ሞገደኛው ዳምጤ…..ኢትዮጵያ ሬድዮን የሰማ ሰው ይህን አጭር ልቦለድ በሚገባ ያውቀዋል። በድምጸ ነጎድጓዱ ጋዜጠኛ ደጀኔ ጥላሁን አስተዋዋቂነት በታላቁ የጥበብ ሰው ፍቃዱ ተክለማርያም ሲተረክ ብዙዎች ሰምተውታል፤ ወደውታል፤ ደራሲውንም አድንቀዋል። የዛሬው ቆይታችንም ከዚሁ ታላቅ ደራሲ እና ጋዜጠኛ ጋር ነው።
ጋዜጠኛ እና ደራሲ አበራ ለማ የሞገደኛው ነውጤ እና የብዙ ተወዳጅ የሥነ ጽሁፍ ሥራዎች ወላጅ ነው። ግንቦት 1 ቀን 1943 ዓ.ም በያኔው የሸዋ ክፍለ ሀገር፤ ሰላሌ አውራጃ፤ ደገም ወረዳ፤ ራሶ የሚባል አምባ፤ ጉዳሌ ተብሎ የሚጠራ ቀበሌ፤ ያበኖ ተራራ ግርጌ ስር ተወለደ። እናቱ ወ/ሮ ማጪያሽወርቅ ተከተል አባቱ አርበኛ ለማ ደግፌ ይባላሉ።
ከወለዷቸው 4 ልጆች አበራ ሁለተኛው ነበር። በተወለደባት ቦታ ስለነበረው እድገት ሲናገር “እንደማንኛውም የገጠር ልጅ ከብት ጥበቃ ተሰማርቼ፤ ውርንጭላ እየጋለብን፤ አካባቢያችን በሚገኘው አርኪሶ የተባለ ወንዝ እየዋኘን፤ ገሳ ለብሰን እንደ ገበሬ ልጅ ነው ያደግኩት” ይላል።
ልጅነቱ ውብ ነበር። ምናልባትም ለሥነ ጽሁፍ የሚሆን ምናብ እንዲቀርጽ ውብ የሆነው ልጅነቱ ሳይጠቅመው አልቀረም። ከሚኖርባት የገጠር ቀበሌ ወደ ከተማ የመጣው በልጅነቱ ነው። በአቅራቢያው ያለችው ትልቋ ከተማ ፍቼ ናት። ነገር ግን ያኔ አውራ ጎዳና ባለስልጣን ባልደረባ የነበሩት አባቱ ከፍቼ አቅራቢያ የምትገኝ በአሥራዎቹ የሚቆጠሩ አባወራዎች የሚኖሩባት አራተ ማርያም የምትባል አምባ፤ ኩሀኖ የምትባል ትንሽዬ ከተማ ውስጥ ኑሮ ጀመሩ።
ያኔ ትምህርት የሚባል ነገር ብዙም አይታወቅም። እንደ ማንኛውም ልጅ ከወንድም እና እህቶቹ እንዲሁም ከሰፈር ልጆች ጋር ሲጫወቱ እና ቤተሰብ ሥራ ሲያግዙ ይውላሉ። ቀኑ በነዚህ በሁለት ተግባራት የተከፈለ ነው።
አንድ ቀን ግን አንድ ጓደኛው ትምህርት ቤት እንሂድ አለው። ትምህርት ቤት የሚባለው ምን እንደሆነ ባይገባውም ጓደኛው ያየውን ለማየት ተከትሎት ሄደ። የሄዱበት ቦታ የሱ ብጤ ህጻናት ተሰብስበው ፊደል ይቆጥራሉ። ለአበራ ነገሩ አዲስ እና ፍጹም የማይገባ ሆነበት። መንፈሱም አልተቀ በለውም። ”ግማሽ ሰዓት ያህል ከተቀመጥኩ በኋላ የሁሉም ሰው ትኩረት ትምህርቱ ላይ መሆኑን ሳረጋግጥ ፈትለክ ብዬ ወደ ቤቴ ሮጥኩ” ይላል ወቅቱን ሲያስታውስ። ወደ ቤቱ እየበረረ ሄዶ የገጠመውን ጉድ ለእናቱ ነገራት። እናትም በወቅቱ ስለ ትምህርት ብዙም ግንዛቤው አልነበራትምና ልጇን ትምህርት ጥለህ ለምን መጣህ ብላ አልወቀሰችውም።
ከቆይታ በኋላ ግን ወደእነ አበራ መንደር አዲስ መምህር መጡ። መምህሩ የደብረ ሊባኖስ ሊቅ ናቸው። መልካም ስም ያላቸው ስለነበሩ ወላጆች ልጆቻቸውን ለመላክ ተነሳሱ። ከላኪዎቹ መካከልም የአበራ ቤተሰቦች ተጠቃሽ ነበሩ። አበራ አሁን ወደ ትምህርት ቤት ሲሄድ እንደ በፊቱ አልደነገጠም። ደስ ብሎት ሄደ። መማርም ጀመረ።
ነገር ግን በመሐል ትምህርቱ ሰለቸውና ለራሱ የአንድ ቀን እረፍት ሊሰጥ ቤቱ ቀረ። አባት ከሥራ ሲመጡ ልጃቸው ሰፈር ውስጥ ይንጎራደዳል። ለምን አልሄድክም አሉ። እንዲያው ልረፍ ብየ ነው ብሎ መለሰ። አመላለሱ እና ኩራቱ ከትምህርት ቤት መቅረት መብቱ እንደሆነ እንደሚያስብ አመላካች ነበር። አባት ተበሳጩ። ጆሮውን ይዘው ወደ መምህሩ ቤት ወሰዱት። ይቅጡልኝ አሉ። መምህሩ ግዴለም ያስቀምጡትና ይሂዱ፤ እኔ እቀጣዋለሁ አሉና አባትን ሸኙ። ትምህርቱ ቀጠለ።
የእለቱ ትምህርት ሲያልቅ እና ተማሪዎች ወደ ቤታቸው ሊሄዱ ሲነሱ አበራ ቆይ ተባለ። ደነገጠ። ተማሪዎች ከሄዱ በኋላ መምህሩ ደቀ መዝሙሩን ጠሩና አበራን ወደ ውስጥ እንዲያስገባው አዘዙ። ደቀመዝሙሩ አበራን ወደ ውስጥ አስገባና ጥፍንግ አድርጎ ከምሰሶ ጋር አሰረ። ከዚያም መምህሩ አጠገቡ ቁጭ ብለው በደህና ልምጭ አበራን ያበራዩት ያዙ። ለቅሶ፤ ልመና፤ መሐላ ወዘተ…ምንም አልፈየደም። መምህሩ የሚበቃውን ያህል ከገረፉት በኋላ ተነስተው ሄዱ።
ከጥቂት ቆይታ በኋላ ሲመሽ ደቀመዝሙሩ እንዲፈታው ታዘዘ። ፈታው እና ራት ተሰጠው። የገዛ ቤቱ እንኳን ለበዓል ቀን ካልሆነ የማያገኘውን ዶሮ ወጥ ነው እራት የሰጡት። ግጥም አድርጎ በላ። ከዚያም ጋቢ ስጠው ተባለና ጋቢ ተሰጠው። አደረ። ጠዋት ሲነሳ በል ቤትህ ሂድና ቁርስ በልተህ ና ተባለ። ወደ ቤቱ በረረ። ከዱላው ይልቅ ዶሮ ወጥ መብላቱን ለእህትና ወንድሙ ለጓደኞቹ ሊናገር ነበር ጉጉቱ።
ከመምህሩ ጋር ፊደል ቆጥሮ ውዳሴ ማርያም እና ዳዊት ደግሞ አዕምሮውም ለትምህርት ዝግጁ መሆኑ ታውቆ ሲጨርስ ወደ ፍቼ ከተማ መጥቶ አበራ እና አስፋወሰን መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገብቶ ትምህርትን ከሁለተኛ ክፍል ጀመረ። በተማሪ ቤት ቆይታውም ከትምህርቱ ባለፈ በጎን በክበባት ተሳትፎውን አጠናከረ። በተለይም ሁነኛ የቦይ ስካውት አባል ነበር።
የሰባተኛ ክፍል ተማሪ እያለ በሚማርበት ትምህርት ቤት የቋንቋ መምህሩ የኔታ ከፋለ ይባላሉ። ኮምጠጥ ያሉ መምህር ናቸው። ያለ በቂ ምክንያት ተማሪን አያሞግሱም። አንድ ቀን የጽሑፍ የቤት ሥራ ሰጡ። የአባቴ ቤት በገጠር በሚል ርዕስ ድርሰት እንዲጽፉ ታዘዙ። ሁሉም ተማሪ ጽፎ መጣ። ደብተር ተሰበሰበ፤ ታረመ። በማግስቱም ተመለሰ። ደብተር ሲመለስ የአበራ ደብተር ግን የለም። በኋላ ስሙ ተጠራ። ቆንጆ ጽሑፍ ጽፈሐል ብለው አሞገሱት። ለወትሮው ሙገሳ የማያበዙት አስተማሪ አበራን አሞገሱት። ደስ አለው። ለተማሪዎች አንብብ ተባለ፤ አነበበ።
ከዚያ በኋላ ወደ ሰላሌ ላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ስላልነበር ወደ ወሊሶ ሄዶ ራስ ጎበና እና ደጃዝማች ገረሱ ዱኪ በሚባሉ ትምህርት ቤቶች እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ ተማረ። በነዚያ ትምህርት ቤቶች በነበረው የትምህርት ቆይታ በትምህርት ቤት ሚኒሚዲያ ውስጥ ንቁ ተሳታፊ ሆነ። ለተማሪዎች እና ለመምህራን ዜና ያቀርባል። ጽሑፍ ያነባል። ደራሲነት እና ጋዜጠኝነትን ያለ ክፍያ ይሰራቸው ያዘ።
12ኛ ክፍል ሲጨርስ በሂሳብ ትምህርት ውጤት አለመሳካት የተነሳ ዩኒቨርሲቲ መግባት ስላልቻለ በኮተቤ መምህራን ኮሌጅ ተወዳድሮ አልፎ የአንድ ዓመት ስልጠና ወስዶ መምህር ሆነ። ኮተቤዎች እዚያው እንዲቆይ እና መምህር እንዲሆን ቢፈልጉም እሱ ግን ወደ ጎንደር ሄደ።
ወደ ጎንደር ሄዶም የቋንቋ እና ተዛማጅ ትምህርቶች መምህር ሆነ። የመጀመሪያ መጽሐፉ የታተመችውም በዚህ ወቅት ነው። ስያሜዋም ኩል ወይስ ጥላሸት የሚል ነበር። የዚህች መጽሐፍ የተለየ ታሪክ የሚሆነው ከመጀመሪያነቷ ባለፈ ለቤት ግንባታ ብር ከሚያበድረው ሞርጌጅ ባንክ በተወሰደ ብድር የታተመች መሆኗ ነው።
ከሁለት ዓመት የመምህርነት ቆይታ በኋላ ግን በ1968 ዓ.ም አበራ ወደታወቀበት የጋዜጠኝነት ዘርፍ ገባ። በጋዜጠኝነት ሥራው በተለይም የሶማሌ እና የኤርትራ ጦርነቶችን ምስል ከሳች በሆነ መልኩ የዘገበ ሲሆን በዚህም የተነሳ የጦር ሜዳው ቀሲስ የሚል ስም አግኝቷል።
ይሁንና ዘገባውን የሚሰራበት መንገድ አንዳንድ ጠላቶችን አስነሳበት። በተለይም ጦሩ በሚሸነፍ ጊዜ የሚያነሳቸው ጥያቄዎች አንዳንድ የጦሩን መሪዎች ያስከፋ ሲሆን በተመሳሳይ ኢትዮጵያን እየወጋ የነበረው ጀብሀም እንዲሁ አበራን ለመግደል ሙከራ አድርጎ ነበር። የጀበሀውን የግድያ ሙከራ በአምቡላንስ አምልጦ ገዳዩ ከተማረከ በኋላ ገዳዩን ቃለመጠይቅ መስራት ችሏል።
በሌላ በኩል ከጦሩ መሪዎች መካከልም ሊገድሉት ያቀዱ የነበሩ ቢሆንም፣ አንድ ወዳጁ የሆኑ መሪ ግን ቀድሞ እንዲያመልጥ ማድረግ እና እንዲተርፍ ማድረግ ችለዋል። የኤርትራው ጦርነት ጣጣ ከግንባር ወደ ቢሮ ከተመለሰም በኋላ ሊለቀው አልቻለም። ከአንድ የበላዩ ከነበረ ኤርትራዊ አለቃው ጋር በነበረ አለመስማማት አለቅየው አበራ የሰራቸው ፕሮግራሞች እንዳይተላለፉ በማድረግ ከሥራው እንዲለቅ እና ወደ አዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዲሄድ ተደርጓል። ከ4 አመት ቆይታ በኋላ ነበር ኢትዮጵያ ሬድዮን የተሰናበተው።
በአዲስ ዘመን በነበረው ቆይታም ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ የገጠመው ሲሆን እዚህም አንድን ሹም አስከፍተሀል በሚል ነበር ሥራውን እንዲለቅ የተደረገው። በአዲስ ዘመን በነበረው ቆይታ ተጠቃሽ የሚሆን አንድ ታሪክ አለ። ይሄውም በአንድ ወቅት ጓድ መንግሥቱ በተገኙበት የቀረበ አንድ ተውኔት ላይ የጻፈውን ሂስ በተመለከተ ነበር።
በወቅቱ አንዳንዶች እንዴት ጓድ መንግሥቱ እንኳን አይተው ባደነቁት ተውኔት ላይ ሂስ ትሰጣለህ በሚል የከፋ ትችት ሰንዝረውበት ነበር። እሱ በበኩሉ እኔ የማየው በገዛ አይኔ ነው እንጂ በሳቸው አይን አይደለም፤ ስለዚህ መጻፌ አግባብ ነው ብሎ ሞግቷል። ከዚያ በኋላ ደግሞ የቴአትሩ አዘጋጅ በተሰጠው ሂስ በመበሳጨት መልስ አዘጋጅቶ የመጣ ሲሆን መልሱም 20 ገጽ ነበር። በዚህም የተነሳ በአንድ ዕትም ባለማለቁ በተለያዩ እትሞች የወጣ ሲሆን በአስገራሚ ሁኔታ የደርግ ኃላፊዎች በምላሹ መሰጠት ደስተኛ አልነበሩም።
ከለውጥ በኋላ በዘመነ ኢህአዴግ አዕምሮ በተሰኘ ጋዜጣ ላይ የሰራ ሲሆን እዚያም ቢሆን ከመንግሥት ጋር ተቆራቁዞ ለስደት ተዳርጓል። ከሦስት ዓመታት በፊት እስከተመለሰበት ጊዜ ድረስም ለ28 ዓመታት በኖርዌይ በስደት ቆይቷል። በኖርዌይ ቆይታው ሞገደኛው ነውጤን ጨምሮ በርካታ ሥራዎቹ ወደ ኖርዌይ ቋንቋ የተተረጎሙ ሲሆን በኖርዌይ የደራሲያን ማህበር ኖሬዊያዊ ቋንቋን የማይናገር የመጀመሪያው አባልም አመራርም ሆኗል። በዚያም ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን እንዲሸለምም አድርጓል።
በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ የሚኖረው አበራ ባለትዳር እና የሶስት ሴት ልጆች አባት ነው። ሶስቱም በአገረ ኖርዌይ የሚኖሩ እና ለቁምነገር የበቁለት ናቸው።
እሱ ግን በተደጋጋሚ እንደሚናገረው በስደት የኖረበት ዘመን የተደሰተበት ወቅት አይደለም። ስለዚህም አጋጣሚውን ባገኘ ቁጥር ወደ አገሩ ለመመለስ አላመነታም። ለዚህም ነው ሰሞኑን ከኖርዌይ ኤምባሲ በተደጋጋሚ እየተደወለ እና ኢሜይል እየተላከ ከአገር እንዲወጣ ቢወተወትም እምቢኝ ያለው።
በዚህ ወቅት እንደ ሲ ኤን ኤን እና ቢቢሲ ያሉ ሚዲያዎች የሚሰሩትን ዘገባ የጋዜጠኝነት መስፈርትን የማያሟላ ነው የሚለው ጋዜጠኛ እና ደራሲ አበራ፣ ለኢትዮጵያውያን ወጣት ጋዜጠኞች ምክር አስተላልፏል።
የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች በእናት አገር ላይ የተቃጡትን ጥቃቶች እየተከታተሉ በመዘገብ ርቀት ከጥንት ጀምሮ አኩሪ ተግባራትን መፈጸማቸውን ጠቅሶ፣ በኦጋዴን፣ በኤርትራ፣ በትግራይ የእናት አገርን ሉዓላዊነት ለማስከበር በተደረገው ተጋድሎ ሁሉ ጋዜጠኞቻችን ከፊት ሆነው ዘግበዋል። ለታሪክ የሚቀር ሰነድና ምስልን ቀርጸው አስተላልፈዋል ሲል ያስታውሳል።
ከጋሽ ጳውሎስ ኞኞ የአጼው ዘመን የኦጋዴን ዘመቻ አንስቶ በደርግና በዶክተር ዐቢይ አመራር ዘመን ጋዜጠኞች ሙያዊ ድርሻቸውን እየተወጡ ናቸው ያለው ደራሲና ጋዜጠኛው፣ ላንድ ጋዜጠኛ ቁርጠኝነት፤ ተነሳሽነት፤ እሙን ዘጋቢነት ልዩ መለዮውም መሆን ያለበት ነው ይላል።
ጋዜጠኛው ለማን? ምን? እንዴት? መቼ? የት? የሚሉትን ጠንቅቆ ማወቅ አለበት ሲል ያስገንዝባል። ጠላትን በጦርነት ብልጫ ብቻ ሳይሆን በአጸፋ ፕሮፖጋንዳም ጭምር በልጦ መገኘት ያለውን ጠቀሜታ ጋዜጠኛው ማወቅ ግድ እንደሚለው ነው ያመለከተው። በጦር ግንባር ላይ የሚደረግ የተዋጣለት የመስክ ዘገባ የወገንን ጦር ከማጀገኑም በላይ የጠላትን ጦር የሚያፍረከርክ ምትሐት ነው መሆን ያለበት ሲልም አስገንዝቧል።
የዘመኑ ጋዜጠኞች ያደረ አፋሽ ዘጋቢያን ከመሆን ይልቅ በግንባር ላይ ከተሰለፈው ጦር ጎን ሆነው በጀግንነት ቢዘግቡ እጅግ ፍሬያማ ይሆናሉ ያለው ደራሲና ጋዜጠኛ አበራ ለማ፣ በውጤቱም እጅግ አኩሪ ታሪክ ሊያስመዘግቡ አንደሚችሉ ተናግሯል። ‹‹ጋዜጠኞች ሁሉም መርማሪና አዳዲስ የሙያውን እውቀት ማጥመድ የሚችሉ መሆን አለባቸው። እኛ ቀዳሚዎቹ ጋዜጠኞች ያልነቃ ጋዜጠኛ አደንቋሪ ጋጋኖ ነው የሚል ጽኑ እምነት አለን። ”ብሏል ።
ደራሲ አበራ ከጋዜጠኝነቱም ባለፈ ደራሲም እንደመሆኑ መጠን 20 የድርሰት ሥራዎችን በአማርኛ እና በሌሎች ቋንቋዎች በግል እና በጋራ አሳትሟል። አሁንም ለአዲስ ሥራ ዝግጅት ላይ ነው።
ለወጣት ደራሲያን ባስተላለፈው መልዕክት ላይም “በሥነ ጽሑፍ ዓለም ውስጥ መኖር የፈለጉ ወጣቶች ብርቱ አንባቢዎች መሆን አለባቸው። እየተማሩ እያነበቡ እየተመራመሩ የራስን የፈጠራ ሥራ ማጎልበት ስልታዊ አካሄድ ነው። በዕውቀት ላይ የተመሠረተ የፈጠራ ስራ ተደራሽነቱ ኃያል ነው። ለከፍተኛ ትምህርት ጉድኝት ያልታደሉ ጸሐፍት ቢያንስ ቢያንስ አጫጭር ኮርሶችን እና ወርክሾፖችን በመሳተፍ የቲዮሪ ትጥቃቸውን ማጥበቅ ይችላሉ። ” ሲል አመልክቷል።
የዕረፍት ቀን ውሎ
ደራሲውንና ጋዜጠኛውን የእረፍት ቀኑን በምን እንደሚያሳልፍ ጠየቅነው። ”የእረፍት ጊዜዬን በወጉ ነው የምጠቀምበት። መጽሐፍ አነብበታለሁ። የሥነ ጽሑፍ ሥራዬን እሰራበታለሁ። በባህላዊ መድኃኒት እጽዋቶች እንክብካቤና ጥቅም ላይ እመራመራለሁ ሲል መለሰለን።
ጠዋት ጠዋት ለአንድ ሰዓት ዮጋ ስፖርት እንደሚሰራ፣ ወዳጅ ዘመድ እንደሚጠይቅበት ፣ አስደሳች ቦታዎችን በተለይም እጽዋት የነገሱበትን እንደ ዞማ ቤተ መዘክር ያሉበትን ስፍራዎች እንደሚጎበኝ ገለጸልን።
ኖርዌይ ውስጥ ካለሁ በእረፍት ጊዜዬ የመርከብ ሽርሽርን የበለጠ እፈቅዳለሁ። አስደሳች ቦታዎችን ሙዚየሞችን፣ የሕዝብ መዝናኛ ስፍራዎችን መጎብኘት ያስደስተኛል። ”ብሎናል። የዕለቱ ቆይታችንም በዚህ ተጠናቅቋል።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ታኅሳስ 17/2014 ዓ.ም