በዓለም ዙሪያ በጦርነት ውስጥ ያለፉ አገራት ተሞክሮ እንደሚያሳየው ጦርነት ከሰብዓዊ ቀውሱና ከቁሳዊ ውድመቱ በተጨማሪ ለረዥም ጊዜ ሊቆይ የሚችል የምጣኔ ሀብት ቀውስን ይወልዳል:: ጦርነቱ በቀጥታ የሚያደርሰው ውድመት እንደተጠበቀ ሆኖ ለራሱ ለጦርነቱ የሚበጀተው መዋዕለ ነዋይ የተረጋጋን የአገር ካዝና የማናጋት አቅሙ እጅጉን ግዙፍ ነው::
ስመጥር የምጣኔ ሃብት ምሁራን፣ በተለያዩ መድረኮች ከሚሰጣቸው አስተያየቶችና ለንባብ ካበቃቸው የህትመት ስራዎች መረዳት እንደሚቻለውም፣ መጠኑ ቢለያይም መንግስታት ብድር እንዲጠይቁ ከሚያስገድዱ ክስተቶ አንዱና ዋነኛውም ጦርነት ነው:: ጦርነት ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅና በግብር ብቻ መወጣት የሚከብድም ጭምር ነው::
ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አመታት ያለፈችበት የሰሜኑ ጦርነትም ከሰብዓዊ ቀውሱ ባሻገር በምጣኔ ሀብቷ ላይም ከፍተኛ ጉዳት አስከትሏል::
ጦርነቱ የንግድ እንቅስቃሴ እንዲስተጓጎል፣ ምርትና ምርታማነት እንዲያሽቆለቁል፣ ኢትዮጵያ ከአጎአ የንግድ ትስስር እንድትሰረዝ፣ ብድር እንዳታገኝ እንዲሁም መጠነ ሰፊ ለሆነ የሀብት ውድመት ምክንያት ሆኗል:: ጦርነቱ ሀገሪቱ ለመንገድ፣ ለጤና ተቋማትና ለትምህርት ቤቶችና ሌሎች መሰረተ ልማት ብሎም ግልጋሎቶች ማዋል የነበረባትን ሀብትም ቀምቷታል::
በአንድ አገር ኢንቨስትመንት ለመሳብ ብሎም ኢንቨስተሮችን ለመሳተፍ የሰላም ድባብ ወሳኝ ነው:: ኢንቨስተሮች ደግሞ መዋእለ ነዋያቸውን ፈሰስ ከማድረጋቸው አስቀድሞ የሚጠይቁትም የአገሪቱን ሰላም መሆን ነው:: በአንድ ሀገር የተረጋጋ ከባቢ ከሌለ በሀገር ውስጥ ያሉትንም ሆነ በሀገሪቱ መዋዕለ ነዋይ ማፍሰስ የሚፈልጉ ባለሀብቶችን እምነት እንደሚያሳጣ እርግጥ ነው::
የሰሜኑ ጦርነትም ኢንቨስትመንታቸውን ማስፋፋት ወይም አዲስ መቋቋም የሚፈልጉ የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ ኢንቨስተሮችን ተስፋ በእጅጉ ሲፈትንም ቆይቷል:: ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሁሉም ሰው ጓዳ የገባው የዋጋ ግሽበት እስከ 35 በመቶ (የምግብ ብቻ 42 በመቶ) መድረሱ የጦርነቱ ጫና ውጤት መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው::
በመሰል ኢኮኖሚ መንገጫገጭ ውስጥ ያለፉትን አመታት ለማሳለፍ የተገደደችው ኢትዮጵያ፣ ከወራቶች በፊት በአፍሪካ ኅብረት ጥላ ሥር በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ በፌዴራል መንግሥትና በሕወሓት መካከል የሰላም ስምምነት እውን መሆኑን ተከትሎ የሰላም አየር መተንፈስ መጀመሯም የሚታወስ ነው::
ይህም የሰላም መንገድ ለኢትዮጵያ ትልቅ ድል ነው:: በሰላም እንጂ በጦርነት ያተረፈ ሀገር አለመኖሩን በመረዳት ግጭትና ጦርነት ይብቃን መባሉ እጅግ የሚደገፍና የሚያስደስት ነው:: በሠለጠነ አካሄድ የሰላም መንገድ ማራመድም ፋይዳው ዘርፈ ብዙ ነው::
የሰላም ስምምነት ሰላምን ከማምጣት ባሻገር ምጣኔ- ሀብቱን ሲደቁሱ የነበሩ ችግሮች እንዲቀረፉ፣ ምጣኔ- ሀብቱን በማነቃቃት፤ በማሳደግ ምንአልባትም ይጠፋ የነበረውን ሀብት በመመለስ ከፍተኛ የሆነ አዎንታዊ አስተዋጽኦ እንዳለው አይካድም::
ሰላም ስምምነቱ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ለማሳደር ለሚተጉ ሀገራትና ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት የተወሰዱ እርምጃዎች እንዲቀለበሱ የዋጋ ንረት ከዚህም በላይ ከፍ እንዳይል፣ የውጭ ምንዛሬ ክምችት የለየለት አደጋ ውስጥ እንዳይገባ፣ በሀገሪቱ አለመረጋጋት ውጥናቸውን ገታ አድርገው የነበሩ ባለሀብቶች ለመመለስ ትልቅ እፎይታን ይሠጣል::
ይሁንና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከጦርነቱ በፊትም በሁለት እግሩ ያልቆመና ወደፊት ለመሄድ በመንገዳገድ ላይ እንደነበር ሊዘነጋ አይገባም:: አሁን ላይ የወደመው ኢኮኖሚ በምን ያህል ጊዜ ሊያገግምና ሊያንሰራራ እንደሚችል በውል ለመለየት ጥናት ቢያስፈልግም በጦርነት በደቀቁ አገራት እንደምናየው ረጅም ዓመታት ይጠይቃል::
የኢትዮጵያም በቀላሉ ሊታይ የሚገባው አይደለም:: ሌላው ቀርቶ በጦርነቱ ሳቢያ የወደሙ መሠረተ ልማቶችን ለመተካት እና ሌሎች ግንባታዎችን ለማካሄድ ከፍተኛ ገንዘብን የግድ ይላል:: ቢሊየኖችን ሳይሆን ትሪሊየኖችን ይጠይቃል::
ከድህረ ጦርነት በኋላም የኢትዮጵያ የተቀዛቀዘው ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴ እንዴት ነው ሊነቃቃ እና ዳግም ሊያንሰራራ የሚችለው? በአጭር ጊዜስ እንዴት ወደ አስተማማኝ ተክለ ቁመና መመለስ ይችላል የሚለውም የወቅቱ አንገብግቢ ጥያቄ ነው:: ከዚህ ሰው ሰራሽና ተፈጥሮ ያመጣውን የኢኮኖሚ ቀውስና ኋላቀርነት ለአንዴና ለመጨረሻ እንዴት እንወጣለን የሚለውም እጅጉን ወሳኝ ነው:: ለዚህ ችግር መፍትሄ ሰላምና መረጋጋትን ማስፈን የመጀመሪያው ይሆናል:: ከዚህ ባሻገር ግን ኢኮኖሚን በሚመለከት ጥገና ሳይሆን ስር ነቀል ለውጥ ማድረግ የግድ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል::
ፕሮፌሰር አለማየሁ ገዳን ጨምሮ አለማችን ያፈራቻቸው ስመጥር የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች፣‹‹በጦርነት ውስጥ ያለፈ የምጣኔ ሀብት፣ ጦርነቱ ከተቋጨ ማግሥት ጀምሮ ወደ ማገገሚያው መንገድ ካልተመራ ስብራቱ ከባድ ይሆናል:: ከድቀት ለመውጣትም ራሱን የቻለ የማገገሚያ እቅድ ማርሻል ፕላን ያስፈልገዋል›› ይላሉ:: ለዚህ እሳቤ በምሳሌነት የሚያጣቅሱት ደግሞ የሁለተኛውን የዓለም ጦርነት ነው::
በወቅቱ ይህ ጦርነት ካደረሰው የምጣኔ ሀብት ድቀት ለመሻር ሀገራት ወደ ማገገሚያውና መፍትሄው መንገድ ለመራመድ ጊዜ አላባከኑም:: ለምሳሌ ጀርመኖች እኤአ በ1947 በማርሻል ፕላን /The Marshall Plan /፣ የቀድሞዋ ሶቪየት ህብረት የአሁና ሩሲያ እኤአ በ1947 በሞልቶቭ ፕላን/ Molotov Plan/ እንዲሁም ጃፓን እኤአ በ1949 በዶች ፕላን /The Dodge Plan /የምጣኔ ሃብት ማገገሚያ መንገድ ተራምደዋል::
በእርግጥም ጦርነት ውስጥ ያለፈ ምጣኔ ሃብት እንደ ጤናማው ወቅት ሁሉ በመደበኛ ፖሊሲና ስትራቴጂ ተመርቶ ውጤታማ መሆን አይቻለውም:: ጦርነት ወይንም ግጭቶች የሚያመጡት የኢኮኖሚ ድቀት በዘዴና በተቀናጀ ጥረት ብሎም መንገድ ካልተመራ የሚያደርሰው አደጋ ከፍተኛ ነው::
ምንም እንኳን ኢትዮጵያ በተለይ ባለፉት ሁለት አመታት ያለፈችበት ቀውስ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት እና ኢኮኖሚያዊ ድቆሳው ጋር ፈፅሞ የማይነፃፀር ቢሆንም ክስተቱ ያስከተለውን ኢኮኖሚያዊ መንገጫገጭ በቀላሉ ሊታይ የሚገባው አይደለም::
ይህ እንደመሆኑም እንደ እኔ እምነት ኢትዮጵያ ኢኮኖሚዋን አስተማማኝ ቁመና ላይ ለማድረስ፣ ከለውጡ ማግስት በመተግበር ላይ የሚገኘው ‹‹አገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም›› ይበልጥ ውጤታማ ማድረግ የሚያስችል እቅድና ትግበራ ያስፈልጋል:: ድህረ ጦርነት የኢኮኖሚ ልማት ትግበራውን መሪነት ከውጭ ኃይሎች ይልቅ አገራዊ በሆነ መሠረት ባለው ዕውቀት፣ ተሞክሮና ጥበብ የተዘጋጀ፣ በአገራዊ ፖሊሲና ስትራቴጂ፣ እንዲሁም በኢትዮጵያውያን ሙያተኞች መመራት ይኖርበታል::
በድህረ ጦርነት የኢኮኖሚ ልማት ከሁሉ በፊት በቀላሉ መልማት የሚችሉ ዘርፎችን በመለየት ቅድሚያ የሚሰጣቸውን በቅደም ተከተል ማልማት የግድ ይላል:: ኢኮኖሚው በመታደግ ሂደት በተለይም ትልቁን የአገሪቱ ኢኮኖሚ መሸከም የሚችለው የወጣት ኃይል ተሳቢ ያደረጉ ተግባራትን ማከናወንና ወጣቱን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የኢኮኖሚው ሁነኛ አካል ማድረግ የግድ ያስፈልጋል::
የማክሮ ኢኮኖሚ መዛባቶችን ማስተካከል፣ ቢሮክራሲያዊ የአሰራር ዘዴዎችን ማስወገድና መዋቅራዊ ማነቆዎችን መፍታት፣ አዳዲስ ዕድሎችንና የዕድገት ምንጮችን ለመፍጠር አስፈላጊውን መደላድል ማበጀት ፤ የእስካሁን ስኬቶችን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር የፖሊሲና ተቋማዊ ማዕቀፎችን ደረጃ ማሻሻል፣ የግድ ይላል::
የወቅቱን ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ያገናዘበ (prudent) የፊስካል ፖሊሲን ቁመና ማስጠበቅ፤ የታክስ አስተዳደሩንና ፖሊሲን በማጎልበት የታክስ ገቢን ማሻሻል፤ የመንግስት ኢንቨስትመንት ውጤታማነት መፈተሽ፤ ተወዳዳሪነትን የሚያውኩ ስርዓቶችን ለመቆጣጠር የሚያስችለውን ህግና ሥርዓት አጠናክሮ መተግበር ይገባል::
የግሉ ዘርፍ ኢንቨስትመንት በግብርና ምርምርና ጥናት ላይ እንዲሳተፍ ማበረታታት፣ የመካከለኛና ከፍተኛ የመስኖ ልማትን ለማስፋፋት እንዲቻል የግሉንና የመንግሥትን ዘርፍ (PPP) ጥምረት የሚጎለብትበትን መንገድ ማመቻቸት ያስፈልጋል::
በተለየ ሁኔታ ለግብርናው ዘርፍ የሚያገለግሉ የፋይናንስ አገልግሎቶችን ለምሳሌ አነስተኛ የብድር ስርዓት፣ የአዝእርት ኢንሹራንስ፣ እንዲሁም የቅደም አቅርቦት ኮንትራክት (forward contract) ተግባራዊ ለማድረግ የሚያግዝ የሕግ ማዕቀፍ ከማዘጋጀት ባለፈ በአግባቡ ማስተግበር ሊዘነጋ አይገባም::
የአገራችን ታሪካዊ፣ ባሕላዊ፣ እና ተፈጥራዊ መስህቦች ማራኪና ተደራሽ እንዲሆኑ ማድረግ፣ የቱሪስት መዳረሻዎችን ማስተዋወቅ፣ የቱሪዝምና ሌሎች አገልግሎቶችን አሰጣጥን ደረጃን ማዘመን፤ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎችን ማልማት፣ ሆቴሎችና ሬስቶራንቶች የግብርና የአገር ውስጥ ምርቶችን እንዲጠቀሙ የሚያስችል የገበያ ትስስር መፍጠርና ማጎልበትም ይገባል::
በመሠረታዊ የኢኮኖሚ ልማት ሥራዎች ትግበራ በተለይም እያንዳንዱን ፕሮጀክቶች ከገበያ ጋር ማስተሳሰርና እና የሚመጋገቡትን መንገድ ከወዲሁ አስቦ መንቀሳቀስ ወሳኝ ነው:: እያንዳንዱ የፕሮጀክት ሃሳብ በቴክኒክና በፋይናንስ አዋጭ ስለመሆኑም በቂ ጥናት ሊደረግበት የግድ ነው:: ቀደም ሲል በዚህ በኩል የነበሩ ክፍተቶች በአግባቡ በማጥናት ቀዳዳዎችን መዝጋት ያስፈልጋል::
ከተለያዩ ምሁራዊ አስተያየቶችና ለንባብ ያበቃቸው ስራዎች መረዳት እንደሚቻለውም፣ የድህረ ጦርነት መልሶ ግንባታና ልማት የተፈለገውን ግብ መምታት እንዲችል ከሁሉ በላይ ከመደበኛው የምጣኔ-ሐብታዊ አጠቃቀም በተለየ መልኩ የሀገርን ገንዘብ ማስተዳደር ግድ ይላል:: የገንዘብ ነክ ማዋቅራዊ አሰራርን ማስተካከልም ይገባል::
የኢኮኖሚ መልሶ ግንባታና ልማት ሁለቱ መሠረታዊ ነገሮችን ይፈልጋል:: አንደኛው ገንዘብ ሲሆን ሁለተኛው የተገኘውን ገንዘብ በአግባቡ ኢኮኖሚን በሚቀይሩ የኢኮኖሚ መርሃ ግብሮችና ፕሮጀክቶች ላይ ስለመዋላቸው እርግጠኛ መሆን ነው::
ለመልሶ ግንባታው በተለያየ መንገድ ሊገኙ የሚችሉ ድጋፎችን በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል ከወዲሁ ውጤታማ የሆኑ ፕሮጀክቶችን መቅረፅ ያስፈልጋል:: በተለይም ገንዘቡ በሙሰኞች እጅ እንዳይገባ በመንግሥት ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ተደርጎበት ለታቀደለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ማድረግ የግድ ነው::
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ፀጋዎች የበለፀገች አገር ናት:: እነዚህን ፀጋዎች ታቅፎ በድህነት መኖር ነውር ነው:: በተለይም በቀላሉ በምግብ እህል ራሷን ለመቻል የሚያግዙ መንገዶች መከተልና የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ትኩረት አድርጎ መስራት ይገባል:: ሁሉም ዜጋ ከችግሩ እንድንወጣ መረባረብና ወገቡን ጠበቅ አድርጎ መስራት አለበት::
በከፍተኛ ተነሳሽነትና ቁርጠኝነት ከተሰራና ጥሩ ኢኮኖሚውን ለማጎልበት አጋዥ የሆነ ውጤታማ የማንሰራሪያ ዕቅድ መተግበር ከተቻለ አጠር ባለ ጊዜ ውስጥ ኢትዮጵያ ቀደም ካሉት አመታት በተሻለ የኢኮኖሚ ደረጃ ለማስቀመጥ የሚያስችሉ መልካም አጋጣሚዎች እንዳሉም ልንጠራጠር አይገባም::
የበጋ ስንዴ በመስኖ የማልማት ሥራ በዚህ ሙቀት ከቀጠለ በምግብ እህል ራሷን ከመቻል ባለፈ ቀደም ሲል የነበረ ድክመታችንን ለይተው ኢኮኖሚያችንና ፖለቲካችንን ለመዘወር እጃቸውን የሚያስገቡ ምእራባውያን አደብ የሚያስይዝ መሆኑ አያጠራጥርም:: እንደ አገር ወደ ተቀናጀ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ለመሸጋገር የምናደርገውን ጉዞ ቀላል ያደርገዋል::
የአርሶ አደሩ ምርትና ምርታማነቱን እንዲጨምር የተለያዩ ድጋፎችን ማመቻቸት፣ ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ ልዩ ትኩረት መስጠት ብሎም ጥያቄያቸውን በፍጥነት መመለስ፣ ከቀረጥ ነፃ እድሎችን መፍጠርን ጨምሮ የተለያዩ ማበረታቻዎችን ማመቻቸት የግድ ይላል:: በተለይም የገበያ ሥርዓቱን ጤናማነት ለማስጠበቅ መሠራት ያለባቸው ሥራዎች እንደ ከዚህ ቀደሙ ያዝ ለቀቅ ሳይሆን በግንባር ከተደረገው ጦርነት ባልተናነሰ ሊቃኝ ይገባል::
መዋዕለ ነዋያቸውን ለማፍሰስ የሚፈልጉ አካላትን መተማመን ከፍ ማድረግና መገንባት፤ ብድርን ጨምሮ የተለያዩ ድጎማዎችን በማድረግ ምቹና ሳቢ ሁኔታዎችን መፍጠር፤ የምርት ግብዓቶች በከፍተኛ ትኩረት ለማቅረብ መረባረብም ያሻል::
በጦርነት ሰበብ ወይም ጦርነቱ በፈጠራቸው ተፅዕኖዎች የደረሰውን ኢኮኖሚያዊ ጉዳት የማስተካከል ኃላፊነት ለመንግሥት ብቻ የሚተው መሆንም የለበትም:: ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል በተሰማራበት ክፍለ ኢኮኖሚ የየድርሻውን መወጣት ይኖርበታል::
ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት ሰላምን ለማፅናት አሻራን ከማሳረፍ ባሻገር በተለይ የኢኮኖሚው ዋነኛ ስብራት የሆነውን የውጭ ምንዛሪ እጥረት ለማስተካከልና ግኝቱን ከፍ ለማድረግ ሕጋዊ መንገድን መከተል ቀዳሚ አማራጩ ሊያደርግ ይገባል::
ኢኮኖሚው እንዲያንሰራራ በማድረግ ሂደትም በጦርነቱ ምክንያት ጉዳት ለደረሰባቸው ዜጎች ሰብዓዊ ድጋፍ ማድረግ ሊዘነጋ አይገባውም:: የተጎዱ ወገኖችን መካስ፣ ማቋቋምና በአይምሮና በስነልቦና እንዲፈወሱ ማድረግ፣ የወደሙ መሰረተ ልማቶችን መጠገንና ወደቦታቸው መመለስ እንዲሁም ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ ማድረግ ለይደር የሚተው መሆን የለበትም::
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ግንቦት 11/2015