የጽንሰ ሃሳብ ብያኔ፤
በቅድሚያ «እሴት» እና «ትንሳኤ» የሚሉት ሁለት ቃላት የተሸከሟቸውን ጽንሰ ሃሳቦች ፈታ አድርገን ለማብራራት እንሞክር፡፡ በጥንታዊያኑ የግሪክ ፈላስፎች መርህ መሠረት በአከራካሪና አወያይ ጉዳዮች ለመግባባት እንዲቻል አስቀድሞ መልዕክቱን በተሸከሙ ቃላት ብያኔ ላይ መግባባትና መስማማት ግድ ይሏል፡፡ ይህንን ጠቃሚ መርህ በአሜንታ በመቀበል የጠቀስናቸው ሁለት መሪ ቃላት እንደምን ለርዕሰ ጉዳያችን ተሸካሚነት እንደተመረጡ ወደ ማብራራቱ እንዝለቅ፡፡
በአገራችን በተፋለሰ ትርጉም አገልግሎት ላይ ከዋሉ የቃላት አጠቃቀሞች መካከል አንዱ «እሴት – Value» የሚለው ከቀዳሚዎቹ መካከል አንዱ ነው። በብዙ መንግሥታዊና ሕዝባዊ ተቋማት ውስጥ «የመሥሪያ ቤታችን እሴቶች» ተብለው የሚዘረዘሩት አስር ወይንም አስራ አንድ የሚሆኑ ቃላት ደመቅ ተደርገው ተጽፈው በዋናው የተቋሙ መግቢያ በር ላይ ተለጥፈው ማንበብ የተለመደ ነው፡፡ ከእነዚህ አማላይ ቃላት መካከል «ቅንነት፣ ታማኝነት፣ ግልጽነት፣ ተጠያቂነት፣ ፍትሐዊነት፣ አጋርነት ወዘተ.» የሚሉት ጥቂቶቹ ናቸው።
«ጽድቁ ቀርቶ በቅጡ በኮነነኝ» እንዳለቸው ብሂለኛ ማራኪዎቹ ቃላት በታጀሉበት መዛግብተ ቃላት ውስጥ ተከብረው ቢቀመጡና ጉዳያችንን ያለ ጉቦ፣ መማለጃና መጉላላት ማስፈጸም ብንችል የጽድቅ ያህል ቆጥረን ገዢውን መንግሥታችንን ባመሠገንን ነበር፡፡ የሚገርመው ተቃርኖ ብዙ የተገልጋዮች እምባ እየመነጨ የሚገኘው እነዚህ «እሴቶች» ጎላ ብለው በተጻፉባቸው ተቋማት ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ ማስረጃ የሚጠይቅ አካል ካለ «አለሁ!» ይበለንና ምስክርነቱን እንስጥ፡፡ «መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ » ይሏል እንዲህ ዓይነት ግራ የሚያጋባ ሁኔታ ሲያጋጥም ነው፡፡
ይህ «እሴት» እየተባለ የሚንቆለጳጰሰው «ዘመናይ የጊዜው ቃል» የማይገባበት ዐውድ የለም እስኪባል ድረስ ጠሪው ብዙ ነው፡፡ የአንድን ተፈላጊ ነገር የአገልግሎት ጠቀሜታ (Utility Value) ለመግለጽ «እሴቱ ከፍ ያለ ነው» ይባላል፡፡ አንድ ሸቀጥ በልውውጥ፣ በግዢና ሽያጭ መካከል ሲንከላወስ ስናይ ከፍተኛ እሴት (Economic Value) ተጨምሮበታል እንላለን፡፡ ጥበባዊ ውበትን ለመግለጽ (Aestetice Value) ሥነ ጥበባዊ እሴቱ ወዘተ. እያለን ቃሉን ስናጎላምስ እንውላልን፡፡ ቃላት ማደጋቸውና መስፋታቸው የተለመደ ተፈጥሯዊ ባህላቸው ስለሆነ ይህ አካሄድ ክፋት ይኖረዋል ማለት አይቻልም፡፡ ችግር የሚሆነው ቀልብ ስንነሳው ብቻ ነው፡፡
በተለይ ከተቋማዊ ብያኔ ጋር አቆራኝተን ጥቂት እንበል፡፡ «ቅንነት፣ ታማኝነት፣ ግልጽነት…» የሚሉት ቃላት በየተቋማቱ ነፍስ ዘርተው ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉት በእያንዳንዱ ሠራተኛ ሕይወትና የአገልግሎት አሰጣጥ ሲገለጡ እንጂ ግዑዙን ተቋም በራሱ ቅን፣ ታማኝ፣ ግልጽ እያልን ብናሞካሸው ምንም ፋይዳ አይኖረውም፡፡ እንደዚህ ጸሐፊ እምነት እነዚህ አማላይና ውብ ቃላት የሠራተኛው መርህ እንዲሆኑ መሥራት ቢቻል ይበልጥ ትርጉም በሰጡ ነበር፡፡
እሴት፡- አፈጣጠሩና አጠቃቀሙ፤
የእያንዳንዱ ግለሰብ ሕይወት የሚቀረጸው ከተለያዩ የአኗኗር እርከኖች ውስጥ በሚቀስማቸው እውቀቶች አማካይነት ነው፡፡ እነዚህ እውቀቶች «ትክክል ወይንም ስህተት፣ ሰናይ ወይንም እኩይ፣ የሚበጅ ወይንም የማይበጅ፣ የሚጠቅም ወይንም የማይጠቅም ወዘተ.» ተብለው የሚፈረጁ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ይህንን ጠነን ያለ ገለጻ ትንሽ ጠለቅ ብለን እናፍታታው፡፡
የእያንዳንዱ ሰው ማንነት የተገነባው በንብርብር አለት በሚመሰል የማንነት ውቅር ነው፡፡ ወይንም ቀለል ባለ ምሳሌ አናብራራው ካልን የእያንዳንዱን ሰው የማንነት ግንባታ በቀይ ሽንኩርት (Onion diagram እንዲሉ) ልንመስለው እንችላለን፡፡ ከቀይ ሽንኩርት ላይ የመጀመሪያው ልጣጭ ቢነሳ ቀጥሎ የሚገኘው ሌላ ልጣጭ ነው፡፡ ሦስተኛ፣ አራተኛ፣ አምስተኛ ጊዜ ብንልጥም የምናገኘው ያንኑ ልጣጭ እንጂ እንደ ብርቱኳን ወይንም እንደ ሙዝ በባህርይው ከልጣጭ የሚለይን ሌላ አካል አይደለም፡፡
የሰብእና ግንባታ የሚጀምረው መጀመሪያ ከቤተሰብ ነው፡፡ ቀጥሎ ከሚኖርበት ውስን ማሕበረሰብ (Community)፣ ከፍ ሲልም ከዙሪያ ገባው ኅብረተሰብ (Society)፣ ላቅ ሲል ደግሞ ከየእምነት ተቋማቱ አስተምህሮ፣ የትምህርት ሥርዓቱ፣ የአርአያ ሰብ አስተዋጽኦዎች ወዘተ. የንብርብሩ ዓይነት ብዙ ነው፡፡ ስለዚህ የአንድን ሰው ማንነት «እንደ ሽንኩርት» የላይኛውን ማንነቱ ገለጥ ማድረግ ቢቻል የሚወጣው የቤተሰቡ የሕይወት ልምምድ፣ ደግመን ገለጥ ብናደርግ የማሕበረሰቡ የአኗኗር ዘይቤ፣ እየጠለቅን ብንሄድ የእምነቱ ተጽእኖ፣ በትምህርቱ ሥርዓት የተቀረጸበት አቋም፣ የአርአያ ሰብ ግለሰቦች ወይንም የኪነ ጥበባትና የሚዲያ ባለሙያዎች አሻራ ያረፈበት ማነነቱ ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ የንብርብር አሻራዎች በሙሉ የሚገኙት ይሁነኝ ብለን ለመማር ፈቃደኛ ስንሆን ብቻ ሳይሆን ድብቁ የአእምሯችን ክፍል (Subconscious) አያጠራቀመም ሊሆን ይችላል፡፡
በአንጻሩ በንብርብር ማንነታችን ጥልቅ አስኳል ውስጥ የምናገኘው ዋነኛው የሕይወታችን «ቅመም» እሴታችን የምንለውና የምንኖርለት የሕይወታችን ትርጉም ነው፡፡ እሴት በዕለት ተዕለት ስናነሳውና ስንጥለው እንደምንውለው ቀላል ጽንሰ ሃሳብ አይደለም፡፡ ይህ እሴት የአንድ ግለሰብ ትሩፋት ብቻ ሳይሆን ግለሰቡ እየኖረበት ያለው ማሕበረሰብ፣ ከፍ ሲልም ኅብረተሰቡ ይሁነኝ ብሎ የተጋራው (Shared value) ሊሆን ይችላል፡፡
ለምንድን ነው በርካታ ሰዎች ለትውልድ አካባቢያቸው የተለየ አክብሮት የሚሰጡት? ስለምንስ ነው የልጅነታቸው ታሪክ ሲነሳ «ልጅነቴ ማርና ወተቴ» እያሉ ለማንጎራጎር የማያፍሩት? ይህ ጸሐፊ ባደገበት አካባቢ አብዛኞቹ የዕድሜ እኩዮቹ ወይ ፖሊስ አለያም የኪነ ጥበብ ባለሙያ ሊሆኑ የቻሉበት ምክንያት በማሕበረሰቡ ውስጥ የፈጥኖ ደራሽ ፖሊሲ በጎ ተጽእኖ (የእሴት ትሩፋቱ) በቀላሉ የሚገመት ስላልነበረ ነው፡፡
ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን በአጋጣሚ በአንድ አካባቢ እግር የጣለውን ባይተዋር ሰው መግደል ወይንም በኢሰብአዊ ድርጊት ግፍ መፈጸም እንደ እኩይ ድርጊት ሳይሆን እንደ ጀብድ ወይንም ጀግንነት በሚቆጥር ማሕበረሰብ ውስጥ «እሴቴ» ብሎ የኖረ አንድ ግለሰብ ይህንን መሰሉን እኩይ ድርጊት ሲፈጽምና በማሕበረሰቡ ሲጨበጨብለት «ላፈሰሰው የንጹሕ ሰው ደም» ከፈጣሪ ዘንድ ተገቢውን ዋጋ እንደሚቀበል እንኳን ላያምንበት ይችላል፡፡ ሰው መግደል ለእርሱ ከአደን እንደሚገኝ ግዳይ ቀላል እንደሆነ ሊሰማውም ይችል ይሆናል፡፡
ቀለል ያለ ሌላ ምሳሌ እንመልከት፡፡ በአንዳንድ ማሕበረሰብ ዘንድ ለሴት ልጅ ውበት እንደ ትክክለኛ መሥፈርት የሚታየው ቅላቷ፣ ሰልካካ አፍንጫዋ፣ «ችቦ አይሞላም» የሚባልለት ወገቧ ወዘተ. ሊሆን ይችላል። በሌላው ማሕበረሰብ (የአንዳንድ የአፍሪካ ወንድም እህቶቻችን አመለካከትና እሴትን ይመለከታል) ዘንድ ውብ የምትባል ሴት የገዘፈ መቀመጫ ያላት፣ ደልዳለ
ሰውነቷ የሚሞናደል፣ ደረቷ ሰፋ ብሎ የተለጠጠ ወዘተ. ዓይነት ሴት «ከዓይን ያውጣሽ እየተባለች የቁንጅና አክሊል ሊደፋላት ይችላል፡፡» ስለዚህም ነው እሴት ከግለሰቦች ልቆ የማሕበረሰብ ወይንም የኅብረተሰብ መታወቂያና መለያ ሊሆን ይችላል ተብሎ የሚታመነው።
ሁለተኛውና መለስተኛ ትንተና የሚያስፈልገው «ትንሳኤ» የሚለው ቃል ነው፡፡ ትንሳኤ በአጭሩ ሞትን ድል አድርጎ መነሳት ማለት ነው፡፡ በተለየ ሁኔታ ቃሉ አዘውትሮ የሚጠቀሰው በክርስትና አስተምህሮ ውስጥ ነው፡፡ በቅርቡ በአገራችን ከሚከበሩ ሃይማኖታዊ በዓላት አንዱ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ በዓል ከመሆኑ አኳያ ቃሉ ላይ አጽንኦት ሰጥተን ጫን ብንል ክፋት የለውም፡፡
ክርስቶስ ከመወለዱ አስቀድሞ ለሺህ ዘመናት ያህል ለእሥራኤል ልጆች «መሲህ» እንደሚመጣላቸውና ከኃጢአት እስራትና ከግዞት አርነት እንደሚያወጣቸው በነብያቶቻቸው አፍና በጽሑፎቻቸው ሲነገር ኖሯል፡፡ ትንቢቱ እውን ሆኖ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም መወለዱ እውን ሲሆን ግን ወገኖቹ አይሁዳውያን ሊቀበሉት አልወደዱም፡፡ ስለዚህም የአወላለዱ ምሥጢር ተሰውሮባቸው፣ ሕይወቱና አኗኗሩ ግራ አጋብቷቸው፣ ትምህርቱና ስብከቱ ስላልጣማቸው ሞት ፈርደው ሰቀሉት፣ ቀበሩት፣ ከሞት የመነሳቱን ትንቢት ፉርሽ ለማድረግም በበድኑ ላይ ቋጥኝ ድንጋይ ዘጉበት፡፡ ይህ ሁሉ መከራ ቢወድቅበትም አመጣጡ በመለኮታዊ አጀንዳ መሠረት ስለነበር ሞትን ድል ነስቶ በመነሳት በትንሳኤው ከበረ፤ ሞት ሊይዘው ስላልቻለም አሸናፊነቱን አረጋገጠ፡፡
«ያልታደልሽ እንዴት አደርሽ!»
«የኢትዮጵያውያን ልዩ መገለጫዎች» በመባል የሚታወቁ በርካታ የጋራ እሴቶች እንዳሉን ለማናችንም ግልጽ ነው፡፡ እርግጥ ነው እያንዳንዱ ማሕበረሰብ የራሱ ብቻ የሆኑ በርካታ የሆኑና እርሱ ብቻ የሚገዛላቸው እሴቶች እንዳሉም መካድ አይቻልም፡፡ እውነታው ይህንን ይምሰል እንጂ በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል የሚገኙ ማሕበረሰቦቻችን ለባእድና ለእንግዳ ሰው ትልቅ ከበሬታ እንደሚሰጡ ትናንታችን ምስክር ነው፡፡
ከየት መጣህ? ስለምን ምክንያት እዚህ ተገኘህ? ከሚለው የሥጋት ምርመራ በፊት (ያውም ከሆነ) «ቤት የእግዚሃር ነው» ብለው በማስገባት ያላቸውን ያጎርሳሉ፣ ያጠጣሉ፣ ያሳርፋሉ፡፡ በአራቱም የአገሪቱ አቅጣጫ ለእንግዳ ሰው የነበረን እሴት በእኩልነት የተቀበልነው የጋራችን (Shared Value) መርህ ነበር፡፡ ይህ የሆነው «እንግዳ ተቀበሉ» ተብሎ በአዋጅ ስለተለፈፈ ሳይሆን የኅብረተሰባችን የአኗኗር አስኳል (እሴት) ስለሆነ ነው፡፡ ለዚህም ነው እንግዶችን መቀበል «ኢትዮጵያዊ ባህላችን ነው» እያልን ቱሪስቶችን ስናማልል የኖርነው፡፡
ሌላው ተጠቃሽ የጋራ እሴታችን «እጅን ከንጹሕ ደም መከልከል» ነበር፡፡ በብዙ የአገራችን ማሕበረሰቦች ዘንድ «ደም ደምን ይጠራል» የሚል እምነት ስለዳበረ ማንም ሰው በምክንያትም ሆነ ያለ ምክንያት የሰውን ነፍስ ለማጥፋት መፍጠን የተለመደ አልነበረም፡፡ «ግፉ በዘራችን ላይ ይደርሳል» የሚለው እምነት ለበርካታ ማሕበረሰቦቻችን የአኗኗራቸው ገዥ መርህ ነበር፡፡
ለሽምግልናና ለሽበት የሚሰጠው ክብርም ሌላኛው የፀና የጋራ እሴታችን ነበር፡፡ በየትኛውም ማሕበረሰባችን ውስጥ ለሽበትና ለዕድሜ ፀጋ የሚሰጠው ከበሬታ እኩል ተመሳሳይ ሊሰኝ የሚችል ነው፡፡ እንደ ሥልጡን ነን ባይ አገራት «ከጃጁ አይበጁ» በሚል ድፍረት በዕድሜ የከበሩ አባቶችና እናቶች በእሽቅድምድም ወደ ጡረታ ቤት አይወረወሩም፡፡ ይህ የሆነው «የሽማግሌ እርግማን የፈጣሪን ቁጣ ያስከትላል» የሚለው እምነት በእጅጉ ሥር ስለሰደደ ነው፡፡ «የሚያድግ ልጅ አይጥላህ፤ የሚሞት ሽማግሌ አይርገምህ» መባሉም ስለዚሁ ነው፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ብርቱ አገራዊ እሴቶቻችን የአብዛኛው ኅብረተሰባችን እሴቶች ሆነው አክብረናቸው ኖረናል፡፡ እነዚህ እሴቶች ለግለሰቦች የተለዩ በረከቶች ብቻ ሳይሆኑ የአገር መታወቂያ ሆነው የኖሩ እሴቶች ጭምር ናቸው፡፡ ይህ ማለት ግን እነዚህና መሰል ሌሎች በርካታ እሴቶች በአንዳንድ ክፋት የተጠናወታቸው ግለሰቦች አይጎድፉም ማለት አይደለም፡፡ በየትኛውም ማሕበረሰብ ውስጥ «ከባቄላ አይጠፋም ዲቃላ፤ ከጠላ አይታጣ አተላ» እንዲሉ ጥቂት ወይንም በጣት የሚቆጠሩ ፀረ እሴት እኩያን ሙሉ ለሙሉ አይኖሩም ማለት አይቻልም፡፡
ዛሬ ዛሬ እንደ አገር መታወቂያችን የሆኑን እሴቶቻችን እየተናዱ አደጋው ሲከፋብን ማስተዋል የተለመደ ሆኗል። እሴቱን ገድሎ ያራቆተ ኅብረተሰብ እርቃኑን በቆመ ግለሰብ ይመሰላል፡፡ ኅብረተሰብአዊ እርቃንነት ደግሞ የሚያስከትለው አደጋ የከፋ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ ለዘመናት እየዘመርንላቸውና እየዘየ ርንላቸው የኖርነው እሴቶቻችን ብዙዎቹ ተዋርደዋል፣ ወድቀዋል፣ ወይንም እየሞቱ ወደ ቀብር በመጓዝ ላይ ናቸው፡፡
እንግዶችን አክብሮና ተከባብሮ ከመኖር ይልቅ ገድሎና አዋርዶ መፎከር የባህል ያህል የተለመደ አገራዊ ክስተት ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡ የንጹሐንን ደም በከንቱ ማፍሰስ፣ ነፍሳቸው የተረፈውን በእገታ ይዞ ሚሊዮን ብሮችን የቤዛ ዋጋ መጠየቅ ጆሮን ጭው ከማድረግ አልፎ ተርፎ ተላምደናቸዋል፡፡ ሽበትና ሽምግልና «የገለባ ያህል ቀሏል፡፡» አባቶችን አለማክበር፣ ሲገስጹም ማናናቅ አዘውትረን እየሰማንና እያየን ያለነው «አገር በቀል እፍረታችን ሆኗል፡፡»
በአጭሩ ሕያዋን ብለን ስናሞካሻቸው የኖርነው፣ የሕይወታችን መርህም አድርገን የተገዛንላቸው፣ የሥነ ምግባር መመሪያ እንዲሆኑን የተቀበልናቸው በርካታ አገራዊ እሴቶቻችን እየሞቱ ሲቀበሩ እንደሚውሉ ለጉድ በጎለተን በዚህ የዕድሜያችን ጀንበር ፍንትው ብሎ ሲፈጸም እያስተዋልን ነው፡፡
የእሴቶቻችን ገዳዮች ደግሞ ጥቂቶች ሳይሆኑ የተደራጁ ብዙኃን መሆናቸው ነው፡፡ ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሕዝቡ ሆ እያለና የዘንባባ ዝንጣፊ እያውለበለበ «ሆሳዕና» ብሎ ከተቀበለው በኋላ በጥቂት ቀናት ይሰቀል ብለው በግፍ እንደገደሉት፤ እኛም «ሆሳዕና» እያልን ቱሪስቶችን እያማለለን ስንጋብዝባቸው የኖርነው እሴቶቻችን ዛሬ ላይ ሞት እያወጅንባቸው እርቃናችን ተገልጧል፡፡ ብዙዎቹንም ገድለን ቀብረናቸዋል፡፡
የግፍ ድርጊቶችን ተጠይፎ አጥፊዎችን ከመገ ሰጽ ይልቅ «የእብድ ገላጋይ» በመሆን ድንጋይ የተቀባበ ልንባቸው ታሪኮቻችንም ብዙዎች ናቸው። ሽማግሌና የእምነት አባት ሲናቅ፣ ሲዋረድና ሲሰደብ አልፎም ተርፎም የግፍ እርምጃ ሲወሰድበት ደንዝዘንም ሊሆን ይችላል፤ «ሕግን ከተኛበት መንበር ላይ ለመቀስቀስ» ድምጻችን የሰለለ ይመስላል፡፡ አገራዊ እሴቶቻችን እየሞቱብን ኀዘናችን በርትቷል የምንለውም ስለዚሁ ነው፡፡
ዳግም በትንሳኤ ተነስተው ያንሰራራሉ ብለን እንዳናምንም ክፉኛ የዘረኝነት ቋጥኝ ተጭኗቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ሆይ! የእህል ርሃብተኛነትሽ በእርዳታም ሆነ በልጆችሽ ጥረት ምናልባትም ሊቃለል ይችል ይሆናል። የድርቅ መከራሽም ፈጣሪ በሚሰጠን የዝናብ ጠል ሊለመልም ይችላል፡፡ የእሴቶችሽ መፈራረስ በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ ግን ለፍጻሜሽ አንጃልሽ፡፡ ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ፡፡
አዲስ ዘመን መጋቢት 20/2015