በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማግስት እንደገና የተቋቋመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከ75 ዓመታት በላይ እድሜ ያስቆጠረ አንጋፋ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው።የዓለም ሰላምና ደህንነት እንዲጠበቅ፣ አስፈላጊ በሆኑባቸው ስፍራዎች ሁሉ ሰብአዊ ድጋፎች እንዲደረጉ መስራት፣ ሰብአዊ መብቶችን ማስጠበቅ እና ዓለም አቀፍ ህግ እንዲጠበቅ መስራት አቢይ ተልእኮዎቹ ናቸው።
ይህን መስራት የሚያስችሉት የተለያዩ ግዙፍ ተቋማትም በስሩ አሉት።ተቋሙም ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን የዓለምን ሰላም ለማስከበርና የሰው ልጆችን ሰብዓዊ ክብር ለመጠበቅ ተግቶ እየሰራ መሆኑን ይገልጻል።
የተለያዩ አገሮችና ወገኖች እንደሚሉት ግን ተቋሙ ከአመሰራረቱ ጀምሮ የምዕራባውያን ተጽዕኖ ያረፈበትና በእነሱ እሳቤና እቅድ የሚመራ ነው፣ የዓለምን ሁለንተናዊ ጉዳይ እንደማያይ የሚዘወረውም በምዕራባውያኑ ባለጸጎች ስለመሆኑ እነዚህ አካላት ያስገንዝባሉ።በአንዳንድ አገሮች እየተፈጠረ ያለው የሰብአዊ መብት ጥሰትና ፍትህ የጎደለው አሰራርም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው።
ለዚህ ዋና ማስረጃ ሊሆን የሚችለው ድርጅቱ ሥልጣንና ሃላፊነቱን በሁሉም አገራት ህጉን መሰረት አድርጎ በእኩል ደረጃ ሲተገበር አለመታየቱ ነው። ያደጉ አገራት ባላደጉት ላይ የሚፈጽሙትን የመብት ጥሰት መከላከል አለመቻሉ ጠንካራ አለመሆኑን ያመለክታል።አዎን ጠንካራ አይደለም፤ እነዚህ አገሮች ከተቋሙ ህግ ውጪ ሲንቀሳቀሱ አቁሙ ማለት ቀርቶ በጉዳዩ ላይ መረር ያለ ትችት ሲያቀርብ አይታይም።የታዳጊ አገራት በርካታ ችግሮችን የሚመለከትበት መንገድም ባደጉት እና የተቋሙ ዘዋሪ በሆኑት የበለጸጉት አገሮች የሚቀየስ መሆኑም ይገለጻል። ይህም ተቋሙ በሚሰጠው ፍርድና ፍትህ ላይ ላይ ጥያቄ እያስነሳ ይገኛል።
የድርጅቱ ተቋማት አሁን የሚገኙበት ቁመና በጭራሽ በሰብአዊነት ጎራ የሚያሰልፋቸው አይደለም። ለደሃ አገራት ከአደጉት የምዕራቡ ዓለም አገራት በተለየ መልኩ ተገቢ ያልሆነ ብያኔ ሲሰጥና ከድርጅቱ መርህ ውጪ በሆነ መልኩ አገራቱን ማዘዝ ውስጥ ሲገባ እየታየ ነው። በድርጀቱ፣ በተቋማቱ እና በኃላፊዎቻቸው በኩል በሰብአዊነት ስም ኢሰብአዊነትን የሚያስፋፋ ንግድ እየተፈጸመ ነው። ይህም ሁኔታ የተቋሙ ድርጅቶች ወይ በሴረኞች ተጠልፈዋል አልያም ለስውር ተልዕኮ በሰብዓዊነት ስም እንዲንቀሳቀሱ ተደርገው የተመሰረቱ ሊሆኑ ይችላሉ ያሰኛል።
የግጭት ነጋዴዎች ሲባል ነበር የማውቀው፤ የኑሮ መሰረታቸው ግጭትን ማቀጣጠል የሆነ ማለት ነው።ለካስ የኢሰብአዊነት ነጋዴዎችም አሉ። በሰብአዊነት ሽፋን ኢሰብአዊ ተግባርን የሚፈጽሙ፣ የሚያስፋፉ ማለቴ ነው።ስብዕናን ሳይላበሱ በሰብዓዊ ተግባር ላይ ተሰማርተናል እያሉ በሰብዓዊ ፍጡር ላይ ግፍ ይፈጸም ዘንድ አድምተው የሚሰሩ አገሬ ላይ ያሉ በግብረ ሰናይ ድርጅት ስም የተሰማሩ የውጭ ድርጅቶች ድርጊትና እንቅስቃሴም ይህን ያመለክታል።
ስለእውነት ቆመናል፤ የሰው ልጆችን ችግር ለመቅረፍ እየሰራን ነው።የሚሉ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች እውን ምግባራቸው ሰናይ ነው? ዓላማቸውስ ለሰዎች ሰብዓዊ ክብር መጨነቅ ነውን? ብለን ብንጠይቅ፤ የቆሙለት ዓላማና የሚያከናውኑት ተግባር ለየቅል ሆኖ እናገኘዋለን።
ለዚህ ማሳያ ይሆነን ዘንድ ኢትዮጵያ ውስጥ እየፈጸሙ ያሉትን ተግባር መመልከት ይበቃል።የተመድ ድርጅቶች በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ሕወሓት እየፈጸመ ያለውን የሰላም ማደፍረስ ተግባር እንዲያቆም ከማድረግ ይልቅ እንዲቀጥልበት የሚያደርግ ተግባር እያከናወኑ ናቸው። በሃይል ሥልጣን ለመያዝ ባለው ጽኑ ፍላጎት የአገር ሉዓላዊነትን የደፈረ፣ ሕዝብን ያስጨፈጨፈ ቡድንን ማውገዝ ሲገባቸው ተጎጂ አድርገው በመመልከት በሰብአዊ ድጋፍ ስም እያደረጉለት የሚገኘው ድጋፍ ኢሰብአዊነታቸውን ቁልጭ አርጎ ያመለክታል።በሰብአዊ መብት ጥሰት ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ላይ መቅረብ ያለበትን ቡድን ወደ መንግስትነት ሊመልሱት ከሚሰሩ ቡድኖች ጋር እየሰሩ ናቸው።
እነዚህ ተቋማት ላበቃለት ቡድን ድጋፍ በመስጠት ቀና እንዲል አድርገዋል፤ ራሱ በጫረው እሳት ተቃጥሎ እርስ በርሱ መገናኘት አቅቶት የነበረ ቡድን በዘመናዊ የመገናኛ መሳሪያ እንዲገናኝ እና እንዳሻው እንዲፈነጭ አድርገዋል።በአንጻሩ የኢትዮጵያውያን ስቃይ እንዲጨምር ፣ የአገሪቱ እድገት እንዲገታ፣ ገጽታዋ እንዲበላሽ ሰርተዋል።በአገሪቱ ሉዓላዊ ጉዳይም ጣልቃ ገብተዋል፡፡
ከወር በፊት ተመድ ሰብአዊ ተግባር አከናዋኝ ያላቸው ተቋማቱ ሃላፊዎች በህገወጥ ተግባር ሲሳተፉ ተገኝተው የተሰጣቸውን ማስጠንቀቂያ ችላ በማለት ለሰሩት ስህተት ማረሚያ ይሆን ዘንድ የተወሰኑ ኃላፊዎችን የኢትዮጵያ መንግስት ከአገር እንዲወጡ ማድረጉ ይታወቃል። ድርጅቱ ሁኔታውን ረጋ ብሎ መመርመር ሲገባው ዋና ጸሀፊው በተወሰደው እርምጃ መደንገጣቸውን ገለጹ። ሕዝብ ሲጨፈጨፍ አይደነግጡም፤ ሃላፊዎች ሲባረሩ ደነገጡ። ይህ የድርጅቱ ልክ፡፡
ለትግራይ ሕዝብ እርዳታ ጭነው የሄዱ ከባድ መኪኖች በሽብርተኛው ቡድን ተጠልፈው ታጣቂ እንዲያመላልሱ ሲደረግ ዋና ጸሀፊው አልደነገጡም፤ ለምን ብለው አጥብቀው አልጠየቁም። የመኪኖቹ በሚጠበቀው ልክ አለመስራት በትግራይ ረሃብ እንዲከሰት ሊያደርግ ይችላልና ጉዳዩ ያሳስበናል ሲሉም አልተደመጡም።
ድርጅቶቹ ከተመሰረቱበት ዓላማ ውጪ በመንቀሳቀስ በአገራችን ሰላም እንዲመጣ ሳይሆን የእርስ በርስ ትርምስ እንዲስፋፋ ከዚያም ያሰማራቸው ወገን ስውር ዓላማ እንዲሳካ ሰርተዋል። እነዚህ ተቋማት ሽብርተኛውን ቡድን በሚደግፉ ምዕራባውያን መንግሥታት የሚዘወሩ ናቸው። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት የሚፃረርና አገሪቱን ወደ ባሰ ብጥብጥ ውስጥ የሚከት ተግባር ነው፡፡
ሰብዓዊ እርዳታ ያለ አድልኦ ለሁሉም ወገን እናቀርባለን የሚሉት እነዚህ ድርጅቶች ከትግራይ ውጪ ያለውን በሕወሓት ወረራ ሳቢያ የተፈናቀሉ ወገኖች ስቃይና ሮሮ የማይሰሙ፣ ቢሰሙም ተገቢውን ምላሽ የማይሰጡ መሆናቸውን ተመልክተናል። ምክንያቱም መርጠው የሚሰሙ ናቸው፤ የሚሰሙት የሕወሓትን ድምጽ ብቻ ነው። ሰብዓዊ እርዳታን ለሰው ልጆች በፍትሃዊነት ከማቅረብ ይልቅ በዚያ ሽፋን የማይፈልጉትን መንጠቅና ለሚፈልጉት ማጉረስ መሆኑንአመላክተዋል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መተዳደሪያ ቻርተር የአገራትን ሉዓላዊነት ባከበረ መልኩ ዓለምአቀፍ ችግሮች የሚፈቱበትና ከግጭት ነፃ የሆነ የሰው ልጆች መብትና ነፃነት የተከበረበት ዓለም መፍጠር የድርጅቱ ዋንኛ ስራና ተግባር ቢሆንም፣ ከዚሁ ድርጅት የተቀዱት በሰብአዊ ተግባር ተሳትፈናል የሚሉ ተቋማትና ኃላፊዎች ግን ከዚህ መርህ እጅጉን ረቀዋል። ይህ ማንነታቸውም እንደጠቅስነው ኢትዮጵያ ውስጥ ባደረጉትና እያደረጉ ባሉት ተግባር ቁልጭ ብሎ ታይቷል፡፡
ይህ ሁሉ ለምን ሆነ ነው? ጥያቄው።ድርጅቱም ሆነ በስሩ ያሉት ተቋማት የተመድን ዓላማ ሳይሆን እያስፈጸሙ ያሉት ለተመድ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረጉ ያሉትን ምእራባውያን መንግስታትን ዓላማ ነው። የቆሙለትን ዓላማ ከማስፈጸም ይልቅ የሚንቀሳቀሱበትን ሀብት ለሚደጉማቸው መንግስት ወይም ቡድን ወግነው እየሰሩ ናቸው። ጨዋታው ይሄ ነው። ውሻ በበላበት ይጮሃል እንደሚባለው። ድርጅቱም በስሩ የሚገኙ ተቋማትም ከዚህ አይነቱ ጨዋታ ሊወጡ ይገባል፡፡
ከምስረታው ጀምሮ በእነዚህ ምእራባውያን ተጽዕኖ ውስጥ የሚገኘው ድርጅቱ በተቋማቱ አማካኝነት እየተገበራቸው ባሉ ስራዎች የዓለም ህዝብ ድርጅቱን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መልኩ እምነት እያጣበት ነው።የድርጅቱ አባል ሀገሮችም /በተለይ ከምእራባውያኑ ውጪ ያሉት/ የድርጅቱን አካሄድ እየተቃወሙ ናቸው። ድርጅቱ የምእራባውያኑን ፍላጎት መሰረት ያደረገ እርምጃ መውሰድ እንደሌለበት እያስገነዘቡ ናቸው።ይህ እርምጃ ድርጅቱ ወደ መስመሩ እንዲመለስ የራሱን ሚና ይጫወታል።
በዚህ ተቋም ላይ ያለው ዓለምአቀፋዊ ቅቡልነት ጭራሽ ደብዛው ከመጥፋቱ በፊት ተቋሙም ራሱን ሊመረምር ግድ ይለዋል። ለዓለም ፍትህ መከበር ፣ በዚህች ምድር ላይ እውነት እንዲነግስ የሚሰራ በዓለም ህዝብ እውናዊ ተቀባይነትን ያገኘና ከበለጸጉት አገራት ፍላጎት ነፃ የሆነ ዓለምአቀፋዊ ተቋም ለዓለም ህዝብ ያስፈልጋል።ያ ሲሆን በሰብአዊ ተግባር ሽፋን የሚፈጸም ኢሰብአዊ ንግድ ያበቃል። አበቃሁ፤ ቸር ያሰማን።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 17/2014