ኢትዮ ቴሌኮም በአገሪቱ ሁሉም መአዘናት እያስጀመረ ባለው በ4ተኛው ትውልድ የኢንተርኔት አገልግሎት ምረቃ ለመታደም ደሴ ተገኝቻለሁ። ደሴ ከተማ በአማራ ብሄራዊ ክልል ውስጥ ከሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች አንዷ ስትሆን፣ ከአገራችን ርዕሰ መዲና አዲስ አበባ ሰሜን ምሥራቅ አቅጣጫ 400 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች። ከባህር ወለል በላይ በ2470 እና 2250 ከፍታ ላይ፣ በአስደናቂው የጦሣና የአዘዋ ተራሮች ተከባ በድምቀት ትታያለች። የአየር ንብረቷ በአብዛኛው ወይን አደጋ ሲሆን፣ ለሰው ልጆች መኖሪያ በእጅጉ ተስማሚና ተናፋቂ ናት።
ከተማዋን በስተምስራቅ የቃሉ ወረዳና ኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ፣ በስተደቡብ አልብኮና ደሴ ዙሪያ ወረዳዎች ፣በስተምዕራብ ሰንሰለታማው የጦሣ ተራራና ደሴ ዙሪያ ወረዳ በስተሰሜን የኩታበርና ተሁለደሬ ወረዳዎች ያዋስኗታል።
ደሴ ከተማ ለምን “ ደሴ “ የሚል ስያሜ ተሰጣት? መነሻው ምንድን ነው ? በሚል ለሚነሱ ጥያቄዎች ተዋቂና የእድሜ ባለጸጋ አባቶችን ጠቅሰው ታሪክ ፀሐፊዎች መላምቶችን አስቀምጠዋል። አሁን ሰኞ ገበያ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ጠላ በመሸጥ የሚተዳደሩ “ ደሴ “ የሚባሉ ሴት ነበሩ። ከሩቅ አካባቢ የሚመጡ ነጋዴዎች በበቅሎና በአህያ ለገበያ ጭነው የሚመጡት ዕቃ ሳይሸጥ ሲቀርና ሲተርፍባቸው እኝህ ሴትዮ ቤት ያስቀምጡ ወይም በገበያተኛ አባባል ደፍተው ይሄዱ ነበር።
ታዲያ ሁልጊዜ እርስ በርስ ሲያወሩ “ እቃየን ደሴ ቤት አስቀምጫለሁ “ ደሴ ቤት እንገናኝ ይባባሉ ነበር ይባላል። በዚህም የወ/ሮ ደሴ ቤት መቀጣጠሪያም ሆነ። ታዲያ በዚያው አብዛኛው ገቢያተኛ ሴትየዋን በአካል የሚያውቃቸውም ሆነ የማያውቃቸው ደሴ ቤት የማለት አባዜ ተጠናወታቸውና በዚያው የቦታውም ስም ደሴ ተብሎ እስካሁን ቀጥሏል የሚሉ አሉ።
ሌላኛው አፄ ዮሐንስ በአካባቢው በመጡበት ወቅት አካባቢውን ሲቃኙ በልምላሜውና በተፈጥሯዊ አቀማመጡ ስለተማረኩ “ ደስ “ የሚል ቦታ ነው ሲሉ ደስታዬ ነው፤ ደስ ብሎኛል በሚል ስሜት በዚያው “ ደሴ “ የሚለውን ስያሜ ይዟል የሚሉም አሉ።
አፄ ቴዎድሮስም በአካባቢው ዘልቀው ጀሜ አካባቢ በሰፈሩበት ወቅት ድንኳናቸውን ተክለው ነበር። በጊዜው የተጠቀሙባትን ድንኳን “ ደስታ “ የሚል ስያሜ ነበራት። ከዚሁ ከድንኳኗ ስያሜ ጋር በማመሳሰል አካባቢውንም ደስታ “ ደሴ “ ብለው ሰየሙትም ይባላል። ደሴ ከተማ ደሴ ተብላ ከመሰየሟ በፊት ላኮመልዛ ተብላ ትጠራ እንደነበር ይነገራል።
የሆነው ሆኖ የዛሬ ምልከታዬ ስለከተማዋ ታሪክ ሳይሆን በመላ ዓለምና በሀገራችን እየተስፋፋ ያለውን የኮሮና ወረርሽኝን በመከላከል በኩል በከተማዋ የሚደረገው እንቅስቃሴ እና የህበረተሰቡ ግንዛቤ ላይ ነው።
ዕለቱ አሁድ ነበር ወደ ውቧ እና የውቦች ከተማ ደሴ የገባነው። አብረውኝ ከተጓዙት መካከል ከአንዱ በስተቀር ከተማዋን የሚያውቃት የለም፤ስለዚህም ሁሉም ነገር ለአብዛኞቻችን አዲስ ነው። እስከ ኮንቦልቻ ያለውን በሰማዩ ጋሪ ቀሪውን 20 ኪሎ ሜትር በመኪና ተጉዘን ነበር ወደ ከተማዋ የገባነው፤ወደ ከተማዋ ከገባን በኋላ መጀመሪያ ያደረግነው ወደ ማረፊያ ሆቴላችን ሄደን ንብረቶቻችን ማስቀመጥ እና ጥቂት እረፍት መውሰድ ነበር፤ይህን ካደረግን በኋላ በእጅጉ ወደጓጓንላት ከተማዋ ወደ መቃኘቱ ገባን። ዞር ዞር ብለን ማየት ጀመርን።
የኮሮና ወረርሽኝ ስጋት እንደ ሀገር አሳሳቢ በሆነበት በዚህ ወቅት ደሴን ከረገጥን አንስቶ በከተማዋ ማስክ ያረገ አላየንም ማለት ይቻላል። ኮሮና ደሴ ላይ የለም የተባለ ይመስል ይመስላል። እኛ ብቻ ነን ማስክ ያደረግነው ማለት ይቻላል። ማስካችንን በአግባቡ ማረጋችንን እያረጋገጥን ወደ ገበያ ወጣን።
በመጀመሪያ የሄድነው ወደ ጢስ ገበያ ነበር፤ጢስ ደግሞ ምን የሚሉት ገበያ አለው ትሉኝ ይሆናል። ደሴ ላይ ገበያ አለው እንጂ ፤ በጣም። ወሎዎች አንድም የሚታወቁት በጢሳጢሶች ነው። እነዚህን ጢሳጢሶች ሴቶች በብዛት ይፈልጓቸዋል። የሚጨሱ ነገሮች ናቸው ጢሳጢሶች የተባሉት።
ጢሶቹ ለአይን በሚማርክ መልኩ በቀለም ፣በአይነት፣ ባላቸው የሽታ ጣእም የተደረደሩ ናቸው። ጢሶቹን እዚያ እየሞከሩ መግዛት ይቻላል።
በእነዚህ ጢሶች መአዛ አማካይነት ገበያ በሙሉ በአስገራሚ መአዛ ተሞልቷል። ታዲያ እኛ (ከአዲስ አበባ) የመጣነውን በደሴዎቹ አጠራር (የመሐል አገር ሰው) እንግዶችን በሁለት መንገድ ነው ያስተናገዱን።
አንደኛው አንዳች ነገር እንድንገዛቸው በእንክብካቤ እና በቁልምጫ ጥሪ ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ “ኮሮና የሚመጣው ከአዲስ አበባ” ነው የሚል መረጃ ስላላቸው በስጋትም ጭምር ነበር።
እኔም ስጋታቸው ስለገባኝ የሚሸጡትን ቁስ ዋጋ ከመጠየቅ ይልቅ ለምን የአፍ እና የአፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል እንደማይጠቀሙ ጠየኳቸው፤ለመልሱ ማሰብም አላስፈለጋቸውም ለምን እናደርጋለን ? የሚባለው በሽታው.. ማነው ስሙ … “ኮሮና” ያለው እኮ እዚያ መሐል ከተማ ዘንድ ነው፤ እዚያ ምን ሊያደርግ ይመጣል ብለው አረፉት።
በተናገሩት ሀሳብ እኔም ጓደኞቼም በመደናገጥ እርስ በእርስ ተያየን … ከዚያም ማድረግ የምንችለው መረጃ መስጠት ስለሆነ ስለበሽታው አስከፊነት የመተላለፊያ መንገዶች እኔም ጓደኞቼም በቻልነው አቅም ለማስረዳት ሞከርን።
እንዷማ …እረ.. እነሱ ወይ ፍንክች! “እንዲያውም ከከተማ የምትመጡት እንዳታስተላልፉብን ነው ስጋታችን እንጂ በከተማችንማ ይህ በሽታ የለም፤” ብላ አረፈችው። ይህን ተናግራ እንደጨረሰች ሌላኛዋ ኮሮና ቢመጣም ባህላዊ በሆኑ መድሐኒቶች (ጢሳጢሶችን) ጨምሮ ሊከላከሉት እንደሚችሉ ነገረችን።
ብቻ ቅንነታቸው ጨዋነታቸው እና እንግዳ አክባሪነታቸው ቢማርከኝም በበሽታው ላይ ያላቸው አቋም ማስቀየርና በሽታው በአግባቡ ለመከላከል ግን ከፍተኛ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ የሚጠይቅ መሆኑን ታዝቢያለሁ።
በእርግጥ ወደ ከተማዋ በአንዳንድ ቦታዎች ስንዟዟር በሽታውን ለመከላከል የተለጠፉ መልዕክቶች ይታያሉ፤በተለይ ፒያሳ በተባለው ስፍራ አልፎ አልፎ የእጅ ንጽሕና መጠበቂያ ውኃ እና የተለያዩ ቁሳቁስ ተቀምጠዋል። ነገር ግን ሕዝቡ ሲጠቀምባቸው አይታይም።
ስለዚህም የማኅበራዊ ሚዲያ አንቂዎች፣ ፖለቲከኞች፣ መምህራን፣ ተማሪዎች፣ … ዕውቀትና አቅም አለን የሚሉ ሁሉ ተረባርበው የኅብረተሰቡን ግንዛቤ መለወጥና ሕዝብን በሽታው ሊያደርስበት ከሚችለው ችግር ለመታደግ መስራት ያለባቸው ይመስለኛል።
በጣልያን መጀመሪያ የኮሮና ቫይረስ መግባቱ ሲነገርና መንግሥት የጥንቃቄ መልእክት ሲያስተላልፍ ቸልተኞች ብዙ ነበሩ። በመጠጥ ቤቱ፣ በኳስ ሜዳው፣ በአምልኮ ቦታዎች … እየተሰባሰቡ የመንግሥትንና የጤና ባለሙያዎችን አያከብሩም ነበር፤ ነገር ግን ሄዶ ሄዶ በቀን በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ማጣትና ከቤት እንዳይወጡ በወታደር እስከመጠበቅ ደረሱ።
በአንጻሩ የቫይረሱ መነሻና ከፍተኛ ተጠቂ የነበሩት ቻይናውያን የሚሰጡ ምክሮችን ያለማቅማማት ተግብረው በአጭር ጊዜ ከቫይረሱ አደጋ እየወጡ ነው፤ አዳዲስ ተጠቂዎች ከሀገራቸው እየተገኙ አይደለም። ቻይና ወደ መደበኛ ሕይወት ከተመለሰች ቆይታለች፤ ስለዚህም ታሞ ከመማቀቅ… እንደሚባለው እንደጣሊያን ሳይሆን እንደቻይና እንማር እንንቃ!! መልዕክታችን ነው።
በሀገራችንም በሽታውን ለመከላከል በስፋት ሲሰራ ቆይቷል። በአዲስ አበባ ማስክ ሳያደርጉ መንቀሳቀስ ክልክል ነው። በትራንስፖርት ላይም እንዲሁ ማስክ ሳያደርጉ መንቀሳቀስ ያስጠይቃል። በአዲስ አበባ አንዳንድ ችግሮች ቢታዩም በክልል ካለው አኳያ ግን ጥሩ የሚያሰኝ ነው።
አዲስ አበባ ብቻዋን በሽታውን ተከላክላ ግን አንደ ሀገር የትም አይደረስም። ሁሉም በሮቿ ክፍት ያደረገችው አዲስ አበባ መዳን የምትችለው ወደ እርሷ የሚተሙት በሽታውን በበቂ ሁኔታ መከላከል ሲችሉ ነው። እናም ከአዲስ አበባ ውጪ የሚገኙ ከተሞች በሽታውን ለመከላከል ትኩረት መስጠት ይኖርባቸዋል። ሁሉም ኃላፊነቱን መወጣት ሲችል ነው እንደ ሀገር በበሽታው ላይ ድልን መቀዳጀት የሚቻለው።
የልቤ ደርሶ
አዲስ ዘመን ግንቦት 28/2013