በመዲናችን አዲስ አበባ ሰሞኑን “ግብር ለሀገር ክብር” በሚል መሪ ሀሳብ የገቢ ንቅናቄ ማስጀመሪያና ለግብር ከፋዮች እውቅና አሰጣጥ ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡ በዚህ ዝግጅት ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ የአዲስ አበባ ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ተጋባዥ እንግዶች የፕሮግራሙ ታዳሚ ሆነዋል፡፡
በዝግጅቱ ላይ አቶ ደመቀ መኮንን ንግግር ያደረጉ ሲሆን፤ በንግግራቸውም “የተጀመረውን የሀገር እድገት ለማስቀጠል አሰራርን በማበልጸግ በግልጸኝነት የተሞላ የግብር አሰባሰብ ስርዓት ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በበኩላቸው፤ ግብርን በወቅቱ እና በኃላፊነት መክፈል የከተማችንን ብሎም የሀገርን ገቢ የማመንጨት አቅም እንደሚያሳድግ አመልክተዋል፤ ግብርን በታማኝነት መክፈል የስልጡንነት እና የታማኝነት ምልክት መሆኑንም በወቅቱ ባስተላለፉት መልእክታቸው አስታውቀዋል፡፡
በዝግጅቱ ላይ ይሄን መሰል መልዕክቶች ከማስተላለፍ ባለፈ፤ በ2014 በጀት አመት ሞዴል ግብር ከፋይ ለሆኑም 300 ለሚጠጉ ታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅና ተሰጥቷል፡፡ ይሄ ደግሞ የግብር ሥርዓት ተገዢነትን ከማጎልበት በተጓዳኝ፤ ሌሎች ወደ ስርዓቱ እንዲገቡ የሚያነሳሳ መልካም ተግባር ነው፡፡ ይሁን እንጂ በእለቱ እውቅና የተሰጣቸው ግብር ከፋዮች ቁጥር ሲታይ አዲስ አበባ ውስጥ ካለው የሕዝብ ቁጥርና የግብር ከፋይ መጠን ጋር ሲነጻጸር በቂ አይደለም፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የገቢዎች ቢሮም በቀጣይ ከዚህ ቁጥር የሚልቁ ታማኝ ግብር ከፋዮችን ለማፍራት እንደሚተጋ ነው በዚሁ መድረክ ላይ ቃሉን የሰጠው፡፡
ቢሮው እንዳስታወቀው፤ በበጀት አመቱም 100 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ እየሰራ ነው፡፡ ይሄን ከማሳካት አኳያም ባለፉት ሰባት ወራት ለመሰብሰብ ከአቀደው 59ነጥብ11 ቢሊዮን ብር ውስጥ 58ነጥብ43 ቢሊዮን ብር ሰብስቧል፡፡ ይህም ከእቅዱን 98ነጥብ8 በመቶ ነው፡፡ በንቅናቄ መድረኩ ላይ እንደተገለጸው፤ በአዲስ አበባ ብቻ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ግብር ከፋዮች አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 300 ያህሉ ብቻ ተገቢውን መረጃ በማሟላት ግብራቸውን በወቅቱ እየከፈሉ ይገኛሉ። ይህ የሚያሳየው እንደ ሀገር ያለን የግብር አሰባሰብ ስርዓታችን ደካማ መሆኑን ነው፡፡ ሆኖም ለአንድ ሀገር ዜጎች ግብርን በወቅቱና በታማኝነት መክፈል ግዴታ ነው። ከዚህም ባለፈ ዜጎች ለሀገር የሚታመኑበት ለሀገራቸው ያላቸውን ፍቅር የሚገልጹበት ነው።
አሁን ባለው ሀገራዊ እውነታ አብዛኞቹ ግብር ከፋይ ዜጎቻችን ህግና ስርዓትን ጠብቀው የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱና በታማኝነት የሚከፍሉ አይደሉም። ከዚህ ይልቅ ስለልማት ስራዎች መጓደልና ስለድህነት አብዝተው የሚያወሩና በዚህም መንግስትን ተጠያቂ ለማድረግ የሚሞክሩ ናቸው። ይሁን እንጂ ኃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ ግዴታቸውን ሳይወጡ /ሳንወጣ በሀገር ጉዳይ ላይ የምንሰጠው አስተያየት ልክነት የጎደለው ከመሆን ባለፈ፤ በሞራል መመዘኛም ቀልሎ የሚታይ ፤ መታረም የሚገባው ከትናንት ይዘነው የመጣነውና ዛሬን እየሸፈነብን ያለ ችግር ነው።
ግብር መክፈል ከዚህም ባለፈ የስልጡንነትና የዘመናዊነት መገለጫ ጭምር ነው፡፡ ግብር ለምን እንደሚሰበሰብ በአግባቡ ማወቅና ለአላማው ተገዥ መሆን ዘመንን የመዋጀን ያህል የሚታሰብ አስተሳሰብ ልዕልና ነው። ይህንን እውነታ በህብረተሰቡ ውስጥ በአግባቡ በማስረጽ ጠንካራ ባህል አድርጎ ለማስቀጠል ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን መስራት ወሳኝ ነው ። በአመት አንድ ጊዜ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን መፍጠር መብቱን በሚገባ ተረድቶ ግዴታው ላይ የተዘናጋውን ግብር ከፋይ ማህበረሰብ ወደ ትክክለኛው መንገድ ይመልሰዋል ተብሎ አይታመንም፡፡ የግብር ጉዳይ እንደኛ ባሉ ሀገሮች በትውልዶች ውስጥ እንዲሰርጽ በሀገራዊ የትምህርት ስርዓት ውስጥ ሊካተት የሚገባ አጀንዳ ሊሆን ይገባል።
ስለመሰረተ ልማት፣ ስለመብራትና ውሃ፣ ስለሆስፒታሎች፣ ጤና ጣቢያና መንገድ፤ ስለሌሎችም ማህበራዊ አገልግሎቶች ጥያቄ እናነሳለን። ጥያቄ ማንሳታችን ተገቢ ነው። ጥያቄ ያነሳነው ግዴታችንን ተወጥተን ነው ወይስ ሳንወጣ? የሚለው ነውና ጉዳዩ በቀላሉ ሊታይ የሚገባው አይደለም። ሀገር ሳንሰጣት የምትሰጠን ነገር የላትም፡፡ ከትላንት እስከዛሬ እየተቀበልን ያለነው የሰጠነውን ነው፡፡ ዛሬ ላይ የምንከፍለው ግብር ነገ ላይ መንገድና መብራት፣ ሆስፒታልና ንጹህ ውሃ ሆኖ ደጃችን የሚመጣ ነው፡፡ ለሀገር መስጠት ለራስ መስጠት ነው፤ ከዚህ የራቀ ሌላ ትርጉም የለውም፡፡
በሰለጠነው ዓለም የሰለጠነው ማህበረሰብ ግብርን ሲከፍል ደስ እያለው ነው። ምክንያቱም እንደ ዜጋ ከመንግስት የሚፈልጋቸው ማናቸውም ነገሮች ግብር ከፋዩ በከፈለው ገንዘብ የሚሰሩ በመሆናቸው ነው፡፡ እጃችንን ለመስጠት ሸሽገን፣ አገልግሎት ላገኘንበት ነገር ወደኋላ እያልን መንግስትን ማማረሩ ተገቢ አይደለም፡፡ መንግስትን ልንጠይቀው የምንችለው፤ ወይም ተጠያቂ ልናደርገው የሚገባን ግዴታችንን እስከ ተወጣን ድረስ ብቻ ነው፡፡ ያም ማለት እኛ በታማኝነት ግብር እየከፈልን መንግስት በታማኝነት የማያገለግለን ከሆነ ያኔ መንግስትን የመጠየቅ ያልተገደበ መብት አለን፡፡
ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ግብር ሳንከፍልና የግብር ማጭበርበር ተግባር እየፈጸምን ሀገር አልተለወጠችም፣ መንግስት እየሰራ አይደለም . . . ማለቱ መሰረት የሌለው ክስ ነው፡፡ ሀገርን ማገልገል ራስን ማገልገል ነው፡፡ ለሀገር መስጠት ለትውልዱ መስጠት ነው፡፡ ይህ ለሁሉም፣ በተለይም ለግብር ከፋዩ የኅብረተሰብ ክፍል ግልፅ መሆን አለበት። ይህን እውነት ይዘው ነው የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆኔፍ ኬኔዲ “ሀገሬ ለእኔ ምን አደረገችልኝ ሳይሆን እኔ ለሀገሬ ምን አደረኩላት” ሲሉ በምድረ አሜሪካ ሕዝባዊ ንቅናቄ የጀመሩት፡፡ ያ ንቅናቄ ነው የዛሬዋን አሜሪካ የፈጠራት፡፡
እኛም እንደ ሀገር፣ እንደ ማኅበረሰብ ለመቀጠልና ለመጠቀም “እኔ ለሀገሬ ምን አደረኩ?” በማለት ራሳችንን መጠየቅ አለብን። ይህ አንዱና ወደ ለውጥ የሚመራን አቅጣጫ ነው፡፡ ይሄ አቅጣጫና ንቅናቄ ደግሞ እንደ ግብር መክፈል ትንሽ ከሚመስሉ፣ ግን ደግሞ የእድገትና የለውጥ የጀርባ አጥንት ከሆኑ ነገሮች የሚጀምር ነው፡፡ እንደ ዜጋ ለሀገራችን የሚጠበቅብንን ካላደረግን የምንፈልገው እድገትና ለውጥ አይመጣም፡፡ ሀገራዊ ለውጥ ያለው ግለሰባዊና ማህበራዊ ለውጥ ውስጥ ነው፡፡ ያ ለውጥ ደግሞ ሀገር ከመውደድና ለሀገር ከመቆርቆር የሚጀምር ነው፡፡
ያ ለውጥ ግብርን በወቅቱ ከመክፈልና ያገለገለችንን ሀገር መልሰን ስናገለግላት ነው፡፡ ራሳችንን ብቻ አፍቅረን፣ አመት በመጣ ቁጥር የሚጠበቅብንን ግብር ሳንከፍል ሀገር ወዳድ ነን ማለት አንችልም፡፡ የሀገር ፍቅር በወሬ ሳይሆን በተግባር የሚገለጽ ነው፡፡ በንቃትና በተሳትፎ የሚረጋገጥ ነው፡፡ ለሀገራችን እስካልነቃንና እስካልበቃን፣ እስካልሰጠንና ግዴታችንን እስካልተወጣን ድረስ ሕዝብ መንግስትን መንግስትም ሕዝብን ከመውቀስና ከመወቃቀስ አንድንም፡፡ እውቀት መር የሆነ ማህበራዊ ንቅናቄ ያስፈልገናል፡፡ ያም ግብር ለሀገር እድገትና ብልጽግና ዋነኛው መሳሪያ መሆኑን መገንዘብና ማስገንዘብ ነው፡፡
ሀገራችን በፖለቲካውም ሆነ በየትኛውም እንቅስቃሴ ውስጥ ገብቶት ሀገር የሚመራ፣ ገብቶት ዜጋ የሆነ ሕዝብና መንግስት ያስፈልጋታል፡፡ ግብር ስንጠየቅ ውሸትና ማጭበርበርን የምናስቀድመው ንፍገትን ከስግብግቦች ወርሰን ነው፡፡ በሀገር ጉዳይ ላይ የገባው ዜጋ ግብር ለመክፈል አያንገራግርም፡፡ ወይም ደግሞ ክፈል እስኪባል፤ ወይም ተገዶና ተከሶ ግብር እስኪከፍል አይጠብቅም፡፡ ለእንዲህ አይነቱ ትላንት ለነበረ፣ ዛሬም ላለ፣ ነገም ስላለመቀጠሉ ማረጋገጫ ከሌለው ሀገራዊ ችግር እራሳችንን ማራቅ አለብን፡፡
ግብር መክፈልን ግዴታችን ብናደርግና ንቁ ግብር ከፋይ ማኅበረሰብ ብንሆን፣ የልማት ስራዎቻችን ከዚህ ከፍ ባለ ደረጃ ላይ በደረሱ ነበር። ይህ ግን ሊሆን አልቻለም፤ ለዚህ ደግሞ የግብር አከፋፈል የተበላሸ ባህላችን ተጠያቂ ነው። ግብር ሀገርና ሕዝብ ትውልድም የተሳሰሩበት፣ የተጋመዱበትና አንዱ ያላንዱ ህልውና የማያገኙበት ነው፡፡ እኛ በምንከፍለው ግብር ነገ ላይ እኛና የእኛ ልጆች እንደሚጠቀሙበት፤ የሀገር እድገት፣ የማኅበረሰብ ለውጥ በእኛ በታማኝነት ግብር መክፈል ውስጥ የተቀመጠ የመሆኑ ተጠየቅ ነው፡፡
ሰው ለሀገሩ ለመስጠት ከሳሳ እዛ ጋ ነው ትልቁ ድህነትና ኋላ ቀርነት ያለው፡፡ ሀገር በክብር፣ በልዕልና እያኖረችን ለሀገር መሰሰት ማለት የነውሮች ሁሉ ነውር፤ የነውር ጥግ ነው፡፡ ለሀገር መስጠት ለራስ መስጠትና ለሚመጣው ትውልድ መልካም ነገርን ማቆየት ነው፡፡ ለሀገር መስጠት ሀገራችን ለዋለችልን ውለታ የማይመጥናትን ትንሽ ነገር ማድረግ ነው፡፡ የእኛ ልጆች ነገ ላይ በመልካም ሀገርና በመልካም ማኅበረሰብ ውስጥ እንዲኖሩ ዛሬ ላይ ካለን ላይ ቆርሰን፣ ከሰራነው ላይ ገምሰን ለሀገራችን ልንሰጥ ይገባል፡፡
ደስ እያለን በኃላፊነት መንፈስ የሚጠበቅብንን ግብር መክፈል ባህላችን ልናደርገው ይገባል፡፡ ቀደም ሲል እንደሰማነው፣ አዲስ አበባ ውስጥ ካሉ በርካታ ግብር ከፋዮች ውስጥ 300 ብቻ የሚሆኑት ናቸው ግዴታቸውን አውቀው ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ያሉት፡፡ ሌሎቻችንስ፣ ለሀገራችን ታማኝና ብቁ መሆን ለምን አቃተን? እንደ ሀገር የግብር ከፋዮችን አሃዝ ስናየው ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ አብዛኞቹ በሚባል ደረጃ ተገደውና ተለምነው የሚከፍሉ ናቸው፡፡ በአንድ ሀገር ላይ የማኅበረሰቡ የግብር መክፈል ንቃት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ግዴታ ብቻ ሳይሆን ደስ ብሎን ግብር መክፈልን ልማድ እስካላደረግን ድረስ ከድህነት እና ከኋላቀርነት የምንወጣበት መንገድ እያራቅነው የመሄዱ እውነታ ብዙም ለጥያቄ የሚቀርብ አይሆንም፡፡
እንደሀገር የራቁብን የስኬት መንገዶች፣ ያልተከፈቱልን የሰላም በሮች ይህን ከመሰለውና ግዴታን ካለማወቅ በሚመነጩ አጉል ልማዶች የመነጩ ናቸው፡፡ ስልጣኔ መብትን መጠየቅ ብቻ ሳይሆን ግዴታንም ማወቅ ነው፡፡ በአንዱ ውስጥ አንዱን አጉድሎ ስልጣኔ የለም፡፡ መብትና ግዴታ መሳ ለመሳ ሲሄዱ ነው ሀገር ሰለጠነች፣ ማኅበረሰብ ዘመነ የሚባለው፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ መጋቢት 18 ቀን 2015 ዓ.ም