የዓለምን የፖለቲካ ሽኩቻ ከቀየሩና ተጠያቂነትን ካሰፈኑ የፖሊሲ ሥርዓቶች አንዱ ከላይ ለርዕሴ የመረጥኩት ጽንሰ ሀሳብ ነው። ጽንሰ ሀሳቡ በታማኝነትና በፍትሐዊነት፤ በተራማጅ እሳቤም ሰብዓዊነትን መሠረት አድርጎ የሚንቀሳቀስ ሲሆን በዋናነት ወንጀለኞችን ለፍርድ የሚያበቃ፤ ተበዳይን ደግሞ ለበደሉ የሚመጥን ካሣና መጽናናትን የሚሰጥ ነው።
በኢትዮጵያ ለሰብዓዊ መብቶች መከበርና ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ተግባራዊነት ከመቼውም ጊዜ በላይ አስፈላጊ እንደሆነ በተለያዩ የመንግሥት አካላት መገለጹ ይታወሳል፤ እየተገለፀም ነው። የሰሜን ኢትዮጵያን ጦርነት ጨምሮ ባለፉት አራትና ከዛ በላይ ዓመታት ውስጥ የነበሩ፣ ማንነትን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች የሽግግር ፍትሕን አስፈላጊነት ያጎሉ እንደነበሩ የፍትሕ ሚኒስትሩ ዶክተር ጌዲዮን ጤሞቲዎስ መግለጻቸው አይዘነጋም።
ያሉብን ወቅታዊ እና ሀገራዊ ችግሮች ፍትሕ የሚሹ መሆናቸው ግልጽ ነው። በተለይ በሰብዓዊነት ላይ የደረሱና እየደረሱ ያሉ የሕግ ጥሰቶች፣ በተለይ ማንነትን መሠረት ያደረጉ ሕዝባዊ ጥቃቶች በዳይና ተበዳይን ለሕግ በማቅረብ ረገድ አፋጣኝ መፍትሔ የሚሹ ናቸው።
እንደ ሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዓላማና እቅድ በንግግር የሚፈቱ፣ በእርቅ የሚቋጩ በካሣና በተጠያቂነት እልባት የሚያገኙ ሀገራዊ ችግሮች አሉ። የሁሉም ሂደት ፍጻሜ ፍትሐዊነት መሆኑ አጠያያቂ ባይሆንም ጎን ለጎን አብረው የሚመጡ የአንድነት እና የእኩልነት መንፈሶችም በዚህ ሂደት የሚታዩ ናቸው።
እንደ ባለሙያዎች አስተያየት፣ የሽግግር ፍትሕ አራት ዓላማዎች አሉት። በእኚህ ሁሉን አቀፍ ዓላማዎቹ በኩል ነው ተጨባጭ ለውጥን ሊያመጣ የሚችለው። የመጀመሪያው እውነትን መፈለግና ማወቅ፤ መረዳትም ነው። ለየትኛውም ፍትሕ ቀዳሚ መስፈርት ሆኖ የሚያገለግለው እውነት ነው። ከእውነት ተነስተን ነው ፍትሕ ሊያመጡልን ወደ’ሚችሉ፣ ወደ ሌሎች ደረጃዎች የምንሸጋገረው።
ሁለተኛው የተጎዱ ግለሰቦችን፣ አካባቢዎችን መልሶ ማቋቋም ነው። የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲን በተመለከተ ይሄ ፍትሕና ተጠያቂነትን ለማምጣት ሁለተኛው እርከን ነው። በመረጃና በዓይን እማኝ አማካኝነት በተደረሰ እውነት ላይ ተንጠራርተን የሰብዓዊ ጥሰት የደረሰባቸውን ወገኖች ልንታደግ የምንችለው በዚህ ዓይነቱ ሂደት ነው።
ሦስተኛው የሽግግር ፍትሕ ዓላማ የወንጀል ተጠያቂነትን ማስፈን ነው። በእውነት በተመራ አቅጣጫ ሰብዓዊነት ላይ ቆሞ የወንጀል ተጠያቂነት ላይ ይደርሳል። ምንም አሻሚ ነገር የለውም። ሂደቱ በራሱ ቅልብጭ ያለና ለፍትሕ መንገድ የሚጠርግ ሆኖ እናገኘዋለን።
አራተኛውና የመጨረሻው የዓላማ ሂደት ደግሞ ተመሳሳይ ነገር እንዳይከሰት ምን አይነት ለውጥና ማሻሻያ ያስፈልጋል? የሚለው ነው። ይህ እንግዲህ የሕግ ማሻሻያ ወይም የፖሊሲ ለውጥ ሊሆን ይችላል። ከዚህ ባለፈ እውቀትና ምክንያታዊነትን ባስቀደመ መልኩ የምክክርና የተግባቦት ሂደት ላይ ሊመሠረት ይችላል።
በእነዚህ አራት ዓላማዎች መካከል ወሳኝ የሚባል ነገር የለም። አራቱም ወሳኝ ሆነው ለውጥ የሚያመጡ ዓላማ ማሳኪያዎች ናቸው። የሚጠበቀውን አስተማማኝ የፍትሕና የተጠያቂነት ለውጥ ለማስፈን አንዱ ከአንዱ መቆራኘት ይጠበቅበታል። ከእውነት ወደ ሰብዓዊነት፤ ከዛም ወደ ተጠያቂነትና “ቀጣይ ምን ይደረግ?” ወደ’ሚል ተጠየቅ የተሸጋገረ የዓላማ ሂደት ነው ሊታደገን የሚችለው።
ልዩነት ውበት የመሆኑን ያክል አንዳንዶቻችን ለንትርክ እንጠቀምበታለን። ውበት ያደረጉት በብዙ አጊጠውበታል። ልዩነት ያደረጉት እንደዚሁ በብዙ ከስረውበታል። የሆነው ሆኖ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ልዩነታቸውን ለነውጥ በተጠቀሙ ግለሰቦችና ቡድኖች ፖለቲካና ፖለቲከኞች ውስጥ ገብቶ በሰብዓዊነት ላይ ጉዳት ያደረሱን የሚሞግት የፍትሕ ውሀ ልክ ነው።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዓለም አቀፍ እውቅና ያለው ከትላንት ወደ ዛሬ የተሻገረ ሞጋች የፍትሕ ሚዛን ነው። ከነባሩ የፍትሕ አካሄድ ጎን የቆመ ግን ደግሞ በተለየ ሁኔታ እውነት እና ፍትሕን ይዞ ለጭቁኖች የሚወግን የሽግግር ፖሊሲ ነው። ከቃሉ እንደምንረዳው የፍትሕ ፖሊሲው ሽግግር ነው። ከጦርነት ወደ ሰላም፣ከሰላም ወደ ተጠያቂነት፣ ከተጠያቂነት ወደ ካሣ የሚደረግ ሽግግር።
የነበሩና ያሉ ሀገራዊ ችግሮችን እያጠራ ወደ ሰላም የሚወስድና አንድነትን የሚፈጥር ሁሉን አቀፍ ተልዕኮ ነው። ዓለም ላይ ሁሉም ሀገራት በሚባል ደረጃ በሽግግር ፍትሕ ጸንተው የቆሙ ናቸው። እንደ ሀገርና እንደፖለቲካ ሥርዓቱ ሁሉም ሀገር የራሱ የሆነ ችግርና መከፋፈል ይኖረዋል።
በዚህ ሳያበቃ ፖለቲካው በወለዳቸው እንከኖች የሚሰቃዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ይኖራሉ። ይሄ ብቻ አይደለም ዘርና ብሔር እየተቆጠረ መርጦ ባልተወለደበት ማንነቱ እየተለየ የሚቀጣ ይኖራል። በዚህም ሳያበቃ በጦርነትና በእርስ በርስ ግጭት የተጎዱ ዜጎች ይኖራሉ። እነዚህ ሁሉ ከዋናው የፍትሕ ሥርዓት ባለፈ ፍትሕ የሚያገኙት በሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ በኩል ነው።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ መሠረቱ ከዲሞክራሲ ግንባታ ጋር አብሮ ነው። በተለይ የሁለተኛውን የዓለም ጦርነት መገባደድ ተከትሎ በሰብዓዊነት ላይ ለሚደርሱ ፖለቲካዊ ግፎች ተጠያቂነትን ለማስፈር ከየትኛውም ጊዜ በላይ ሩቅ ተጉዟል።
ፖለቲካ ከሀገር ለሀገር ነው። ይሄን እውነት የሳቱ፣ ጽንፍ የረገጡ ፖለቲከኞች ራሳቸውን ለመጥቀም ሲሉ የሚሄዱበት ከሥርዓት ያፈነገጠ አካሄድ ሀገርና ሕዝብን ጎድቶ ያውቃል። ከፍ ሲልም በብሔርና በጎሳ እየተቧደኑ በፖለቲካ አለመግባባት የተፈጠሩ ችግሮች የሰውን ልጅ ለዘመናት አስቃጥቶታል።
ከሀገራት ልምድ እንደምንገነዘበው፣ ከውስን ቡድኖች የመነጩ፣ እነዚህን መሰል ያልተገቡ አካሄዶች እንዲከሽፉና ተጠያቂነት እንዲኖር የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ የአንበሳውን ድርሻ ሲወስድ ቆይቷል። መጪው ጊዜ የሰላምና የአንድነት እንዲሆን ችግሮች በእርቅና በምክከር፣ በውይይትና በተግባቦት እንዲፈቱ የመሠረት ድንጋይ ሆኖ የሠራና እየሠራ ያለ ሰላም መር አስተሳሰብ ነው።
የሽግግር ፍትሕ ጣልቃ ገብነት ማንንም ሲጎዳ አልታየም። በውጪ ሀገራት ጣልቃ ገብነት የሚታይ ሳይሆን የዛን ሀገር ሕግና ደንብ ተከትሎ የሚሠራ ነው። በሌላ መንገድ በሥርዓት ለሥርዓት የሚሠራ የሕግና የደንብ ውጤት ነው። የሚፈራ ከሆነ ሊፈሩት ከቻሉ ወንጀለኞች ብቻ ናቸው የሚፈሩት። ምክንያቱም ወንጀለኞችን ተጠያቂ ለማድረግ የሚሠራ ስለሆነ።
በሀገራችን ባለፉት ጊዜያት አቅም ሆነ በቅርቡ በተካሄደው የሰሜኑ ጦርነት ጎጂና ተጎጂ መኖሩ የማያጠያይቅ ቢሆንም፣ ከዚህ ወዲያ ፍትህ የሚፈልጉና እውነት የራቃቸው የማኅበረሰብ ክፍሎች ስለመኖራቸው እሙን ነው። ለእንዲህ አይነቱ ፖለቲካ ወለድ ችግርና ድምጽ አጥተው ድምጻቸው ለተዋጠባቸው የማኅበረሰብ ክፍሎች የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ መፍትሔ ነው።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ የሥርዓት ሕግ ነው። አይቶና መዝኖ ፈትሾና አረጋግጦ ለፍትሕና ለተጠያቂነት በሩን የከፈተ፣ ሁሉን አቀፍ ጽንሰ ሀሳብ ነው። በተለይ እንደ እኛ ሀገር ላሉ፣ በዘርና በብሔር ለተቧደኑ ተቧድነውም ላላበቁ በብኩርና ለሚጋፉ የሥልጣን ጥመኞች ደንበኛ ማስታገሻ ነው።
ከበርካታ ውጣ ውረዶች በኋላ፣ ዓለም ሰንኮፏን ጥላ በአዲስነት ቀና ያለችው እንዲህ ባለው የሽግግር ፍትሕ እሳቤ ነው። ዩጎዝላቪያና ቺሊ የዚህ ሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ተቋዳሽ ሀገራት ናቸው። አፍሪካ ውስጥም ተመሳሳይ ነገር መኖሩን እንደ ሩዋንዳና ደቡብ አፍሪካ ባሉ ሀገራት መረዳት ይቻላል። በአፍሪካ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ እሳቤ በበረታ መንገድ መቀንቀን የጀመረው የነጮችን የቅኝ ግዛት ተልዕኮ ታኮ ነው።
በተለይ በቅኝ ግዛት ወቅት በነበረውና ከዛ በኋላም በተፈጠረው የነጮች የበላይነት የፈጠረው የመብት ጥሰትና የሰብዓዊነት እንግልት እንዲሁም ደግሞ እንደ ሩዋንዳ ባሉ፤ በዘርና በብሔር የማንነት ጥያቄ በተነሳባቸው ሀገራት የሽግግር ፍትሕ ባለውለታ አልነበረም ማለት አይቻልም።
የሩዋንዳ የዘር ፍጅት በሽግግር ፍትሕ ነው የተቋጨው። በደቡብ አፍሪካ የአፓርታይድ ሥርዓት ማብቂያ ከማግኘቱም ባለፈ የሰብዓዊ ጥሰት የፈጸሙ አካላት በዚህ የሽግግር ፍትሕ በኩል ተዳኝተዋል። ቺሊና አንዳንድ የላቲን አሜሪካ ሀገራት ይሄን መንገድ በመምረጥ ተበዳይን በመካስ፣ በዳይ ለፍርድ የሚቀርብበትን ሂደት ሥራ ላይ አውለዋል።
በቀላል አማርኛ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ “የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ” ልንለው እንችላለን። የዲሞክራሲ ግንባታ ሂደት ግን ከፍ ብለን በጠቀስናቸው አራት የፍትሕ ፖሊሲ ዓላማዎች በኩል የሚያልፍ ነው። ያም በእውነት፣ በሰብዓዊነት፣ በተጠያቂነትና ተመሳሳይ ችግሮች እንዳይፈጸሙ በማድረግ በኩል ነው።
ፍትሕን በማስፈን፣ ተጠያቂነትን በማለማመድ ከሕዝብ ወደ መንግሥት፤ ከመንግሥት ወደ ሕዝብ የሚወርድ የሽግግር ፍትሕ ያስፈልጋል። መንግሥት እየጠየቀና ሕዝብ እየተጠየቀ፣ መንግሥት እየተናገረና ሕዝብ እያዳመጠ የሚመጣ የተሟላ የሽግግር ፍትሕ የለም።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ያለሕዝብ ተሳትፎ ምንም ነው። ለሕዝብ ፍትሕ እስከቆመ ድረስ ሕዝብን ባሳተፈና ባማከለ መንገድ ነፍስ የሚዘራ ነው። ነጻ በሆነ መንገድ ሕዝብን ቀርቦ በማወያየት እንዲሁም ለሥራው ምቹ ሁኔታዎች ተፈጥረውለት በዚህ መሰል እንቅስቃሴ ውስጥ የሚያተርፍ እንጂ በጫናና በመሰል አካሄዶች ወደ ፍትሕ የሚያመራ አይደለም።
ሕዝብ ካለፈው ተምሮ መጪውን ተስፋ በማድረግ የጋራ ሀገር እንዲገነባ በሕዝብና በመንግሥት መካከል የገባ የእርቅና የተጠያቂነት ፖሊሲ ነው። ይህ ፖሊሲ እንደ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በእርቅና በአስታራቂነት የሀገርን ቀጣይነት የሚያረጋግጥ ሲሆን፤ ጎን ለጎንም በሀገርና በሰብዓዊነት ላይ ጥሰት የፈጸሙ አካላትን እንዲጠየቁ አቅጣጫ የሚያስቀምጥም ነው።
የፖለቲካ አስተሳሰብ ለሁሉም ማኅበረሰብ እኩል ካልወገነ ይሄ በራሱ እንደመብት ጥሰት የሚቆጠር ነው። ከመብትና ከግዴታ ጋር በተያያዘ አስገዳጅ በሆነ ሥርዓት የዜጎች መብት ጥያቄ ውስጥ የሚገባ ከሆነ ጉዳዩ የመብት ጥሰት ያለበት የአንድ ወገን ውግንና ይሆናል።
እንዲህ ያለው ፖለቲካዊ ሥርዓት ነጻና ፍትሐዊ፣ ተጠቃሚነትንም ያረጋገጠ ማኅበረሰብ መፍጠር ላይ ጥያቄ ይነሳበታል። እነዚህን መሰል ክፍተቶች ዜጎች በፖለቲካ ተጽዕኖ ውስጥ እንዲወድቁ ከማድረጉም ባለፈ የመብት ጥሰት ሆኖ የሚቀመጥ ነው የሚሆነው። ይህን መሰል ሥርዓት እንዲስተካከል ካስፈለገ የሽግግር ፍትሕን የመሰለ ብሔራዊ ምክክር ያስፈልጋል።
ሀገራችን በአሁኑ ሰዓት ማኅበራዊና ሀገራዊ ለውጥን በሚያመጡ በሁለት ንቅናቄዎች ውስጥ ናት። አንዱ ወደ ሥራ ሊገባ እያኮበኮበ ያለው የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ ለጽሑፌ መነሻ ሀሳብ ያደረኩት የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ነው። ሁለቱም አሁን ላለችው ሀገራችንና አሁን ላለው ብሔር ተኮር ፖለቲካ የመፍትሔ ምንጭ ይሆናሉ ተብሎ ይታመናል።
የሁለቱም የንቅናቄ ዓውድ ፍትሕን ማስፈንና ተጠያቂነትን ማምጣት ነው። ተራማጅ በሆነ የሀሳብ የበላይነት ሰላም ተኮር በሆነ እንቅስቃሴ ነውጠኞችን ማጥራትና ተጎጂዎችን መካስ ላይ ያተኮረ ነው። የሁለቱም ንቅናቄ ማዕከል ሕዝብ ነው። ሕዝብን ጠይቆና አወያይቶ በመረጃ በተደገፈ እውነት ወደፊት መቀጠል ነው።
ሀገራችን ሕልውናዋ ጥያቄ ውስጥ በገባበት በዚህ ሰዓት ሰላም ለማምጣትና ፍትሕን ለማስፈን የእነዚህ ሁለት ኃይሎች ወደ ሥራ መግባት ብዙ ነገሮችን ያስተካክላል። ከድህነትና ከእርስ በርስ ጦርነት በቀር ዘመኑን የሚመጥን የጎላ ታሪክ የሌላት ሀገራችን ሰንኮፏን ጥላ ወደ ፊት እንድትቀጥል ሕዝባዊ ምክክር ማስፈለጉ እሙን ነው።
ከዚህ በተጓዳኝ እንደ ነውር የምንቆጥራቸውንና የምናፍርባቸውን የእርስ በርስ አለመግባባቶች በመፍጠር በሀገርና በሕዝብ ላይ ጉዳት ያደረሱ አካላትን ለሕግ ከማቅረብ አኳያ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ኃላፊነት ያለበት ሲሆን፤ መጪው ጊዜ በእርቅና በፍቅር፣ በሰላምም የምንቀበለው የጋርዮሽ እንዲሆን ከእነዚህ ሁለቱ አበይት ርዕሰ ጉዳዮች ጋር ሕዝብ መተባበር ግዴታው ይሆናል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ሚያዝያ 9 ቀን 2015 ዓ.ም