ይህ ሰሞን የምግብ (የዳቦ) ጉዳይ ሀገራዊ አነጋጋሪነቱ ጎልቱ የወጣበት ጊዜ ነው። የኢትዮጵያ መንግሥት በሀገሪቷ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ስንዴን ኤክስፖርት ልናደርግ ነው ብሎ በይፋ ከማብሰሩ አፍታም ሳቆይ ቦረናን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በተከሰተው ደርቅ ምክንያት የምግብ እህል ተረጂዎች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩ፣ እንደ ስንዴና ጤፍን የመሰሉ መሰረታዊ የሰብል ምርቶች ላይ እጥረት መከሰቱና የመሸጫ ዋጋቸውም ጣሪያ መንካቱ አወዛጋቢና በርካታ ጥያቄ የሚያስነሳ ጉዳይ ሆኖ ሰንብቷል።
በርካታ የሀገር ውስጥና የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃንም ስለስንዴ የተትረፈረፈ ምርት በመንግሥት አካላት የተነገረውን መሬት ላይ ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማነጻጸር ሲያነሱና ሲጥሉ የሰነበቱበት ሰሞን ነበር።
ምግብ ከአየር (Oxygen) ቀጥሎ ለሰው ልጅ ከሚያስፈልጉት መሰረታዊ ፍላጎቶች መካከል አንዱ እንደሆነ አንድና ሁለት የለውም። የምግብ ጉዳይ ከፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ከኢኮኖሚያዊ መስተጋብራችን ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ነው።
በአንድ ሀገር ፈጣን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ዕድገት ለማምጣትና ዘላቂ የልማት አቅም ለመገንባት ወሳኝ ነው። የምግብ ፍላጎቱና አቅርቦቱ የተሟላለት ሕዝብ ጤናማ፤ አምራች፤ ረዥም ዕድሜና አስተማማኝ የፈጠራ ብቃት ይኖረዋል። በአንጻሩ የምግብ ፍጆታው ያልተረጋገጠለትና በረሃብ ቸነፈር የሚጠቃ ሕዝብ በአእምሮና በአካል የበለጸገ አይሆንም ፤ አምራች ዜጋም ሊሆን አይችልም። ይህ ደግሞ በሀገር እድገትና ልማት ላይ የሚያስከትለው ችግር በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡ የምግብ እጥረት ቀውስ ያለባቸው ሀገራት ለተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶችና ፖለቲካዊ አለመረጋጋቶች የመጋለጣቸው ሁኔታም የተለመደ ነው።
በምግብ እራስን አለመቻል ከዚህም አልፎ ሙሉ የኢኮኖሚ ነጻነትና ብሄራዊ ክብርንም ያሳጣል። የምግብ ፍላጎታቸውን ያላሟሉና ሲረዱ የቆዩ ሀገራት ለተለያየ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖዎች የመጋለጥ እድላቸው እጅግ በጣም ከፍተኛ ነው። ነፃነቷን ጠብቃ የቆየችው ሀገራችን የዚህ ዕውነታ ተጋሪ ናት ።
የምግብ ዋስትና ጉዳይ ከ1970ዎቹ ጀምሮ የተያዘ ሰፊ ጽንሰ ሃሳብ ነው። በ1990ዎቹ መጨረሻ ግን ከሚሊኒየሙ ግቦች የመጀመሪያው ከሆነው ረሃብን የማጥፋት ዘመቻ ጋር እንዲያያዝ ተደርጎ በመታሰቡ ኢትዮጵያን ጨምሮ ብዙ ሀገሮች የፖሊሲዎቻቸው አካል ካደረጉት ቆይተዋል።
በዓለም የምግብ ድርጅት (FAO) ትርጓሜ መሰረት የምግብ ዋስትና (Food Security) ተረጋገጠ የሚባለው በአንድ ሀገር ያሉ ሁሉም ሰዎች ንቁና ጤናማ ሕይወት ለመኖር የሚያስፈልጓቸውን በቂ፣ ጤናማና የተመጣጠነ ንጥረ ነገር ያለው የምግብ አማራጭ ለማግኘት የሚችሉበት የኢኮኖሚ አቅምና አቅርቦት ሲኖራቸው ነው፡፡ የምግብ ዋስትና አንደምታው የራስን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የውስጥ ፍጆታን ከማሟላትም የዘለለ ነው፡፡
የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ የምርት እጥረትና የዓለም አቀፍ ገበያ ውጣ ውረድ በሚያጋጥምበት ሁኔታም ለዜጎች በቂ የምግብ ምርት ሳያስተጓጉል የሚያቀርብ የምርት፤ የግብይትና የመጠባበቂያ ክምችት ሥርዓት የመዘርጋት እንዲሁም የኢኮኖሚ አቅም ማዳበርንም ያካትታል፡፡
ዛሬ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከስምንት መቶ ሚሊዮን የሚበልጥ ሕዝብ በምግብ እጥረት ችግር ወይም የምግብ ዋስትናው ባልተረጋገጠበት ሁኔታ ውስጥ የእንደሚገኝ የዓለም የምግብ ድርጅት (World Food Program) ሪፖርት ያመላክታል፡፡ ወደ ሁለት ቢሊዮን የሚገመት ሕዝብ ደግሞ ጠቃሚ ቫይታሚኖችንና ማዕድናትን እንደማያገኝ ይገለጻል። ይህ ሁኔታ የተደበቀ ረሃብ (የምግብ እጥረት) (hidden hunger) መከሰቻ ተብሎ ይታወቃል፡፡
በአፍሪካ ደረጃ የምግብ እጥረት የሚፈትነው ሕዝብ ቁጥር በጠቅላላው 21% ሲሆን፣ ከሰሃራ አፍሪካ በታች ከሚገኙት ውስጥ ደግሞ ከሕዝቡ 25% የሚሆነው በምግብ እጥረት ችግር እጦት የሚንገላታ መሆኑን አሃዛዊ መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም 13 ነጥብ 7 በመቶ የሚሆኑ ጨቅላ ሕጻናት በተመጣጠነ ምግብ ዝቅተኛ ክብደት ያላቸው ሲሆን 30 ነጥብ 7 የሚሆኑ ከ 0 እስከ 5 ዓመት እድሜ ያላቸው ሕጻናት ደግሞ የቀነጨሩ መሆናቸውን የዓለም አቀፍ የተመጣጠነ ምግብ ሪፖርት ያሳያል።
አህጉረ አፍሪካ 9 ቢሊዮን የሚያክለውን የአህጉሪቱን ሕዝብ መመገብ የሚያስችል ለእርሻ ተስማሚ የሆነ መሬት ባለቤት እንደሆነች ቢነገርላትም ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኞቹ ሀገሮች ይህንን ሀብት በአግባቡ ባለመጠቀማቸው ህዝቦቻቸውን ከምግብ እጥረት ፣ ከተረጂትና ከድህነት ማላቀቅና የምግብ ዋስትናን በአሰተማማኝ መልኩ ማረጋገጥ ትልቅ ፈተና ሆኖባታል።
የፓን አፍሪካ ባንክ (The Pan-African bank) ያወጣው መረጃ እንደሚያሳየው፤ አህጉሪቱ ለእርሻ ተስማሚ የሆነውን 65 በመቶ የሚደርሰውን የተፈጥሮ ሀብቷን በተገቢው ሁኔታ ጥቅም ላይ ማዋል ብትችል እ.አ.አ በ 2050 9 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ የሚገመተውን የዓለም ሕዝብ መቀለብ የሚያስችል እምቅ አቅም እንዳላት ያትታል። ሆኖም «ጽድቁ ቀርቶ በወጉ በኮነነኝ» እንደሚሉት ብሂል ሆኖ አብዛኞቹ በአህጉሪቱ ስር የሚገኙ ሀገራት ዋና መለያቸው ረሃብ፣ የምግብ እጥረት፣ የምግብ ዋስትና ማጣትና የመሳሰሉት ክስተቶች ሆነው ዘመናትን ዘልቋል። ይህ አህጉሪቱ ጤናው የተጠበቀና አምራች ህብረተሰብ እንዳይኖራት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል።
አህጉሪቷ የራሷን የግብርና ምርቶች በዓለም ገበያ በመሸጥ እንደሌሎቹ ሁሉ ተጠቃሚ የመሆን ሰፊ እድል ቢኖራትም፣ ዛሬም የምግብ ዋስትናዋ በከፊል የተንጠለጠለው በውጭ እርዳታና ተሸምቶ በሚገባ የምግብ እህል ላይ ነው። በዚህም ምክንያት አህጉሪቱ ካላት ውስን ጥሪት ላይ በአመት ወደ 75 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ በማውጣት ለዚሁ ዓላማ ስታውል እንደቆየች የአፍሪካ ልማት ባንክ (African Development Bank) ሪፖርት ይጠቁማል።
በኢትዮጵያም ተጨባጭ ሁኔታ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ እንደ ሀገር ካሉ ችግሮች መካከል አንደኛው ነው፡፡ በ 2022 ቱ የዓለም የረሃብ ምደባ መሰረት (Global Hunger Index) ኢትዮጵያ ከ 121 የዓለም ሀገራት ውስጥ 104ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠች
ሲሆን በሀገሪቱ የምግብ ዋስትናቸው ያልረጋገጠ ላቸው ዜጎች ቁጥር ወደ 22.3 ሚሊዮን ይደርሳል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ ሁሉም አይነት ከምግብ ጋር የተያያዙ ችግሮችን እያስተናገደች መሆኑን ይፋ አድርጓል።
ሀገሪቱ እንደ ስንዴ፣ ሩዘ፣ አተር፣ ምስር፣ ፓስታ፣ መኮረኒ… ያሉ ምርቶችን ከውጭ ለማስገባት በየአመቱ ከፍተኛ ወጪ ትከሰክሳለች። ለምሳሌ ስንዴን ከውጭ ለማስገባት በየአመቱ ከ 700 ሚሊዮን ዶላር እስከ አንድ ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም ለአተር በአማካይ በየአመቱ 50 ሚሊዮን ዶላር እንደምታወጣ ከግብርና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ሀገራችን ሰፊና ለም መሬት፣ ተስማሚ ሥነ ምህዳር፣ ግዙፍ የውሃ ሀብት እና በእንስሳት ሀብት የተቸረች ናት። ይሁንና ከ74 ሚሊዮን ሄከታር ሊታረስ የሚችል የመሬት ሀብቷ ያልዘመነ የአስተራረስ ዘዴን በመጠቀም እየታረሰ የሚገኘው 13 ሚሊዮን ሄክታር ብቻ ነው። ይህም በአብዛኛው ሕዝቡ ተጠጋግቶ የሚኖርባቸውን ደጋና የወይና ደጋ አካባቢዎችን አካቶ የያዘ ነው።
በእነዚህ ቦታዎች የሚካሄደው አብዛኛው የግብርና ስራም አሁንም ድረስ ኋላቀር የአስተራረስና የግብዓት አጠቃቀም ዘዴን የሙጥኝ ያለ ነው። ከግብርና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ማዳበሪያ የሚጠቀመው አርሶ አደር 62 በመቶ ብቻ ነው ። እንዲሁም የምርጥ ዘር አቅርቦታችን 25 በመቶ፣ የሜካናይዜሽን አጠቃቀማችን 6 በመቶ፣ በመስመር የመዝራት ባህላችን 28 በመቶ ላይ እንደሚገኝ መረጃው ያመላክታል። በዚህ መልኩ የሚታረሰው መሬት የሚሰጠው ምርት በሄክታር አነስተኛ በመሆኑ በምግብ እራሳችንን መቻል ቀርቶ በግብርናው ዘርፍ የተሰማራውን ሰፊውን አርሶ አደር እንኳን በበቂ ሁኔታ መግቦ ማሳደር አልቻለም።
በአንፃሩ ከተሞች በአብዛኛው ሊባል በሚችል መልኩ ከገጠር በሚቀርቡ የግብርና ምርቶች ላይ ጥገኛ በመሆናቸውና የአብዛኛው ነዋሪም የኢኮኖሚ አቅም ካለው የኑሮ ውድነት አንጻር የማያወላዳ በመሆኑ የምግብ ዋስትና ችግሮችን በመሠረታዊነት ማቃለል አልተቻለም። በመሠረታዊ ምግቦች ደረጃ ሲታይ ዜጎች የሚያገኙት የካሎሪ መጠን በጣም ዝቅተኛ ነው፡፡
ሰፊ የከብትና የእንስሳት ሀብት ባለቤት እንደሆንን ቢነገርም “ላም አለኝ በሰማይ ወተቷንም አላይ” እንደሚባለው ሀገራዊ ብሂል ሆኖ ሥጋ፣ ዶሮ፣ ወተት፣ ቅቤ፣ አትክልትና ፍራፍሬ… የመሳሰሉት በማእድናት የበለጸጉ ምግቦች ለአብዛኛው ዜጋ ብርቅ ወደመሆን ደረጃ ተሸጋግረዋል። የኑሮ ውድነቱና የገበያው መመሰቃቀል ደግሞ ችግሩን በይበልጥ እንዲከፋ አድርጎታል።
በአንድ ሀገር የምግብ ዋስትና ተረጋገጠ የሚባለው አብዛኛው ሕዝብ በቂ፣ ጤናማና የተመጣጠነ ምግብ በአስተማማኝ ሁኔታ ማግኘት ሲችልና በየእለቱ ከ 2,100 በላይ የካሎሪ መጠን ሲያገኝ ነው። የምግብ ዋስትና ስለመረጋገጡ ሌላው መመዘኛ ለተመጣጠነ የምግብ እጥረት የሚጋለጠው ሕዝብ ቁጥር ከጠቅላላው ሕዝብ 5 በመቶ በታቸ ሲሆን ነው። በመሆኑም በእነዚህ መመዘኛዎች ሚዛን ሲፈተሽ በሀገራችን የምግብ ዋስትናን ያልተረጋገጠ ከመሆኑ ባለፈ በተለይ በገጠር የሚኖረውን ማህበረሰብ ከፍተኛ ለሆነ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት፣ ለአካልና ለአእምሮ እድገት ውስንነት (በተለይ ከ5 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊ ህጻናት) ተጋላጭ እንደሆኑ ጥናቶች ያመላክታሉ።
ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር መካከል አብላጫውን ቁጥር የሚይዘው ማህበረሰብ (80 በመቶ የሚሆነው) የኑሮው መሰረት ግብርና ነው። የሀገሪቱም አኮኖሚ በአብዛኛው ግብርናው ላይ የተንጠለጠለ ነው። ግብርና ከጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት 34 ነጥብ 1 በመቶ መያዙና 79 በመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ገቢም ከዚሁ ዘርፍ የሚገኝ መሆኑ ነው። ያም ሆኖ ይህ ሁሉ የሰው ሃይል የተሰማራበት ግብርናችን በምግብ ራሳችንን የመቻል ፍላጎታችንን አላሳካልንም።
ለምሳሌ በአስራኤል በእርሻ የተሰማራው ሕዝብ ከጠቅላላው ሕዝብ ውስጥ 2 ነጥብ 5 ፐርሰንት ብቻ ሲሆን ይህን ጥቂት የሰው ሀይል ይዞ የሚካሄደው ግብርና የሚካሄደው ደግሞ 20 ፐርሰንት በሆነው ለም መሬት እና 60 ፐርሰንት በሆነው ደረቅ መሬት ላይ ነው። ከዚህ አኳያ በእርሻ የተሰማራው ሕዝብ ቁጥርና የሚታረሰው የመሬት መጠን ከእኛ ጋር ሲወዳደር እዚህ ግባ የሚባል ባይሆንም የእርሻው ምርታማነት እራስን ከመቻል አልፎ የተትረፈረፈ የግብርና ምርት በተለይም የፍራፍሬና የአትክልት ውጤቶችን ኤክስፖርት በማድረግ በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት ሀገሮች ተርታ እንድትሰለፍ አስችሏታል። በዚህም እስራኤል በአመት 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚደርስ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ታገኛለች።
እስራኤል በዓለም ላይ ከፍተኛ የወተት ምርት ከሚያመርቱ ሀገራት አንዷና ዋነኛዋ ናት። በዓመት ከአንድ የወተት ላም በአማካይ እስከ 13,000 ሊትር ወተት ታመርታለች። አብዛኞቹ ሀገራት ከአንድ ሄክታር በአማካይ እስከ 500 ኩንታል ቲማቲም የሚያመርቱ ሲሆን እስራኤል ግን በመስኖ ልማት ከአንድ ሔክታር እስከ 3000 ኩንታል ቲማቲም የምታመርትበት ደረጃ ላይ ደርሳለች ። የእኛ አማካይ ምርት ከ 350 እስከ 400 ኩንታል አይዘልም።
በሌላ በኩል በእስራኤል በምርትና በድህረ ምርት ወቅት ያለው የብክነት መጠን 0.5 በመቶ ብቻ ሲሆን የእኛ ግን ከኋላቀር አስተራረስ፣ ዘር የመዝራት፣ የአጨዳና የውቂያ የግብርና እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ ከአጠቃላይ ምርታችን 25 በመቶ የሚሆነው ለብክነት ይዳረጋል።
እስራኤልን ሀገር በግብርናው ውጤታማ እንድትሆን ካደረጓት መሰረታዊ ምክንያቶች አንዱ የመስኖ እርሻን ለማካሄድ የምትጠቀመው ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ነው። ለምሳሌ 62 % የሚሆነው ለመስኖ ጥቅም ላይ የሚውለው ውሃ የሚመረተው የተወገደ ውሃን መልሶ በማጣራት (waste water) እና ጨዋማ ውሃን ጨዋማ ወዳልሆነ ውሃ መልሶ በመቀየር (brackish water) ነው።
ከዚህም ባሻገር 75 በመቶ የሚሆነው የመስኖ እርሻ የሚከናወነው የጠብታ መስኖ ቴክኖሎጂን (drip irrigation) ስራ ላይ በማዋል ነው። ከዚሁ ጎን ለጎን በመላ ሀገሪቱ የሚካሄዱት ዘርፈ ብዙና ተጨባጭነት ያላቸው (applicable) የጥናትና ምርምር ተግባራት በአብይነት ይጠቀሳሉ። በእኛ በኩል ምንም እንኳን አሁን አሁን ብዙ መሻሻሎች ቢኖሩም አብዛኛው የግብርና ስራ ከሳይንሱ በጣም በራቀ ሁኔታ የሚከናወን ነው። ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማካሄድ፣ በማስተዋወቅና በማስፋት በኩልም ብዙ መንገድ ይቀረናል።
ይህ የሚያሳየን ነገር በሰው ሀብትም ሆነ በተፈጥሮ ሀብት ባለጸጋ ብንሆንም የተሰጠንን ሀብት በብቃትና በጥበብ በመጠቀም ባለመቻላችን በሚፈለገው ደረጃ ውጤት ላይ አለመድረሳችን ነው። ይህም በመሆኑ ግብርናችን የተፈጥሮ አደጋን ሆነ ሰው ሰራሽ አደጋን በዘላቂነት መቋቋም አንዳንችል አድርጎናል። በአሁኑ ወቅት ቦረናን ጨምሮ በሶማሌ፣ በደቡብና ሌሎችም አካባቢዎች ከብት በቁም እስከ መሞት ያደረሰው ድርቅና ከድርቁ ጋር ተያይዞ የተከሰተው ሰብአዊ ቀውስ ለዚህ ጥሩ ማስረጃ ነው።
ችግሮችን የምናነሳው ከሰራን በግብርናው ዘርፍ ያለውን መጥፎ ታሪክ መለወጥ እንደሚቻል ለማመላከት እንጂ ሂደታችን በሙሉ ጨለማ አድርጎ ለማሳየት አይደለም።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የግብርና ምርትን ለማሳደግ የማይናቅ ጥረት ሲደረግ ቆይቷል። ከእነዚህ ጥረቶች መካከል ለማዳበሪያና ለምርጥ ዘር አቅርቦት፣ ለኩታ ገጠም እርሻ፣ ለሜካናይዜሽን አገልግሎት… ወዘተ መስፋፋት የተሰጠው ትኩረት ይጠቀሳል። ከዚህ አንጻር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በስንዴ ልማት ላይ እየታየ ያለው የምርትና ምርታማነት እመርታ ይበል የሚያሰኝ ነው። ስንዴ በመኸር ብቻ ሳይሆን በበጋ መስኖም እንዲለማ በማድረግ ውጤት ማምጣት እየተቻለ ነው።
ለምሳሌ የበጋ ስንዴ ልማት ስራዎች ከተጀመሩ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ በዘጠኙ ክልሎች በመስኖ አምራች ያልነበሩ አካባቢዎች ወደ ስንዴ ምርት እንዲገቡ ተደርጎ አመርቂ ውጤት መታየቱን የግብርና ሚኒስቴር ሪፖርት ያመላክታል። በዚህም ኢትዮጵያ በ 2015 አመት ብቻ በመስኖና በዝናብ ከ160 ሚሊዮን ኩንታል የተሻገረ የስንዴ ምርት ታገኛለች ተብሎ ይጠበቃል።
እስካሁን በመኽር ከ112 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት የተገኘ ሲሆን፣ ከበጋ የመስኖ ስንዴ ደግሞ 52 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይጠበቃል ነው የተባለው። ያለውን የገበያ ንረት ከማረጋጋት፣ ከምርት አቅርቦት…ወዘተ ጋር ተያይዘው የሚስተዋሉ ችግሮች እንዳሉ ሆኖ ስንዴ በዚህ መጠን መመረት መቻሉ ለዘመናት ከረሀብተኝነት አባዜ ለመገላገል ጥረት ስታደርግ ለቆየች ሀገር ትልቅ እመርታና ሰፊ ዕድልም ይዞ የሚመጣ ነው።
ይህ መልካም ውጤት ቀጣይነት እንዲኖረው ከተሰራ በቅርብ ጊዜ ውስጥ በዋና ዋና የምግብ እህሎች እራሳችንን ከመቻል አልፈን ከውጭ ድጋፍና ተመጽዋችነት ለመላቀቅ ሰፊ እድል አለን የሚል እምነት አለኝ ። ይሁንና በምግብ እራስን መቻል ብቻውን የምግብ ዋስትና ያረጋግጣል ማለት እንዳልሆነ የዘርፉ ምሁራን ደጋግመው የሚገልጹት እውነታ ነው፡፡
ምክንያቱም የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ በተጓዳኝ ሌሎች በርካታ ስራዎችን መስራት የሚጠይቅ በመሆኑ ነው። በሀገራችን ከሚታየው ፈጣን የሕዝብ ቁጥር እድገት፣ የተፈጥሮ ሀብት መመናመን፣ የአየር ንብረት ለውጥ መለዋወጥ፣ ከግብአት አቅርቦት ውስንነት…ወዘተ አንጻር የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ፈተናው ቀላል እንዳልሆነ ግልጽ ነው።
ከዚህ አኳያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከዚህ በታች የተዘረዘሩት መሰረታዊ ነገሮች ላይ ቅድሚያ ሰጥተን መስራት እንዳለብን አምናለሁ ።
1/ በሁሉም የግብርና ዘርፎች (አይነቶች) ምርትና ምርታማነትን በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ፤
2/ ለእርሻ ስራ ያልዋሉ አዳዲስ መሬቶችን ወደ ሥራ በማስገባት የተፈጥሮ ሀብታችንን በአግባቡ መጠቀም፤
3/ የምግብ ምርቶች ላይ የሚታዩትን ውስብስብ የገበያ ሥርዓቶችን በየጊዜው እየተፈተሹ መፍትሄ ማበጀት፤
4/ ከእርሻ እስከ ገበያ ድረስ ባሉት ሂደቶች ያለውን የምርት የብክነት መጠን መቀነስ ፤
5/ የግብርና ስራን በዘመናዊ ቴክኖሎጂና በሜካናይዜሽን አገልግሎት ለማስደገፍ የሚደረገውን ጥረት አጠናክሮ መቀጠል፤
6/ የአካባቢ ጥበቃና የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምን ከግብርና ሥራ ጋር አቀናጅቶ መሥራት፤
7/ ከተለመደው የአመጋገብ ባህላችን ባሻገር አዳዲስ የአመጋገብ ባህሎችን ማበረታታት።
በእኔ እምነት እነዚህ መሰረታዊ ነገሮች ላይ ግዜ ሳናጠፋ መስራት እንዳለብንና አገራችንን ከተደቀነባት የምግብ ዋስትና ስጋት እንውጣ ባይ ነኝ ። ይህ ባልሆነበት የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ አዳጋች ነው ብዬ እሰጋለሁ።
ዳግም መርሻ
አዲስ ዘመን መጋቢት 19 ቀን 2015 ዓ.ም