ሀገር የዜጎቿ መልክ ናት፡፡ በተለይ እንደ አርበኞቻችን ባሉ፣ በሀገር ፍቅር ስሜት በተነኩ ነፍሶች በኩል ሲሆን ትርጓሜው ለየት ይላል፡፡ ከዚህ እውነት በመነሳት ኢትዮጵያና ጀግንነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው ማለት እንችላለን፡፡ ልክ እንደ እጅና ጓንት፣ ልክ እንደመዳፍና አይበሉባ ከዘመን ዘመን፣ ከትውልድ ትውልድ ስማችን በኩራት ሲጠራ ቆይቷል፡፡ አርበኝነት ከታሪክነት ባለፈ በእያንዳንዳችን ነፍስ ላይ የበቀለ የኢትዮጵያዊነት አለላ መልክ፤ ብዙ ትላንትናዎችን የፈጠረ የዘመን ቀለማት ነው፡፡
ለዚህ ደግሞ በተለያየ ጊዜ በጠላት ላይ በወሰድንው የበላይነት ያስመዘገብናቸው አኩሪ ብሔራዊ ድሎች ምስክሮች ናቸው፡፡ ከእነዚህ እሙን የታሪክ ድርሳናት ውስጥ አርበኞቻችን ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ፡፡ የትላንቷ ኢትዮጵያ የዛሬዋም መልካም ምድር በአርበኞቻችን እንባና ደ ም የተቀለመች ናት፡፡
አገራችን ሲነኳቸው በሚቆጡ፣ ሲደፍሯቸው በኅብረት በሚነሱ ጥቁር ሕዝቦች የጸናች ናት። በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በወርቅ ቀለም ከተጻፉ ክቡር ስሞች ውስጥ “አርበኛ የሚለው ቃል ቀዳሚው ቃል ነው። በዘመናት የጥቁሮች ታሪክ ውስጥ ፋና ወጊ ሆኖ ዛሬም ድረስ በክብር ይጠራል፡፡ ከአፍሪካ አልፎ በዘመናዊው የአውሮፓ ሥልጣኔ ውስጥ የኃያላኖቹ የእግር እሳት ሆኖ ዛሬም ድረስ አለ፡፡ የቆምንው በዚህ ታላቅ እውነት ላይ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ያቆማት ይሄ ታላቅ ተግባርና ስሟ ነው፡፡
ለአፍሪካም ሆነ ለዓለም ፋና ወጊዎች ሆነን ቀደምት ሥልጡን ሕዝቦች በመባል የምንጠራው በሀገራቸውና በርስታቸው ቀልድ በማያውቁት አባቶቻችን ደምና አጥንት ነው፡፡ ከትላንት እስከዛሬ ለሀገርና ሕዝብ ክብር ሲሉ ራሳቸውን እንደ ሻማ ያቀለጡ በርካታ አባቶች አሉን። ርስቴን አልሰጥም፣ የሀገሬን ዳር ድንበር አላስነካም ሲሉ የሞቱ፣ የተንገላቱ ብዙ የሀገር ባለውለታ አርበኞች በትላንትና በዛሬ ውስጥ አሉ፡፡
እኔና እናንተም የእነዚህ ባለውለታ አርበኞቻችን የደም ፍሬ ነን፡፡ የዛሬዋ ኢትዮጵያ በዚህ ልክ በዓለም አቀፍ ደረጃ ጎልታና ታፍራ እንድትታይ ያደረጉት እነሱ ናቸው፡፡ በዓድዋና በካራማራ፣ በኦጋዴንና በአምባላጌ ታላቅ ገድልን በመፈጸም የማይሞትና የማያረጅ ዘላለማዊ ክብርን የሰጡን ባላደራ ትውልዶች ነበሩን፡፡
ቋያ በታጠቁ ጥቁር ክንዶች፣ ጽናት ባነገቱ ሕያው ነፍሶች ከባርነት ወጥተናል፡፡ ዘመን በማይሽረው የአርበኝነት ተጋድሎ ብዙ የጠላት ወረራዎችን በድል አልፈናል፡፡ በአባቶቻችን ደም፣ በአርበኞቻችን አጥንት በዓለም ላይ ታላቋን የነጻነት ምድር ኢትዮጵያን ፈጥረናል። እናም ብኩርናችን በሆነው የአንድነትና የወንድማማችነት ስም ቀጣይዋን ባለታሪክ ሀገር ለመፍጠር የአባቶቻችን የፊተኛነት ዳና እንደሚያስፈልገን እሙን ነው፡፡
ክብራችን ሳይጎድል፣ ነጻነታችን ሳይነካ ዳር ድንበራችን ሳይደፈር ከትላንት እስከዛሬ በክብር የምንጠራው ነፍሳቸውን ለሀገር በሰጡ አባቶቻችን ሞት ነው እያልኩ ነው፡፡ ሁላችንም የሞት ፍሬዎች ነን፡፡ የዛሬው እኛነታችን በዚህ ልክ የተገኘው ሞት በተከፈለበት የዛኛው ትውልድ ጀብድ ነው፡፡ ጀብዱ የሚቆም አይደለም፤ በዚህኛውም ትውልድ የሚደገም የውርስ ጀብድ ነውና፡፡
በአባቶቻችን ደም የበቀልን በአጥንታቸው የታፈርን የበርካታ ተጋድሎዎች ውጤቶች ኅብር ነን። ብዙዎች በሚናፍቁት ማንም በሌለው ሀገራዊ ታሪክ ውስጥ የምንኖር ሕዝቦች ነን፡፡ በታላቅ ክብርና ሞገስ ከትላንት እስከዛሬ ተራምደናል፡፡ ለኢትዮጵያ ክብርና ነጻነት ደማቸውን ባፈሰሱ እውነተኛ የሕዝብ ልጆች ከጭቆና ወተን አንገታችንን ቀና አድርገናል፡፡
ኢትዮጵያን ተባብረው በገነቧት ጽኑ ክንዶች ታቅፈን ወደ እሚደነቅ ብርሃን ተሸጋግረናል፡፡ በአባቶቻችን ብዙ ሞትና መከራ አርነት ወጥተን ስማችንን በታሪክ ድርሳን ላይ በወርቅ ቀለም ጽፈናል፤ ክብር ለዛኛው ትውልድ ይሁንና፡፡ ይሄን በመሰለው የታሪክ ዓውድ ስር ከእኛስ ምን ይጠበቃል? የሚል ጥያቄ መነሳቱ ግድ ነው፡፡ መጪው ትውልድ ከአባቶቻችን ገድል እኩል የእኛንም ገድል ገልጦ እንዲያነብ እና ታሪክ ሠሪ እንዲሆን የጀግንነት ሰርጥ ልንሰጠው ይገባል፡፡
ከእውነት ሁሉ እውነት ሀገር ናት፡፡ ሀገር የሁላችን ክብር ናት፡፡ የደስታችን አጥቢያ የኅዘናችን መድረሻ ናት። ስለ ሀገር አባቶቻችን ያስተማሩን እውነት ይሄ ነው። ከታላላቆቻችን የሰማንው፣ ከፊተኞቻችን ያወቅነው ጥበብ ይህ ነው፡፡ በነፍሶቻችን ላይ የአባቶቻችን የአደራ ቃል አለ፡፡ ይሄን የአደራ ቃል ይዘን ነው የምንኖረው፡፡
አርበኝነት በእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ ያለ። ከእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ደም ውስጥ የሚቀዳ የሉዓላዊነት ድንበር ነው፡፡ የእያንዳንዳችን ትላንት፣ የእያንዳንዳችን ዛሬና ነገ በአርበኞቻችን ሞት የተገኘ ነው፡፡ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን እንደ ድርና ማግ ፈትለውና ሸምነው በትውልድ ልብ ውስጥ የቋጩት፣ የዚያኛውም ዓለም ጀብደኛ ነፍሶች ናቸው፡፡
በእነዚህ ነፍሶች ውስጥ መኖር ለሀገርና ሕዝብ የሚከፈል የዜግነት ግዴታ ይመስለኛል፡፡ በነዚህ ነፍስ ውስጥ መኖር ራስን ለሌሎች ሕልም ገምሶ እንደመስጠት እቆጥረዋለሁ፡፡ በአባቶቻችን ደጋግ ነፍሶች ዛሬ እኔና እናንተ ወልደን ከብደን እድሜ ቆጥረናል፡፡ ብርቱ ሕዝብ፣ ሥልጡን ሀገር ተብለን በዓለም አደባባይ ተመስክሮልናል።
ነገ ለሚፈጠረው አዲስ ትውልድ ደግሞ እኔና እናንተ እናስፈልጋለን፡፡ በአባቶቻችን ሐቅ እንደኖርን ሁሉ በእኛም ሐቅ የሚኖር ትውልድ ይመጣልና ራሳችንን ለኃላፊነት ማዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ አባቶቻችን በዚህ ልክ ባይኖሩ ኖሮ አሁን ላይ እኛ በዚህ ልክ አንገኝም ነበር፡፡ አባቶቻችን ለእኛ እንዳስፈለጉ ሁሉ እኛንም የሚፈልግ ትውልድ ይመጣልና አስፈላጊ ዜጋዎች ሆነን መቆም የዜግነት ግዴታችን ነው፡፡
በአባቶቻችን መኖር ኖረናል፡፡ በተስፋቸው ለምልመናል፤ በእውነታቸው ደምቀናል። አሁን ሌሎችን የማኖር የእኛ ተራ ነው፡፡ ተነጋግሮ በመግባባት ለሌሎች የምናስፈልግበት፣ ለሌሎች የምትሆን ምቹ ሀገር ለመፍጠር የአርበኝነት ሥራ የምንሠራበት ሰዓት ላይ ነን። ዛሬ መልካም ነገር ለመሥራት ከቀኖች ሁሉ ትክክለኛው ቀን ነው፡፡
በዚህ ቀን ላይ መልካም ሥራ በመሥራት በእኛ በኩል ለሚመጣው አዲስ ትውልድ ስንቅ ለመሆን መነሳት ይጠበቅብናል፡፡ የእኛ ዛሬ በአባቶቻችን የተፈጠረ ነው፡፡ የልጆቻችንም ነገ በእኛ መልካም ዛሬ የሚፈጠር ይሆናል። የሀሳባችን መልካም መሆን ለራሳችን ብቻ ሳይሆን በዙሪያችን ላሉም በረከትና መልካምነትን ነውና ሁሉን ነገር ከሀሳብ እንጀምር። ሕልምና ራዕያችን ለሌሎች እንዲጠቅምና እንዲበጅ አድርገን እናዘጋጀው፡፡
አባቶቻችን የኢትዮጵያ የትላንት ብሩህ መልኮች ነበሩ፡፡ አርበኞቻችን ለእያንዳንዳችን ደማቅ ዛሬ የሞት ዋጋ የከፈሉ የመልካም ልቦች ባለቤት ነበሩ፡፡ ሁላችንም ለሁላችን እናስፈልጋለን፡፡ አወቅንም ሳትንም አስፈላጊዎች ሆነን ነው ወደ ምድር የመጣነው። በአባቶቻችን የአርበኝነት ተጋድሎ ዛሬ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ተፈጥረዋል፡፡ ነገ ደግሞ በእኔና በእናንተ የአርበኝነት ተጋድሎ የሚፈጠር ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ይኖራል። ከእኛ በኋላም ያለው ትውልድ እርስ በርሱ የሚደጋገፍ ነው የሚሆነው፡፡ ደምቀው የተጻፉ ብዙ ትላንትናዎች በእያንዳንዳችን ዛሬ ውስጥ አሉ፡፡
ለሕይወታችን እጅግ አስፈላጊ ሆነው አጠገባችን የቆሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ለመኖራችን ብርታት ሆነው በትላንትና በዛሬአችን ውስጥ የበቀሉ ደጋግ ነፍሶች ስለመኖራቸው አልጠራጠርም፡፡ ይህን እውነት ወደ ሀገርና ሕዝብ ስናመጣው አርበኞቻችንን እናገኛቸዋለን። አርበኞቻችን የእኔና የእናንተ የጋራ እውነት ናቸው፡፡ እውነታቸው ከእኛ አልፎ ወደ ልጅ ልጆቻችን እንዲሸጋገር በተራመዱበት የአንድነትና የወንድማማችነት መንገድ ላይ መቆም ያሻናል፡፡
በዓለም አደባባይ ብዙዎች አንገታቸውን ቀና ማድረግ ተስኗቸው አቀርቅረው በሚኖሩበት በዚህ ዘመን ቀና ብለን እንድንራመድና ማነህ ስንባል “ኢትዮጵያዊ!!!” ነን ብለን በኩራት እንድንናገር ያደረጉን እነሱ ናቸው፡፡ በጥቁርነት ውስጥ ዘለዓለማዊ ክብርን፣ ዘለዓለማዊ ነፃነትን ያጎናጸፉን በዛኛው ትውልድ ማሕጸን ውስጥ የበቀሉ አርበኞቻችን ናቸው፡፡
ዛሬ በሀገራችን ላይ ጀብድ ለመሥራት የእኔና የእናንተ ተራ ነው፡፡ ዛሬ የእኔና የእናንተ የድል የተስፋ ቀን ነው፡፡ ታሪክ ከማውራት ወጥተን ታሪክ የምንሠራበት ዘመናችን ነው፡፡ እንደሚታወቀው ሀገራችን ኢትዮጵያ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በብዙ ችግርና መከራ ውስጥ የምትገኝበት ሰዓት ላይ ናት፡፡
ከትላንት በባሰ የእኛን አንድነት የእኛን አብሮነት የምትፈልግበት የችግር ጊዜ ላይ ናት፡፡ ከውስጥም ከውጪም ጠላቶች ተነስተውባታል፡፡ አንድነቷን ኅብረቷን ለመሸርሸር የተንኮል ሴራዎችን የሚያሴሩ ግለሰቦች፣ ቡድኖች፣ ሀገሮች ሳይቀሩ የተነሱበት ጊዜ ነው፡፡ እንደ አባቶቻችን ትውልድ የማይረሳውን የጀግንነት ተግባር ፈጽመን ለማለፍ ትክክለኛው ሰዓት ላይ እንገኛለን፡፡
ከእኔነት ወጥተን ለሀገራችን ምርጥ ምርጡን ለማድረግ በአንድነት የምንቆምበት የተጋድሎ ጊዜ ላይ ነን፡፡ አባቶቻችን በዓድዋ ጣሊያንን በካራማራ ሶማሌን እንዲሁም በሌሎችም የጦር ግንባር ዘምተው በአርበኝነት በርካታ ድሎችን በማስመዝገብ ዛሬ ላለችው ኢትዮጵያ ምሳሌ ሆነዋል፡፡ እኛም ነገ ለምትፈጠረው አዲሷ ሀገርና አዲስ ትውልድ የሚሆን አኩሪ ሥራን የምንሠራበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ እንደ አባቶቻችን የኢትዮጵያውያን ደማቅ ቀለሞች ሆነን ስማችንን ከትውልድ አብራክ ውስጥ እንጽፍ ዘንድ ዛሬ የእኛ ቀን ነው፡፡ ሀገራችን በውስጥም በውጪም እዬዬ እያለች ነው፡፡
ብዙ እንባዎች፣ ብዙ ዋይታዎች የሚሰሙበት ሰሞን ላይ ነን፡፡ የሕዝቦች በአንድነት መቆም ግድ የሚልበት የጭንቅ ሰዓት ላይ ነን፡፡ በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በማኅበራዊው ሕይወታችን ውስጥ ሀገራችን የእኛን አርበኝነት የምትፈልግበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ አሁን ለሀገራችንም ሆነ ለሕዝባችን ምርጡን የምንሠራበት ምርጥ ወቅት ላይ እንገኛለን። ኢትዮጵያን እወዳለሁ የሚል ሁሉ ከወሬ ባለፈ በተግባር የሚፈተንበት ጊዜ ነው፡፡
እኔ የሀገሬ ለቅሶ ይሰማኛል፡፡ እንድረዳት በእናታዊ አሳዛኝ አይኖቿ ስታየኝ አያታለሁ፡፡ የሀገሬ በአንድነት ተነሱ ድምፅ ይሰማኛል፡፡ የኢትዮጵያ ሕመም የእያንዳንዳችን ሕመም ነው፡፡ በመከራዋ ውስጥ መከራችን አለ፡፡ ዛሬውኑ እንዳባቶቻችን በአንድነት በመቆም ሀገራችን ችግር እልባት መስጠት ይኖርብናል፡፡
አብዛኞቹ ችግሮቻችን አንድነትን፣ ሕዝባዊነትን የሚሹ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መፍትሔዎች ደግሞ በእኔና በእናንተ እጅ ውስጥ ናቸው፡፡ እኔና እናንተ በአንድነት ከቆምን ችግሮቻችን ሁሉ እሳት እንዳየው ቅቤ ቀልጠው እንደሚጠፉ ጥርጥር የለኝም፡፡ የእስካሁኑ ችግሮቻችን ከአንድነት ማጣት፣ ከመለያየት የመጡ ናቸው። ባለመነጋገር፣ ባለመደማመጥ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ መለያየታችን የፈጠራቸው ችግሮቻችን ናቸው ዛሬ ላይ በየቦታው መከራ ሆነው የሚያሰቃዩን።
አርበኛ ለመባል የግድ ጦር ሜዳ ሄደን መዋጋት አይጠበቅብንም፡፡ አርበኛ ለመባል ጦርና ጎራዴ ወይም ደግሞ መሣሪያ መታጠቅ አይኖርብንም። በብዕራችን መልካም ነገር በመጻፍ አርበኛ መሆን እንችላለን። በተግባራችን አስፈላጊዎች በመሆን ታሪክ መሥራት እንችላለን፡፡ በእያንዳንዱ ሀገራዊ ችግር ላይ በነቃ ተሳትፎ መፍትሔ በማምጣት የዚህኛው ትውልድ አርበኛ መሆን እንችላለን፡፡
እንደ ሀገር ለሚነሱብን አፍሪካዊም ሆነ ዓለም አቀፍ ተቃውሞዎች በአንድነት በመቆም ጀብዱ መሥራት እንችላለን፡፡ በተሠማራንበት የሥራ መስክ ላይ ሀገርና ሕዝብ የሚጠቅም አመርቂ ውጤት በማምጣት አርበኛ መሆን እንችላለን፡፡ ጥሩ ነገር በመሥራት፣ መልካም ነገር በማሰብ፣ በዙሪያችን ላሉ አስፈላጊዎች ሆነን በመቆም . . . አርበኛ መሆን ይቻላል፡፡
መልካም ሥራ ለመሥራት ከተዘጋጀን ጀብድ ልንሠራባቸው የምንችልባቸው በርካታ ሀገራዊ ጉዳዮች አሉ፡፡ ችግሩ ግን ካበደው ጋር ማበድ፣ ድንጋይ ካነሳው ጋር ድንጋይ ማንሳታችን ነው። ሀገራችን በአስተሳሰባችን ውስጥ ናት፡፡ ከቆሻሻ አስተሳሰብ ወጥተን ወደ’ሚደነቅ ብርሃናዊ እውነት መምጣት ይኖርብናል፡፡ አብዛኞቻችን ታሪክ ከመሥራት ይልቅ ታሪክ በማውራት የምንኖር ነን፡፡ ዛሬ ላይ ታላቅ ነገር ለመሥራት ከመሞከር ይልቅ በአክሱምና ላሊበላ እየተደነቅን ስራ ፈ’ተን የምንቀመጥ ብዙዎች ነን። ትልቅ ለመሆን ከመጣር ይልቅ ትልቅ ነበርን ብለን ያለፈን በማውራት ጊዜ የምናጠፋ ሁሉ ነን፡፡
ትልቅ ነገር ለመፍጠር ከተዘጋጀን ይቻለናል። አባቶቻችን ባልዘመነና ባልሰለጠነ ዘመን ነው ዓለምን ጉድ ያስባለ ታሪክ የሠሩት፡፡ እኛም የዛሬዎቹ ትውልድ በብዙ ነገሩ ምቹና ስልጡን በሆነ ዘመን ላይ ነን። ለሕዝባችንም ሆነ ለሀገራችን ታሪክ ለመሥራት ከመቼውም ጊዜ በላይ ምቹ ዘመን ላይ ነን፡፡ የአባቶቻችንን ወኔ ለብሰን ላሉብን ሀገራዊ ችግሮች መፍትሔ በማምጣት የዜግነታችንን እንድንወጣ በማሳሰብ ላብቃ፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 7 ቀን 2015 ዓ.ም