በምናባቸውን ወደ አንድ ምንም ወደሌለበት ባዶ ቦታ እንሂድ። አካባቢው ላይ የሚታይ ምንም ዓይነት ነገር የለም። ቤት የለም፤ ተሽከርካሪ የለም፤ ሱቅ የለም፣ ሞባይል የለም፣ ቲቪ የለም፣ … ምንም የለም፤ ምድርና ሰማይ ብቻ። ከእንቅልፋችን ስንነቃ እዚህ ባዶ ቦታ ላይ ራሳችንን ብናገኝ ምን ይሰማናል? ምንስ እናደርጋለን? ለቤተሰባችን ደውለን ያለንበትን ሁኔታ እንዳንናገር ስልክ የለም። ፎቶ አንስተን እንዳንለጥፍ ካሜራ የለም፤ እንዲሁም ኢንተርኔት የለም።
ይህ ሁሉ በሚሆንበት ጊዜ በቦታው ጋር ከመገኘታችን የተነሳ አንድ እኛ ጋር ያለ ነገር አለ፤ እርሱም ከራሳችን ጋር ማውራታችን። በምናየው ነገር መገረም፤ ወይንም መፍራት፤ ወይንም አንዳች ነገር ለማድረግ ማሰብ ወዘተ። በውስጣችን የሚመላለስ ብዙ ነገር እርሱ እኛ ጋር አለ። ይህ ቦታ … ነው።
ካለንበት የትኛውም አካባቢ የተወሰነ እርቀት ስንሄድ የምናገኛቸው ሁለት ተቋማት አሉ። የትምህርት ተቋማት እና የእምነት ተቋማት። በሁለቱም ተቋማት ውስጥ ዜጎች ይቀረጻሉ በሕይወት ዘመናቸው ውጤታማ ሆነው ለመኖር የሚያስፈልጋቸውን ስንቅ ይሰንቃሉ። በእምነት ተቋማት በተለየ ሁኔታ ከዕድሜ ዘመንም ስለሚያልፈው ዘመንም። የሁለቱ ተቋማት ሚና በማህበረሰባዊ እድገት ውስጥ ነጥቦችን ለማንሳት የጽሑፉን ርዕስ “የተማሪ ቤት፤ የእምነት ቤት”ብለነዋል።
የትምህርት ሚኒስቴር ድረ-ገጽ የስታትስቴክስ ክፍል ውስጥ የተቀመጡት አኀዞች መካከል መረጃው በተጠናቀረበት ጊዜ (2011 ዓ.ምህረት) ከ 45 ሺ በላይ ትምህርት ቤቶች፣ ከ26 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች እንዲሁም ከ 688ሺ በላይ መምህራን በዘርፉ የተሰማሩ መሆኑን ይነግረናል።
የተማሪዎቹን ቁጥር ስናይ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ከበርካታ ሀገራት አጠቃላይ የህዝብ ብዛት አንጻር የሚበዛው ነው። ከአፍሪካ የካሜሮን ወይንም የኮትዲቫር ህዝብ ከእኛ ተማሪ ቁጥር አንጻር አንሰው የሚገኙ ናቸው። ትልቅ ኃይል፤ አቅም ያለው ሆኖ መቀረጽ የሚቻል ከሆነ ብንል አንሳሳትም።
በዚህ ጽሑፍ ወደ ተማሪቤትም ሆነ የእምነት ቤት ጎራ ብለን መልካም ተጽእኖን መፍጠር የግድ የሆኑ ተቋማት መሆናቸውን እናነሳለን። እንደመንደርደሪያ የዜና ቅኝት ውስጥ የተወሰኑ ነጥቦችን እናንሳ፡-
ከዜና ቅኝት
አንድ – አዲስ አበባ ከሰሞኑን ያልተለመደ ሊባል የሚችል የትራፊክ መጨናነቅ ገጥሟታል ጉዳዩም የሚዲያ ሽፋን ያገኘም ነበር። የትራፊክ አስተናባሪው የመንግሥት አካል የሰጠው ምክንያት የትምህርት ቤቶችን መከፈት ነው። ለጉዳዩ መፍትሔው ምንድን ነው ለሚለው ጋዜጠና ከተሰጠው መልስ መካከል በግል መኪናቸው ተማሪዎቻቸውን የሚያመላልሱ ወላጆች የተማሪ አውቶቡስ መጠቀም እንዲችሉ ማግባባት አንዱ መሆኑ ተጠቅሷል። የተሰጠው የመፍትሔ ሃሳብ ትክክለኛነትን እዚህ ጋር ከማንሳት እንቆጠብና በዜና ቅኝታችን አሻግረን የተማሪዎቻችን ብዛት ለሀገር ጫና ወይንስ ሀብት የሚለውን ጥያቄ አየት አድርገን እንለፈው። ወጪ የሚወጣባቸው ተማሪዎች ለሀገር የሚሰጡት እንዲኖራቸው ታስቦ መሆኑ በራሱ ችግር ባይሆንም ውጤቱ በሚለካበት ጊዜ በቦታው ላይ ተማሪዎቹ በመፍትሔ ሰጪነት አቅም ካልተገኙ ኪሳራው የተማሪዎቹም ሆነ የወላጆች ብቻ አድርጎ ማሰቡ ስህተት ላይ የሚጥለን ይሆናል።
ሁለት – በወቅታዊ ጦርነቱ የተነሳ በትግራይ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች እና ወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ሲማሩ የነበሩ መደበኛ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች በጊዜያዊነት እንደሚመደቡ እንደሚያደርግ ትምህርት ሚኒስቴር ያስታወቀውም ከሰሞኑን ነው። ሀገር እንዲህ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስትገባ የእንግልቱ ቀጥተኛ ተካፋይ የሚሆኑት እኒሁ ተማሪዎች ናቸው። ከተማሪዎቹ ጀርባ ቤተሰብ በአጠቃላይ ደግሞ ሀገር። ይህ ዜና የትምህርት ሚኒስቴር የፊት ገጽ ላይ ከሚገኙት ወቅታዊ ዜናዎች መካከል አንዱ መሆኑ ጉዳዩ የተሰጠውን ትኩረት የሚያሳይም ይሆናል። የሚዲያ ቅኝታችን ተማሪዎች በሰንደቅዓላማ ማውጣት ስነስርዓት ላይ የሚዘምሩት ክልላዊ መዝሙር ላይ ያደርሰናል።
ሦስት – “ከደቡብ ክልል ውጪ ሌሎች ክልሎች ተማሪዎቻቸውን የሚያዘምሩት ክልላዊ መዝሙር ይዘት ይህን ይመስላል፤ ባለሙያዎችም የሰጡን አስተያየት እንዲህ ነው”ብሎ ዘገባውን ያቀረበው ደግሞ ሸገር 102.1 ነው። የሸገር ዘገባን ሲሰሙ በዘገባው ላይ ተተርጉመው የቀረቡት ግጥሞች የያዙት መልዕክት ድንጋጤ የፈጠረባቸው ሰዎች መኖራቸውን ማስተዋል ችለናል።
ክልሎች በተማሪዎች የሰልፍ ስንስርዓት ላይ የሚያዘምሩት መዝሙር ይዘት ሊታሰብበት እንደሚገባም አስተያየት ተሰጥቷል። ምክንያቱም በተማሪ ቤት በኩል ተደርጎ የሚዘራው ዘር የሚዘራው በሚሊዮኖች ላይ ነውና ጥንቃቄ ስለሚያሻው። ኢትዮጵያ ዛሬ ላይ ያላቸው ትላንት የተዘራው ዘር ውጤት መሆኑን መዘንጋትም እንደማይገባ በማስታወስ። በትምህርት ቤት የተዘራው ዘር ይህ ከሆነ እንዴት ይህ ዓይነት ጦርነት ሊቀር ይችል ነበር? ተብሎ ቢጠየቅ ስህተት ላይ የሚጥል አይሆንም። ችግር ፈቺነት ሳይሆን ችግርን ማብዛት የሚዘራበት አዕምሮ እንዴት የትራፊክ ፍሰትን ሊቀርፍ የሚችል መፍትሔ ላይ ይደርሳል ችግሩ ሲመጣ ጊዜያዊ መፍትሔ ላይ ይጠመዳል እንጂ ብለን ጉዳዩን አያይዘን ብናየውም አይከፋም።
አዲሱ የትምህርት ስርዓት በሙከራ ደረጃ በ 2014 እንዲሁም በ 2015 ዓ/ም ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ የሚገባ መሆኑን የሚነግረን ዜና ስንሰማ ደግሞ ነገን ተስፋ በማድረግ ትንፋሽ እንውሰድ። ተስፋ የምናደርገው መልካሙ ለውጥ ውጤት ይዞ ይገኝ ዘንድ በተማሪ ቤት እና እምነት ቤት መንደር ቀጥሎ ያሉትን ደቂቃዎች እንጠቀም።
ተማሪ ቤት – ከራሳችን ጋር የሆንበት ስፍራ
ቦርገን የተሰኘ ፕሮጀክት “ትምህርት በማህበረሰብ ላይ ያለውን ተጽእኖ” ለማሳየት ባወጣው ጽሑፍ ውስጥ ካነሳቸው ነጥቦች መካከል ትምህርት ዴሞክራሲያዊ ማህበረሰብን ለመፍጠር ያለውን ሚና በቀዳሚነት ያነሳል። ፍራንክሊን ዲ. ሮዝቬልት በበኩላቸው “ምርጫቸውን በጥበብ መምረጥ የሚችሉ ሰዎች በሌሉበት ቦታ ዴሞክራሲ ስኬታማ መሆን አይችልም፤ ሰዎች እንዲህ ሆነው የሚቀረጹት ደግሞ በትምህርት ነው። ስለሆነም ትምህርት የዴሞክራሲ መሰረት ነው” ማለታቸውን ይጠቅሳል።
ዓለም በአሸባሪዎች ስጋት ውስጥ ባለችበት በዚህ ወቅት የተማሪዎች አዕምሮ በአሸባሪዎች ሃሳብ እንዳይሞላ ማድረግ መቻል ቀጣናዊ ፖለቲካን ሰላማዊ ለማድረግ አስፈላጊ መሆኑን እንዲሁ ጽሑፉ ያነሳል። ከእዚህ ነጥብ አንጻር ኢትዮጵያ እንዲሁም መላው የአፍሪካ ቀንድ ፖለቲካ ወደ መረጋጋት መሄድ እንዲችል የተማሪ ቤቱ ሚና በቀላሉ የሚታይ አለመሆኑን እንረዳለን።
ኢኮኖሚን ለመገንባት፣ መሪዎችን ለመቅረጽ፣ ችግሮችን መፍታት የሚችል ማህበረሰብ ሆኖ ለመገኘት፣ ከሌሎች ጋር በሰላም መኖር መቻልን እሴት ለማድረግ ወዘተ ከትምህርት ውጪ ምን መሳሪያ አለ? ብሎ ለሚጠይቀን ምላሻችን “ምንም” ነው። ኔልሰን ማንዴላ “ትምህርት ዓለምን ለመቀየር ኃያሉ መሳሪያ ነው። ” ማለታቸውን ስናነሳ መሳሪያዎች ሁሉ የሚመረቱበት መሳሪያ ትምህርት መሆኑን በቀላሉ መረዳት ያስችለናል። በሌላ አገላለጽ ወደ ነገ የሚያደርሰን ፓስፖርት።
ከመደበኛ ትምህርትቤት ወጣ ብለን የተማሪነት ልብን የያዙ ሁሉ ትምህርት ስለሚያገኙበት የትምህርት ህይወት እናንሳ። ትምህርት ቤት የሚለውን ቃል ከመጠቀም ይልቅ ተማሪ ቤት ማለት የሚቀናቸው ሰዎች አሉ። እኒህ ሰዎች በአብዛኛው በዕድሜ የገፉ ሰዎች ናቸው። በእነርሱ ጊዜ ተማሪ ቤት ይባል እንደነበር ማሰብም ይቻላል። “ተማሪ – ቤት” የተማሪው መገኛ ቤት መሆኑን ሲገልጽ፤ “ትምህርት – ቤት” የሚለው ደግሞ ትኩረቱን ከተማሪው ወደ ትምህርቱ ማድረጉን ያስረዳናል። የተሻለው የተማሪ መገኛ ቦታን በማመልከት ተማሪ-ቤት ማለት ወይንስ ትምህርት – ቤት? የሚለውን ጥያቄ ለአንባቢው እንተውና ለእዚህ ጽሑፍ ሲባል እንደአስፈላጊነቱ ሁለቱንም እየተጠቀምን እንዝለቅ።
በምናባቸው ወደ ሄድንበት ምንም ነገር ወደሌለበት ስፍራ በድጋሚ እንሂድ። በአካባቢው ላይ የሚታይ ምንም ዓይነት ቤት የሌበት ቦታ። ምንም ዓይነት ተሽከርካሪ፤ ሱቅ፣ ሞባይል፣ ቲቪወዘተ የሌለበት ምድርና ሰማይ ብቻ የሚታይበት ቦታ። ከእንቅልፋችን ስንነቃ እዚህ ባዶ ቦታ ላይ ራሳችንን ብናገኝ ምን ይሰማናል? ምንስ እናደርጋለን? የሚለውን ጥያቄ ጠይቀን ነበር። ምናልባት ወደፊት ዝምብለን በእግራችን መሄድን እንመርጥ ይሆናል። ይህን የምናደርገው ግን አስበን መሆኑ ግልጽ ነው። ከራሳችን ጋር አውርተን። ከራሳችን ወደ ራሳችን ዘርን ዘርተን። ይህ ቦታ ትምህርት ቤት ነው። ከየትኛውም ቦታ ትምህርት የሚቀረፍበት አስተሳሰብ ማሳያ። ምንም የለም ከሚባለው ቦታ ሳይቀር ትምህርት ሊወሰድ እንደሚችል የሚያስረዳ። ምንም ባይኖር በዓይናችን ከምናየው የምንማረው ያለበት። በእጃችን ዳስሰን የምንማረው የማናጣበት። አሽትተን የምንማረው ሊጠፋ የማይችልበት ወዘተ እርሱ ቦታ የትኛውም ቦታ ነው፤ ትምህርት ቤት። የሰው ልጅ በተገኘበት ቦታ ሁሉ ትምህርት አለ፤ ሁሉም ቦታ ትምህርትቤት ነው፤ ትምህርትን ለሚፈልግ ልባም መሆን ያስፈልጋል።
የሰው ልጅ ወደ ራሱ ሲመለከት፤ ወደ ቀልቡ ወይንም ትኩረቱ ሲመለስ ትምህርት ቤት ውስጥ ራሱን ያገኛል። ወደ ራስ በመመልከት ውስጥ በትምህርትቤት ህይወት ውስጥ መኖር እንችላለን። ሁሌም መማር ሁሌም ማደግ። “ገንዘብ በሃያ ልብ በአርባ” የሚባለው አባባል ይህ ዓይነቱ ማንነት በቀላሉ የሚገኝ አለመሆኑን ምራቅ መዋጥን የሚጠይቅ መሆኑን ያሳየናል።
ትምህርት የማያገኝበት ምንም ስፍራ የለም። በሁሉም ስፍራ ትምህርት አለ። ለግል ሕይወታችን ሊተገበር የሚችል ትምህርት። ባለንበት ቤተሰብም ሆነ በሥራ ህይወት እንዲሁም በማህበረሰባችን ውስጥ ልናመጣው የሚገባውን ተጽእኖን ማሳደር የሚያስችል ትምህርት። ሁሉም ስፍራ ትምህርት አለ፤ ሁሉም ስፍራ ትምህርት ቤት ነው። የምንማረው ትምህርት ጤናማነት ላይ መነጋገርን ይጋብዝ ይሆናል እንጂ ትምህርትቤት ያልሆነ ስፍራ የለም።
በምድራችን ሆነ በዓለማችን ያለው ምስቅልቅል ውስጥ ያለውን ትምህርት መርምሮ ገንዘቡ ማድረግ የሚችል ሰው እርሱ ጠቢብ ይባላል። ከፍርስራሽ ውስጥ ሌላ ፍርስራሽ ከማምረት ትምህርትን መውሰድ መቻል ስንቱ ይታደለዋል?
የተማሪነት ልብ የበዛለት ዜጋ እንዲሁም ለትምህርት ዋጋን የሰጡ ሚሊዮን ተማሪዎች የሚኖሩባት ሀገርን ህልም ማድረግ አለብን። የመደበኛ የትምህርት ስርዓቱ ውስጥ የሚያልፈው ተማሪ ብዛት እጅግ ብዙ ሆኖ ይሰማናል። በብዙ ቁጥር የተገለጸው ተማሪ ግን መዳረሻው መፍትሔ አፍላቂነት ሳይሆን ሲቀር ጥያቄ የሚያጭር ነው። እንደ ሀገር ተማሪነትን ባህል ማድረግ መቻል እንዳለብን ያለንበት ወቅት በሚገባ የሚያስረዳ ነው። አይደለም መደበኛ ትምህርት የሚሰምባቸው ቦታዎች ይቅሩና ሌሎች ቦታዎችም የትምህርት ማዕከላት መልካም ተጽእኖን መፍጠሪያ ስፍራዎች ማድረግ ይኖርብናል። የበዛ ሂደት ነገርግን ተጨባጭ ለውጥ የማይመጣበት ከሆነ ልፋታችን ሁሉ መና መሆኑ ነውና ስለመፍትሔው መጨነቅ የሁላችንም ኃላፊነት ብናደርገውስ? ብለን በመጠየቅ ስለ ሁለተኛው ቤት እናንሳ፤ የእምነት-ቤት።
የእምነት – ቤት
በምናባችን ያየነው ስፍራ ሌላው ስሙ የእምነት-ቤት ነው። ምንም የሌለበትን ስፍራ ወደ ምንፈልገው መቀየር እንድንችል የሚያስፈልገንን ሁሉን አቀፍ አቅም የምናገኝበት።
ሃይማኖቶች እንደ ስርዓታቸው በአካልም ሆነ በሚዲያ አማካኝነት ሃይማኖታቸውን በስፋት የሚያስተምሩበትን ሁኔታ እናስተውላለን። ከማስተማር እስከ ተዓምራት አገልግሎት። ካላንደር በሚዘጋው ቀንም ትኩረት የሚሰጣቸውን የሃይማኖቱን ቀናት በሰፊው የሚዲያ ሽፋን ተሰጥቷቸው ይታያል። የሃይማኖት መሪዎቹም ባገኙት አጋጣሚ የእምነቱ ተከታዮች ሊኖሩት የሚገባን ሕይወት ያስተምራሉ፤ በመግለጫዎቻቸውም ወቅታዊ መልዕክትን ያስተላልፋሉ። ለምን ያህል ሰው አሁንም በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ፤ ምናልባት ከተማሪዎች ቁጥር ለላቀው ህዝብ ወይንም የእምነቱ ተከታይ።
ካለንበት የተወሰነ እርቀት የእምነት ተቋም የመኖር ዕድሉ ከፍተኛ መሆኑን ፀሐፊው ይገነዘባል። አምልኮ ለማከናወኛ የሚደረገውም ግንባታም ሆነ ሌሎች እንቅስቃሴዎች በኢኮኖሚ ውስጥ የሚኖራቸው ሚና በቀላሉ የሚታይ አለመሆኑን ማሰቡ ተገቢነት ይኖረዋል። የእምነት – ቤት ያለውን ሚና በማህበራዊ እሴት ግንባታ ላይ ለሌላ የሚተው አለመሆኑ ጎልቶ የሚወጣው ነጥብ ነው።
የእምነት ተቋማት የማህበረሰብን እሴት ከመገንባት አንጻር ያላቸው ሚና አንድ ሁለት የሚባል አይደለም ካልን የእኛን ነባራዊ ሁኔታ እየፈተሽን ንባባችንን እንቀጥል። ቤተ እምነቶች እንደ እምነታቸው አስተምሮ ተከታዮቻቸውን ለመቅረጽ ጥረት የሚያደርጉ መሆናቸው ትርፉ ለቤተእምነቶቹ ብቻ ሳይሆን ለእያንዳንዱ ዜጋ እንዲሁም በድምሩ ለሀገር ነውና አሁንም ግምገማችንን ለራሳችን እናድርግ። እኛ ኢትዮጵያውያን በአብዛኛው ራሳችንን በሆነ እምነት/ሃይማኖት የመግለጽ አቋም ላይም እንገኛለን፤ ይህንንም ገምግመን እንለፈው።
የእምነት ተቋማቱ ቁልፍ በሚባለው የግለሰባዊ ህይወታችን ውስጥም ሚናቸውን ተቀብለን እናስተናግዳለን። በአብዛኛው በውልደት፣ በጋብቻ እንዲሁም በሞት ወቅት ሚናቸው ይጎላል። ለነፍስ ከሚሆነው ነገር አልፎ ደግሞ በልማት ሥራ ውስጥ ያላቸው ሚናም በቀላሉ የሚታይ አይደለም። የእምነቱ ተከታዮች በግል ህይወታቸው፣ በቤተሰባዊ ህይወታቸው፣ በሥራ ህይወታቸው እንዲሁም በማህበራዊ መስተጋብሮቻው ሊኖሩት የሚገቡት እሴቶች በእምነት ተቋማት መድረክ ላይ የሚጠፋ አይደለም።
አንባቢው ራሱን ቢፈልግ ያለፉት 24 ሰዓታት በጣም ከራቀ ባለፉት 7 ቀናት ምናልባትም በጣም ከራቀ ያለፉቱ 30 ቀናት ውስጥ የእምነት ተቋማትን አገልግሎት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋዘሪ መንገድ የመቀበል ዕደሉ ከፍ ያለ እንደሆነ ፀሐፊው ያስባል። ይህ የሚነግረን የእምነት ተቋማት በሕይወታችን ላይ ያላቸው ድርሻ ቀላል አለመሆኑን ነው። መንግሥት ባለው ዝቅተኛ የታችኛው መዋቅር ቀበሌ/ወረዳ ዜጎችን በሳምንት አንድ ጊዜ ማግኘት የሚችልበት ዕድሉ ጠባብ ነው። ነገርግን የእምነት ተቋማት በአንጻራዊነት ከመንግሥት በተሻለ ሁኔታ ዕድሉ አላቸው። ይህን በምናይበት ጊዜ ተማሪ-ቤት እና የእምነት-ቤት ያላቸው ተጽእኖ የመፍጠር ዕድል በጉልህ የሚታየን ይሆናል።
ፓትሪክ ፋጋን የተሰኙ ግለሰብ “የእምነት ተጽእኖ በማህበረሰባዊ ህይወት ላይ ያለውን ድርሻ” የሚያሳይ ጽሑፍ www.heritage.orgላይ አሳትመዋል። ጽሑፋቸው የእምነት እሴቶች ቦታ በተሰጠባቸው ጊዜዎች የታየ ምርታማነት በአጠቃላይ ውጤታማነት ትምህርት ሊሆን እንደሚገባ ይገልጻል።
ግለሰቡ ባደረጉት ጥናት ከሃይማኖታዊ ልማዳች መካከል ጸሎትን ነጥሎ በማውጣት ጥናት አድርገዋል። በጥናቱ ውስጥ ከተሳተፉት 94% ጥቁሮች፣ 91% ሴቶች፣ 87% ነጮች ለጸሎት ቦታ የሚሰጡ ሆነውም መገኘታቸውን ይገልጻሉ። በጸሎት እንደሚያምኑና በሥራቸው ውጤታማነት ላይ ጸሎት አዎንታዊ ተጽእኖ እንዳለው እመነታቸው መሆኑን ምላሽ የሰጡ ናቸው። 87% የሚሆኑት በመደበኛነት መጸለይን የሚደግፉና ለማድረግ ከፍተኛውን ጥረት የሚያደርጉ ሆነው ራሳቸውን ገልጸዋል። ይህን ሃይማኖት እከተላለሁ ብለው ራሳቸውን መግለጽ ያልቻሉ ሰዎች ማለትም ሃይማኖት የሌለው ሰው አድርገው ራሳቸውን ከገለጹት መካከል 20% የሚሆኑት በየዕለቱ የሚጸልዩ ሆነው ተገኝተዋል።
በእዚህና በሌሎችም በጉዳዩ ላይ ከተደረጉ ጥናቶች መረዳት የሚቻለው መደበኛ የሆነ የእምነት ተግባራት ለግለሰብም ሆነ ለማህበረሰብ ያለው ጥቅም ከፍተኛ መሆኑን ነው። ከባድ ለሚባሉ ማህበራዊ ችግሮች መውጫ መንገድ ተደርጎም የሚታሰብ በእምነት ተቋማት አካባቢ የሚሠራው ሥራ ነው። በጸሎት፤ በመንፈሳዊ ትምህርት፤ የተማሩትን ለመተግበር የሚደረጉ ጥረቶች ወዘተ ማህበራዊ እሴትን የመቅረጽ ዕድልን ይሰጣሉ።
በሃገራችን ነባራዊ ሁኔታ መንግሥትና ሃይማኖት ያላቸው መለያየት ህዝብን ለማስተዳደር አስፈላጊ ቢሆንም ይህ ማለት ግን በደፈናው የእምነት ተቋማትን ማሳደድና ዋጋ የሌላቸው እንደሆኑ አድርጎ ማሰብ እንዳይደለ ግንዛቤው ያስፈልጋል። ኢትዮጵያም የዚህ ዓይነቱ ግንዛቤ በኪሳራ ውስጥ እንድታልፍ እንዳደረጋት ያለፉት ዓመታትን በሚገባ መቃኘት አስፈላጊ ይሆናል።
የተማሪ-ቤትን ወቅታዊ ዜናዎችን መነሻ በማድረግ ካነሳናቸው የሚዲያ ቅኝት ነጥቦችን ወደ ገንዘብ ብንቀይር ሀገሪቱ በመደበኛ ትምህርት ላይ የምትመድበው በጀት እንዲሁም የሰውኃይል ፍላጎት ከፍተኛነትን እንረዳለን። በተመሳሳይ ሁኔታ የእምነት ተቋማትም በግንባታም ሆነ በሌሎች ወጪዎች የሚበጅቱት በጀትና የሚያውጡት ከፍተኛ ወጪ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ ያለው ድርሻ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ከእያንዳንዱ ግለሰብ በተወሰነ እርቀት ላይ የሚገኙት እኒህን ተቋማት ውጤታማ ማድረግ የሚያስችል የፖሊሲ አቅጣጫን መከተል ለኢትዮጵያ ይበጃል።
የጀመርነውን ሃሳብ ወደ መዝጊያው ለመምጣት መልካም ተጽእኖን የመፍጠር አቅምን እንደ ሀገር የመገንባት አስፈላጊነትን እናንሳ። ጠንካራ ኢኮኖሚ ያላቸው፣ በጦር አቅማቸው ከፊትለፊት የተሰለፉት ሀገራት የጋራ የሚያደርጋቸው ሁለት ነጥብ እውነተኛ እውቀትን የሚያሲይዝ ጠንካራ የትምህርት ስርዓት ያላቸው መሆኑና እሴት-ተኮር ህይወትን ዜጎቻቸው እንዲኖራቸው ማድረጋቸው ነው። ከጃፓኖች ጥንካሬ ጀርባ የፈጠሩት የትምህርት አቅምና እሴትን ማዕከል ያደረጉ ልጆች አስተዳደጋቸውን ልናነሳ እንችላለን። የዓለማችን ጥራት ያላቸው ትምህርትቤቶች የምትገኙባት አሜሪካም መሰረቷን በጥንቃቄ እንድትመሰረት የረዳት ተማሪቤቶች እውነተኛ የትምህርት ቤቶች በመሆናቸው እንደሆነ ልዩ ልዩ ጥናቶች ያሳያሉ።
ኢትዮጵያ ዛሬ በብዙ አጣብቂኝ ውስጥ ብትገኝም፤ ከእዚህ አጣብቂኝ እንደምትወጣ ተስፋ የሚያደርጉ ልቦች የነገዋን ኢትዮጵያ ብሩህ ከማድረግ አንጻር ሥራቸውን መፈለግ አለባቸው። ቀዳሚውና ዋናው ትኩረት የሚሻው ሥራ ለመፍትሔ የሚሆን እውቀትን የያዙ ዜጎችን ቁጥር መቁጠር መጀመር ነው። ዲግሪ ወይንም ማስተርስ ያለውን ከመቁጠር መፍትሔ መስጠት የሚችል አቅም ላይ የደረሱ ዜጎችን ወደ መቁጠር ማደግ አለብን። እዚያ ላይ ደግሞ መልካም ስብእና እንዲጨመርበት የእምነት ተቋማት ስፍራቸውን ይያዙ።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 13/2014