ ጊታር፣ እና ኡድ የተባሉ የሙዚቃ መሣሪያዎችን እንደሚጫወትም ይነገራል ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ብዙዎች አሊን ከድምጻዊነትም በላይ በታጋይነት ያነሱታል፡፡ በፈረንጆቹ 2019 ከቢቢሲ ጋር ባደረገው ቆይታ ስለዚህ ጉዳይም ተጠይቆ “የተመልካቹና ስለኔ የሚያወራ ሰው የሚያውቀውን ነው የሚያወራው። ታጋይ መሆኔን ወይም እምቢተኛ ከሆንኩኝ የሰው ትርጓሜ ነው። ስለ አሊ ቢራ የዛ ሰው ትርጓሜ ነው። ስለዚህ እኔ ሰዎች አሁን እንዳልሽኝ ታጋይ ነው ሲሉ፤ እርግጥ ታጋይ ማለት ትልቅ ነገር ነው። ስለ ሀቅ የሚታገል ከሆነ። እኔ የሀቅ ታጋይ ነኝ ብዬ ነው ራሴን የምፈርጀው። አንዳንድ ሰዎችም እንደዛ ይሉኛል። በተቃራኒውም የሚሉኝም አሉ። የሀቅ፣ የመብት፣ የሰላም፣ የበጎ ነገር ታጋይ ነኝ እላለሁ።” ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡
አሊ ዓለም አቀፍ ሰው ነው፡፡ በርካታ ቋንቋዎችን አቀላጥፎ ይናገራል፡፡ አቀላጥፎ ከሚናገራቸው ቋንቋዎች ውስጥ ኦሮምኛ፣ አማርኛ፣ ሶማሊኛ፣ አፋርኛ፣ ሃረሪኛ፣ አረብኛ እና እንግሊዝኛ በዋናነት ይጠቀሣሉ።
ሙዚቃዎቹም ዓለም አቀፍ መልእክቶችን የያዙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጉዳይም ሲያወጋ “በኦሮምኛ ‘ሲን ጃለዳ’ ካልኩ በአማርኛ ‘እወድሻለሁ’ ማለት ነው። በእንግሊዘኛ ‘አይ ላቭ ዩ’ ማለት ነው። በኦሮምኛ ‘ሲን ጃለዳ’ ስለሆነ በሌሎች ቋንቋዎች መተርጎም አይችልም ማለት አይደለም። ተተርጉሞ ‘ግሎባል’ (ዓለም አቀፍ) ይሆናል። በፈረንሳይኛ፣ በቻይንኛም ይሁን በፈለገው ቋንቋ እወድሻለሁ፣ እወድሻለሁ ነው።” ብሏል
በመቀጠልም ‹‹አንድ ጊዜ አፍረንቀሎ ውስጥ ሳለን ሳንሱር ተደርጎ ነበር። ዘፈን በአማርኛ ተርጉሙና አምጡ ተብለናል። እኛ ማታ ለኮንሰርት ተዘጋጅተናል፤ እና ሁሉንም ነገር (ወደ 30 ዘፈን) በአማርኛ ተርጉሙ ተባልን። በኦሮምኛ “ጃለላ” ፍቅር ማለት ነው። ዘፈኑ ውስጥ ለአንዲት ልጅ ወይም ለፈለገው ነገር ፍቅር ሊኖረው ይችላል። ሰውየው “ጃለላ” ማለት ምንድን ነው? ሲለኝ ፍቅር ነው እላለሁ።
‘አዎ፤ ፍቅር ማለት እንደሆነ እናውቃለን፤ ግን እናንተ የምትሄዱበት መንገድ ይህ ፍቅር ምን አይነት ነው?’ አለኝ። ይታይሽ እንግዲህ አንድን ቃል በሁለት ቦታ ለመክፈል አይደለም “ጃለላ” የተባለው። “ጃለላ” ፍቅር ነው። የእናት፣ የአባት፣ የአገር ሊሆን ይችላል። ሙዚቃ መልዕክቱን ለሰው የሚያደርሰው የአንድ ቋንቋ ብቻ ሆኖ አይደለም። የዓለም ነው። በጎም መጥፎም ቢሆን። ሁሉም ቦታ ስላለ ነው።” ብሏል፡፡
ሰዎች በሙዚቃው እና በዓለም አቀፋዊ ሰብእናው ቢያውቁትም እሱ ግን ራሱን የሚገልጸው በተማሪነት ነው፡፡ “እኔ ተማሪ ነኝ፤ እኔ ብቻ ሳልሆን ምድር ላይ ወደ 7 ቢሊዮን ከምናምን ተማሪዎች አሉ። ከነዛ መሀል አንዱ ነኝ። ራሴን የማየው በዛ አይነት መንገድ ነው። ዛሬም እማራለሁ፤ ነገም እማራለሁ፤ ትላንትም ተማርኩ።”ብሏል፡፡
አሊ ቢራ ታዋቂ በሙዚቃው ሙያ ከግማሽ ክፍለ-ዘመን በላይ ለሚቆጠሩ ዓመታት ላበረከተው አስተዋፅኦም ከጅማ እና ድሬደዋ ዩኒቨርሰቲዎች የክብር ዶክትሬት ተሸላሚ ለመሆን የበቃ ሲሆን፣ ባለፈው ዓመትም የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት እጅግ ትልቁን የክብር ሽልማት፤ የወርቅ ኒሻን አበርክቶለታል፡፡
ባለቤቱ ሚስስ ሊሊ ማርቆስም በገዳ ሥርዓት መሠረት የ ‘ኦርሜሱ’ (ኦሮሞ ማድረግ ) ስነ-ሥርዓት ተደርጎላት ‘ኢሊሊ ቢራ’ ተብላ ተሰይማለች፡፡ ትርጉሙም የፀደይ አበባ ማለት ነው፡፡ ከዚህም ባለፈ በጣም በርካታ ሽልማቶችን ከተለያዩ አካላት በየጊዜው ተረክቧል፡፡
በአሊ ዙሪያ ያዘጋጀነውን አጭር ጽሁፍ የምንጨርሰው አሊ ከብዙ አስርት ዓመታት በፊት በዘፈነው እና ዛሬም ድረስ በብዙዎች እንደ መጽሐፍ ቃል በሚጠቀሰው ስንኝ ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡-
ረቢሞ ነሙማ ከን ሴራ ጀሊሴ
ሀቲ ቴኛ ተካ ማልቱ አዳን ኑ ባሴ
ትርጉም
ፈጣሪ ወይንስ ሰው ነው ህጉን የቀየረው
በእናታችን አንድ ሆነን የለያየን ምንድን ነው
የአንድ እናት አባት ልጅ ለራስ ወንድም ነው
ለምን ነው እንደ አውሬ ልጅ የምንጠላላው፡፡
አበቃን፤ ቸር ይግጠመን፡፡
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ጥር 16/2014