ለመንደርደሪያ ያህል፤
“የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት” (Goodwill Ambassador) ጽንሰ ሃሳብ ተጠንስሶ የዳበረው በአሜሪካ ውስጥ ሲሆን ዘመኑም ከ250 ዓመታት በፊት እንደነበር የታሪክ ሰነዶች መረጃውን በዝርዝር አቆይተውልናል። እንደ ብዙ የታሪክ ዘጋቢዎች እምነት ከሆነ (አንዳንዶች የተለየ ሃሳብ አላቸው) በበጎ ፈቃድ ጀማሪነት ደማቅ አሻራቸውን በማኖር ቀደምት ፈር ቀዳጅ ከሆኑት መካከል ሀገረ አሜሪካ እንደ ሀገር እውን እንድትሆን በአዋላጅነት (Founding Fathers of the United States እንዲሉ) ታላቅ አክብሮት የተሰጣቸው ቤንጃሚን ፍራንክሊን (እ.ኤ.አ 1706 – 1790) ናቸው።
ቤንጃሚን ፍራንክሊን በዚህ አንድ ጉዳይ ላይ ብቻ ሳይሆን በበርካታ አስተዋጽኦቸው ጭምር በታሪክ ባለሙያዎች የሚዘከሩት የቀለምና የዕውቀት ቀንድ (Polymath) እየተባሉ ነው። ደራሲ፣ ሳይንቲስት፣ የአዳዲስ ቴከኖሎጂዎች ፈጣሪ፣ የፖለቲካ ፈላስፋ፣ ዲፕሎማት፣ አታሚና አሳታሚ፣ ወዘተ. ሲሆኑ፤ አዲሲቷ የዘመኑ ጨቅላ አሜሪካ ፈጥና ከዳዴነት ወደ ፈጣን እርምጃ እንድትሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ ካደረጉ ጥቂት ልጆቿ መካከል ዋናው መሠረቷ እኚህ ሰው ነበሩ። የታላቋ ሀገር ታላቅ ሰው እየተባሉ የሚጠቀሱት ቤንጃሚን ፍራንክሊን ሀገራቸው ከእንግሊዝ የጭቆና አገዛዝ አርነት መውጣቷ የታወጀበትን የነፃነታቸውን ድንጋጌ (Declaration of Independence) እና የመጀመሪያውን የአሜሪካ ሕገ መንግሥት በማርቀቅም ስማቸውን ያጻፉት በወርቅ ቀለም ነው።
እኚህ ታላቅ ባለታሪክ የበጎ ፈቃድ መልእክተኛ ሆነው ወደ ፈረንሳዩዋ ዋና ከተማ ፓሪስ በማቅናት በወቅቱ ሥር ሰዶ የነበረውን የእንግሊዝ የቅኝ ገዢነት አቅም ለማዳከም ያደረጉት ጉዞና ጥረት እንደ ሰላም መልእክተኛ ስላስቆጠራቸው “የበጎ ፈቃድ አምባሳደር” አገልግሎት መሠረት ጣይ ተደርገው እንዲቆጠሩ አስችሏቸዋል። ዝርዝር ታሪኩ ሰፋ ስለሚል ለመንደርደሪያ መነሻነት ይኼው ይበቃ ይመስለናል።
ረጅም የዕድሜ ፀጋ የተጎናጸፈው ይህ የመልካም ተግባር ተልዕኮ ለተለያዩ ዓላማዎች ማስፈጸሚያነት እየተተገበረ ዛሬ በዓለም አቀፍ ደረጃ በርካታ ሥራዎች እየተከወኑበት የዓለማችን ተቀዳሚ ተጠቃሽ መልካም የአገልግሎት መገለጫ ለመሆን ችሏል።
የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት “ክብር” የሚሰጣቸው ዜጎች በሀገራቸው ውስጥ ብቻም ሳይሆን ከሀገራቸውም ውጭ አንድም በእውቀታቸው፣ አለያም በዝናቸው፣ ወይንም በበጎ ፈጣሪነታቸው የዓለም ማሕበረሰብና የሀገራቸው ሕዝብ አርዓያ ሰብ አድርጎ በአንቱታ ያከበራቸው ግለሰቦች ናቸው። አምባሳደሮቹ በጤና፣ በፖለቲካ፣ በማሕበራዊ ዘርፎች፣ በኢኮኖሚና በበርካታ የበጎ ስራ መስኮች የላኪያቸውን ወይንም የስምሪት ሰጭያቸውን ተቋም በመወከል ተወስኖ የተሰጣቸውን በጎ ዓላማ ለማስፈጸም ቅስቀሳ፣ የማስተማርና የማግባባት ተልዕኮ የሚወጡ ባለአደራዎች ሲሆኑ የተልእኳቸው ዋነኛ መርህም ሰብዓዊነትና ገለልተኛነት ነው።
ለምሳሌ፡- የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በሥሩ ላሉት በርካታ ተቋማት የበጎ ፈቃድ መልእክተኛ አድርጎ የሚሾማቸው ግለሰቦች ከሀገራቸውም አልፈው በዓለም አቀፍ ደረጃ በሥነ ጥበባት፣ በሥነ ጽሑፍ፣ በሳይንስ፣ በልዩ ልዩ የመዝናኛ ኢንዱስትሪዎች በስፖርትና በተለያዩ ማሕበራዊ አገልግሎት አበርክቷቸው ፍሬያማ የሆኑና የሰላም መልእክተኛ ለመሆን ፈቃደኛ የሚሆኑ ታዋቂና ዝነኛ የሆኑ ግለሰቦችን ነው።
የመንግሥታቱ ድርጅት አንዱ አካል የሆነው ዩኒሴፍ በጎ ፈቃደኛ አምባሳደሮችን መሾም ከጀመረበት እ.ኤ.አ ከ1954 ዓ.ም ጀምሮ በመላው ዓለም ዓላማውን እንዲያስፈጽሙ እጅግ በርካታ ግለሰቦችን ሲያሰማራ ኖሯል። በአሁኑ ወቅትም በተለያዩ አህጉራትና ሀገሮች አምባሳደሮችን በማሰማራት ከአገልግሎቱ ጎን እንዲሰለፉ እያደረገ ይገኛል።
እኛስ በሀገራችን?
በዛሬይቱም ሆነ በትናንትናዋ ኢትዮጵያም የተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት በጎ ተጽእኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን እየመረጡ “የበጎ ፈቃድ አምባሳደር” ሹመት በመስጠት በይፋ ሲያስተዋውቁና ሲያሰማሩ ማየት እንግዳ አይደለም። ችግሩ ግለሰቦቹን ለበጎ ሥራ ሾሞ ማሠማራቱ ላይ ሳይሆን የሾማቸው ተቋም ከሚሾሙት ግለሰቦች ጋር ምን ያህል ተቀራርቦ ይሠራል? በእርግጡስ ለሥምሪት የሚረዳ መመሪያ ታስቦበትና ተጠንቶ ተዘጋጅቷል ወይ? የሚለው ይሆናል። እነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች በብዙ ተቋማት ዘንድ እየተፈጸሙ ነው ለማለት በፍጹም የሚያስደፍር አይደለም።
በርካታዎቹ ሥምሪት ሰጭ ተቋማት “አደረጉ” ለማለት ብቻ “እከሌ” የተባለውን ተጽእኖ ፈጣሪ ዜጋ ለበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት ሾሙ የሚል ዜና ካሰራጩ በኋላ ሚሽኑ ውጤታማ ያለመሆኑ ብቻ ሳይሆን፤ ማንን እንደሾሙ እንኳን የሚዘነጉ መኖራቸው የአደባባይ ምሥጢር ነው። የሀገራችንን የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት አገልግሎት በተመለከተ በአጠቃላይ ድምዳሜ ላይ ለመድረስ በአያዎ (Paradox) ባህርይው ብንመለከተው የተሻለ ይሆናል።
“አያዎ” ሁለት ተቃራኒ ቃላት የተጣመሩበትን ጽንሰ ሃሳብ የሚወክል ቃል ነው። አይ (አሉታዊ) እና አዎ (አወንታዊ) ትርጉሞችን መሆኑን ልብ ይሏል። ከዋናው የመነሻችን ሃሳብ ጋር በማያያዝ ሁለቱን ተቃራኒ ሃሳቦች እንፈትሽ። የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት አገልግሎት በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት ይታወቃል ወይ? የአገልግሎት አደራ ተሰጥቷቸው የሚሰማሩ ዜጎችስ ይኖራሉ ወይ? – መልሱ “አዎን በሚገባ” የሚል ይሆናል።
በአምባሳደሮቹ የተልዕኮ ሥምሪት የተገኘው ውጤትና ፍሬስ እንደሚጠበቀው ያበበና የጎመራ ነወይ? ብለን ጥያቄውን ብናራዝም በምናገኘው መልስ እርግጠኞች ስለማንሆንና መረጃውም በይፋ ለሕዝብ ስለማይገለጥ መልሳችን በጥርጣሬ መታጀቡ አይቀርም። ደፈር ካልንም የአምባሳደሮቹ ሹመት በሚዲያ ሲነገር እንሰማ ካልሆነ በስተቀር በውጤታማነታቸው ረገድ “አይ ዕውቀቱ የለንም” እንደምንል ለመገመት አይከብድም። ይህ ፍሬ ቢስነት አይመለከተንም የሚሉ የበጎ ፈቃድ አምባሳደሮችን ያሰማሩ ተቋማት “አለን!” የሚሉ ከሆነና እኛም መኖራቸውን እናረጋግጣለን የሚሉ ለምሥክርነት የሚቆሙ ግለሰቦችና ተቋማት ካሉ ለእነርሱ ባርኔጣችንን ከፍ አድርገን አክብሮታችንን እንገልጽላቸዋለን።
በራስ የደረሰን ገጠመኝ እያጣቀሱ ሃሳብን ማካፈል ይበልጥ ቅቡልነት ስለሚኖረው ይህ ጸሐፊ ከዚህ ሃሳብ ጋር የሚያያዘውን የራሱን ተሞክሮ እንደሚከተለው ያስታውሳል። ባለፉት ሰባት ዓመታት ውስጥ የተለያዩ ተቋማት ይህንን ጸሐፊ የበጎ ፈቃድ አምባሳደር ሆኖ እንዲያገለግላቸው ጥያቄ አቅርበውለት፤ እርሱም ጥያቄዎቹን በአሜንታ ተቀብሎ ለተጠየቀበት አገልግሎቶች ራሱን ቢያዘጋጅም፤ ገና ከጅምሩ ሳይተገበሩ የቀሩትን ፍሬ አልባ የይስሙላ ግብዣዎች የሚያስታውሰው በቁጭት ነው።
ሚያዝያ 28 ቀን 2008 ዓ.ም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምግብ፣ የመድኃኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደር ቁጥጥር ባለሥልጣን “የበጎ ፈቃድ የጤና ቁጥጥር አምባሳደር” በሚል ማዕረግ ጸሐፊው “ትውልድን ከአደገኛ ዕፆች ለማዳን በሚሠራው ሥራ ውስጥ እንዲሳተፍ ከወቅቱ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ዲሪባ ኩማ እጅ በደመቀ ሥነ ሥርዓት ታጅቦ የአደራውን ማጽኛ ሠርቲፊኬት ተቀብሎ ነበር።
ይህንን ታላቅ “ሹመት” ከተቀበለ በኋላ የሥራ ሥምሪቱ በግልጽ ይደርሰኛል ብሎ ሲጠባበቅና እርሱም በምን አቅጣጫ አሻራውን ለማሳረፍ እንደሚችል ገና ሃሳቡንና እቅዱን ሳያሳካ ተልዕኮው ለምንም እንቅስቃሴ ሳይታደል ጉዳዩ የውሃ ሽታ ሆኖ ቀርቷል። ምናልባትም የኃላፊዎች መለዋወጥ ምክንያት ሳይሆን እንደማይቀር ይገመታል። ቀድሞውንም ቢሆን ታስቦበትና በጥናት ተደግፎ ስላልተጀመረ ሊሆን ይችላል።
ሁለተኛው የአምባሳደርነት ጥሪ የቀረበለት ከትምህርት ሚኒስቴር ሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና የፈተናዎች ኤጀንሲ ይባል ከነበረው መንግሥታዊ ተቋም ሲሆን፤ ዓላማውም “በፀረ ኩረጃ” እንቅስቃሴ ላይ እንዲያተኩር ታስቦ ነበር። ይህም አደራ አንድ ሁለቴ በተዘጋጁ ፕሮግራሞች ላይ የኩረጃን አስከፊነት በተመለከተ በተቋሙ ግቢ ውስጥ የተወሰነ ገለጻና ቅስቀሳ ከመስጠት ያለፈ ውጤት ሳይመዘገብበት ተልዕኮው ከሽፎ ሊቀር ችሏል። ምክንያቱ ምን እንደሆነ ለመጠየቅ ቢሞከረም ማንም መልስ ሊሰጥ የሚችል ሰው ስለጠፋ “ሾላ በድፍን” እንዲሉ “በተከድኖ ይብሰል” ታልፎ ተረስቷል።
ሦስተኛውና በደማቅ ሥነ ሥርዓት ለአሥራ ሁለት ያህል ዜጎች የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት “ሹመት” የተሰጠው ለገቢዎች ሚኒስቴር “በታክስ አምባሳደርነት” ለማገዝ ታስቦ ሲሆን፤ የአደራውን ሠርቲፊኬት የተቀበልነውም ከክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እጅ ነበር። ይህ ሹመት የተከናወነው በአፍሪካ ኅብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውስጥ ሲሆን፤ ሥነ ሥርዓቱም በቀጥታ የሚዲያ ሥርጭት ሕዝብ እንዲከታተለው ተደርጎ ነበር።
እንደ እውነቱ ከሆነ ከቀዳሚዎቹ ሁለት ውጤት አልባ ሹመቶች ይልቅ ይኼኛውን የታክስ አምባሳደርነት ኃላፊነት አቅም በሚፈቅድ ልክ በተለያዩ መድረኮች በማስተማር፣ ለንግዱ ማሕበረስብ ግንዛቤ በማስጨበጥና በቅስቀሳ ላይ በመሳተፍ ከኅሊና ወቀሳና ከአደራ በልነት ነጻ ለመሆን ሙከራ ተደርጓል።
በአንጻራዊ መልኩም ቢሆን የዚህኛው ተቋም አገልግሎት ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል። የታክስ አምባሳደርነቱ እንቅስቃሴ በመሃሉ ተገትቶ ለዓመታት ያህል በዝምታ ሊቀዛቀዝ የቻለው የወቅቱ የገቢዎች ሚኒስትር የነበሩት ክብርት ወ/ሮ አዳነች አቤቤ የአዲስ አበባ ከንቲባ በመሆን የኃላፊነት ለውጥ በማድረጋቸው ነበር።
ከዓመታት ሽልብታ በኋላ ሚያዝያ 24 ቀን 2015 ዓ.ም የተቋሙ አዲሷ ሚኒስቴር ክብርት ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሤ እና የገቢዎችና የጉምሩክ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የየቅርንጫፉ ተወካዮች በተገኙበት በሚሊኒዬም አዳራሽ በተከናወነ ሥነ ሥርዓት ከአሁን በፊት ላገለገሉት አምባሳደሮች ተገቢው ሽኝት ተደርጎ እና አዳዲስ ለተሾሙት አምባሳደሮችም ተገቢው እውቅና ተሰጥቷቸው በአዲስ ኃይልና ትጋት ወደ ተግባር እንቅስቃሴ እንዲገቡ የሚኒስቴር መ/ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች አርአያነት ያለው ተግባር አሳክተዋል። ስለተደረገው የነባሮች ሽኝትና የአዲስ አምባሳደሮች አቀባበል ይህ ጸሐፊ ልባዊ ምሥጋናውን እያቀረበ ለአዳዲስ አምባሳደሮቹ መልካም የውጤት ዓመታት እንዲሆኑላቸው ምኞቱን ይገልጻል።
በተጓዳኝ መነሳት የሚገባው ሌላው ተሞክሮ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሥር ተቋቁሞ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ያደረገውና በአሁኑ ወቅት ተዳክሞ እንቅስቃሴው ስለተቀዛቀዘው የኢትዮጵያ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ ቡድን ይሆናል። ይህ አገልግሎት ከተጀመረ ከአሥር ዓመታት በላይ ያስቆጠረ ሲሆን የተቋቋመበት ቀዳሚ ዓላማም የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዋና አጀንዳ በማድረግ ለተፋሰሱ ሀገራት መሪዎች ሀገራችን የምታራምደውን የጋራ ተጠቃሚነት መርህ በሕዝብ ስም ለማድረስ ነበር።
በዚሁ ዓላማ መሠረትም የተሰባሰቡት የቡድኑ አባላት ዋና አጀንዳቸው የሆነውን የህዳሴ ግድብ የጋራ ተጠቃሚነት የጸና ዓላማ ለተፋሰሱ ሀገራት ለማረጋገጥ በግብጽ፣ በሱዳንና በኡጋንዳ በመገኘት ለመንግሥታቱ መሪዎችና በተዋረድም ለሚመለከታቸው አካላት በሙሉ ለማስረዳት ተሞክሯል። ወደ ጅቡቲና ወደ ኤርትራ በማቅናትም የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱን ለማጠናከር ጥረት ተደርጓል።
ወቅቱና ዘመኑ የሚያበረታታውን ይህንን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ማሳለጫ አገልግሎት አጥብቆ ከመያዝና ከማጠናከር ይልቅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስለምን በቸልታ ጉዳዩን ተመልክቶ ቡድኑ ተዳክሞ እንዲበተን እንደተፈለገ ሊገባን አልቻለም። ይህ ጸሐፊ በተለይ ለተወሰነ ጊዜ የቡድኑ ጊዜያዊ ሰብሳቢ ስለነበር ሚኒስቴር መ/ቤቱ ቡድኑን እንዲያሰባስብ ተደጋጋሚ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ ሊያገኝ ባለመቻሉ ጩኸቱ ሰሚ ሊያጣ ግድ ሆኗል። ስለዚህ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ቡድኑ ፈርሶ ከሆነ በግልጽ ለቡድኑ አባላት ተገልጾ በክብር ቢሰናበቱ፣ ካልሆነም እንደገና አገልግሎቱ እንዲያንሰራራ ቢደረግ መልካም ስለሚሆን የሚመለከታቸው የሚኒስቴሩ የሥራ ኃላፊዎች ቢያስቡበት መልካም ይሆናል።
የሆነው ሆኖ የሀገሬ የበጎ ፈቃድ አምባሳደርነት አገልግሎትም ሆነ እንደ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ ያሉ ተልዕኮዎች ቢጠናከሩ የየተቋማቱን ውጤታማነት ከፍ ሊያደርጉና በሀገሪቱ የገጽታ ግንባታ ላይም የራሳቸውን በጎ አሻራ ማሳረፍ ስለሚችሉ፤ መሰል አገልግሎቶች በተጠናና አደረጃጀቱ መልክ ባለው ሁኔታ ተዋቅሮ በጎ ተጽእኖ ፈጣሪ ዜጎች ከየሙያ መስካቸው እየተመረጡ ቢሰማሩ ፋይዳው አይሆንም፤ ላቅ ያሉ ውጤቶችም ይመዘገቡበታል፤ ይህ ጸሐፊም ይሄንኑ አጥብቆ ያምናል። ኢትዮጵያ ሆይ! በዚህ ጉዳይ ላይ መላ በይበት። ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 9/2015