‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› ሲባል አንድ ነገር ብቻ ያለው ሰው ያንኑ አንድ ነገሩን እንዳያጣው በጥንቃቄ መያዝ እንዳለበት አጽንኦት ለመስጠት የምንጠቀመው አባባል እንደሆነ ግልጽ ነው:: ታዲያ በግል ሕይወታችንም ሆነ በዙሪያችን ባሉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ እንደ አይናችን ብሌን የምንሳሳላቸው እልፍ ጉዳዮች ስለመኖራቸውም የማይታበል ሃቅ ነው:: አገርን ስናነሳ ደግሞ ለአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያ ከጉዳይም በላይ የማይደራደሩባት፤ መተኪያ የሌላት ሕይወታቸውን አሳልፈው የሚሰጡላት ትልቅ ጉዳያቸው መሆኗ ሳይታለም የተፈታ ነው::
‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› የሚለው አባባል ታዲያ ኢትዮጵያውያን የነጻነት ተምሳሌት የሆነችው ብቸኛዋ ኢትዮጵያ አገራቸው አንድ አይናቸው እንደሆነች ቢገልጹባት ያንስባቸው ከሆነ እንጂ አይበዛባቸውም:: አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን አንድና ብቸኛ የሆነችውን ኢትዮጵያ አገራቸውን እንደ አይናቸው ብሌን በማየት ኢትዮጵያን ከሚዋጓት ጠላቶቿ ታድገው፣ ሰላሟን አጽንተው፣ የተረጋጋ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ መስተጋብር ለመፍጠር ከላይ ታች የሚሉትም በዚሁ ምክንያት ነው::
እንደሚታወቀው በአንድ አገር የተረጋጋ ፖለቲካና ኢኮኖሚ መገንባት የሚቻለው የተረጋጋ ሰላምና ጸጥታን ማስፈን ሲቻል ነው:: የተረጋጋ ፖለቲካል ኢኮኖሚ ለመፍጠር በብዙ እየተጋች ያለችው ኢትዮጵያ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ዛሬ የገፏትን ሳትጋፋ፣ የጠሏትን ሳትጠላ፣ የረገሟትን መርቃና የወጓትን በይቅርታ አልፋ ‹‹ጦርነት ይብቃ ሰላምን እናጽና›› በማለት የሰላም መቀነቷን አጥብቃ ጉዞዋን ወደ ብልጽግና አድርጋለች:: ያም ቢሆን ታዲያ ከብልጽግና ጉዞዋ ላያስቀሯት በመንገዷ እየገቡ የሚያደናቅፏት ከበቂ በላይ የሆኑ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች አላጧትምና ዱካዋን እየተከታተሉ ፋታ ነስተዋታል::
ኢትዮጵያ ከጀመረችው የብልጽግና ጉዞ ሊያደናቅፏት ከተኮለኮሉ እልፍ ደንቃራዎቿ መካከል አንዱና ዋነኛው ኢኮኖሚዋን የሚያንገራግጨው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ነው:: እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የተመሰረተው በግብርናው ዘርፍ እንደመሆኑ የግብርና ምርቶቿን ወደ ውጭ ገበያ በመላክ የውጭ ምንዛሪ ታገኛለች:: ከግብርና ምርቶቿ መካከልም ቡና ቀዳሚውና የኢኮኖሚው ዋልታና ማገር የጀርባ አጥንት ነው:: ‹‹አረንጓዴ ወርቃችን›› በማለት የምናንቆለጳጵሰው ቡና በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ትልቅ ድርሻ ያለው በመሆኑ አንድ አይናችን ነው ማለት ይቻላል:: የዚህ ጽሁፍ ዋና ማጠንጠኛም ‹‹የኢኮኖሚ ዋልታ ቡና ቡና…›› በማለት ለተዜመለትና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት በመሆን በቀዳሚነት ለሚጠቀሰወ ቡና በመሆኑ ስለ ቡና ስናነሳ ደግመን ደጋግመን ‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› እንላለን::
የቡናን ዘርፍ በዋናነት የሚመራው የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን በበኩሉ ኢትዮጵያ ከዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንድትችል ዘርፍ ብዙ ሥራዎችን መሥራቱም ‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› ከሚል እሳቤ በመነሳት ነው:: ከሰሞኑም የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የኢትዮጵያ ሀብት የኢኮኖሚው የጀርባ አጥንት የሆነውን ቡና በምርትና ምርታማነቱ፣ በጥራትና በግብይት ሂደቱ የተዋጣለት እንዲሆን እና በአጠቃላይ የኢትዮጵያን ቡና ለማሳደግ በሚል በእንግሊዝኛ የታተመውን የዓለም የቡና መመሪያን ለመጀመሪያ ጊዜ በአማርኛ ተተርጉሞ ወደ ሥራ እንዲገባ አድርጓል::
በወቅቱ ከቡና አምራቹ እስከ ላኪ ያሉ አጠቃላይ የቡና ቤተሰቦች እንዲሁም የሚመለከታቸው የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የተገኙ ሲሆን፤ በግብርና ሚኒስቴር የግብርና ኢንቨስትመንትና ግብዓት ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶክተር) ተገኝተው መልዕክት አስተላልፈዋል:: በመልዕክታቸውም በመጽሐፍ መልክ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ የተተረጎመው የቡና መመሪያ መዘጋጀቱ ለዘርፉ መሻሻልና ዕድገት ትልቅ ጠቀሜታ ያለው መሆኑን ገልጸዋል:: ይሁንና በዕለቱ ዋና አጀንዳ ከሆነው የዓለም የቡና መመሪያን የያዘው መጽሐፍን ከማስተዋወቅ በተጨማሪ ለቡና ላኪዎችና አቅራቢዎች ያስተላለፉት መልዕክት ትልቅ ቁም ነገር የተሸከመ ስለመሆኑ ለመረዳት የሚያዳግት አልነበረም::
በመልዕክታቸውም ቡና የኢትዮጵያ ሀብት መሆኑን በመግለጽ፤ አገሪቷ የቡና ሀብቷን ወደ ውጭ ገበያ በመላክ ከሀብቷ መጠቀም እንደሚገባትና በተለይም በአሁን ወቅት ቡና ወደ ውጭ ገበያ እየተላከ ባለመሆኑ ኢትዮጵያ ከዘርፉ በምታገኘው የውጭ ምንዛሪ ግኝት ላይ የበረታ ተጽዕኖውን እያሳደረ መሆኑን ጠቅሰው ‹‹ቡና ላኪዎችና አቅራቢዎች እባካችሁ በእጃችሁ ያለውን ቡና ወደ ገበያ አውጡ›› በማለት ተማጽነዋል::
ከተማጽኗቸው መረዳት እንደሚቻለው ታዲያ በአሁን ወቅት በዓለም ገበያ የቡና ዋጋ መውረዱን ተከትሎ ኢትዮጵያውያን ቡና ላኪዎች የኢትዮጵያ ሀብት የሆነውንና በውድ የገዙትን ቡና ወደ ገበያው እያወጡ እንዳልሆነ ነው:: እርግጥ ነው ንግድ ለትርፍ እንጂ ለጽድቅ የሚሠራ ሥራ አይደለም ይሆናል:: እናም ቡና ላኪው ቡናውን የገዛበት ዋጋ አሁን ካለው የዓለም የቡና ዋጋ ጋር ሲነጻጸር ሰፊ ልዩነት ያለውና ወደ ኪሳራ የሚወስድ ይሆናል:: ያም ቢሆን ታዲያ ‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› ነውና ብሂሉ አንድና ብቸኛ ለሆነችው አገራችን ቅድሚያ በመስጠት ኪሳራውን ስለ አገር ተቀብለው አጋርነታቸውን ማሳየት ከቡና አምራቹ፣ አቅራቢውና ላኪው ይጠበቃል::
እርግጥ ነው በአሁን ወቅት አገር ያላትን ሀብት አሟጣ በመጠቀም አንቆ የያዛትን የውጭ ምንዛሪ እጥረት መቅረፍ እንድትችል ከቡና ቤተሰቦች ብዙ ይጠበቃል:: ከዚህም ባለፈ አገር ከገጠማት ኢኮኖሚያዊ ቀውስ መውጣት እንድትችል እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ኃላፊነት ያለበት ቢሆንም አሁናዊ መረጃዎች የሚያነጣጥሩት ግን ኢትዮጵያ ከቡና የምታገኘውን የውጭ ምንዛሪ እያገኘች እንዳልሆነ በመሆኑ ‹‹…አገርን ያላችሁ እስኪ እንያችሁ…›› የሚለው ሙዚቃ ከጣሪያ በላይ ተከፍቶ ከቡና ቤተሰቦች ጆሮ ይደርስ ዘንድ አገር ትጠይቃለች::
ታዲያ ይህን ታላቅ አገራዊ ጥያቄ ስግብግብ ነጋዴዎች የቱንም ያህል ቢከፉና አገር ማግኘት የሚገባትን ጥቅም ለማሳጣት የቱንም ያህል ቢጥሩ ‹‹ውሃ ቢወቅጡት እምቦጭ›› ነውና ተረቱ የትም የሚያደርሳቸው አይደለም:: ምክንያቱም ኢትዮጵያ የወላድ መካን አይደለችም ‹‹ኢትዮጵያዬን አገሬን›› የሚሉ በየዘርፉ የሚዋደቁላት እልፍ ልጆች አሏት:: ኢትዮጵያ በገጠሟት ዘርፈ ብዙ ችግሮች ውስጥ የግል ጥቅማቸውን ወደ ጎን አሽቀንጥረው በመጣል የአገርን ጥቅም በማስቀደም አንገታቸውን ደፍተው ለኢትዮጵያ የሰሩ በርካቶች ናቸው:: በዚህ ምክንያት ታዲያ ኢትዮጵያ በየጊዜው ከሚደገስላት የሞት ድግስ ትወጣለች:: ፈራረሰች አለቀላት አበቃላት ሲሏትም አቧራዋን አራግፋ ጸንታ ትቆማለች:: ይህ የሚሆነው ታዲያ በታማኝና ቆራጥ ልጆቿ ነው:: በመሆኑም ታማኝና ቆራጥ የሆኑቱ ቡና ቤተሰቦች ብቸኛ ለሆነች አገራቸው ጥሪ ፈጣን ምላሽ ይሰጣሉ::
ምክንያቱም ኢትዮጵያ ከገጠማት ኢኮኖሚያዊ ቀውስ መውጣት የምትችለው በታማኝ ልጆቿ በመሆኑ ነው:: ‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› ነውና በአሁን ወቅት መንግሥት አንድና የሁላችንም አገር የሆነችው ኢትዮጵያ ጎዶሎዋን እንሙላ ቀዳዳዋን እንሸፍን በማለት እያስተጋባ ላለው የተማጽኖ ጥሪ በተለይም ቡና አልሚዎች፣ አቅራቢዎችና ላኪዎች አጠቃላይ የቡና ቤተሰቦች ‹‹ጆሮ ዳባ ልበስ›› ሳትሉ የድርሻችሁን መወጣት ይጠበቅባችኋል:: ምክንያቱም ሁሉም የሚያምረው በአገር ነው የሚባለው አገር መተኪያ የሌላት ከኪሳራም ሆነ ከትርፍ በላይ በመሆኗ ነው::
በመጨረሻም ‹‹…ሰዎች እንረዳ ቢገባን ትርጉሙ ሁሉም በአገር ነው… በማለት አንጋፋው ድምጻዊ የክብር ዶክተር ጥላሁን ገሰሰ፤ ነግዶ ማትረፍ፣ ዘርቶ ማጨድ፣ ወልዶ መሳምና ለብሶ ማጌጥ የሚቻለው አገር በነጻነት ታፍራና ተከብራ ስትኖር ነው…›› እያለ በማይጠገበውና ዘመን ተሻጋሪ በሆነው ዜማና ግጥም ለአገር ቅድሚያ እንድንሰጥ ያዜመልንም ዜማ በማስታወስ ከማብቃቴ በፊት ደግሜ ‹‹አንድ አይን ያለው በአፈር አይጫወትም›› እላለሁ ሰላም!
ፍሬሕይወት አወቀ
አዲስ ዘመን ግንቦት 11/2015