መርድ ክፍሉ
በአገሪቱ ባለፉት አምስት ዓመታት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚማሩ ተማሪዎች በፖለቲካ አስተሳሰብ ልዩነት ሲደባደቡና ሲገዳደሉ ማየት የተለመደ ተግባር ነበር።የራሳቸው የፖለቲካ ዓላማ ያላቸው ግለሰቦች ሃሳባቸውን የሚደግፉላቸውን ተማሪዎች በመሰብሰብ ከፍተኛ ተቃውሞና ውድመት ሲያደርሱ እንደነበርም አይዘነጋም።ተማሪዎችም ከትምህርት ተስተጓጉለው ጊዜያቸው ሲቃጠልና ወዳልተፈለገ ዓላማ ሲገቡም ተስተውሏል።
ባሳለፍነው ዓመት ደግሞ የኮሮና ወረርሽኝ በመከሰቱ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የነበሩ ተማሪዎች ወደየቤታቸው እንዲበተኑ ተደርጓል።እነዚህ ተማሪዎች ታድያ ወደ አካባቢያቸው ሲመለሱ በበጎ ፈቃድ ብዙ ሥራዎችን አከናውነዋል።ስለኮሮና ወረርሽኝ ግንዛቤ ከመስጠት አንስቶ ለተቸገሩ ገንዘብ በማሰባሰብ የተለያዩ ድጋፎችም ማከናወናቸው በተለያዩ ጊዜያት በዚህ አምድ ስር በወጡ ፅሑፎች አስነብበናል።
የስብዕና ልህቀትና የአስተሳሰብ ለውጥን በመደበኛ ትምህርት ብቻ ማሳካት አይቻልም።ከመደበኛ ትምህርት በተጨማሪ በህብረተሰቡ አስተሳሰብ ለውጥ ላይ የሚሠሩ ማዕከላት እገዛ ያስፈልጋል።የጋራ ጥረት ለውጤት ያበቃል።በአስተሳሰብ ለውጥ ላይ የሚሠሩ ሥራዎች ተከታታይነት ከሌላቸው የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት አያስችልም።ምክንያቱም ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ያማከለ መሆን ስላለበት ነው።
ሃሳብ የመጀመሪያው የሀብት ምንጭና የአንድ ሀገር ዕድገት መለኪያ ሲሆን፤ ትኩረት ተሰጥቶ ሊሠራበት ይገባል።አሁን ባለው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ በማህበረሰብ ደረጃ ቀናና የበለጸገ አስተሳሰብ ማምጣት ለፍትሐዊ ዕድገት ቁልፍ መሳሪያ በመሆኑ በአስተሳሰብ ላይ ብዙ መሥራትና የመወያያ መድረኮችን ማበራከት ያስፈልጋል።ወደ ግለሰብ፣ ቤተሰብና ማህበረሰብ በማውረድ ሁሉም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ማድረግም ይገባል፡፡
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የማህበረሰብ አገልግሎትን እንደ አንድ ሥራ ይዘው እየተንቀሳቀሱ ሲሆን፤ በዚህም በርካታ ውጤት አምጥተዋል።በተለይ ተቋሙ የሚገኝበትን አካባቢ ከማልማት ጀምሮ አርሷደሮችን በመደገፍና በምርምር የተገኙ የግብርና ግብዓችን እያቀረቡ ይገኛሉ።ይህንን ሥራ ተማሪዎችም በመከተል በሰብል ስብሰባና በሌሎች ሥራዎች እገዛ ማድረግ እየተለመደ መጥቷል።ነገር ግን ተማሪዎች በበጎ አድራጎት ሥራ ላይ ተሰማርተው የተቸገሩትን እንዲደግፉ የተቀመጠ ነገር የለም።
ዛሬ በጅማ ከተማ በተማሪነት ወቅት የመሰረቱትና ለተቸገሩ ድጋፍ በማድረግ ላይ የነበሩት “እኛ ለእኛ በጎ አድራት ማህበር” በአሁን ወቅት በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን፤ ስሙንም “አንድ ብር ለወገኔ የበጎ አድራጎት ማህበር” በሚል ለውጧል።የአንድ ብር ለወገኔ በጎ አድራጎት ማህበር ሰብሳቢ ዳግም ጌቱ ጋር ቆይታ አድርገናል።እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
የማህበሩ አመሰራረት
ማህበሩ የተመሰረተው ዳግምና ጓደኞቹ የአስራ ሁለተኛ ክፍል ተማሪዎች በነበሩበት ወቅት ነው።የተመሰረተው በጅማ ከተማ ውስጥ ነው።ዋና ዓላማው በችግር ላይ የሚገኙ ሰዎችን በተቻለ አቅም መርዳትና በወጣቱ መንፈስ ላይ የረጂነት ስሜት እንዲመጣ ለማስቻል ነበር።በአሁን ወቅት የማህበሩ አባላት በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ እየተማሩ የሚገኙ በመሆኑ ሃሳቡን በተለያዩ ቦታዎች ለማስፋት ጥረት እየተደረገም ነው።
ቀደም ብሎ የማህበሩ ስም እኛ ለእኛ በጎ አድራጎት ማህበር ይባል ነበር።አሁን ግን በተለያዩ ቦታዎች የሚንቀሳቀስ በመሆኑ አንድ ብር ለወገኔ በሚል እንዲቀየር ተደርጓል።የነበረው ስም ከአገራዊ በጎ አድራጎት እንቅስቃሴ ጋር በመመሳሰሉ እንዲቀየር ተደርጓል።አንድ ብር ለወገኔ የበጎ አድራጎት ማህበር በይፋ በዩኒቨርሲቲዎች ላይ በመንቀሳቀስ ላይ ነው።
ማህበሩ የሠራቸው ሥራዎች ማህበሩ ከተመሰረተ ጀምሮ የተለያዩ ሥራዎችን አከናውኗል።ከዚህም ውስጥ በጌድዮ አካባቢ በደረሰ መፈናቀል ምክንያት ችግር ላይ ለወደቁ ሰዎች በከፍተኛ ትምህርት ደረጃ በሃዋሳ፣ በባህርዳር፣ በሚዛን ቴፒ እንዲሁም በሌሎች ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የገቢ ማሰባሰብ ሥራ ተሠርቷል።በተጨማሪም አልባሳትን ማሰባሰብ ድጋፍ ለማድረግ በጌድዮ ዞን ወናጎ ወረዳ ድረስ በመሄድ ተሰጥቷል።
በካንሰር ህመም የሚሰቃዩ እህቶችን ለማዳን ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው።ከአንድ መፅሐፍ ማሳተም የሚፈልግን ወጣት በመደገፍ መፅሐፉ ወደ ገበያ እንዲገባ ተደርጓል።ከመፅሐፉ የሚገኘው ሙሉ ገቢ ለካንሰር ታማሚ እንዲውል ተደርጓል።በቅርቡ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የነበረች ተማሪ በአሁን ወቅት በሐይወት ባትኖርም እሷንም ለማትረፍ ማህበሩ ሰፊ እንቅስቃሴ አድርጎ ነበር።በወቅቱ የኮሮና ወረርሽኝ እየተዛመተ የነበረ ቢሆንም ብዙ ገንዘብ እንዲሰበሰብ የተደረገ ሲሆን፤ ሒይወቷን ማትረፍ አልተቻለም።ነገር ግን የተሰበሰበው ገንዘብ ለቤተሰቦቿ እንዲላክ ተደርጓል።
በሌላ በኩል የሕፃናት ማሳደጊያዎችን በየጊዜው በመጎብኘት ድጋፎች ይደረጋሉ።የተለያዩ የኮሮና ወረርሽኝ ግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ማህበሩ አከናውኗል።ከደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች እንዲሁም ከሲዳማ ክልል የቀይ መስቀል ማህበር ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው።አንድ ብር ለወገኔ የበጎ አድራጎት ማህበር በሚል በቅርቡ ከሲቪል ማህበረሰብ አደረጃጀት ኤጀንሲ እውቅና አግኝቷል።ማህበሩ በተወሰኑ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ብቻ ነው የሚንቀሳቀሰው።በዩኒቨርሲቲዎች ላይ ብዙ ጊዜ ለበጎ ሥራ ትብብር ማድረግ ላይ ውስንነቶች አሉባቸው።
ማህበሩ በአገር አቀፍ ደረጃ ለመሥራት ሃሳብ ያለው ሲሆን፤ በወጣቱ ላይ የበጎ አድራጎት ንቅናቄ እንዲኖር ለማስቻል እንቅስቃሴ እየተደረገ ቢሆንም በዩኒቨርሲቲዎች ላይ ይህ ሃሳብ እንዲሰፋ ለማድረግ ፕሮግራሞች በየጊዜው ይዘጋጃሉ።በሌላ በኩልም በዩኒቨርሲቲዎች ዕርዳታ ሲያስፈልግም የተለያዩ ድጋፎች ይደረጋሉ።የገንዘብ መዋጮዎችን በማድረግ አስፈላጊ ለሆኑ ጉዳዮች እንዲውሉ እየተደረገ ይገኛል።የማህበሩ ዋና ዓላማ ሥራዎችን አገር አቀፍ በማድረግ በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ተደራሽ የማድረግ ዓላማ ተይዞ እየተሠራም ነው።
የህብረተሰቡ አቀባበል
የበጎ አድራጎት ሥራዎች ሲሠሩ የማህበረሰቡ አቀባበል ሁለት ዓይነት ነው።አንዱ በደንብ ተረድቶ ገብቶት የማህበሩን ሃሳብ ለመደገፍ በጣም የሚጥር ሲሆን፤ የተወሰነው የማህበረሰቡ ክፍል ደግሞ የማህበሩ ሥራ አጠራጣሪ ወይም ደግሞ ሥራው የሚሠራው ለግል ጥቅም እንጂ ለማህበረሰቡ አስበው አደለም ብሎ የሚያምን አለ።በጎ አድራጎት ሥራ በመተማመን ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ማህበሩ ለሚሠራቸው ሥራዎች የሚፈለገውን ያህል ማስረጃ ማቅረብ ስለማይችል ሁኔታውን ከባድ ያደርገዋል፡፡
ድጋፍ በሚሰበሰብበት ወቅት በሚሰጥ ፈቃድ ነው ወደ ሥራው የሚገባው፤ ነገር ግን ለሚሠሩት ሥራዎች ሁሉ ማስተማመኛ ማቅረብ አይቻልም።ዕርዳታዎች በሚሰባሰቡበት ጊዜ የተወሰነ ቅሬታ የሚያቀርቡ ሰዎች አሉ።በማህበር ውስጥ የሚገኙት ሰዎች ሊጠቀሙበት እንጂ ለሰዎች ድጋፍ ሊሰጥ አይደለም ብለው የሚያነሱ ሰዎች አሉ።
በዚሁ ልክ ደግሞ ማህበሩ የሚሠራቸው ሥራዎች ጥሩ ናቸው ብለው የሚያበረታቱ መልካም ሰዎች አሉ።ስልክ በመደወል ምን እናግዝ ምን እንርዳ የሚሉ ሰዎች አሉ።ከማህበረሰቡ ውስጥ መረዳት ያልቻለውን በማስረዳት ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው።በሁለም ቦታ ላይ ያለው የመረዳዳት ባህል ሌላ ጊዜ ብንጣላ እንኳን ችግር ሲመጣ አንድ የመሆን ሁኔታዎች ስላሉ ጥሩ ነው፡፡
ማህበሩን ያጋጠሙ ችግሮች
ማህበሩ ሲመሰረትም አሁንም አባላቱ ተማሪዎች ናቸው።አባላቱ ውስጥ ያለው ፍቅርና የበጎ ሥራ ሃሳብ ነው።የተቸገሩትን ለመርዳትና ለማገዝ በአባላቱ ከፍተኛ ተነሳሽነት አለ።የማህበሩ አባላት ድጋፎችን ለማግኘት ከፍተኛ እንቅስቃሴ ያደርጋሉ።አባላቱ የገንዘብ አቅም ባይኖራቸውም ፍላጎት ስላላቸው ብዙ ሥራዎች አከናውነዋል።
የበጎ ሥራዎች እንዲበራከቱ ጥረት ቢደረግም በዚህ ሰዓት ዩኒቨርሲቲዎች ትብብር እያደረጉ አይደለም።ሥራዎች ከመሠራታቸው በፊት ወደ መሰላቸት እንዲገባ እያደረገ ነው።ምክንያቱም በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ተማሪዎች በጎ ተግባራት ላይ እንዲሳተፉ የተቀመጠ ነገር የለም።
አንድ ፈቃድ ለማግኘት ወራት ድረስ የሚፈጅ ሲሆን፤ ቀደም ብሎ በነበሩበት ትምህርት ቤት የተሻለ ድጋፍ ይደረግላቸው ነበር።ከመምህራንና ከትምህርት ቤት ኃላፊዎች ጋር ተባብሮ የመሥራት ሁኔታዎች ነበሩ።አሁን ግን ዩኒቨርሲቲ ላይ አንዱ ሲፈቅድ ሌላው ትብብር አላደርግም ሊል ይችላል።ይህ የአሠራር ችግሮች ማህበሩን እየፈተኑት ይገኛሉ።በመንግሥት ቢሮዎች መመላለሱ አሰልቺ እየሆነ መጥቷል።
በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚገኙ በጎ ፈቃደኛ ተማሪዎችን ለማበረታታት አሠራሮች ሊቀየሩ ይገባል።አስፈላጊው ነገር ተሟልቶላቸው የሚሠሩበት ነገር ቢመቻች መልካም ነው።እነዚህን እንቅፋቶች ለማለፍ ወሳኙ ነገር ትዕግስት ማድረግ ነው።
ፈቃድ ለማግኘት ቢሮዎች ላይ ረጅም ሰዓት ማሳለፍ ያስፈልጋል።በዚህም ከትምህርት ሰዓት መቀነስ የግድ እያለ ይገኛል።የፈጀውን ሰዓት ፈጅቶ በጎ ፍቃደኞች ሲገኙ ድጋፍ ለመሰብሰብ ምንም ዓይነት እንቅፋቶች ገጥመውን አያውቁም።ከባዱ ነገር ከላይ እንዲህ ማድረግ አትችሉምና ሰው አይሰጥም ይከብዳችኋል በሚል ምክንያት ፈቃድ ለመከልከል የሚሞከርበት ጊዜ አለ።
ወደ ዕርዳታ ማሰባሰብ ሲገባ ህብረተሰቡ ድጋፍ ለማድረግ የተዘጋጀ በመሆኑና ኢትዮጵያዊ ሆኖ ድጋፍ ለማድረግ የሚሰስት ባለመኖሩ ዕርዳታ ለመሰብሰብ ችግር አልነበረም።በቅርቡ ሕይወቷ ያለፈውና ዕርዳታ ሲሰባሰብላት የነበረችውን ወጣት ለማሳከም በነበረው ጥረት የኮሮና ወረርሽኝ ቢኖርም ሰዉ ድጋፍ አላቋረጠም ነበር።ነገር ግን ደጋፎችን በቋሚነት ለመሰብሰብ የሁሉም ትብብር ያስፈልጋል።ለበጎ አድራጎት ሥራ በጣም የተመቻቸ መንገድ ሊኖር የግድ ይላል።
የማህበሩ ቀጣይ እቅዶች
በአሁን ወቅት አንድ ብር ለወገኔ በሚል በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ኤጀንሲ ተመዝግቧል።በቅርቡም ማሟላት ያለበትን አሟልቶ ፈቃድ ያገኛል።ማህበሩ በቀጣይ አገር አቀፍ ለመሆን በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ እምቅ አቅሞች ያሉ ሲሆን፤ መንግሥትም ይህን ተረድቶ ትብብር ሊያደርግ ይገባል።ተማሪ ሲባል ሲመረቅ ሳይሆን በትምህርት ላይም እያለ መሥራት አለበት።
ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉት የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ላይ የጋራ የበጎ አድራጎት ምክር ቤት ተቋቁሞ አገር አቀፍ ችግሮች ላይ በፍጥነት የሚደረስበት ሁኔታ ቢፈጠር መልካም ነው።በአጭር ጊዜ ነገሮችን መጨረስ የሚችል ወጣት በመኖሩ በዩኒቨርሲቲዎች ላይ እንደ ልብ እንቅስቃሴ እንዲደረግ ትብብር ቢያደርግ ብዙ ሥራዎች ለማከናወን እቅድ አለ።
በየዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ማህበሩ አባላት ያሉት ሲሆን፤ አባላቱ በያሉበት ኮሚቴ አቋቁመው እየሠሩ ይገኛሉ።በቀጣይ በተወሰኑ ዩኒቨርሲቲዎች ላይ ያለውን የአባላት ቁጥር ለማሳደግ ጥረት ይደረጋል።በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ላይ ኮሚቴዎች ኖረው እነሱ ደግሞ አገራዊ የሆነ ኮሚቴ አቋቁመው ቢመሩ ከፍተኛ ለውጥ ማምጣት ይቻላል።ምክንያቱም በየዩኒቨርሲቲው የሚገኘው ተማሪ በጎ ፈቃደኛ ሆኖ ለማገልገል ከፍተኛ ፍላጎት አለው።ይህን ወደ ተግባር ለመለወጥ ማህበሩ ይሠራል።
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 15/2013