በሰሜን ኢትዮጵያ የነበረው ጦርነት እልባት አግኝቶ አሁን የወደሙትን የመተካት ሂደት ላይ ነን። ከወደሙት ሁሉ የትውልድ መተኪያ የሆነው ትምህርት ቤት አንዱ ነው። ከሰሞኑም የደብተር ማሰባሰብና ሌሎች የትምህርታዊ ዘመቻ እንቅስቃሴዎች ተጀም ረዋል።
ትምህርት ቤት የሁሉም ነገር መነሻ ነው። የሰለጠነ ዜጋ የሚፈጠርበት ነው። በጦርነት ሳይሆን በሀሳብ የበላይነት የሚያምን ዜጋ የሚፈጠርበት ተቋም ነው። ስለዚህ ከምንም ነገር በላይ ለትምህርት ቤቶች ትኩረት ሊሰጥበት ይገባል።
በሰሜኑ ችግር ወቅት ጦርነቱ ብዙ ነገር እያወደመ እንደነበር ብዙዎች ብዙ ብለዋል። ችግሩ ግን አሁን ጦርነቱ እልባት አግኝቶ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን የመገንባት ዘመቻ ሲጀመር እነዚያ ‹‹ጦርነቱ እያወደመ ነው..›› ሲሉ የነበሩት አሁን የሉም።
መጀመሪያውኑም ጫጫታው ለአገርና ዜጋ የመቆርቆር ሳይሆን የመቃወም ሱስ ነበር ማለት ነው። የሚደረገውን ነገር ሁሉ መቃወም ብቻውን ደግሞ አገር አያቀናም። እዚህ ላይ ከአንድ የሥራ ባልደረባዬ የሰማሁትን አስተውሎት ልጥቀስ። ስለማህበራዊ ሚዲያዎች እያወራን ነው።
ማህበራዊ ሚዲያዎች የሀሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግር ማሰራጫ በመሆን በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ተአማኒነትን ማግኘት የቻሉት መደበኛዎቹ ሚዲያዎች ትክክለኛውን መረጃ በወቅቱ ማድረስ ባለመቻላቸውና የሕዝብ ለሕዝብ መልካም ግንኙነት ላይ ባለመሥራታቸው ነው የሚል የተለመደ ሀሳብ ነበር።
ይህ ባልደረባችን ግን ሌላ መከራከሪያ አነሳ። ማህበራዊ ሚዲያዎች (በተለይም ዩ ትዩብ) የሚሰሩት መደበኛ ሚዲያዎቹ ያልዳሰሱትን ለመዳሰስ ሳይሆን፤ ወይንም መደበኛ ሚዲያዎቹ ቆፍረው ያላገኙትን መረጃ ለሕዝብ ለማድረስ ሳይሆን… ክፍያ ስለሚያስገኝላቸው ነው። ልክ እነርሱ ሌላውን ‹‹ለሆዳቸው ያደሩ…›› እንደሚሉት ሁሉ እነርሱም ለሆዳቸው አድረው ነው ሀሰተኛ መረጃ በማሰራጨት እንጀራቸውን የሚጋግሩ።
በአጠቃላይ ደጋግመን እንዳልነው፤ መንግሥት ያሰበውን ነገር ባሰበበት ልክ መሄድ፣ ሰላምና ልማት ፈላጊ ዜጎች ከመንግሥት ጎን መቆም እንጂ ሁሉንም እናዳምጥ ከተባለ ችግር ነው። ይህ አካሄድ ዘላቂ ሰላምና ልማት አያመጣም።
ወደ ተነሳንበት ትምህርት ቤቶች መልሶ ግንባታ ስንመለስ፤ ምንም እንኳን የትኛውም አገልግሎት ሰጪ ተቋም በዚህ ዘመን የግዴታ ቢሆንም የትምህርት ቤቶች ግን የተለየ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል። ምክንያቱም ቀደም ሲል ያልነው አይነት ጨካኝና ይሉኝታ ቢስ ዜጋ የሚፈጠረው ሥልጣኔ ሲጠፋ ነው፤ ሥልጣኔ ደግሞ የሚዳብረው በትምህርት ነው። ለዕድገትም ቢሆን አምራች ዜጋ የሚፈጠረው በትምህርት ነው።
የትምህርት ቤቶች ነገር ምን ያህል አሳሳቢ እንደሚሆን እስኪ የአዲስ አበባ ጎዳናዎችን ልብ ብላችሁ ታዘቡ። መዋዕለ ሕጻናት ትምህርት ቤቶች ውስጥ መዋል የነበረባቸው ልጆች ከእናቶቻቸው ጋር ልመና ላይ ናቸው። የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ መሆን የነበረባቸው ልጆች የመንገድ ላይ ሚዛን ወይም ሌላ የሚሸጥ ነገር ይዘው ይዞራሉ። እነዚህ ልጆች ትምህርት እየተማሩ አይደለም።
በመሆኑም ተባብረን የወደሙትን ትምህርት ቤቶችን ካላስገነባን እና ለሰላም ዘብ ካልቆምን እነዚህ ልጆች ወደ ትምህርት ቤት አይመለሱም፤ እነዚህ አይመለሱም ብቻ ሳይሆን ጭራሽ ተጨማሪ የሚመጡም ይኖራሉ። ምክንያቱም እነዚህ ልጆች የመጡት (ሁሉም ባይባልም) በአካባቢያቸው ሰላማዊ እንቅስቃሴ ስለሌለ ነው። በዚህ ከቀጠለ እነዚህ ልጆች አድገው ወጣት ሲሆኑ ያልተማረ ወጣት ይሆናሉ ማለት ነው። እነርሱ ወጣት በሚሆኑበት ዘመን የዓለም ሥልጣኔ ምን ላይ እንደሚደርስ መገመት ቀላል ነው።
መንግሥትም በዚህ ጉዳይ ላይ ትልቅ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል። በብዙ የገጠር አካባቢዎች በሰፈር ሽፍቶች ምክንያት ሳይቀር ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል። ስለዚህ እነዚህ የተዘጉ ትምህርት ቤቶች ተከፍተው ሥራ መጀመር አለባቸው። ሌሎች አዳዲስ ትምህርት ቤቶችም መገንባት ይጠበቅብናል።
ትምህርት ቤቶች ለሁለት ዓመታት ያህል ተዘግተው ከቆዩባቸው አካባቢዎች አንዱ የትግራይ ክልል ነው። የትግራይ ክልል ሕጻናትና ወጣቶች አቋርጠው የቆዩትን ትምህርት እንዲጀምሩ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ርብርብ አሁኑኑ ያስፈልጋል። ምክንያቱም በአንዲት አገር ውስጥ ችግር የደረሰበት የህብረተሰብ ክፍል ካለ ችግሩ ለሁሉም ስለሚተርፍና እንደ ኢትዮጵያዊ መደጋገፍ ስለካለብን ነው። መበልጸግ የሚቻለው በአንድ አካባቢ እድገት ብቻ ሳይሆን ከሁሉም አካባቢ ያሉ ችግሮችን በመቅረፍ በሕብረት መጓዝ ሲቻል ነው።
በነገራችን ላይ ድጋፍና ርብርብ ማለት የግድ ሚሊዮን ብሮችን መስጠት ማለት ብቻ አይደለም። በሀሳብ ጉዳዩን መደገፍ ትልቅ ትብብር ማድረግ ነው። እዚህ ሁሉ ጥፋት ላይ ያደረሰን እኮ በሀሳብ መቃወም ነው። የሚደረገውን የመልሶ መገንባት እንቅስቃሴ ሁሉም አካላት ድጋፍ ቢሰጡትና ቢያበረታቱት ገንዘብ መስጠት የሚችሉት ሰዎች ድጋፍ ብቻ ይገነባዋል።
አሁን ችግር የሆነው በገንዘብና አይነት መደገፍ የሚችሉ ሰዎች ሲደግፉ በገንዘብም በሀሳብ መደገፍ የማይችሉ ሰዎች የሚፈጥሩት ውዥንብር ነው። የሚደግፈውን ሰው ማሳቀቅ፣ ሌላ የውዥንብር ዘመቻ መክፈት፣ ለእነ እገሌስ በማለት ደጋፊው በገለልተኝነት ስም እንዲተወው ማድረግ የመሳሰሉት እንቅፋት ናቸው።
መምህራንም በዚህ ወቅት ዋጋ ሊከፍሉ ይገባል። የመምህርነት ሙያ የሚታወቀው ‹‹እንደ ሻማ ቀልጦ ለሌሎች ማብራት›› በሚለው ነው። ምቾት በሌለው ነገር ውስጥ ችግርን ተቋቁሞ ማስተማር ነገ የህሊና እረፍትን ይፈጥራል።
እዚህ ላይ ከሰሞኑ ቢቢሲ በሰራው ዘገባ ትግራይ ክልል ውስጥ የታየውን እንጥቀስ። መምህሩ በጠፍጣፋ ድንጋይ ላይ እየጻፈ ሲያስተምር ነበር። ከዚህ ድርጊት ሁለት ነገር እንማራለን ማለት ነው።
አንደኛ፤ የመምህሩን ቁርጠኝነት፣ ተነሳሽነትና ለሙያው ያለውን ተገዥነት ነው። መምህሩ በድንጋይ ላይ እየጻፈ እንዲያስተምር የሚያስገድደው ህግ ባይኖርም ለሙያው ባለው ክብርና ኃላፊነት ድንጋይ ፈልጎ ልጆቹን ማስተማሩ ነው።
ሁለተኛው ደግሞ የምንማረው ችግር ብልሃትን የሚፈጥር መሆኑን ነው። መምህሩ እግረ መንገዱን የድሮ ታሪክን እያስታወሰ ትምህርት ቤቶችን ማውደም ምን ያህል አክሳሪ እንደሆነ እያሳየ ነው። ከዚህም ባለፈ ፈጠራን ለተማሪዎች እያለማመደም ነው። በችግር ጊዜ ተረጋግቶ ከታሰበ ብልሃት እንደሚወለድ ተማሪዎቹ በቀላሉ መገንዘባቸው አይቀርም።
ስለዚህ በቀጣይ ትምህርት ቤቶች ተጠግነው ወደ ሥራ ሲገቡ ሁሉም ነገር በአንድ ጊዜ ላይሟላ ይችላልና በእንዲህ አይነት ጽናትና ቁርጠኝነት ማስተማር ያስፈልጋል። ቢሮ እስከሚገኝ ዳስ እና ዛፍ ሥር ሆኖ ማስተማር ያስፈልጋል ማለት ነው። የመምህርነት ሙያ ልክ እንደ ወታደር አገር በማዳን ሕዝብን በመታደግ ለታሪክ የሚነገር ነውና በትምህርት ዘርፉ ውስጥ ያሉት ተዋናይ የመምህሩን አርአያነት ሊከተሉ ይገባል።
ይህንን ስል ምናልባት ‹‹ለተቀማጭ ሰማይ ቅርቡ ነው›› ያሰኝ ይሆናል። ምንም ይሁን ምን ግን ትምህርት ቤቶችን ወደ ነበሩበት ለመመለስ የሁላችንም ድርሻ ከፍተኛ ነውና ትውልድ ለመቅረጽ ልንረባረብ ይገባል መልእክቴ ነው !
ሚሊዮን ሺበሺ
አዲስ ዘመን ግንቦት 9/2015