የተወለደው ጎንደር ውስጥ እንፍራዝ በምትባል ከተማ አቅራቢያ ነው። በዚህም የተነሳ ብዙዎች እሱን ከጎንደር ሙዚቃ ጋር አያይዘው ያነሱታል። እሱ ግን እኔ እንዲያውም ከኢትዮጵያ ክፍሎች ሁሉ ጭራሽ የማላውቀው ጎንደርን ነው ይላል። በተቃራኒው እሱ የተፈጠረው ለከተማ ኑሮ እንደሆነ ይናገራል።
በእርግጥም ኤልያስ እና አዲስ አበባ የተዋወቁት ገና በልጅነቱ በ8 ዓመቱ ነው። 12 ልጆች ከወለዱት እናትና አባቱ ወ/ሮ ታሪክ ታመነ እና አቶ ተባበል ተፈራ ተለያይቶ አዲስ አበባ ታላቅ እህቱ ጋር መጥቶ መኖር ጀመረ። ብዙም ሳይቆይ ግን ቤተሰቦቹ እሱን ወደ ጎንደር ለመመለስ ሲመካከሩ የሰማው ኤልያስ ከልቡ የሚወዳትን አዲስ አበባን ትቶ ወደ ገጠር መመለስ ባለመፈለጉ ከእህቱ ቤት ጠፋ። ገዳም ሰፈር አካባቢ የሚገኝ ቡና ቤት ውስጥ በመላላክ እና መሰል ስራዎችን በመታዘዝም ስራ ጀመረ።
የሚሰራበት ቡና ቤት ውስጥ ማታ ማታ በማሲንቆ ሙዚቃ የሚያቀርቡ ባልና ሚስት ድምጻውያን ስራቸውን ጨርሰው መሰንቋቸውን አስቀምጠው ሲሄዱ ኤልያስ ማሲንቆዋን እያነሳ መጫወት ይጀምራል። ከዚያም ወደ ሌሎች አካባቢዎች በመሄድ ሙዚቃ መጫወት እና ገንዘብ ማግኘት ጀመረ።
የ12 ዓመት ልጅ እያለ አንድ ቀን አምባሳደር ቴአትር ሙዚቀኛ እንደሚቀጥር ሰማ። ሄዶ ተወዳደረ። ተፈትኖም አለፈ። ነገር ግን የ12 ዓመት ልጅ በህጉ መሰረት ለመንግሥት ሥራ ቅጥር ስለማይበቃ እድሜው 15 ነው ተብሎ ተቀጠረ። በ12 ዓመቱ የነ15 ዓመት ልጅ ነው ተብሎ የተቀጠረው ኤልያስ የ 100 ብር የወር ደመወዝተኛ ሆነ። በወቅቱ ዝነኞቹ እነ አበበች ደራራ እና ጸሀዬ ዮሀንስም አብረው የአምባሳደር ተቀጣሪዎች ነበሩ።
ከዓመት በኋላ አምባሳደር ቴአትር የፊልም ማእከል እንዲሆን ተወሰነና እነ ኤልያስ ወደ ራስ ቴአትር ተዘዋወሩ። ይህ አጋጣሚ ራስ ቴአትር የቴአትር ቤቶች ቁንጮ እንዲሆን አደረገው። ምክንያቱም በድምጻውያን በኩል እነ ጸሀዬ ዮሀንስ ፤ አበበች ደራራ ፤ አስቴር ከበደ ፤ በቴአትሩ በኩል ደግሞ እነ ንጉሱ ዘውገ፤ ደበሽ ተመስገን ፤ ጥላሁን ጉግሳ እና መሰል ኮከብ ተዋንያን አንድ ላይ ተሰብስበው የራስ ቴአትር ተቀጣሪ በመሆናቸው ነው።
ይህ የከዋክብት መሰባሰብ ግን ለኤልያስ አዲስ ተግዳሮት ይዞበት ነው የመጣው። በንጽጽር ከሌሎቹ ድምጻውያን አንጻር በመድረክ አያያዝ ደከም ይላል የተባለው ኤልያስ ከድምጻዊነት ወደ ሙዚቃ ተጫዋችነት እንዲቀየር ተደረገ። ይህ ሁኔታ ኤልያስን እልህ ውስጥ ከተተው። ስለዚህም በቴአትር ቤቱ ውስጥ በሙዚቀኝነት እየተጫወተ ማታ ማታ በክበብ ላይ ደግሞ በድምጻዊነቱ ገፋበት። በክበብ ሙዚቃ ውስጥ ከሚያደንቁት ከሚደነቁት መካከል ደግሞ አንደኛው ዝነኛው የጥበብ ሰው ተስፋዬ ለሜሳ ነበር።
ከሙዚቀኛነት በበለጠ ታዋቂ ድምጻዊ ለመሆን እና ችሎታውን ለማስመስከር የቆረጠው ኤልያስ የራሱን አልበም ለመስራት እንቅስቃሴ ጀመረ። ከዝነኛው የትግርኛ ድምጻዊ ኪሮስ አለማየሁ እና ሌሎች ጋር በመሆን ግጥም አሰባስቦ እና ዜማ ቀምሮ ኪሮስ በክራር ራሱ ኤልያስ ደግሞ በመሰንቆ አዋህደውት ሙዚቃዎቹን ቀረጸ።
የቀረጸውን ሙዚቃ ይዞም ወደ አሳታሚዎች ጋ ሄደ። ነገር ግን እሱ እንዳሰበው አሳታሚዎች ሙዚቃውን ለማሳተም ሳይፈልጉ ቀሩ። ሙከራውን ቀጠለ። አንድ ቀን ወደ ዝነኛው አምባሰል ሙዚቃ ቤት ሄደ። በር ላይ አንድ ወጣት አገኘ። ”ባለቤቱን ፈልጌ ነበር” አለው። ”እኔ ነኝ ባለቤቱ፤ምን ፈልገህ ነው?” አለው።
ኤልያስ ሃሳቡን አስረዳ። ”የቀረጽከውን ሙዚቃ ይዘሃል?” አለው ። “አዎ” አለ። ካሴቱን ተቀብሎት ወደ ውስጥ ገባ እና ማዳመጥ ጀመረ። ውስጥ ከነበሩት ሰዎች አንዱ ስለ ኤልያስ ድምጽ ማማር ሲናገር ኤልያስ ሰማና ደስ አለው። ና ግባ ተብሎ ወደ ውስጥ ሲገባ ያ የኤልያስን ድምጽ ማማር ሲናገር የነበረው ክለብ ውስጥ ሲዘፍን ሰምቶ ያደንቀው እና ያበረታታው ተስፋዬ ለሜሳ መሆኑን አወቀ።
አምባሰል የኤልያስን ሙዚቃ ለማሳተም ተስማማ። ኤልያስ ግን አንድ ፍላጎት ነበረው። እሱም ሙዚቃው እንዲቀረጽ የሚፈልገው በወቅቱ በጣም ዝነኛ ከነበሩት ሮሃ ባንድ ጋር እንዲሆን ነበር። የአምባሰል ሙዚቃ ባለቤት ፍቃዱ ዋሬ በሃሳቡ ተስማማ። ኤልያስም አልበሙን በ አንድ ሺ ብር ለአምባሰል ሙዚቃ ቤት ለመሸጥ ተስማምቶ 25 ብር ቀብድ ተቀበለ።
”እውነቱን ለመናገር እንኳን በአንድ ሺ ብር በነጻም ቢለኝ እሺ ነበር የምለው። የኔ ፍላጎት አልበሙ እንዲወጣ እና እንዲታወቅ ነበር” ይላል ኤልያስ። ከዚያም የሙዚቃው ሳምፕል ሙዚቃ ማሕበር ገብቶ ተገምግሞ አለፈ እና ለቀረጻ ዝግጁ ሆነ። የአልበሙ ቀረጻ ሊካሄድ ሲል ኤልያስ እና ሮሃዎች ተገናኙ። ኤልያስ ከዚያ በፊት ከሙሉ ባንድ ጋር የመዝፈን ልምዱ ስላልነበረው ተቸገረ። እንደምንም አንድ ሁለት ሙዚቃዎች ላይ ተቸግሮ ከዘፈነ በኋላ ግን ለመደው እና የቀረውን ሙዚቃ በቀላሉ ተቀረጸ።
ቀረጻው ካለቀ በኋላ ኤልያስ ከመስሪያ ቤቱ ራስ ቴአትር ጋር ኪነ ጥበብ ለማቅረብ መላው ኢትዮጵያን ዞረ። ጉዞው ተጠናቆ ወደ አዲስ አበባ ሲመለስ በአዲስ አበባ ዋነኛ ሙዚቃ ቤቶች የኤልያስ ሙዚቃ እንደሚወጣ የሚገልጽ ማስታወቂያ ተለጥፎ አየ። በቀጣይ ሰኞ ሙዚቃ እንደሚወጣ ይናገራል ማስታወቂያው።
ካሴቱ ከመውጣቱ በፊት ግን ኤልያስ ሙዚቃውን ለአለቃው ሙሉ ገበየሁ ወስዶ አሰማው። ሙሉ በጣም ተገረመ። ኤልያስም ደስ አለው። ካሴቱ የሚወጣበትን ቀን በጉጉት መጠበቅ ጀመረ። በመሃል ግን በዚያው ሳምንት ያልታሰበ ችግር ተፈጠረ። አንጋፋው ድምጻዊ ዳምጠው አየለ እና ሌላኛዋ ተወዳጅ ድምጻዊት ኩኩ ሰብስቤ ሙዚቃ ለቀቁ።
ኤልያስ ከነዚህ ኮከብ ድምጻውያን ጋር ተፎካክሮ ስኬታማ መሆን እንደማይችል አሰበ። ስለዚህም አሳታሚውን አቶ ፍቃዱን ካሴት መውጫውን ቀን እንዲያራዝምለት ጠየቀው። አሳታሚው በኤልያስ ጥያቄ አልተስማማም። ለሕዝብ ቀጠሮ ሰጥቻለሁ፤ ስለዚህ በዚያ ቀን ነው የሚወጣው አለው። ኤልያስ እና አሳታሚው አልተስማሙም። አሳታሚው ለኤልያስ የተስማመበትን አንድ ሺ ብር ሰጥቶ እና ካሴቱ በተባለው ቀን እንደሚወጣ ቁርጡን ነግሮት ሸኘው። ኤልያስ እያለቀሰ ወደ ቤቱ ተመለሰ።
ከቀናት በኋላ አልበሙ ተለቀቀ። ተደማጭነት አላገኝም ብሎ ሰግቶ የነበረው ኤልያስ ወደ ሙዚቃ ቤቶች ሄዶ ሲያይ ግን እየሆነ ያለው እሱ ካሰበው በተቃራኒው ነበር። ሕዝብ ሙዚቃ ቤት ደጃፍ ላይ ተኮልኩሎ የኤልያስን ሙዚቃ እየሰማ ነው። እነ ዳማይ ዳማይ ፤ ማማዬ ማማዬን የያዘው አልበም የወቅቱ ቁጥር አንድ አልበም ሆነ። ኤልያስም ከሙዚቀኛነት ወደ ታዋቂ ድምጻዊነት ተሸጋገረ።
ዝነኛ የሆነው ኤልያስ አሁንም በራስ ቴአትር በሙዚቀኛነቱ ብቻ ቀጠለ። በድምጻዊነቱ ለመስራት ፈቃደኛ አልነበረም። ነገር ግን መድረክ ላይ ወጥቶ መሰንቆውን ይዞ ሲቆም ሕዝቡ እሱን ለመሸለም ይመጣ ነበር። ከዚያም “በል አሁን ሕዝብ እየጠየቀ ስለሆነ ውጣና ዝፈን፤ እምቢ ካልክ ትታሰራለህ” ተባለ። ዘፈነ። ሕዝቡ ቢስ ቢስ (ይደገም) አለ። ሙዚቃው ተደገመ።
በማግስቱ ጠዋት ቢሮ ሲገባ ደብዳቤ ተዘጋጅቶ ጠበቀው። ደብዳቤውን ይዞ በወቅቱ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር የነበሩት ግርማ ይልማ ቢሮ እንዲገባም ታዘዘ። ደብዳቤው ኤልያስ አልዘፍንም ብሎ እምቢ በማለቱ ሚኒስትሩ እና የቴአትር ቤቱ ስራ አስኪያጅ ተስፋዬ ለማ በጋራ ሆነው ኤልያስን ለማስደንገጥ የጻፉት ነበር።
እንደገባ ሚኒስትሩ ለአዲሱ አልበሙ አድናቆታቸውን ከገለጹ በኋላ ደብዳቤውን አነበቡለት። ደብዳቤው በጣም ጠንከር ያለ ነበር። ከዚያም ኤልያስ ለምን አልዘፍንም እንዳለ ለሚኒስትሩ አስረዳ። በል ካሁን በኋላ እንድትዘፍን ብለው አበረታትተው ድብዳቤውን ቀደው ጣሉት። ከቢሮ ሊወጣ ሲልም “ካሴት አላመጣህልኝም እንዴ?” አሉት። ኪሱ ውስጥ ከያዘው ካሴት ሁለቱን አውጥቶ ሰጣቸው እና እየሳቀ ቢሮውን ለቅቆ ወጣ።
በ1976 ገደማ ከወጣው ከዚያ የመጀመሪያ አልበም በኋላ ኤልያስ በዝነኞች ተርታ ተሰለፈ። እንደ ወቅቱ ዝነኞችም ለሕዝብ ለሕዝብ ዘመቻ ተመረጠ። ለዘመቻው ልምምድ ማድረግም ጀመረ። በወቅቱ ኤልያስ ወደ ፈረንሳይ ከሚሄደው ቡድን መሪ ድምጻዊ የነበረ ሲሆን በሕዝብ ለሕዝብ ዘመቻ ቡድኑ ውስጥ ደግሞ እነ ጥላሁን ገሰሰ ፤ መሀሙድ አህመድ ፤ ጸሐዬ ዮሀንስ ፤ ነዋይ ደበበ ፤ እና ሌሎች ዝነኞችም ነበሩ።
ዘመቻው ከመካሄዱ በፊት ግን ብሄራዊ ቤተ መንግሥት ሙዚቃ እንዲቀርብ ትእዛዝ ተሰጠ። ሁሉም ድምጻውያን ሙዚቃቸውን እንዲያቀርቡም ፕሮግራም ወጣ። ኤልያስ እዚህም ጋ ችግር ገጠመው ። በወጣው መርሃ ግብር መሰረት የኤልያስ ተራ አስረኛ ሲሆን፣ ከሱ በፊት ዘጠነኛ ላይ ያለው ደግሞ ጥላሁን ገሰሰ ነበር።
ኤልያስ ተቃውሞውን አሰማ። እንዴት ከጥላሁን በኋላ አቀርባለሁ አለ። በእርግጥም ጥላሁን ካቀረበ በኋላ ሙዚቃ ማቅረብ በማር ላይ ስኳር እንደመጨመር ነበር። ነገር ግን የኤልያስ ቅሬታ ሰሚ አላገኘም። ታቀርባለህ ተባለ። እምቢ ማለት አይቻልም።
ቀኑ ደርሶ የደርግ ሊቀመንበር ኮለኔል መንግስቱ ሃይለማርያምን ጨምሮ ሁሉም ከፍተኛ ሹማምንት በታደሙበት ሙዚቃው መቅረብ ጀመረ። ኤልያስ እንደፈራውም ጥላሁን ተራው ደርሶ ገብቶ መድረኩን አናወጠው።
ከዚያም ተረኛው ኤልያስ ሆነ። ያኔ አገሪቱ በጦርነት ውስጥ በመሆኗ ከአገር ዘፈን ውጭ የፍቅር ሙዚቃ ተከልክሎ የነበረ ቢሆንም፣ ኤልያስ ማማዬ ማማዬን አቀረበ። የፍቅር ሙዚቃ ናፍቆት የነበረው ሕዝብ አዳራሹን አናወጠው። ጨርሶ ሊወርድ ሲል ይደገም የሚል የሕዝብ ጩከት ተሰማ።
ኤልያስ በሕዝቡ ምላሽ ደስታ እና ድንጋጤ ይዞታል። የፕሬዚዳንት መንግሥቱ ጥበቃ የነበረ ግዙፍ ሰው ወደ ኤልያስ እየሮጠ ሲመጣ ኤልያስ ፈራ። ጥበቃው ተመለስ ፤ ዝፈን እያለ በቁጣ ይጮሃል። ኤልያስ ተመልሶ ሙዚቃውን ደገመ። ሞቅ ባለ አድናቆት ታጅቦ ከመድረክ ወረደ።
ከዚያ በኋላ ወደ ፈረንሳይ ሄዶ ዝግጅቱን አቀረበ። ከዚያ ሲመለስ በርካታ ሙገሳ ቀረበለት። ከፈረንሳይ ከመጣ ከሁለት ወር በኋላ ተጠርቶ የሕዝብ ለሕዝብ ዘመቻ አባል ሆነ። ከዘመቻው ሲመለስ ኤልያስ ለበርካታ ዓመታት ከሰራበት ራስ ቴአትር ለቀቀ። ከ8 ወር በኋላ እንደገና ተጠራ። ከዝነኛ ድምጻውያን ጋር በመሆን ወደ አስመራ ተላከ። ከዚያም ወደ ጃፓን ተላከ። ከጃፓን ሲመለስ ከአሜሪካ የአሜሪካ ግብዣ ደረሰው። ኤልያስ እና ኢትዮጵያም ተለያዩ።
ኤልያስ አሜሪካ ከሄደ በኋላ ድምጻዊነቱን እየሰራ መደበኛ ሕይወቱን ቀጠለ። ለሶስት አስርት ዓመታትም በአሜሪካ ኖረ። ከሙዚቃውም ባለፈ በሌሎች በተሰማራባቸው ሥራዎች ግብር በመክፈሉ የተነሳ አሜሪካ ላይ ጡረታውን አስከብሮ ወደ ትውልድ አገሩ ተመልሷል።
እዚህ አንዳንዴ የምሽት ክበቦች ላይ እየተጋበዘ ሙዚቃውን ያቀርባል። አሁንም ሙዚቃ ለመስራት እና ከሕዝብ ጋር ለመገናኘት እቅድ አለው። እሱ አዲስ ሙዚቃ ባይሰራም እንኳ ግን ፤ ዛሬ ላይ ያኔ የሰራቸው ሙዚቃዎች እንደ አዲስ በአዲስ አበባ ክለቦች በተለያዩ ወጣት ድምጻውያን እየተዜሙ ናቸው። በተለይም ማማዬ ማማዬ ዛሬም ድረስ ከምርጥ ተደማጭ ሙዚቃዎች ተርታ ነው ያለው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ኤልያስ አሁን ላይ የእረፍት ቀኑን ከጓደኞቹ እነ ነዋይ ደበበ ፤ ጸሀዬ ዮሀንስ እና ሌሎችም ጋር በመሆን በመጫወት ያሳልፋል። በተጨማሪም ለእግር ኳስ የተለየ ፍቅር አለው። ቀንደኛ የቅዱስ ጊዮርጊስ ደጋፊ ነው። እድሉን ካገኘ በእረፍት ቀኑ ስቴድየም መግባት እና የሚወደውን ክለብ ማየት ይወዳል።
ኤልያስ ዛሬ ላይ ኢትዮጵያ ያለችበት ችግር ከመቼውም በላይ ከባድ እንደሆነ ያውቃል። ግን እንደምታሸንፍም ያምናል።”በኔ እድሜ እንዳየሁት ኢትዮጵያ ሁሌም በፈተና ውስጥ ናት። ያኔ ኢትዮጵያ ውስጥ በነበርኩበት ጊዜ ብዙ ወጣቶች አልቀዋል። ከዚያ ደግሞ ተላቀቅን ስንል የዘር በሽታ መጥቶ መከራችንን እያየን ነው። ከዚህ የዘር በሸታ ወጥተን መልካም ጊዜን ያምጣልን ነው የምለው። ምንም ቢሆን ምንም ኢትዮጵያዊነት ተሸንፎ አያውቅም። በኔ እድሜ እንዳየሁት ኢትዮጵያን የተፈታተኑ ሲጠፉ ነው ያየሁት” ብሏል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ኅዳር 5/2014