የምንኖርበት አለም ዘመነ መረጃ ነው።መረጃ ጉልበት ነው።የድል እና የሽንፈት መለያው ድንበር መረጃ የመሰብሰብ የማደራጀት እና የመተንተን አቅም ሆኗል።መረጃ የመሰብሰቢያው፤ የማደራጃው፤ የመተንተኛው እና የማሰራጫው መንገዶች ተበራክተዋል።
ዓለም በኢንተርኔት አንድ መንደር ሆናለች።በዚህም የተነሳ የሰው ልጅ ህይወት እጅጉን ዲጂታላዊ ሆኗል።ዲጂታል ገበያ፤ ዲጂታል ጦርነት፤ ዲጂታል ፍቅር፤ ዲጂታል ጠብ፤ ዲጂታል ወዘተ…ብቻ ዲጂታል የሆነው ነገር ብዙ ነው።ዲጂታላዊነት እጅጉን ከተዋሃዳቸው ዘርፎች መካከል ደግሞ አንዱ እና ዋነኛው የዲፕሎማሲው ዘርፍ ነው።
ዲጂታል ዲፕሎማሲው የዲፕሎማሲ አዲሱ ገጽታ ነው።የህዝብ ለህዝብ ዲፕሎማሲ (public diplomacy) አካል የሆነው ይህ የዲፕሎማሲ አሰራር፤ ኢንተርኔትን በተለይም እንደ ፌስቡክ፤ ትዊተር፤ ኢንስታግራም እና መሰል ማህበራዊ መገናኛዎችን በመጠቀም የዓለምን ህዝብ እና የፖለቲካ አመራር ለማግኘት፤ ለማሳመን እና አጋዥ እንዲሆን ለማድረግ የሚሰራበት መንገድ ነው።
ሀገራት በዚህ መልኩ ፖሊሲዎቻቸውን ያስተዋውቃሉ፤ ድርድር ያደርጋሉ፤ የህዝብን አስተያየት ቅርጽ ያስይዛሉ ወዘተ…።በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ ዲጂታል ዲፕሎማሲን የማይጠቀም ሀገር እና መንግስት የሌለ ሲሆን ብዙ ሀገራትም ለዚህ ስራ የተለየ ትኩረት ሰጥተው፤ ዜጎችን አሰልጥነው፤ በጀት መድበው፤ እቅድ ነድፈው ይንቀሳቀሱበታል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በዚህ ዘርፍ ገና ጀማሪ ናት።ስለዚህም ይህን አዲስ የዲፕሎማሲ አሰራር በፍጥነት ተረድተው የሚንቀሳቀሱ ወጣቶች ያስፈልጓታል።ይህን ሀገራዊ ፍላጎት ተረድተው ሀገራቸውን ለማገልገል በፍጥነት ከተሰማሩት ወጣቶች መካከል ደግሞ አንዱ ወጣት ሱሌማን አብደላ ነው።
ሱሌማን የተወለደው በ1988 ዓ.ም ነው።አባቱ ይማም አሊ ሱሌማን ሲባሉ እናቱ ደግሞ አሚናት ይመር ሙክታር ይባላሉ።ሁለቱም የደቡብ ወሎ ቃሉ ወረዳ ነዋሪ ናቸው።5 ወንድ እና 6 ሴት ልጀች ያላቸው የሱሌማን ቤተሰቦች ሱሌማን 7ኛ ልጃቸው ነው።
ሱሌማን እስከ 6ኛ ክፍል ያለውን ትምህርት የተማረው እዚሁ ሀገር ውስጥ ነው።ከዚያ በኋላ ያለውን ግን በውጭ ሀገር ቋንቋ ነው የተማረው።ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኮምፒውተር ሳይንስ ዲግሪ አለው።
ይህ የኮምፒውተር ሳይንስ ባለሙያው ሱሌማን ነው አሁን ላይ የሀገር የዲፕሎማሲ ዘመቻ ዋና አስተባባሪ የሆነው።ምናልባትም የኮምፒውተር እውቀቱ የዲጂታሉን ዓለም አሰራር እንዲረዳ ሳያግዘው አልቀረም።ይህ የኮምፒውተር እውቀት ግን ለብቻው ሱሌማንን ወደ ፖለቲካ አልሳበውም።
በደል የወለደው የዲፕሎማሲ አዝማች
ሱሌማን ወደ ፖለቲካ እንዲሳብ ያደረገው በደል ነው።“ወደ ፖለቲካ የገባሁት በህወሓት ጭቆና ነው።የዩኒቨርሲቲ ተማሪ በነበርኩበት ወቅት ህወሓት የሽብር ወረቀቶች ትበትናለህ በሚል አንድ ቀን አዲስ አበባ መገናኛ አካባቢ አንድ አሮጌ ድልድይ ውስጥ አስገብተው ሲያሰቃዩኝ አመሹ።ወሎ ውስጥ እያለሁም በተደጋጋሚ በሽብር እየከሰሱ ለህግ ለማቅረብ ሞክረዋል።ግን አልተሳካላቸውም።” ሲል እንዴት አይነት በደል እንደደረሰበት ያብራራል።
ያለፈው አገዛዝ ያደረሰበት በደል ግን ሱሌማንን ጸረ ህወሓት ሳይሆን አፍቃሪ ኢትዮጵያ ነው ያደረገው።ይልቁንም ከሀገር ከወጣ በኋላ የፖለቲካ እንቅስቃሴውን በማስፋት ሀገሩን ለመጠበቅ ጥቅም ላይ አዋለው።ብዙውን ሰዓት ያነብባል፤ ሚዲያዎችን ይከታተላል፤ ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ዘገባዎችንም ሆነ ጽሁፎች ይመረምራል።በዚህ መልኩም ስለ ሀገሩ ብቻ ሳይሆን ስለ ዓለም በተለይም ደግሞ ስለ ኢትዮጵያ ጎረቤቶች በደንብ መገንዘብ ቻለ።
ይህን ግንዛቤውን ይዞ ወደ ማህበራዊ ሚዲያ ብቅ አለ።እሱ የመጣበት ሰዓት ሀገር በከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ ጫና ውስጥ የወደቀችበት እና ዲጂታል ዲፕሎማሲው ገና ማቆጥቆጥ የጀመረበት ወቅት ነበር።ጊዜ ሳያባክን ወደ ዘመቻው ገባ።ጥልቀት የታከለባቸው እና የኢትዮጵያ ጠላቶችን ሴራ የሚያጋልጡ ጽሁፎችን ማጋራት ያዘ።ብዙዎች በጽሁፉ ጥልቀት ወደዱት፤ አደነቁት፤ ተከታዩም ሆኑ።በተለይ በህዳሴ ግድብ ዙሪያና ተያያዥ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የሚጽፋቸው ጽሁፎች እጅግ ብስለት የታከለባቸው እና ጠላትን ራቁቱን የሚያስቀሩ ነበሩ።
የሱሌማን ተከታዮች ቁጥር ማሻቀብ ያዘ።ተከታዩ ሲበዛ እሱም አሰራሩን ቀየረ።ተከታዮቹን ይዞ ወደ ትዊተር መንደር ዘመተ።በተለይ የፖለቲካ ውይይቶች በሚበረክቱበት የትዊተር መንደር ሱሌማን እና ያስከተለው የሳይበር ጦር ግብጽን፤ ሱዳንን እና የእነሱ ተላላኪ የሆነውን ህወሓትን ይረመርም ያዘ።
ማህበራዊ ሚዲያ የጊዜ ብክነት ያስከትላል፤ ፋይዳ የለውም የሚሉትን ወገኖች የሱሌማን እንቅስቃሴ ሀሳባቸውን አስቀየራቸው።በዲጂታል ዲፕሎማሲው ዘርፍ ሱሌማን እና ጓዶቹ የሚሰሩት ስራ በመደበኛው ዲፕሎማሲ ላይ ፋይዳ ሲፈጥርም ታየ።ሱሌማን ስለ ዲጂታል ሚዲያው ጠቀሜታ ሲያስረዳ “ማሀበራዊ ሚዲያ ጠቃሚ ነው።ጠቃሚ መሆኑን አምኖ የሚጠቅም ስራ ለሰራበት ሰው እንደ ማህበራዊ ሚዲያ ጠቃሚ ነገር የለም” ይላል።
ሱሌማን አሁን ላይ በማህበራዊ ሚዲያ ብዙ ተከታይ ካላቸው ኢትዮጵያዊያን መካከል አንዱ ነው።በፌስቡክ ከ230ሺ በላይ በትዊተር ደግሞ ከ129ሺ በላይ ተከታይ አለው።ይህን ሰፊ ሰራዊት እየመራም በሳይበሩ ፍልሚያ በርካታ ድሎችን እያስመዘገበ ነው።
በማህበራዊ ሚዲያ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ግብ ኢትዮጵያ እንደሆችም ይነገራል።”ግቤ የኢትዮጵያን ጥቅም ማስከበር ብቻ ነው” ሲል የሚገልጸው ሱሌይማን፣ በተለይ በህዳሴ ግድቡ ዙሪያ ኢትዮጵያውያን ያላቸው ግንዛቤ ከፍ እንዲል እንደሚፈልግም ይናገራል።
ወጣቱ ሱሌማን የሱ እኩዮች በፖለቲካው ዘርፍ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጨመር ይፈልጋል።”ወጣቶች ወደ ፖለቲካው ዓለም ከመጡ የነቃ ተሳትፎ ያደርጋሉ።ዘመናዊ የፖለቲካ ፍልስፍናን ከማመንጨት አኳያ ሀገራቸውን በነሱ የፖለቲካ ፍልስፍና መቅረጽ ይችላሉ።”ይላል።
በእርግጥም አሁን ላይ ካለፈው የማርክሲስት ሌኒኒስት ተቸካይ የፖለቲካ ርዕዮት ተላቅቃ ወደፊት ለመራመድ ለምትፈልግ ሀገር የሱሌማን እና መላው ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ተሳትፎ አስፈላጊነት የማይገለጽ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በኮምፒውተር ሳይንስ ምሩቅ ሆኖ በዲፕሎማሲው ዘርፍ ሀገሩን በፈቃዱ እያገለገለ የሚገኘው ሱሌማን፣ ቀጣይ እቅዱ ኢኮኖሚው እና ሚዲያው ላይ ነው።“ቀጣይ እቅዴ ጠንካራ ሚዲያ ማቋቋም ነው።መጽሀፍ የመጻፍም እቅድ አለኝ።ለሀገራችን መፍትሄ የሚሆን ስራ መስራት የሁልጊዜም እቅዴ ነው።በተለይ ኢኮኖሚያዊ ነገሮች ላይ በሰፊው ለመስራት እሞክራለሁ።››ሲል ያብራራል።
ከሚዲያ አንጻር ኢትዮጵያ ውስጥ የአረብኛ ሚዲያዎች መክፈት ቀላል ስለሆነ እሱን ሸፍኖ የሚሰራ ሚዲያ ማቋቋም እፈልጋለሁ ይላል።ከጎረቤት ሀገራት ጋር የሚኖረንን የኢኮኖሚ እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ማጠናከር የሚችል ለኢትዮጵያም ድምጽ መሆን የሚችል ሚዲያ ለማቋቋም እቅድ አለኝ” ብሏል።
የሱሌማን ሀሳብ በእርግጥም አስፈላጊ እንደሆነ አያጠራጥርም።በግብጽ እና ጀሌዎቿ በሚዘወሩ የአረብ ሚዲያዎች ቀኑን ሙሉ ስትረገም አና ስትኮነን ለምትውል ሀገር የራሷን የአረብኛ ድምጽ ፈልጋ ማግኘት እንዳለባት የታመነ ነው።ሰለዚህም የአረብኛ የሚዲያ ተቋም ማቋቋም እና የመካከለኛው ምስራቅ ቀጠናን በራሱ ቋንቋ ማናገር አስፈላጊ ነው።
ዲፕሎማት ያልሆነ ዲፕሎማት
ሱሌማን ተቋም ላቋቁም ሲል በሌላ መልኩ ሱሌማን ራሱ ከሚሰራው ሰራ ግዝፈት እና አስፈላጊነት አንጻር ራሱ ተቋም ነው በማለት የሚያሞካሹት ሰዎች አሉ።ከነዚህ መሀከል በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካሪ የሆኑት እና በህዳሴ ግድብ ዙሪያ በማህበራዊ ሚዲያ ጠንካራ እንቅስቃሴ በማድረግ የሚታወቁት ሱልጣን አባጊሳ አንደኛው ናቸው።
አቶ ሱልጣን በፌስቡክ ገጻቸው ስለ ሱሌማን የሚከተለውን ብለው ነበር።”በእኛ ሀገር የትዊተር ዲፕሎማሲ እድሜው አጭር ነው፤ አንዳንድ ተቋማት እና ግለሰቦች ቀድመው ጀምረውታል፤ ነገር ግን በሀገራችን ትዊተርን በመጠቀም በዓለም ላይ ተጽእኖ መፍጠር የተጀመረው ባለፉት ጥቂት ወራት ነው ሲሉ ይገልጻሉ።
አቶ ሱልጣን እንደሚሉት፤ ይህን ስራ ሀገር ወዳድ ዜጎች በራስ ተነሳሽነት የሀገራቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ ሲሉ ጀምረውታል።ከነዚህ ተጽእኖ ፈጣሪ የትዊተር ሰራዊት መካከል ቁንጮው ደግሞ ሱሌማን አብደላ ነው።የሱሌማን አብደላ የትዊተር ገጽ በአሁኑ ወቅት በሀገራችን የትዊተር ታሪክ ከክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የትዊተር ገጽ ቀጥሎ ተጽእኖ ፈጣሪ ነው።
‹‹ሱሌማን አብደላ የማይደክም የማይሰለች ዲፕሎማት ያልሆነ ዲፕሎማት ነው።ሚዲያ ሞኒተር ያደርጋል።ከእድሜው በላይ ለሀገር አሳቢ፤ የሀገራችን ዲጂታል ዲፕሎማሲ ላይ መሰረታዊ ለውጥ ያመጣ ወጣት ነው።”በማለትም አቶ ሱልጣን አሞግሰውታል።
በእርግጥም ሱሌማን አብደላ ተጽእኖ ፈጣሪነትን ለማየት ትዊተር ገጹን መመልከት በቂ ነው።እሱ የሚያስተባብራቸው የትዊተር ዘመቻዎች በብዙ መቶ ሺ የመልዕክት ልውውጥ የሚደረግባቸው እና ሚሊየኖች ዘንድ ተደራሽ መሆን የሚችሉ ናቸው።
በቅርቡ ይህ ተጽእኖ ፈጣሪ ወጣት ለሀገሩ በሚያደርገው ትግል ያልተደሰቱ የጠላት ሀገራት ሰዎች በስራው ላይ ተጽእኖ ፈጥረውበታል።ይህ ጉዳይ ከተሰማ በኋላም ብዙዎች መንግሰት ለዚህ ወጣት ጥበቃ እንዲያደርግ አሳስበዋል።
ከነዚህ መካከል አንዱ የሆነው እና ሙክታሮቪች ኡስማኖቭ በሚል ስም የሚታወቀው የማህበረሰብ አንቂ ስለ ሱሌማን ‹‹ ሱሌማን አብደላ በራሱ ተቋም ነው።በርካታ አምባሳደሮች እና ዲፕሎማቶች ያልሰሩትን ስራ ለሀገሩ የሰራ የቁርጥ ቀን የኢትዮጵያ ጀግና ነው።በመካከለኛው ምስራቅ በኢትዮጵያ ላይ እየተሸረበ ያለውን ሴራ በዝርዝር እያስረዳ በርካቶችን እያነቃ ያለ ወጣት ነው።›› በማለት አሞካሽቶታል።
የእረፍት ጊዜ
ሱሌማን ባለትዳር ነው።ነገር ግን እንደ ሰው አርፌ ኑሮዬን ልኑር አላለም።ይልቁንም ለሀገሩ በሚያደርገው እንቅስቃሴ በግል ህይወቱ ላይ ችግር ቢያጋጥመውም እንኳን ሳያፈገፍግ እየታገለ ነው።በዚህ የተነሳም የእረፍት ቀናት ብዙም የለውም።“ትርፍ ጊዜ ብዙም የለኝም።የኔ ትርፍ ጊዜ ሌሊት ከ9 ሰዓት እስከ 10 ሰዓት ነው።እሱም ስፖርት የምሰራበት ሰዓት ነው።የቀረውን ጊዜ ሚዲያ ላይ በመጻፍ፤ የተለያዩ ሚዲያዎች ስለ ኢትዮጵያ ምን እንዳሉ በመከታተል ነው የማሳልፈው” ይላል።
መልዕክት
በኢትዮጵያ እና ኢትዮጵዊነት ላይ ጥብቅ እምነት ያለው ሱሌማን በመጨረሻ መልእክት እንዲያስተላልፍ ጋበዝነው።”ኢትዮጵያ ወደፊት የምስራቅ አፍሪካ ሀያል ሀገር መሆን ትችላለች።እንድትሆንም ከሚተጉ ሰዎች አንዱ እሆናለሁ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።የኢትዮጵያ ችግር በጣም ቀላል ነው።የማንግባባቸው ነገሮች አሉ።እነሱን ከችግሩ መነሻ ጀምረን ተወያይተን መፍትሄ ካበጀንላቸው በቅርብ ዓመታት ራሳችንን ችለን የምንቆም ህዝቦች እንሆናለን።ለኢትዮጵያ ህዝብ የማስተላልፈው መልዕክት አሁን ያጋጠመንን መከራ በጋራ ተሰልፈን ኢትዮጵያ አሸናፊ እንድትሆን ሁላችንም ሀገራዊ ግዴታችንን እንወጣ የሚል ነው” ብሏል።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 28/2014