ከያኒው “ከየት ነህ አትበለኝ ይናገራል መልኬ” ሲል ያቀነቀነው እሱን መሳይ የቆዳ ቀለም ለታደሉ ኢትዮጵያውያን ነው:: ፀይሙ መልኩ ላይ በጣም ያልበዛም ያላነሰም ቁመት ተጨምሮበት በተለምዶ ወንዳወንድ የሚሉትን አይነት ቁመና ተችሮታል።
የሕዝብ እምባ የሚያስለቅሰው፣ ህዝቡ ሲደሰት የደስታ ሳግ የሚተናነቀው፣ ደስታው ኀዘኑ በሚወዳቸው ስሜት ላይ የተመሰረተ በኢትዮጵያ ተወልዶ ለኢትዮጵያ የኖረ የህዝብ ልጅ ነው ፤ አቡሽ ዘለቀ!!
በቤተሰቡ እንዲሁም ባለው ሁሉ ነገር ማመስገንን ችላ ማለት የማይችል፣ ስላለው ነገር ደስታው የማይነጥፍ ነው። ነገሩ ላለው ይጨመርለታል ነውና አመስግኖ ሌላ የሚያመሰግንበት ነገር የሚጨመርለት ሁሌም በምረቃ የተሞሉ ቀናትን የሚያሳልፍ ።
ማንኛውም ሰው ስለ አቡሽ ዘለቀ ስታስብ ቀድሞ ምን ትዝ ይልሀል ተብሎ ቢጠየቅ የብዙሀኑ መልስ ንፁህ ኢትዮጵያዊነቱ የሚል ምላሽ እንደሚሰጥ አያጠራጥርም። ለብዙ ኢትዮጵያውያን የዘለቀን ልጅ ለመውደድ የኦሮሚኛ ቋንቋን አቀላጥፎ መናገርና ማወቅ ግዴታ አይደለም።
አቡሽ ዘለቀ ከአብራኩ የተከፈለ የሶስት ዓመት ከአራት ወር ወንድ ልጅ አለው። ለልጄ የማወርሰው ሰላም የሰፈነበት ሀገር ለልጄ የሚወርሰው መልካም ሥራ መኖር አለበት ይላል።
አቡሽና ልጅነቱ
የእናቱ ወይዘሮ ሙሉ ኤለማና የአባቱ ዘለቀ ጴጥሮስ የአብራክ ክፋይ የሆነው አቡሽ፤ የትውልድ ቀዬውና እትብቱ የተቀበረበት ስፍራ በገዳ ስርዓት ተሸሞንሙኖ ዘመን ካስቆጠረው ኦሮሞነትን ከኢትዮጵያዊነት ሰፍቶ ካበጃጀው ከጉጂ ዞን ቦረና ከተማ ነው።
በፅሁፍ የማይተመን፣ የቃላት ጋጋታ የማይገልፀው አቡሽ፣ በብዙ መውጣትና መግባት ውስጥ አልፏል። በቁጥር የማይነገሩ እልፍ ነገሮች በህይወቱ ውስጥ ተመላልሰዋል።
ከስጋ አባቱ በተጨማሪ ያሳደገውና ሁለተኛ አባቴ ብሎ የሚጠራው አቶ አብዱላሂ ሻንቆ ይባላል። አቶ አብዱላሂ አባት ለልጅ የሚሰጠውን ሁሉ እየሰጠ እንዳሳደገው ይናገራል።
የመላው ኢትዮጵያውያን የልጅነት ትዝታዎችን ሁሉ አሳልፏል። ለጎረቤቱ ሲጠሩት አቤት ሲልኩት ወዴት ብሎ ተልኳል፤ ለሀገር ለወገኑ ፍቅር ኖሮ ያለፈባቸው ጊዜያት በትዝታው ማህደር ላይፋቁ የተፃፉ መሆናቸውንም ይናገራል።
ስሙና እሱ
አቡሽ የሚለው ስያሜ የቅርብ ዘመዶች ለህጻናት የቤት ስም አድርገው ሲጠቀሙበት ነው የሚታወቀው። አቡሽ ግን ከልጅነት እስከ እውቀቱ አቡሽ ተብሏል። ለምን አቡሽ ተብለህ ተጠራህ አልነው፤ በልጅነቴ አባቴ አቡ ብሎ ነበር የሚጠራኝ፤ መጠሪያውን የሰጠኝም አሁን በሕይወት የሌለው ወላጅ አባቴ ነው፤ መጠሪያውን በጣም ስለምወደው ነው የምጠራበት ሆኖ የቀረው ይላል።
ሙዚቃና አቡሽ
በልጅነት ምኞት ልጆች ስታድጉ ምን ትሆናላችሁ በሚባሉበት ወቅት ፓይሌት፣ ኢንጅነር፣ ዶክተር ወዘተ እያሉ ምኞታቸውን ይገልጻሉ፤ እሱ ግን ሙዚቀኛ የመሆን ህልም ነበረው። መዝፈን አትችልም ብሎ ወደ ኋላ የጎተተው ሰው አልነበረም፤ ገና በጨቅላነት እድሜው ከበሮ ይዞ ይዘፍን ነበር፤ ውስጡ እያደገ በመጣው የሙዚቃ ፍቅር ምክንያት ነፍስ ሲያውቅ ብዙ ነገሮችን እያሻሻለ መጣ።
አቡሽ የሚባለው ስም ከድምፃዊነት ጋር ተያይዞ የሚጠራ ስም እንደሚሆን የሚውያቀው ገና በልጅነት እድሜው ነው፤ አቡሽ መዝፈን እንደማይችል ተሰምቶት አያውቅም። እድገቱና ኑሮው ለሙዚቃ ቅርብ እንደነበር ይናገራል። ሙዚቃ ለአቡሽ ብዙ ትርጉም ያላት በወጣትነቱ የማረከችው ጣኦቱ ናት።
ያቤሎ ከተማ ውስጥ ጉሚጋዮ በሚባል ባንድ ውስጥ በ1995 ነበር ከሙዚቃ ጋር የተዋወቀው፤ ለዛሬው እሱነቱ የያቤሎው ጉሚጋዮ ባንድ ትልቅ አስተዋፅኦ ማበርከቱንም መስክሯል።
በጉሚጋዮ ባንድ ውስጥ ጋሽ አክሊሉ የተባሉ ቤዝ ጊታር ተጫዋች በሙዚቃ ህይወቱ ውስጥ በብዙ እንደረዱትና በባንዱ ቆይታው የሙዚቃን ሀሁ የቆጠረባቸው ድንቅ ጊዜያት ማሳለፉንም ይናገራል። ከአምስት ዓመታት በላይ በዚያው ሲያገለግል ቆየ፤ ግንቦት1999 ላይ ግን አዲስ አበባ ጠቅልሎ ገባ።
የአቡሽ ዘፈኖች ያልዳሰሷቸው ነገሮች የሉም ለማለት በሚያስደፍር መልኩ ስለ ፍቅር፣ ስለሴቶች ፣ስለ ሀገር፣ ስለልጅነትና ስለሌሎችም ኢኮኖሚያዊ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮችን አቀንቅኗል። አዲስ አበባ ኑሮውን ባደረገባቸው አሥራ አራት ዓመታት ውስጥ አራት ጥሩ ጥሩ አልበሞችን አውጥቷል።
ስለልጅነት ጊዜ ውድና ውብ ትዝታ ያቀነቀነውን ‹‹ቆንጆ ናፈቀኝ ያጊዜ ›› የተሰኘውን የዘፈኑን ግጥሞች ስንኞች ጀባ እንበላችሁ!
ቅጠሉን እንጀራ፣ አፈሩን ወጥ አርገን
ከበረንዳችሁ ስር፣ ስንጫወት አብረን
አኩኩሉ ስትይ፣ እያልኩሽ አልነጋም
ድምፅሽ ከአዕምሮዬ፣ ተቀርጿል አልወጣም
ናፈቀኝ… ናፈቀኝ…
ናፈቀኝ… ያጊዜ
ናፈቀኝ… ከየት መጣ፣ ከየት መጣሽ
ናፈቀኝ… የማንባባለው
ናፈቀኝ… ዘራችን መዋደድ
ናፈቀኝ… ፍቅር ብቻ እኮ ነው
ናፈቀኝ… ብንጣላም እንኳን
ናፈቀኝ… ቂም አናውቅም በቀል
ናፈቀኝ… በማርያም ጣት ታርቀን
ናፈቀኝ… እንረሳው ነበር
ናፈቀኝ… ናፈቀኝ…
ናፈቀኝ… ያጊዜ
የህይወት ፍልስፍና
ብዙ የህይወት ፍልስፍናዎች ያሉት አቡሽ ሁሉም ፍልስፍናዎቹ ግን ተስፋ ያለመቁረጥ በተባለ ገመድ የታሰሩ ናቸው። ሰው ይወድቃል ይነሳል፣ ያገኛል ያጣል ፣ይደሰታል ይከፋል፣ ይደክማል ይበረታል፣ በእነዚህ የህይወት አዙሪቶች ውስጥ በየትኛውም ፈተና ውስጥ ከባድ የሚሆነው ሰው ወድቆ ሲቀር ነው። ህይወቱ እጅ አትስጥ በርታ በሚል ለራሱ በሚነግረው ሹክሹክታ ውስጥ የበረታ ነው። በሱ የመኖር ታሪክ ውስጥ ኢትዮጵያም እጅ አትሰጥም ያልፋል ይላል።
ኢትዮጵያና አቡሽ
የሀገሩ ጉዳይ ሰርክ የሚያስጨንቀው አፍላ ጎረምሳ ፍቅረኛውን ከሚያፈቅረው በላይ በሀገሩ ፍቅር ላይድን የተነደፈ ነው፤ በሀገር ከመጡበት አምጣ በወለደችው በእናቱም ቀልድ አያውቅም።
በሀገር ጉዳይ የተጨነቀባቸው፤ ከራሱ ተግባብቶ የማያውቅባቸው ራሱን ዝግ ስብሰባ ጠርቶ ከገዛ እኔነቱ ጋር የሚጨቃጨቅባቸው ሀገራዊ ጉዳዮች አሉበት። እንዴት? ለምን? በምን? የሚሉ እልፍ ጥያቄዎችን የታቀፈ በሀሳብ የተሞላ ጭንቅላት የታደለ ነው። መለወጥ በማይችለው ጉዳይ ሁሉ ስለ ሀገሩ የተጨነቀባቸው ብዙ ዓመታት አሉት። ኢትዮጵያን ለማዳን ቆርጠው ከሚኖሩ ሚስጥር ገመናቸው ታዛ መጠለያቸውን ትንፋሽ እህል ውሃቸውን ሀገራቸውን ብቻ ካደረጉ ሰዎች መካከል ነው።
አቡሽ እዚህና እዚያ ጥግ ይዞ መጎሻሸም አይመቸውም፤ የወገን አልኝታነቱን በተግባር ያሳያል እንጂ፤ ለዚህም ተግባሩ የወሎ እና ቦረና አካባቢዎች የቅርብ ቀናት ህያው ምስክሮቹ ናቸው።
በወሎና ቦረና የሆነው እንዲህ ነበር፤ በወቅቱ የሙዚቃ ቪዲዮ ለመስራት ይሰናዳል። ቪዲዮውን ሰርቶ ሳያስረክብ ሁለቱ አካባቢዎች በችግር የተሞላ ጊዜን አሳለፉ። የወገኖቹን ስቃይ እያዩ ማለፍያ የማይችል ነውና ለቀረፃ ያዘጋጀውን ገንዘብ ሙሉ ለሙሉ የእርዳታ እህል ገዛበት።
ድምፃዊ አቡሽ ዘለቀ በሰይፉ በኢቢኤስ
“በሕይወቴም … በልቤም ውስጥ ኢትዮጵያ ናት የምትቀድመው” “አንዳንዱ ያለምንም መሸማቀቅ
ሚዲያ ላይ ወጥቶ “ኢትዮጵያን አፈርሳታለሁ” ብሎ ሲዝት ይውላል። እና ለእንዲህ አይነቱ ውርጋጥ “ኢትዮጵያ አትፈርስም” ብዬ ለመመለስ የሚያስፈራኝ ነገር ምንድን ነው? ይሄን በመናገሬስ ስሜን እና ጥቅሜን እንዴት ላጣ እችላለሁ? እና ደግሞ የምወዳትን አገሬን መታደግ እስከቻልኩ ድረስ ዝናዬንና ተቀባይነቴን ቀርቶ ሕይወቴንስ ባጣ ምን ችግር አለው?«እውቅናዬም ዝናዬም ገደል መግባት ይችላል በሕይወቴ እና በልቤ ውስጥ ግን ኢትዮጵያ ሁሌም ትቀድማለች! “ ሲል የተናገረውም ትክክለኛ ማንነቱን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል።
የምስጋና ችሮታ
በአቡሽ ሕይወት ውስጥ በርካታ ሰዎች አሉ። ከቤተሰብ እስከ ሩቅ ዘመድ ከዘመድ እስከ ባዳ ሕይወቱ ላይ አሻራቸውን ስለማኖራቸው ራሱ አቡሽ ህያው ምስክር ነው። ስማቸው እንዲጠራ የማይሹ፣ ታይታ የማይፈልጉ ብዙ ሰዎች ሕይወቱን እንዳቀኑለት ይናገራል፤ ሕይወቴ በብዙ ሰዎች ዋጋ ነው የቆመው ይላል።
እርሱም ለብዙ ሰዎች ጎዳና ማቅናቱን ይገልፃል። እርሱ በመጣባቸው የማይመቹ መንገዶች የእርሱን እገዛ የሚሹ ሰዎች እንዲያልፉባቸው አይፈቅድም። በተቻለው መጠን በየትኛውም መንገድ ሰዎችን ማገዝ ያስደስተዋል።
ምክር ለጀማሪዎች
ወደ ጥበቡ ዓለም በቅርቡ ለገቡና ለመግባት ፍላጎት ላላቸው ሰዎች እጅ አትስጡ የሚል ምክርም ለግሷል። ሁሉም ሰው ጀማሪን የሚያበረታታና አይዟችሁ ጠንክሩ የሚል አይደለም። አቡሽ የእድሜው ማመስገኛ ቀን ላይ ሲደርስ ከመሬት ተነስቶ አይደለም። ብዙ የማይዘነጉ የሚመስሉ ቀናት የማያልፉ መሳይ መአልትን አሳልፏል።
የሚደግፍ ሰው ያለውን ያህል ሞራል የሚነኩ በእንጭጩ የሚቀጩ ሰዎች አይጠፉምና የማይጠቅሙ ድምፆችን ወደ ጭንቅላት ማስገባት እንደማይገባም ያምናል። አይሆንላችሁም ትከስራላችሁ አትችሉም የሚሉ ሰዎችን ማድመጥ አይገባም ባይ ነው።
ከሁሉ በፊት ራስን ማድመጥ እንደሚያስፈልግ የሚናገረው አርቲስት አቡሽ፣ ለዚያ ነገር በቂና በውስጡ ለሚመጡት ፈተናዎች ዝግጁ ሆኖ መበርታት እንደሚስፈልግም ይመክራል።
በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ በደስታ ያልተዋቡ ቀናት መኖራቸው አይቀርም፤ ቀድሞ መዘጋጀትና መጠበቅ ግን አስፈላጊ እንደሆነ ያምናል። ይሄን ሲሉኝ እሰበራለሁ፣ ያንን ቢሉኝ እጎዳለሁ ብሎ ራስን ለጉዳት ማዘጋጀት ሳይሆን አቅምን ማጠናከር እንደሚስፈልግና እኔ በየትኛው ነገር ጎበዝ ነኝ የሚለውን መለየት ያስፈልጋል። አንድ ነገር ሞክሮ ተስፋ መቁረጥም አይገባም ሲል ይመክራል።
አቡሽና የእረፍት ጊዜ ማሳለፍያዎቹ
አቡሽ የእያንዳንዷን ቀኑን መነሻ እና መድረሻ በፀሎት ተለማምኖ የሚውል ከአምላኩ ተቀራርቦ አዳሪ ነው። ከፀሎት ቀጥሎ የቀኑ የመጀመርያ ሥራው ማታ ሲተኛ በውስጡ የተመላለሱ ነገሮች ካሉ ለእነሱ መፍትሄ መስጠት ነው።
ከሙዚቃ ጋር ከተዋወቀ ጀምሮ ጊዜውን የሚያ ሳልፈው ሙዚቃና ዘፈን ነክ ነገሮች ላይ ነው። አብዛኛውን ጊዜውን ሙዚቃ በመስራትና ለክሊፖቹ የሚያስፈልጉትን ነገሮች በማድረግ ዘፈኖቹን በልምምድ ያሳልፋል።
ቲያትርም ነፍሱን ትገዛዋለች። ቲያትር በጣም ከመውደዱ የተነሳ ሞክሮ ባያውቅም መተወን ደስ ይለዋል። ፊልም ማየት፣ ወቅታዊ ጉዳዮችን መከታተል፣ ዓለም እንዴት ውላ አደረች የሚለውን ጉዳይ ማጣራት፣ ራሱን የመረጃ ሀብታም ማድረግም ይወዳል።
አቡሽ ብረታብረት ሥራም ያስደስተዋል፤ የራሱን ክሊፕ ቪዲዮዎች ሲያዘጋጅ መድረኩንና ሌሎችም ግንባታ ነክ ነገሮች ጋራዥ ገብቶ ይሰራል። እንደዚህ አይነት ሥራዎች መድረክ ላይ ወጥቶ ከመዝፈን ያልተናነሰ ደስታ ያገኛል። የሀገር ጉዳዮች ሲኖሩ በመንቀሳቀስና እርዳታ ሲኖር በማሰባሰብም ያሳልፋል።
ቸር ክረሙ መልካም ነገ!!
ዳግማዊት ግርማ
አዲስ ዘመን ታህሳስ 10/2014