የሆስፒታሉ የድንገተኛ አገልግሎት መስጫ ክፍል ውስጥ ናቸው። ቤተሰብ የሚይዝ የሚጨብጠውን አጥቶ በድንጋጤ ውስጥ ይተራመሳል። የእምባ ጎርፍ ከእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ይፈሳል፤ በስጋትና በትንሽ ተስፋ መካከል የሚፈሱ የእንባ ዘለላዎች። ስሜታቸውን ውጠው ነገሮችን ወደ መስመር ለመመለስ የሚጥሩ የቤተሰብ አባላት ሳይቀሩ ዛሬ አቅም አጥተው ማድረግ ያለባቸውንና የሌለባቸውን መለየት አቅቷቸዋል። ታክሲ ላይ በተነሳ የቃላት ምልልስ ወደ ድብድብ የተቀየረው ጸብ ለመገላገል የገባውን ወጣት ከድንገተኛ አገልግሎት መስጫ ስፍራ በአምቡላንስ እንዲደርስ አድርጎታል።
የሕክምና ሰዎች በየአቅጣጫቸው እየተሯሯጡ ነው። እንዲህ ባለ ወቅት ደቂቃዎች ሳይሆኑ ማይክሮ ሰከንዶች ትርጉም አላቸውና የማይክሮ ሰከንድን ትርጉም ፍለጋ። የሕክምና ሰዎች ያላቸውን እድል ለመጠቀም ጥረት ማድረጋቸውን ቀጥለዋል። ጥረታቸው ግን ሳይሆን ቀረ፤ በሞት ተቀደሙ።
ወጣቱ አንቀላፋ። ገላጋይ እሆን ብሎ አስቦ ስለመፍትሔ ብሎ የገባው ወጣት እስከወዲያኛው አሸለበ። በሚጣሉ ሰዎች መካከል ገብቶ ከመገላገል እንደ ፊልም ቁጭ ብለው ሂደቱን መመልከት ሌሎች በሚመርጡበት ጊዜ የሚጠበቅበትን ለማድረግ የወሰነው ሰው የምድር ቆይታውን ጨረሰ። ሰላምን ፈላጊው ሰው! ይህን ሰው ማንእንበለው አፈዮዲ ወይንስ አፈሐንዲ? ምላሹን እየፈለግን አፈዮዲ እና አፈሐንዲን እንተዋወቃቸው። ከእዚያ በፊት ግን አሮጌውን ቃል እናንሳው ሁሌም የሚደመጠውን ደግሞም አዲሱን!
አሮጌው አዲሱ የአዲስ ዓመት ቃል
አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር የመስከረም የመጀመሪያውን ሳምንት ከሚያጨናንቁት ቃላት መካከል አንዱ “ሰላም” የሚለው ቃል ነው። “የሰላም ዓመት ይሆን” ሳይባል የታለፈበት ዓመት የለምና ሰላም ዘወትር በየዓመቱ እየተሰማ ከዓመት ወደ ዓመት እየተሸጋገረ እዚህ የደረሰ ነው። አሮጌው ቃል ነገር ግን ትርጉሙ ሁሌም አዲስ የሆነ ቃል። አዲሱ ዓመት የሰላም፤ የደስታ፤ የብልጽግና ወዘተ ይሁንልን የሚለው የመልካም ምኞት መግለጫ ከሁላችን ዘንድ የታወቀ ነው።
በሌሎች አገሮችም በተመሳሳይ ሁኔታ አዲስ ዓመት ተመሳሳይ የደስታ ምኞት መግለጫዎች ይሰማሉ። በመሆኑም ቃሉ ያረጀ ይመስላል፤ በየዓመቱ ተደጋግሞ የሚሰማ ስለሆነ። ነገር ግን አሮጌው የአዲስ ዓመት ቃል ግን በሰዎች ሕይወት ውስጥ ያለው ትርጉም ሁሌም አዲስ ነውና እርጅናው አይታወቅበትም። ሰላም ሁሌም አቅም አለውና። ደስታ ሁሌም ደስታ ነውና። በነገር ሁሉ መከናወን ሁሌም የምንፈልገው ነውና።
ሰዎች በቅጽበታዊ ክስተት ሰላማቸውን አጥተው ግራ ቀኙ ገደል ከሆነበት ስፍራ ላይ ይደርሳሉ። በድንገት ከሞት ጋር መገናኘት የቤተሰብን አቅጣጫ በብዙ ሲወስነውም ያገኛሉ። ስለሰላም የምንሰጠው ቦታ መቼም ቢሆን ትርጉም የለሽ ሊሆን አይችልም። ሰላም ዋጋው ውድ ነውና።
እኛ የሰው ልጆች ተስማምተን ብንኖር ምን ልንፈጥር እንደምንችል ሲታሰብ የሚፈጥረው ልዩ ስሜት አለ። የተረጋጋ አገራዊ ሁኔታ ባላቸው አገሮች የተሰራውን ሥራ ስናይ የተረጋጋ አገር በእድገት ውስጥ መሆኑ የሚያነጋገር አይሆንም። የተረጋጋ የፖለቲካ ቁመና ላይ የሚገኙ አገራት አይደለም ዜጎቻቸው እንስሶቻቸውም እንዲሁም እጽዋቶቻቸው ያላቸው ወዝ ማራኪ ነው። አንድ ሰው ሲቀልድ “ኢትዮጵያ ውስጥ ሰው ሆኜ ከምወለድ እንትን አገር ዛፍ ብሆን ይሻለኛል፡፡” አለ። በዚህ ደረጃ ልዩነቱን ለማሳየት መሞከር የሆነ የጎደለው ነገር እንዳለ ቢያሳይም ሰላም የሚሰጠው ነገር ብዛቱን ግን ሊያሳይ ይችላል።
የዛሬው ጽሑፍ መዳረሻ ከአፈዮዲ ወይንም ከአፈሐንዲ ምርጫን ማድረግን የሚጠይቅ ነው። ሁለቱም በታሪክ ፊት የሄዱበት መንገድ አለ። የፈለጉትን ለማሳካት የሄዱበት መንገድ። አትራፊም ደግሞም የኪሳራም መንገድ። አንባቢው ከራሱ ሕይወት አንጻር ምርጫውን ማድረግ ይችል ዘንድ የተዘጋጀ።
አሮጌውን ቃል በሁሌም አዲስነቱ ተመልክተን እንድናነሳው ደጋግመን እንጠይቃለን። ከታሪክ ማኅደር ስለ ሰላም ሆነ ስለ ጦርነት ተከትቦ ከሚገኘው ሁለት በተለያየ ዘመን ከኖሩ መሪዎች ገጽ ላይ ለትምህርታችን መጥነን እንቆርሳለን። “አፈሙዝ ወይንስ አፈሰላም?” የሚል ርዕስ የተሰጠውን ጽሑፍ በመቀየር “አፈዮዲ አፈሐንዲ” ብለነዋል። አፈሙዝ አንዳንዴ ተገደህ የምትይዘው ሊሆን የሚችልበት እድል አለውና። ሁለቱ መሪዎች ከልባቸው ቦታ የሰጡትን የመፍትሔ መፈለጊያ መንገድ የሚያሳይ እርሱን ደግሞ በአንደበታቸው በኩል የሚናገሩት የሆነውን እንመለከታለንና “አፈ” ቅኝትን ጀመርን።
አፈዮዲ – የዮዲት ጉዲት መንገድ
የዮዲት ጉዲት መንገድን “አፈዮዲ” ብለነዋል። ዮዲት ጉዲት የሚለው ስም ሲጠራ የጭካኔ ልክ ወደ አዕምሮችን መምጣቱ አይቀሬ ነው። በወቅታዊ የአገራችን ሁኔታ መላው ኢትዮጵያ በኃዘን ውስጥ እያለፉ ናቸው። የጭካኔ ልክ ይህ ነው ብለን አንዱ ወደ አንዱ ጣቱን እየጠቆመ በድምር ውጤቱ የሰው ልጅ ደም ከየጎራው እየፈሰሰና ቤተሰብ እየፈረሰ ቀዬም እየፈራረሰ፤ የተስፋ ክምችት ጠፍቶ ምሬት አየሩን ሞልቶት እናስተውላለን።
ኢትዮጵያ እንደ አገር እያነባች ቢሆንም የእሳቱ ወላፈን በዋናነት በትግራይ፣ በአማራ እና በአፋር ሕዝብ ላይ መሆኑን እናስተውላለን። እኒህ ሦስቱም ሕዝቦች በአንድ ወቅት የጋራ ጠላት ኖሯቸው ለጋራ ጠላታቸው የየራሳቸውን መጠሪያ ሰጥተዋል። ዮዲት ጉዲት ለትግራይም ሕዝብ ሆነ ለአማራ እንዲሁም ለአፋር የምትጠራበት ስም አላት። የትግራይ ሕዝብ እቺስ ጉደኛ ናት ሲል “ጉዲት” እያለ ይጠራታል። የአማራ ሕዝብ ደግሞ የምታቃጥል እሳት ናት በማለት “እሳቶ” ይላታል። አፋሮች ደግሞ እንደ ሰው ሳይሆን እንደ አውሬ ቆጥረው “አስፈሪ አውሬ (ጋፅዋ)” ይላታል።
በትግራዮች “ጉደኛ” የተባለችው ዮዲት ጉዲት የሄደችበት የጥፋት መንገድ በብዙ አገርን ጎድቶ ኢትዮጵያ ያላትን የበዛ ቅርስ እንድታጣ ሆናለች። ዛሬ በትግራይ እየሆነ ያለው የጦርነቱ ሁኔታ ከጦርነቱ መጀመርም በፊት የነበረው እንዲሁም በሕወሓት/ኢህአዴግ ዘመን የሆነውን ሁሉ ደምረን ስናይ ጉደኝነት ዛሬም ያለቀቀን መሆኑን እንረዳለን። የማጥፋት መንገድ እርሱ የዮዲት ጉዲት መንገድ ነውና ከጥፋት መንገድ ለመውጣት የዮዲትን በቀለኝነት ያለውን ጥፋት መረዳት ያስፈልጋል። ተበድያለሁ የሚል ሰው ሌላውን በመበደል መፍትሔ ላይ ሊደርስ ስለማይችል የፖለቲካ ስሪታችን በቀል ላይ የተመረኮዘ ማድረግ እዚህ አድርሶናል። የኢህአዴግ ፖለቲካ ስሪት መሠረቱ ቂምና በቀልን መነሻ በማድረጉ አሁንም በንጹሐን ሞት የምትታመስ አገር እንድትኖረን አድርጎናል። ከጦርነቱ መለስ እንኳን በሆነው ነገር አንዱ ሌላውን ለመበቀል የሚሄድበት መንገድ የዮዲት ጉዲት መንገድ የጥፋትነት አቅሙ ምን ያህል እንደሆነ እንረዳለን።
ዮዲት ጉዲት በዚህ ደረጃ በክፋት የምትታየው ባለአፈሙዝ ምን ብታደርግ ነው? የሚለው ጥያቄ ወደ ታሪክ መዛግብት በስፋት ገብተን እንድንመረምር የግድ ይለናል። በታሪክ መጽሐፍት ላይ የተጻፈው ያደረገችውን ጥፋት ተመልክተን በዚህ ደረጃ በክፋት የምትገለጥ ያደረጋት ምን ይሆን የሚለውን መጠየቅ የግድ መሆኑን እንረዳለን። የክፋት ምሳሌ፣ የውድመት ምሳሌ፣ የሰይጣን ታላቅ እህት፣ ወዘተ ሆና የተቆጠረችው ዮዲት ጉዲት ንግሯ ውስጥ ያለው እውነት ምን ይሆን ብለን ስንጠይቅ ሃይማኖት የወለደው በቀል ሆኖ እናገኘዋለን። ምክንያቱ ምንም ይሁን በአንድ ቃል ስንጠራው “በቀል”። ክርስቲያኖቹ ላይ አይሁዳዊ/ኦሪታዊ የበቀል ዱላን ማውረድ። ሃይማኖት ሰላምን እንዲሰጥ ሲጠበቅ፤ ሃይማኖት የወለደው ሰላም መንሳትን ለማድረግ አፈሙዝን መያዝ።
በወቅቱ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ የነበረችው አክሱም ከኦሪት (አይሁድ) እምነት ወደ ክርስትና በመዞሯ በዙሪያዋ የነበሩ ነገር ግን የኦሪት እምነታችንን አንለቅም ያሉት ወደ ሌላ አካባቢ ፈለሱ። በመሆኑም ስማቸው “ፈላሻ” ተባለ። እምነትን መሰረት ያደረገ መፈናቀል ወይንም መሰደድ ሲሆን በጊዜ ሂደት የተሰደዱትን ፈላሾችን አስተባብራ ክርስቲያኖችን ለመውጋት ዮዲት ጉዲት ተነሳች። በከፈተችው ጦርነትም ብዙዎች ሞቱ፣ ቅርስ ወደመ፣ በጦርነቱ አሸንፋ ኢትዮጵያን መምራት ቻለች። ለ40 ዓመታት በቆየችባቸው የአገዛዝ ወቅቶች እንዳሻት ለማድረግ ብዙ እርቀት ሄደች። በአካሄዷ ያቄሙት የክርስቲያኑ መስመር የፖለቲካ ሰዎች ጊዜውን ጠብቀው እነርሱም እርሷ የሰራችውን አፈራርሰው የበቀል በትራቸውን አሳረፉ።
ይህ ታሪክ በኢትዮጵያ ምድር የሆነው ከዛሬ 1100 አመት በፊት ቢሆንም ዛሬም የበቀል ስሌት እየሰራ እናያለን። ዛሬም በአፈዮዲ መንገድ ውስጥ በመሄድ የበቀል ሂሳብን ለማወራረድ አፈሙዝን ማንሳት የስሌታችን መግለጫ ሆኗል። ሁሉም የራሱ እውነት ያለው ቢሆንም፤ ነገርግን የምንሄድበት የስሌት መንገድ ለሰላም የምንሰጠውን እርቀትን ያሳያል። ማንኛውም አይነት አለመግባባት ያለ አፈሙዝ ሊፈታ የሚችልበት አገራዊ ባህል ባልዳበረበት ሁኔታ አፍርሶ መስራት መልሶ አፍርሶ መሥራትን እየወለደ እንዲሁ እናዘግማለን።
ዮዲት ፍላጐቷን በሌላ መንገድ ማስረጽ አትችልም ነበር ወይ? ለሚለው ጥያቄ የሚገኘው መልስ ከዘመን አንጻር የጠበበ ሊመስል ይችላል። ነገር ግን ቀጥሎ የምናነሳው ግለሰብ የሄደበት መንገድ ከዮዲት በፊት የሆነ ነበርና አማራጭ ሌላ መንገድ ሊኖር እንደሚችል አመላካች ነው። የክርስትና ሃይማኖትን አጥፍታ የአይሁድን እምነት ማንበር ፍላጎቷ ያደረገችው ሰው የሄደችበት መንገድ በማጥፋት መትከል ነበርና ጉዳቱ የከፋ ሆነ፤ ኢትዮጵያንም ሰበራት። ጠመንጃን የራስን ፍላጎት ለመጫኛ የመጠቀም መንገድ ድሮም የነበረ አሁንም ያለ እንድንልም ሆነናል። የሕዝብ መንግሥት ለሕዝብ ፍላጎት በሚባልበት፤ ዴሞክራሲ የተለያዩ ፍላጎቶችን አቻችሎ ለመኖር ያስችላል በምንልበት ዘመን እና ልዩነቶችን ለመፍታት ጠመንጃ መወልወል ብቸኛው መንገድ አድርገን እየኖርን አለን። የአፈሐንዲ መንገድን ፍለጋ!
አፈሐንዲ – የ ሐንዲው አብራ መንገድ
ወቅቱ ቅርብ ጊዜ አይደለም። በፍጹም ቅርብ አይደለም፤ በጣም እሩቅ፤ ከዛሬ 2500 አመት በፊት። አዎን በኢትዮጵያ የሆነ ታሪክ። የጦርነት ታሪክ። ሳይወዱ በግድ የገቡበትን ጦርነት በድል አጠናቆ የሚሻለውን መንገድ የሰላሙን መንገድ የማሳየት ታሪክ። የሐንዲው አብራ መንገድ።
አሮጌው የአዲስ ዓመት አዲስ ቃል በምንም ዓይነት ጊዜ ውስጥ የማያረጅ መሆኑ ማሳያ። ፍቅር ሆነ ሰላም እንዲሁም ሁለንተናዊ ብልጽግና ፈጽሞውኑ የሚያረጁ ቃላት አይደሉም። አዲስ አመት በመጣ ቁጥር የምንጠራቸው የመልካም ምኞት መግለጫዎቻችን ዓመታትን ተሻግረው ውጤትን የሚያመጡ መሆናቸው ከክርስቶስ ልደት በፊት በሐንዲው አብራ የተሄደባቸው ናቸው።
ዛሬ በጥቂቱ ከታሪክ መዝገብ የፍቅርን መንገድ በመሄድ መፍትሔን ለመፈለግ የወደደውን ሐንዲው አብራን እናንሳው። ይህ ሰው ከክርስቶስ ልደት በፊት ኢትዮጵያን የመምራት እድልን ያገኘ ሰው ሲሆን ዛሬ ከክርስቶስ ልደት ከሁለት ሺ ዓመታት በኋላ እናንሳው። ታሪኩ የዚያን ወቅት ኃያል መንግሥት ትዕቢት ያሳየናል። የፍቅር መንገድ እርቀትንም እንዲሁ።
ፍቅርን ማዕከል ባደረገ የአመራር ዘዬ የሚያምነው ሰው በጠላቶቹ በመወረሩ ምክንያት በማይፈልገው ጦርነት ውስጥ ራሱን አገኘው። የዛሬ ኃያላት አገራት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የያዙት ሚና ግራ በሚያጋባበት ወቅት ውስጥ ሆነን የንጉስ ሐንዲውን ዘመን ስንመለከት የእርሱ ዘመን ኃያላኑን እናገኛቸዋለን። ፋርሶችን!
የዚያን ዘመን ኃያላኖች ፋርሶች ኢትዮጵያን ወርረው በመያዝ የወርቅና ማዕድን የሚገኝባትን “ፊላዬ” የተባለች ከተማን ተቆጣጠሩ። ኃያላኖቹ ፋርሶቹ ሹመትን የሰጡት አርአንዲስም የተሰኘው የግብጽ ንጉስ ይህን ሲሰማ በፋርስ ሥር ካሉት ግብጽ፣ ሜዶን፣ ሊቢያ እንዲሁም ሌሎች ግዛቶች የተውጣጡ ኃያል ወታደሮቹን ይዞ መጣ። ኢትዮጵያውያንም ፈልገው ሳይሆን ተገደው ወደ ጦርነቱ ገብተው ድል ይዘው ለመመለስ ተዋደቁ። ኢትዮጵያውያኑ ድል ቀናቸውና ጦርነቱንም አሸንፈው ንጉስ አርአንዴስን ማረኩ።
የተማረከው ንጉስ ዕጣ ፈንታ ቀጥሎ የመጣው ጥያቄ ነበር። በሐንዲው አብራ መንገድ ግን የንጉሱ ዕጣ ፈንታ ቀላል ነበር። መግደል መንገዱ አልነበረምና አልገደለውም፤ ማጎሳቆልም እንዲሁ የሚጨምረው አንዳች ዕጣ አልነበረውምና አላጎሳቆለውም። በተቃራኒው ቁስሉ እንዲታከም አደረገ። በእንክብካቤ እንዲያዝም። ከእዚያ ግን ምርኮኛው የማይጠብቀውን ነገር ነገረው እንዲህም አለው፤ “እኔ በአባይ የተከለለው የጥንቱ አገሬ ይበቃኛል፤ ፍርድንና ሕግንም ለማክበር ስል አንተንም በነፃነት ለቅቄአለሁ። ነገር ግን ለወደፊቱ ከወሰንህ አትለፍ። ለፋርሱ ንጉስም እንዲህ ብለህ ፃፍለት፤ ንጉስ ሐንዲው ድል አርጎኛል ነገር ግን የራስህን አገር መልሶ ለቆልሃል። ይህንንም ማድረጉ ወዳጅነትህን ፈልጎ ነው። ምክንያቱም ፍቅር ለሠው ልጅ ከእንቁ የበለጠ ነገር ነውና። ይሁን እንጂ በጦር ከመጣህ ለመዋጋት ወደ ኋላ አልልም።”
ምርጫችንን ስንፈልግ
ምርጫችንን ስንፈልግ በዮዲት እና በሐንዲው መካከል እንዋልላለን። እኛ የፈለግነው ብቻ ሳይሆን ሲቀር እናዝናለን። ሳንፈልገው ከኃዘን፤ ስደት፤ ሞት ጋር ስንገናኝ እንተክዛለን። መፍትሔ ፍለጋ የሚሆን መተከዝ ሊሆን ግን ያስፈልገዋል።
እንደትውልድ ቆም ብለን ስሌት መቀየር ይኖርብናል። ተገዶ ጠመንጃ የመያዝን እውነት ብንረዳውም እንደ አገር የአስተሳሰብ ለውጥ አምጥተን የተረጋጋውን መንገድ ለመያዝ ውሳኔ ላይ መድረስ አለብን። ዮዲት የእኔ የምትላቸው ፈላሾቹ ከደረሰባቸው ተነስታ ብለን የጭካኔውን መጠን ትርጉም ልንሰጠው እንችል ይሆናል። ነገር ግን እንደ ሐንዲው ተወግቶም የሚሻለውን መንገድ ማሳየት ይቻላል።
የታክሲ ላይ ጸብ ውስጥ ስለማገላገል ብሎ ሕይወቱን ያጣው ወጣት ለሰላም የሚከፈለውን ዋጋ ርቀት ያሳየናል። ሳይፈልጉ መጎዳት፤ ያለጊዜው መሞት። ግን የግድ የነበረ ውሳኔ።
ምርጫችንን ስንፈልግ በፍጹም ያልተጎዳን ስለሆንን ሳይሆን ነገ ላይ የበለጠ ላለመጎዳዳት በሚጠቅመው እንጂ። የማያረጀውን ቃል ከቅርባችን ለማድረግ ለምን የአዲስ ዓመት መለወጫን እንጠብቃለን። ዛሬም፤ ነገም እንጠቀምበት። አፈዮዲ ወይንስ አፈሐንዲ የቱ ይሆን ችግርን በአፈሙዝ ከመፍታት ስሌት የሚያወጣን? ከሞት ጋር በየደቂቃው እየተጋፈጡ ዋጋን እየከፈሉት ባሉት ሁሉ ጫማ ላይ ቆመን የምንመልሰው ጥያቄ፡፡
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ኅዳር 18/2014