አሸባሪው፣ ብሄረተኛው፣ ጠባቡ፣ እኩዩ የሚሉት ሁሉ ይገልጹታል፤ ህወሃትን:: አሸባሪነት ደግሞ በአዋጅ የተሰጠው ሥያሜ ነው:: የዚህ አሸባሪ ቡድን ፍልስፍና አብዛኛውን ሰው (ፊደል ቆጠረ የሚባለውን ጨምሮ/ መሠረት አልባ አድርጓል:: በአሸባሪነት መንፈሱ ተበክለው በራሳቸው ሣይተማመኑ ማንነታቸውን የከዱ በአጎብዳጅነት ለመኖር የተገደዱ ሰዎች ዛሬም ከመካከላችን፣ ከአጠገባችን አሉ:: አነዚህ ሰዎች አጠገባችን ሆነው የሚሉትን ሁሉ እየሰማን ነው፤ በቅርቡ ደግሞ ያደረጉትን አየን:: ከዚህ በላይ ምን አሳዛኝ ነገር አለ?
ህግ የማስከበር ዘመቻው በተካሄደበት ወቅት በየጉሬው ተለጥፈው ከቆዩ በኋላ መከላከያ ከመቀሌ ወጣ ሲባል በአዲስ አበባ ከተማ ሣይቀር ለጭፈራውና ለሆታው ተጎልጉለው ወጡ:: ኢትዮጵያ ውስጥ ተቀምጦ ኢትዮጵያን መጥላት ይቻል ይሆናል:: ጥላቻን በአደባባይ በእንዲህ መልኩ መግለጽ ግን ያስተዛዝባል::
ለመሆኑ ህብረተሰባዊ ምሶሷችን የት ጠፋ? ታጥቆ አገርን እያናጋ ጦርነት በይፋ የከፈተ፣ ዜጎችን ለከንቱ ዓላማ እያሳለፈ የተጠቀመ፣ ህጻናትን እናቶችን ሣይቀር በእሣት የማገደ አሸባሪ ቡድን ያልጨበጠውን ድል ጨብጥኩ ስላለ በውዳሴ ከንቱ መዝለል ምን የሚሉት ቂልነት ይሆን::
የአሁኑ ይባስ ነው ያሉት የቀደሙት:: እነዚህ ዛሬ ጮቤ ሊረግጡ የወጡ ሰዎች ፊትም ቢሆን ለእኛው ለራሣችን እነማንን እንደሚመስሉ ይነግሩን ነበር:: ለለውጡ መሪዎች ያላቸውን ጥላቻም በቀጥታ ይገልጹም ነበር:: ይህ የሆነው በእነሱ ዘመን ቢሆን ኖሮ ታየኝ::
እንዳሻቸው ሆነውም በሀገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ላይ ሊሳለቁ ይሞክራሉ:: ችለናቸው እንጂ እኮ ትንኮሳቸው ከጾታ ትንኮሶ ይብሳል:: ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት ስንል ይህን ያን አሉ ብለን ምንም አላደረግናቸውም፤ እነሱ አንካሣ ዶሮ ሳይቀድማቸው ሹክ ለማለት እንደሚፈጥኑትም ለማንም ምንም አላልንም፤ እውነቴን ነው የምላችሁ፤ ይኼው አሁን ነው የተናገርኩት::
አሁንም ወደ ሰዋዊ ልቡናቸው ይመለሱ ዘንድ ብዕር ከመምዘዝ ውጭ ሌላ አማራጭ የለንም:: ሌላውን ለማሳመን ለማጥቃት የተቀነባበረ ፕሮፖጋንዳ ሲያስተጋቡ አሜን ብሎ ከሚቀበል ሰው ጋር ነው እንግዲህ እየኖርን ያለነው::
ወዳጄ ውሸት በሕወሃት ተደጋግሞ ከተነገረ እኮ እውነት ነው የሚመስለው:: አሸባሪው ተራ የፈጠራ ወሬ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ እያካሄደ ባለበት በዚህ ወቅት ይህን የማያስተባብል ትውልድ ሳይ አንዳች ፍርሀት እየተሰማኝ ነው:: መከላከያን ገድሎ በሬሣው ላይ ሲጨፍር ከነበረ ቡድን ጋር መጨፈር አገርን በቁም ከመቅበር ይተናነሳል ወይ? በሕወሃት ሣቢያ እኮ የሐገራችን ሉዓላዊነት ተደፍሮ በሱዳን መሬታችን ተይዟል እኮ:: ይህ እንዲሆን ምክንያት ለሆነ ቡድን እንዴት ይጨፈራል፤ ለዚያውም እዚህ አዲስ አበባ ተሁኖ:: ይህም የእናትን ጡት እንደ መንከስ ነው ሊቆጠር የሚገባው::
በተለይ አዲስ አበባ የከተሙና በየመገናኛ ብዙኃን ሥር ተሰግስገው ያሉ የዚህ ቡድን ምስጢራዊ ደጋፊዎች “በሬ ወለደ” የሚል መፈክር እያሰሙ ሲጨፍሩብን ከረሙ:: ምስኪንነት፣ ድህነትና ረሃብ የሚያንገላታው ህዝብ በአሸባሪው ሥር ሲወድቅ ደስታ ከተሰማህ እንግዲያውስ አንተም ያው ነህ:: ምን አተረፍክ ታዲያ? ይኸው መከላከያ ከወጣ ወዲህ ጩኸት በረከተ:: ሕዝቡ ለዕለት ጉርሱ መጨነቁ ሣያንሰው በግፍ እየተገደለ ነው፤ እየተሰደደ ነው::
ጥቂት የአሸባሪው ቡድን ደጋፊ ነኝ የሚለውን ነው አሸባሪው ዋናው የሥልጣኑ ምሰሶ አድርጎ እየተጠቀመበት ያለው:: የእነዚህን ሰዎች ሥነ ልቦና በመመረዝና በመስለብ ላይ ተጠምዷል:: ጆሮ ዳባ ልበስ ያሉቱም እስከ ማምለክ ደርሰዋል፤ መብታቸው ነው:: ግን ቁልጭ ብሎ የሚታይን እውነት ወደ ጎን መተው አይቻልም:: መቼም ማንነቱን የካደና ለፍትህና ለርትዕ መቆም የተሳነው፣ ምክር ግድ የሚሰጠው ባይመስልም ነገን ማመላከት ግን ማገዶ ቢፈጅም ጥሩ አማራጭ ይመስለኛል::
የአሸባሪውን ሕወሀት የተቀነባበረ የሥነ ልቦና ፕሮፖጋንዳ እቅድ መንስኤና ያስከተለውን ውጤት እንኳንስ እኛ መጪው ትውልድም በታሪክ የማይረሳው ነው::
እናንተስ ወገኖቼ ስለምን ከእውነት ተጣላችሁ:: ድርጊታችሁ ሁሉ ሥር የሰደደ ጥላቻ ይመስላል:: እንደኔ እብሪቱ ለማንም አያዋጣም:: አየነው እኮ የ40 እና 50 ዓመት የግዛት እቅድ በጥቂት ሣምንታት ውስጥ ፉርሽ ሲሆን:: ከዚህ መማር አይጠቅመንም ትላላችሁ?
ከሁሉም ሥፍራ የተውጣጡ፤ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን የመከላከያና የደህንነት ሀይሎቻችን ለሃገር፣ ለወገን ብለው መስዋዕት እየከፈሉ የሚጠብቁንን ውጤታቸውን በዜሮ አባዝተው፤ የማይታረቅ ልዩነቶች ፈጥረው እርሱንም በማር ለውሰው ሊያጎርሱን የሚታትሩ ለቡድኑ ደጀን ለመሆን የሚውተረተሩ ሁሉ ሰዋዊ ባህሪ አላቸው ለማለት እኔ በበኩሌ አልደፍርም::
አይታችኋል፤ አንዳንንድ ሰዎች ለቅሶ ቤት ሊያስተዛዝኑ ሄደው ሰው ያስከፋሉ፤ ከሐዘንተኛው ቁማር በልተው ስቀው ተደስተው ጠጥተው ወደ ቤታቸው የሚመለሱበት ሁኔታ አለ:: በአሁኑ ወቅትም የሆነውን ሳስታውስ እንዲሁ ነው:: የኔ ማኛ የኔ እስትፋስ ካሉን በኋላ አንተ ገብስ አቋም፣ አንቺ አይጥ ጥርስ ብለው ከሚፈናገሉ ወገኖች ይሰውረን ማለት ይኼኔ ነው::
የአንዳንድ የአሸባሪው ደጋፊዎች ባህሪ ምን ያስታውሰኛል መሰላችሁ፤ “ጀንጅኜ” አሣምኛታለሁ ብለህ ታስብና በቃ ይቺንማ ለትዳር ነው ብለህ በሁሉ ነገር ስትንከባከባት ቆይተህ መሃል ላይ አንድ ቀን “ቆይ ከሁለታችን ማን ቀድሞ የሚያገባ ይመስልሃል?” የሚል የፍቅረኛሞች መጥፎ አጋጣሚን ያስታውሰኛል:: ምሣሌው ቀላል ነው:: እነዚህን ጭፍን የአሸባሪው ደጋፊዎች መንግሥት በቻለው ሁሉ ሲያግባባ፣ እንደ ታማኝ ዜጋ ሲያያቸው ቆይቶ “እሥራኤላዊያን ወደ ተስፋይቱ ምድር ሲሄዱ የግብጽ ሽንኩርት እንደናፈቃቸው ሁሉ” እነዚህም ድንገት ይነሱና የተነጠፈላቸውን ወርቅ እንደ ፋንድያ ይቆጥሩታል:: የግፉንም ዘመን ይናፍቃሉ::
በየፌስቡኩ አሸንፈናል ብለው መደስኮር ሣያንሳቸው፤ በየክለቡ ፌሽታ ማድረግ፣ ቲሸርታቸውን የተወጋ ቪንቶ ቀብተው “ጄኖሣይድ” ተፈፀመ ብለው ድራማ የሚሰሩ፣ ፕሮፖጋንዳ ያሰከራቸውን ስታይ ወደ ኋላ ሩቅ ዘመን ላይ ያለህ ይመስላል:: 100 ቢሊዮን ብርን የሚያህል ገንዘብ ተሰጥቶ ምንም እንዳላየ ዝም ማለትስ “ፌር” ነው?
ይኼን ስል ምን ትዝ አለኝ መሰላችሁ:: መቼስ አስቂኝ ሰዎች አይጠፉም:: እና መንግሥት በጦርነቱ ወቅት 100 ቢሊየን ብር ለሰብዓዊ ተግባር፣ ለመልሶ ግንባታ አወጣሁ ሲል፤ አንዱ ፌዘኛ “ቆይ አሸባሪው ብሩን እንደ አበል እየተጠቀመበት ነበር ማለት ነው?” አለ:: እውነት ነው አገሪቷ ብዙ የችግር ቀዳዳዎች እያሉባት ሕዝቤ እንዳይራብ ብሎ ያን ሁሉ ገንዘብ ሲሰጥ በጎን ለአሸባሪው የሚሸጉጡ እንደነበሩ ሰምተናል::
በዚህ ወቅት አንድ ነገር ይገርመኛል:: የክልሉ ሕዝብ ተርቧል እያሉ ሲጮሁ የነበሩት አሁን ጥጋብ ስላለ ነው እንዴ ዝም ያሉት? ሰው እንዲራብ ሣንካ የሆነው የአሸባሪው እብሪት መሆኑን እንኳን አልተረዱም:: ቢረዱም አይናገሩም:: አንዳንዱ ሲያድለው ከእንክርዳድ መሀል ስንዴ ሆኖ ይበቅላል:: እንዲህ ዓይነቶቹ ግን ከእንክርዳድ ውስጥ የተገኙ ሌላ እንክርዳድ ናቸው:: እኩይ እሳቤያቸው ወደር የለውምና::
የእነርሱ ሥራ ትግራይ ነጻ ወጥታለች ብሎ ተክለ ሀይማኖት፣ ቦሌና 22 ላይ መጨፈር ነው:: ለነገሩ እንኳን 22 ይቅርና በጠራራ ፀሐይ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኛ ሆነው ከሙያው ባፈነገጠ መልኩ የግል ፍላጎታቸውን እያንፀባረቁ ሲሸልሉም የተገኙ አሉ::
ግድ የለም አንድ ቀን ወደ ሰዋዊ ማንነት ትመለሱ ይሆናል:: አንዱ ወዳጄ እንዳለው፤ ቀንም ሆነ ማታ ድሮም ሆነ አሁን ቤታችሁ ቢዘረፍ አሊያም ቢቃጠል ቀድሞ የሚደርስላችሁ የአሸባሪው ልዩ ሀይል ሣይሆን አጠጋባችሁ ያለው ኢትዮጵያዊ ዜጋ ነው:: እንግዲህ ሀቁ ቢመራችሁም ዋጥ ማድረግ ነው::
በመጨረሻም መንግሥትም እነዚህ የአመለካከት ችግር ያለባቸውን ብዙ የታገሣቸው ይመስለኛል:: ያ ማነው ተሀድሶ ይሉት የነበረውን ማድረግም አይከፋም:: ሥሙንም ቀይሮ ቢሆን ማለቴ ነው:: አመለካከት ላይ መሰራት አለበት:: የጊዜ ጉዳይ ነው ይቀየራሉ:: ፈንገጥ ካለም ቆንጠጥ ማድረግ ይገባል፤ አንድ ፍሬ ህጻንስ ይቀጣ አይደል እንዴ!! ቸር እንሰንብት::
ታንቶስ ወልዴ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 4/2013