ወቅቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለዓመታት ያስተማሯቸውን ተማሪዎች የሚያስመርቁበት ነው። ምረቃውም ተጀምሯል። ምሩቃን ለእዚህ ታላቅ ወቅት እንኳን አበቃችሁ እላለሁ። በተለይ የዘንድሮው ምሩቃን በሰላምና በጸጥታ እንዲሁም በኮቪድ የተነሳ ትምህርታችሁ ሲጓተትባቸው የቆያችሁ እንደመሆናችሁ ይህ ሁሉ አልፎ ለመመረቅ በመብቃታችሁ በድጋሚ እንኳንም ተመረቃችሁ ማለት እፈልጋለሁ።
ሀገራችን ባለብዙ ዩኒቨርሲቲዎች ሆናለች። ከሁለት ዩኒቨርሲቲዎች ከአርባ ወደሚልቁ የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች መሸጋገር ተችሏል። በዚህ ላይ የግሉ ዘርፍ ዩኒቨርሰሲቲዎችና ኮሌጆች አሉ። ከፍተኛ የትምህርት ተቋማቱ እንደመብዛታቸው የሚቀበሏቸውና የሚያስመርቋቸው ተማሪዎችም ከዓመት ወደ ዓመት እየጨመረ ነው። የምሩቃኑ ቁጥር ከአንድ መቶ ሺ መዝለሉን ካለፉት ዓመታት ምረቃዎች መረዳት ይቻላል። ይህ አሀዝ በዚህ ዓመት ወደ ሁለት መቶ ሺ አይደርስም ተብሎ አይታሰብም።
ዩኒቨርሲቲዎቹ መከፈትና መስፋፋት ፣ የትምህርት ክፎሎቻቸውም እየጨመረ መምጣት ከሀገሪቱ ቀጣይ የሰው ሃይል ፍላጎት ጋር አብሮ የሚሄድ ነው ብሎ መናገር ይቻላል። እንደ ዱሮው ተመራቂዎቹን መንግስት ስራ ያስይዛቸዋል በሚል አይደለም ዩኒቨርሲቲዎቹ የሚያስተምሩት። ስራ ማስያዝ የዩኒቨርሲቲዎቹ ጉዳይ አይደለም። ተመራቂው በራሱ ስራ እንዲፈጥር ግን መንገድ ማሳየት ይጠበቅባቸዋል። ተማሪዎች በተመደቡበት የሙያ መስክ ብቁ ሆነው እንዲመረቁ ማድረግ ዋናው ትልእኮው መሆኑ አይጠያይቅም።
ከዚህ አንጻር ሲታይ ግን ዩኒቨርሲቲዎቹ ብዙ ስራ ይጠብቃቸዋል። አሁን የተጠመዱት በህንጻ ግንባታ ላይ ነው። በህንጻ ግንባታቸው ብዙ ርቀት ሄደዋል። በርካታ ውብ ህንጻዎችን በየካምፓሶቻቸው ገንብተዋል፣ እየገነቡም ናቸው። ምድረ ጊቢያቸውን በሚገባ እያስዋቡም ይገኛሉ። መግቢያበሮቻቸውን አሳምሮ እየተገነቡ ናቸው። ቁመናቸው ሲታይ ምቹ የመማር ማስተማር ስራ የሚካሄድባቸው ናቸው።
አንዳንዶቹ በተለይ ቀደም ሲል የተገነቡት ውብ የስፖርት ሜዳዎችንም ገንብተዋል። ይህ ሁኔታ በቀጣይም በሁለተኛው፣ በሶስተኛው እየተባሉ በትውልድ በካፋፈሉት ዩኒቨርሲቲዎችም እንደሚቀጥል ይታሰባል።
ዩኒቨርሲቲዎቹ የተመሰረቱባቸውን አካባቢዎችም በብዙ መልኩ ቀይረዋል። ለአካባቢው ህብረተሰብ የስራ እድል በመፍጠር ፣ በማህበረሰብ አገልግሎት ላይ በመስራት፣ በተከታታይ ትምህርት ለአካባቢውና አቅራቢያቸው ማህበረሰብ የከፍተኛ ትምህርት እድል ፈጥረዋል። በየአካባቢው ባሉት እምቅ ሀብቶች ላይ ጥናት እና ምርምር በማድረግ እየሰሩ ይገኛሉ። የከተሞችን ገጽታ መቀየር ችለዋል። እነዚህ ሁሉ ትላልቅ ስራዎች ናቸው።
ህንጻዎቹ ውስጥ ምን አለ ፤ ከህንጻዎቹ የሚወጡት ተማሪዎች ምን ይዘዋል የሚለው ግን ያሳስበኛል። በቅርቡ በዚህ ጋዜጣ ስፖርትና መዝናኛ ዘርፍ አንድ አምድ ላይ የህክምና መሳሪያ መገጣጠምና ጥገና ላይ የሚያስተምር እንድ ዩኒቨርሲቲ የማስተማሪያ ቁሳቁስ ቢኖረውም ይበላሻል በሚል አያስምሩበትም የሚል ዘገባ ያነበብኩ መሰለኝ። በህክምና መሳሪያ ጥገና ተማሪዎች የቀለም ትምህርት ቀስመው ብቻ እንደሚወጡ አንብቤያለሁ። የዚህ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ የሆነ አንድ ወጣት ስመረቅ ስራ እንድፍጠር ክረምት ላይ የሞባይል ጥገና ስልጠና እንዳገኝ አርጉኝ ብሎ ቤተሰቡን መመጻኑን አንብቤያለሁ። በህክምና መሳሪያ ጥገና ተመርቆ ሞባይል ሊጠግን።
ይህ ለአብነት ነው የተጠቀሰው፤ በየመስኩ ተማሪዎች ከዩኒቨርሲቲዎች በቂ የተግባር ትምህርት ቀስመው እየተመረቁ አለመሆናቸው በስራ ውድድር ወቅት ፍንትው ብሎ ይታያል። የንድፈ ሃሳብ እውቀቱን ይመልሳሉ፤ ተግባሩ ላይ ግን የሉም።
በአንድ ወቅት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ዩኒቨርሲቲዎች ለህንጻ ግንባታ ከፍተኛ በጀት መድበው እየሰሩ መሆናቸውን በመጥቀስ ከዚህ ቀንሰው ለጥናትና ምርምርማዋል እንዳለባቸው አሳስበው እንደነበር አስታውሳለሁ። በዩኒቨርሲቲዎች ኦዲት ላይም ከፍተኛ ችግር እየታየ ያለው ከግንባታው ጋር በተያያዘ ነው። ይህ ሁሉ ምን ያህል በግንባታ ላይ እንደተጠመዱ ያመለክታል። ይህ ተልእኳችሁ እንዳይደለ ተገንዝባችሁ ፊታችሁን ወደ ትምህርት ጥራት አዙሩ። ዩኒቨርሲቲዎች ይህን መሰረታዊ ችግር ለመፍታት መንቀሳቀስ አለባችሁ። ከህንጻ ግንባታ አረፍ ብላችሁ በትምህርት ጥራት ፣ በተግባራዊ ትምህርት ላይ አተኩራችሁ ስሩ።
ይህን ሁኔታ ቆም ብላችሁ ተመልከቱ። እያካሄዳችሁ የምትገኙትን ግንባታም ለተግባር ትምህርት ማዋላችሁን እጠራጠራለሁ። በየጊቢያቸው የሚካሄደው ግንባታ የኢንጂነሪንግ ተማሪዎቻቸውን በተግባር ለማለማመድ ከበቂ በላይ ነው። አንዱ ዩኒቨርሲቲ ከግንባታ ተግ ቢል እንኳ ተማሪዎችን ወደ ሌላው ዩኒቨርሲቲ ወስዶ የተግባር ልምምድ እንዲያደርጉ መስራት ይቻላል። የተግባር ልምምድ ማድረጊያው ቦታ የግሉ ዘርፍ ወይም ከዩኒቨርሲቲው ውጪ ያሉ የግንባታ ስፍራዎች ናቸው ብሎ ማሰብ አይገባም። ከሞኝ ደጅ ሞፈር እንዳይቆረጥ መስራት አለባችሁ። ወደ ሌላ ተቋም ወስዶ የተግባር ልምምድ ማስደረግም የግድ ከሆነ ከግንባታ አረፍ ብላችሁ የሚከፍልም ካለ እየከፈላችሁ ተማሪዎቻችሁን የተግባር ልምምድ እንዲያደርጉ ስሩ።
በዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስር በኩል ተማሪዎች የተግባር ልምምድ እንደሚያደርጉ ቢጠበቅም የግሉ ዘርፍ ተማሪዎች እቃ ይሰብራሉ ብሎም ይሁን ሰግቶ ተማሪዎቹን ሊያቀርባቸው ፍላጎት እንደሌለው ይገለጻል። ይሄ በተለያዩ መድረኮች ይነሳል፡፤ ጉዳዩ ሁሌም እንዳይነሳ ማድረግ የሚያስችል መላ መፈለግ ይኖርበታል። ይህን ማድረግ ባልተቻለበት ሁኔታ በየአመቱ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎችን መቀበሉና ማስመረቁ ኪሰራ ነው፤ ትውልድንም ይገድላል።
ተማሪዎቻቸው በኮንስትራክሽን መስክ ያሉ ከሆኑ በዘርፉ ባልተማሩ ወይም ብዙም ባልተማሩ ወገኖች የሚሰሩ ስራዎችን ሳይቀር እንዲያውቁ እንዲደርፍሩም ጭምር ማድረግ ይገባል። በአንዴ ኢንጂነር ተብለው ሳይት ላይ እንዲቆሙ ሳይሆን ማድረግ የሚገባው በግንባታው ዘርፍ ትንሹ ስራ ውስጥ ሳይቀር እንዲያልፉበት ማድረግ ነው።
ይህን ለማድረግም ተማሪዎቹ አመለካከት ላይ መስራት ያስፈልጋል። ተማሪዎቹ እንደተመረቁ አይደለም ዓመታትን ቆይተውም ኢንጂነር መሆን እንደማይችሉ መሬት ላይ ካለው እውነታ እነሱም እየተረዱ ናቸው። ዩኒቨርሲቲዎችም ይህን ጉዳይ አስቀድመው እንዲገነዘቡና ራሳቸውን እንዲያዘጋጁ ሊረዷቸው ይገባል።
በግንባታው ዘርፍ ያሉትን የትኛዎቹንም ስራዎች ለመስራት ዝግጁ እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል። ወረቀታቸውን የሚወስድባቸው የለም። ትንሹን ስራ እየሰሩ ወደ ትልቁ መድረስ ይችላሉ። ተመርቆ ከመቀመጥ እንዲሁም ባልተካኑት ሙያ ውስጥ ገብቶ ከመፈተን የራስን የስራ መስመር ሀሁ ብሎ መጀመር ምንም ችግር የለውም። ይህን ማድረግ ከተቻለ የተማሩበትን መስክ ትተው ወደ ሌላ ተራ ስራ ፍለጋ እንዳይሄዱ ወይም ቁጭ ብለው ስራ በመፈለግ ጊዜያቸውን እንዳያባክኑ ማድረግ ይቻላል።
ተማሪዎቻቸው ፈቅደውም ይሁን ተገደው ተመድበው የሰለጠኑበትን መስክ እንዲወዱት ማድረግ አድርጉ። ተማሪዎቹ በትንሹ ከዚያ ሙያ ጋር ከሶስት ዓመት ያላነሰ አብረው የሚቆዩ እንደመሆናቸው ሙያውን ለመውደድ እድሉ አላቸውና እንዲወዱት ማድረግ ላይ መሰራት አለበት። በዘርፉ ከየት እስከየት በመስራት ወደ ሚፈልጉት ስፍራ መድረስ እንደሚቻል ማመላከት ያስፈልጋል።
እነዚህን ማድረግ ከታቸለ ተማሪዎች የሙያቸውን የትኛውንም ስራ ደፍረው መስራት ይጀምራሉ። እንደ ተመረቁ ስራ ጠባቂ መሆናቸው ቀርቶ ስራ ፈጣሪ ወይም ስራ ፈላጊ ይሆናሉ። ከበሲቪል ምህንድስና ተመረቀው በሌላ ሙያ ስራ አይፈልጉም። ለእዚህ ሁሉ ግን የዩኒቨርሲቲዎቻችን ከተጠመዱበት የህንጻ ግንባታ አረፍ ብለው ጥራት ላይ አተኩረው መስራት አለባቸው።
ዘካርያስ ዶቢ
አዲስ ዘመን ሰኔ 27/2013