በኢትዮጵያ የስነቃል ታሪክ ውስጥ ለሁላችንም ቅርብ የሆነ፣ “ካለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል” የሚል አባባል አለ:: ይህንን አባባል በዝምታቸው ራሳቸውንና ሌሎችን ሊጎዱ ዝምተኞች ማናገሪያነት ተጠቅመንበት እናውቃለን:: እየተጠቀምንበትም እንገኛለን::
ይሄን አገርኛ አባባል አሁን ላለው ወቅታዊ ሁኔታ እንዲመች አድርጌ ‹ካለመነጋገር ደጃዝማችነት ይቀራል› ስል ለውጨዋለው:: በዚህ ስነቃል ውስጥ አሁናዊቷን ኢትዮጵያ በደንብ እንመለከታለን ብዬ አስባለሁ:: በዝምታ ለተመሰረተ ፖለቲካ፣ በዝምታ ወደ ጦርነት ለሚገቡ ፖለቲከኞቻችንና በዝምታ ክብርና ማንነቱን በማጣት ላይ ላለ ህዝብ ጥሩ ማሳያ ይሆናልም እላለሁ::
እውነት ነው ካለመነጋገር ብዙ ነገር ቀርቶብናል:: እድልና በረከታችንን ጨምሮ ክብርና ልዕልናችንን አጥተናል:: እድገትና ስልጣኔአችንን ተነጥቀናል:: ባለመነጋገራችን ምን ያልሆንው አለ? ደጃዝማችነታችንን ብቻ አይደለም እንደ አገር፣ እንደ ማህበረሰብ ከፊት ሊያቆሙን የሚችሉ ኃይልና ሞራላችንን አላሽቆብናል::
ልክ እንደ ዝም አይነቅዝም አይነት ከዝምታ ጋር የተቆራኙ አባባሎች አሉን:: ዝምታ አንዳንድ ቦታ ላይ ዋጋው የማይተመን ቢሆንም አሁን ባለው የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም ግን የሚሰራ አይደለም:: ከጦርነትና ከመገፋፋት የሚያወጣን ብቸኛው መንገድ መነጋገር ነው::
ዝም ይነቅዛል፤ እንደ ዝም የሚነቅዝና የሚመረቅዝ ነገር የለም:: አፍ ካላወሩበት፣ አፍ ካልተናገሩበት ይሸታል:: አእምሮ ካልተማከሩበት፣ ተነጋግረው ካልተግባቡበት ችግር ፈጣሪ ወደ መሆን ነው የሚሸጋገረው:: በፍቅርና በመቻቻል መንፈስ አብረን ካልኖርን ሰውነት ትርጉም ያጣል::
አሁን ላይ እንደ አገር መከራ ሆነውብን እያስጨነቁንና ወደ ጦርነት እየመሩን ያሉ ችግሮች በዝምታ ያለፍናቸውና በመነጋገር መፍትሄ ያልሰጠናቸው እንከኖች እንደሆኑ ምስክር አያሻንም:: እነዚህ ችግሮቻችን በዘላቂነት መፍትሄ እንዲያገኙ ከዝምታ ወጥተን መነጋገር መቻል አለብን:: በብሄራዊ ምክክር ኮሚሽን በኩል ለአጀንዳነት ቀርበው ህዝብ ተመካክሮ መፍትሄ እንዲሰጥባቸው ዝም ያለ አንደበታችንን መፍታት አለብን::
ዝምታ ውበት ነው እያሉ የሚነግሩን ሰዎች ናቸው ነውጥ እየፈጠሩብን ያሉት:: እንዳንናገርና “ለምን?” ብለን እንዳንጠይቅ አፋችንን ይለጉሙትና በእኛ ዝምታ ውስጥ የራሳቸውን ፍላጎት ያስፈጽማሉ:: ዝም ባለ አፍ ዝንብ አይገባበትም እያሉን የራሳቸውን የተንኮል ሀሳብ ያስፈጽሙብናል::
ህዝብ መጠየቅ አለበት:: ህዝብ መናገር አለበት:: መንግስትም ህዝብ ከህዝብ ጋር፣ መንግስት ከህዝብ ጋር የሚወያዩበትን የምክክር መድረክ መፍጠር አለበት:: በመናገር ካልሆነ በዝምታ የሚፈታ ችግር የለም:: ዝም ያሉ አፎች ለሌሎች መጠቀሚያ ከመሆን ባለፈ ለራሳቸው የሚፈይዱት አንዳች ነገር የለም::
ስለአገራችን ስንል ዝምታችንን መስበር አለብን:: ፖለቲከኞች በህዝብ ዝምታ የሚያተርፉ ናቸው:: ህዝቡ ላይ የዝምታ አዚም ይለቁበትና የራሳቸውን የፖለቲካ ፍላጎት ውስጥ ውስጡን ያካሂዳሉ:: ህዝብ ያልተናገረበት ፖለቲካ ደግሞ የኋላ ኋላ ራሱን ህዝብን ዋጋ የሚያስከፍል ነው::
በሰሜኑ ጦርነት እንደ ህዝብ የተጎዳ ማንም የለም:: ፖለቲከኞች በሞቀ ቤታቸው ውስኪያቸውን እየተጎነጩ፣ እንዲህ አድርግ እንዲያ አድርግ ከማለት ባለፈ የደረሰባቸው አንዳች ጉዳት የለም:: እናም የምንናገረው ለራሳችን ስንል እንደሆነ አውቀን በአገራዊ ምክክር መድረክ ላይ በንቃት መሳተፍ ይኖርብናል::
ህዝብ በሚናገርባት አገር ላይ የፖለቲከኛ የበላይነት የለም:: አገራችን በፖለቲከኞች የአንባገነን አገዛዝ ስቃይዋ የበዛው በህዝብ ዝምታ ነው:: ህዝብ ሲናገር መንግስት ስርዐት ይይዛል:: ህዝብ ዝም ሲል ግን መንግስት መረን ይወጣል:: ፖለቲከኛ አንዳርጋቸው ጽጌ ይህንን የህዝብ ዝምታ ተንተርሶ የጻፈው አንድ መጽሀፍ አለ፣ “ህዝብ አይደናገር፣ እኛም እንናገር” የሚል::
ህዝብ እንዳይደናገር መንግስት መናገር አለበት:: መንግስት እንዳይደናገር ህዝብ ዝምታውን መስበር አለበት:: አገር ማለት የህዝብ ድምጽና የመንግስት ጆሮ ማለት ናት:: ዝም ባልን ቁጥር ራሳችንን ለፖለቲከኞች ምቹ ከማድረግ ባለፈ ጥቅም የለንም:: ዝም ባልን ቁጥር ችግሮቻችን እንዲቆጣጠሩን ከማድረግ ባለፈ አስተዋጽኦ አይኖረንም::
ትላንትና ዛሬ በመካከላችን ተፈጥረው እያተራመሱን ያሉ ችግሮቻችን እንዲረግቡ የሚናገር አንደበት፣ የሚያደምጥ ጆሮና መፍትሄ ለማምጣት የተሰናዳ አእምሮ ያስፈልገናል:: ይሄን ሁሉ ጊዜ ምክክር . . . ምክክር እያልን የምንነጋገረው የስቃዮቻችን ማብቂያ ምክክር ስለሆነ ነው::
ይሄን ሁሉ ጊዜ ስለ ብሄራዊ ምክክር የምናወራው ህዝብ የራሱን ችግር በራሱ ለመቅረፍ የተሻለ እድልን ስለሚፈጥርለት ነው:: ህዝብ ከፖለቲካ ነጻና ገለልተኛ በሆነው በብሄራዊ ምክክር ኮሚሽን በኩል የመፍትሄ ሀሳቦችን በማዋጣት አገራችን ዳግመኛ ወደ ጦርነትና ወደ ጥላቻ የማትገባበትን የራሱን የሰላምና የአንድነት መንገድ መጥረግ አለበት::
በአደናጋሪዎች ስንደናገር ኖረናል:: በራስ ወዳድ ፖለቲከኞች መከራችንን ስንበላ ኖረናል:: በሌላም በሌላ ወቅታዊና ነባር አጀንዳዎች ከከፍታችን ዝቅ ብለን እንደነበር የሚታወቅ ሀቅ ነው:: እነዚህ ሁሉ አገራዊ ችግሮቻችን በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ የእለት ተዕለት ህይወታችን ላይ እክል ፈጥረውብን ቆይተዋል::
በጊዜ ካልተገቱ ከዚህም በላይ ስጋት እንደሚሆኑብን ሳይታለም የተፈታ ነው:: አሁን ጊዜው እዛም እዚህም የተፈጠሩ ችግሮቻችንን ይዘን ወደ ህዝብ የምንቀርብበትና የጋራ መፍትሄ የምናመጣበት ነው:: ከችግሮቻችን ጋር ተቃቅፈን የምናመጣው ለውጥ የለም፤ ተነጋግረንና መክረንባቸው ድጋሚ እንዳይጎዱን ማድረግ ለነገ የማንለው ኃላፊነት ነው::
ሰጥተን የምንቀበለው የለም:: በጋራ ጉዳያችን ላይ ሰጪና ተቀባይ እኛው ነን:: ችግሮቻችን ከእኛው ወጥተው እኛኑ እንደጎዱን ሁሉ ከእኛ ወጥተው በእኛ ተፈትተው እኛኑ እንዲጠቅሙን ማድረግ የእኛ ኃላፊነት ነው:: በችግሮቻችን ላይ መንግስትን መጠበቅ ሞኝነት ነው:: በእርግጥ መንግስት የማህበረሰብ ጠባቂ እንደመሆኑ የራሱ ሚና ሊኖረው ይችላል። ሆኖም ግን እኛው ፈጥረን እኛው ባሳደግናቸው ችግሮቻችን ላይ መንግስትን ፊተኛ ማድረግ ተገቢ ነው ብዬ አላስብም::
አሁን ላለችው ኢትዮጵያ መነጋገር ከመደናገር መውጫ ብቸኛው የማርያም መንገዷ ነው:: ለዘመናት ባለመነጋገር ተደናግረናል:: ተደናግረን ወደ ጦርነትና ወደ አላስፈላጊ አገርና ህዝብን ወደሚጎዳ ድርጊት ገብተናል:: ለአደናጋሪዎች ምቹ ሆነን ስንደናገርላቸው ነበር:: ተደናግረንም የተደናገረች አገር ፈጥረናል::
አሁን መደናገር ይበቃናል:: በመነጋገር አደናጋሪዎችንም ተደናጋሪዎችንም ወደ ትክክለኛውው የሰላም መንገድ የምናመጣበት ሰሞን ነው:: ህዝብ ሲደናገር አገር ነው የሚደናገረው:: አገር ስትደናገር ትውልድ ነው የሚደናገረው:: ህዝብ አገርና ትውልድ በተደናገሩበት ሁኔታ ውስጥ የሚፈጠር ምንም በጎ ነገር የለም::
ህልሞቻችን የራቁን በተደናገረ ማንነት ውስጥ ስለፈለግናቸው ነው:: እንደ አገር ተስፋዎቻችን የራቁን በጥላቻ ውስጥ ስለሻትአናቸው ነው:: መጀመሪያ ከመደናገር እንውጣ፣ ከመደናገር እንድንወጣ አደናጋሪዎቻችንን እንወቃቸው:: አደናጋሪዎቻችንን ለማወቅ ደግሞ የጋራ ምክክርና ውይይት ያስፈልገናል::
የምክክርና የውይይት መድረክ ልዩነታችንን ትተን አንድ የምንሆንበት፣ ስለጋራ ጥቅማችን የምንሟገትበት መድረክ ነው:: በዚህ እውነት ላይ ስንገኝ ብቻ ነው ሰላማዊና የተረጋጋች አገር መፍጠር የሚቻለን::
ዝምታ ለአደናጋሪዎች እውቅና መስጠት ነው:: አለመነጋገር ለኢትዮጵያ ጠላቶች መንገድ መክፈት ነው:: ከዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ ህልምና ራዕዮቻችንን መደበቅ ነው የሚሆነው:: አገራችን በእኔና በእናንተ የኃይልና የማናለብኝነት አካሄድ ደክማለች:: ህዝቡ በፖለቲከኞች የውሸት ትርክት ተጎሳቁሏል::
ይህንን የምንሽረው በውይይት ነው:: የምንታከመው በምክክር ነው:: ጦራችንን ጥለን ለተግባቦት በነጻ አእምሮ እንቀመጥ:: ለሰላም ልባችንን እንክፈት:: ሁላችንንም የሚያግባባ አንድ ቀላል እውነት ላንሳ። ጦርነት አንድ ትርጉም ቢኖረው “አለመነጋገር” ይሆናል:: ሰላም አንድ ነጠላ ትርጉም ቢኖረው “ውይይት” ይሆናል::
እንደተረዳችሁት በሰላምና በጦርነት መካከል ያለው ልዩነት እጅግ የጠበበ የመነጋገርና ያለመነጋገር ክፍተት ነው:: ግን ይህቺ ትንሽዋ ልዩነት በምንም የማይተካ ዋጋ ነው የምታስከፍለን:: ዓለም በዚህ ትንሽ ልዩነት ዋጋ የከፈለና እየከፈለ ነው ያለው::
እስከዛሬ የከፈልነውን ዋጋ በመነጋገር ማስተካከል እየቻልን፣ ባለመነጋገራችን ተጎድተናል። ባለመነጋገር ወደ ጦርነት ስንገባ ዛሬአችንን ብቻ አይደለም ዋጋ የምንከፍለው የብዙ ነገዎቻችንንም ጭምር ነው የምንከፍለው:: ጦርነት ዛሬ ጀምሮ ነገ ቢያበቃ እድፉ በዛሬና በነገ መካከል የሚቀር አይደለም፤ ወደ ከነጎዲያም የሚሄድ ነው የሚሆነው::
እነዛ ከነገወዲያዎች ደግሞ በትላንት ጦርነት ዋጋ የምንከፍልባቸው ናቸው ማለት ነው:: ጦርነት ነገን የሚሰርቅ ሌባ ነው:: ሌብነቱ ደግሞ በአንድ ነገር ላይ ብቻ አይደለም፣ በብዙ ነገር ላይ ነው:: የአድዋ ድል መቶ ዓመታትን ተሻግሮ ዛሬም ድረስ በኩራት እንዘክረዋለን። ነጮች ደግሞ ከእኛ በተቃራኒ ዛሬም ድረስ አንገታቸውን ይደፉበታል::
ልክ እንደዚህ ጦርነት ዳፋው ዘላለማዊ ነው:: በሰሜኑ ጦርነት ኢትዮጵያ ትላንቷን ብቻ አይደለም ነገዋንም ተሰርቃለች:: በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በማህበራዊው ዘርፍ ውስጥ ከትላንት ወደ ዛሬ የተሻገረ፤ ከዛሬም ወደ ነገ የሚሄድ ይሄ ነው የማይባል ዋጋ እየከፈለች ነው::
ኢትዮጵያ ጦርነት ብዙ ትላንቶቿን ያበላሸባት አገር ናት:: ከዚህ ባለፈ ብዙ ዛሬና ብዙ ነገዎቻችንም በዛ ታሪክ የሚጠሩ ናቸው:: ጦርነት ዛሬዋን የሰረቀባት አገር ሰላም ብቻ ነው የሚበጃት:: ጦርነት ትላንቱን ያበላሸበት ህዝብ፣ ነገውን ለማቃናት አንድነት ብቻ ነው የሚጠቅመው:: በምክክር ከጦርነት የጸዳ ነገ ያስፈልገናል::
ነጋችን የሰላም እንዲሆን ዛሬ ላይ ሰላም በሚያመጡ የጋራ ጉዳዮቻችን ላይ መምከር አለብን:: በጦርነት መጠራት ውርደት እንጂ ከፍታ የለውም:: ኢትዮጵያዊነት የሚያምረው በጠላቶች ላይ በመነሳት እንጂ ከወንድም ጋር ሲገፋፋ አይደለም:: ታሪክ መስራት ከፈለግን ታሪክ ልንሰራባቸው የሚገቡ ብዙ የድህነትና የኋላቀርነት ነውሮች አሉብን፤ በእነሱ ላይ እንነሳና ታሪክ እንስራ::
መግደል ታሪክ መስራት አይደለም:: መሞትም እንደዛው ባለታሪክ አያደርግም:: ምርጡ ታሪክ የሰላም ታሪክ ነው። ምርጡ ታሪክ ይቅርታ ያለበት፣ ወንድማማችነት የበቀለበት የአብሮነት ታሪክ ነው:: ከመግደልና ከመሞት ወጥቶ ተነጋግሮና ተወያይቶ አገር መስራት ነው ባለታሪክ የሚያስብለው::
ከመግደልና ከመሞት ጋር የተያያዘ የጀግንነት ታሪካችን እዚህ ጋ መቆም አለበት:: መሳሪያ ታጥቀን ውረድ እንውረድ የምንባባልበት አሸናፊ የሌለበት የስሜት ጉዟችን እዚህ ጋ ይገታ:: በጎራዴ ፋንታ ብዕር የጨበጡ፣ በመሳሪያ ቦታ ሀሳብ የታጠቁ በውይይት . . . የሚያምኑ ነፍሶችን አገራችን ትሻለች::
ውይይት በማሰብ ለሚኖር ለሰው ልጅ የተሰጠ አንዱና ዋነኛው የመግባቢያ መንገድ ነው:: እንስሳት ሳይቀሩ ደመነፍሳዊ በሆነ ተፈጥሮ ተከባብረውና ተቻችለው በሚኖሩባት ምድር ላይ የሰው ልጅ ለዛውም ከመሰሉ ጋር ተነጋግሮ መግባባት ያቅተዋል ማለት ዘበት ነው:: ስሜትና እልኸኝነት እስካላሸነፈው ድረስ፤ አለማወቅ እስካልጋረደን ድረስ ማለት ነው::
የተቆጣጠረንን የስሜትና የራስ ወዳድነት ካባ እስካላወለቅን ድረስ ግን በሀሳባችን ጦርነትን ካልሆነ ሰላም ማምጣት አንችልም:: ከሁሉ በፊት አገር መቅደም አለባት:: አገር ያልቀደመችበት ሀሳባችን ነው ለጦርነት እየዳረገን ያለው:: ስለሰላም የማሰቢያ ጊዜ እንዳይኖረን ያደረገን ከአገር በፊት ራሳችንን የመጥቀም ልክፍታችን ነው::
ችግሮቻችን የበለጡን፣ ችግሮቻችን ዋጋ እያስከፈሉን ያሉት ከራስ ወዳድነት በጸዳ አእምሮና ልብ ስላልተነጋገርንባቸው ነው:: ችግር የሚፈታው ችግሩን በፈጠረው ጭንቅላት ሳይሆን ለመፍትሄ በተዘጋጀ ጭንቅላት ነው:: ብዙ ጊዜ ተነጋግረን የማንግባባው ወይም ደግሞ ከጦርነት ወደ ጦርነት የምንሄደው ጦርነቱን በፈጠረው ጭንቅላት ለውይይት ስለምንቀመጥ ነው::
ችግር ፈጣሪ ጭንቅላት ችግር ፈቺ ሆኖ አያውቅም:: ኢትዮጵያዊነትን ባስቀደመና ወንድማማችነትን ባስከተለ የሀሳብ ልዕልና ለውይይት እስካልተቀመጥን ድረስ በችግሮቻችን ከመበለጥ አንድንም:: ከፊታችን ባለው አገራዊ ምክክር ሰንኮፋችንን ጥለን በታደሰ ኃይል ቀና እንድንል ችግር ፈቺ ሀሳብ ያስፈልገናል እያልኩ ላብቃ::
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2015