የጽንሰ ሃሳብ ማፍታቻ፤
“ግዞት፡- እስራት፣ ቅጣት፣ አንድን ሰው ከሚኖርበት አካባቢ፣ አገር፣ ባህል፣ ሥነ ልቦና፣ ማሕበራዊ መስተጋብር ወዘተ. በማውጣት ባዕድ ወደ ሆነ ማሕበረሰብ፣ ቦታ ወይንም አካባቢ በልዩ ጥበቃና ክትትል ውስጥ እንዲኖር አስገድዶ ማኖር ሲሆን ግዞተኛ ደግሞ በግዞት ላይ ያለ ሰውን ይመለከታል። ” ከመዛግብተ ቃላት የተውጣጣ ብያኔ (Definition) ነው።
ግዞት ከባርነት ትርጉም ጋር ተቀራራቢ ይዘት ያለው ይምሰል እንጂ በጽንሰ ሃሳብ ደረጃ ባህርያቸው ደመቅ ብሎ ይለያል። “ባርነት የሰው ልጅ እንደ መናኛ ሸቀጥ አልባሌ ዋጋ ተተምኖለት በፈንጋዮች ወይንም በአስገባሪዎች አማካይነት ለገበያ ቀርቦ የሚሸጥበት ወይንም በቁስ የሚለወጥበት ኢሰብአዊ (ሰይጣናዊ) ተግባርም የኑሮ ዘይቤም ነው። ”
በአንፃሩ ግዞት በአሸናፊ ጦረኞች፣ ወራሪዎች፣ በሹመኞች ወይንም በማዕከላዊ የመንግሥት ገዥዎች ትእዛዝና እውቅና አሸናፊነትን ወይንም የሥልጣን አቅምን ለማሳወቅ ወይንም ለመያዣነት ግለሰቦችን ወይንም በርከት ያሉ ሰዎችን ወደ ተለየ ሥፍራ ወስዶ ማስፈር ነው።
አንዳንድ አገራዊ የግዞት ታሪኮችን እናስታውስ። እብሪተኛው የፋሽስት ሠራዊት ኢትዮጵያን ወሮ በቆየባቸው ዓመታት (ከ1928 እስከ 1933 ዓ.ም) በርካታ ዜጎቻችንን አዚናራ በሚባል የአገሩ አካባቢና በቀይ ባህር ላይ ወደሚገኝ ናኩራ ወደተባለ ደሴት በማጋዝ ከፍተኛ ፋሽስታዊ ድርጊት ፈጽሞባቸዋል።
ከዓመታት በፊት “ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር ከተዋሃደችበት ታሪክ ጋር ተያይዞ” ስማቸው በተለያዩ መልኮች ደጋግሞ የሚነሳውን ክቡር ቢትወደድ አስፍሃ ወ/ሚካኤልን ይህ ጸሐፊ አዲስ አበባ ይገኝ በነበረ መኖሪያ ቤታቸው ተገኝቶ በፋሽስት ወረራ ዘመን ተግዘው በአዚናራ ደሴት በነበሩበት ወቅት ሕይወትና ተስፋ ምን ይመስል እንደነበር ጠይቋቸው የሰጡትን ዝርዝር መልስ በአንድ መጽሔት ላይ ታትሞ ተነቧል። የግዞት አስከፊነት ምን ያህል የመረረና የከበደ እንደሆነ ከእኚህ አባት ምስክርነት የማላውቃቸውን ብዙ እውቀቶች ቀስሜያለሁ።
ያንን የእርሳቸውን ክፉ ትዝታ በሚገባ እንዲወክልልኝ በክብር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል “የአዝናራ እስረኛ” ግጥም ውስጥ ከተካተተው ረዥም ተራኪ ሥራ ውስጥ ጥቂት ስንኞችን እንደሚከተለው እጠቅሳለሁ።
“ቀና ቢሉ ሰማይ ጎንበስ ቢሉ ምድር፣
ቀኝ ቢያዩ ጋራ ግራ ቢያዩ ባሕር፤
ቦታው የጭካኔ የጭንቅ የመከራ፣
ጥንትም ኖሯል ለካ ቦታው ልማደኛ፤
ባለም ጦርነት ላይ ገብቶበት እስረኛ፣
መቃብር ሆኖታል ለጀርመን ምርኮኛ።
ባንድ ወገን ባሕር ነው፣ ባንድ ወገን ተራራ፣
እዚያ መካከል ነው የእስረኞች ስፍራ።
ባፈሳ ተይዘው እየተጎተቱ፣
ከኢትዮጵያ ወጥተው እየተንገላቱ፣
በዱር በበረሃ ታመው እየሞቱ። ”
ትረካው አልተቋጨም። ሙሉው ግጥም “የቅኔ አዝመራ” ከሚለው መጽሐፍ እንዲነበብ እያበረታታሁ ግዞትን ወደ ተመለከተ ሌላ የታሪክ ማስታወሻ ልለፍ።
እብሪተኛው የሱማሊያ ጦር በ1969 ዓ.ም ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅትም እንዲሁ በርካታ ዜጎቻችን ደናን (ደናኔ) ወደተባለ አካባቢ በቁጥር በርካታ ወገኖቻችንን በግዞት አፍልሶ ወስዷል። ከግዞተኞቹ መካከል ጥላሁን አትሬሶ “የእኛ ሰው በሶማሊያ እስር ቤቶች”፣ የከበደች ተክለአብን “የት ነው?” በሚል ርዕስ ያሳተመችውን ድንቅ የግጥም መድብል እና ሊሻን አጎናፍር “የምድረ በዳው እረኛ” በሚል አርእስት የተጻፉትን መጻሕፍት ማንበቡ የመራሩን የግዞት ሕይወት ምንነት በሚገባ መገንዘብ ይቻላል። ከግዞተኞቹ መካከል አንዱ የነበሩት ዶ/ር ጥበቡ ኃይለ ሥላሴ የደናንን የግዞት ሥፍራ የገለጹት እንዲህ በማለት ነበር።
“የደናን እስር ቤት በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጊዜ ጣሊያን ደቡብ ሱማሊያን ወርራ በነበረበት ወቅት የተቋቋመ ወህኒ ቤት ነው። ከውጭ ለሚያየው የማይደፈር ጥንታዊ ምሽግ ይመስላል። ከምድር ወደ ላይ ከፍታ እና በረዥሙ የታጠረው የድንጋይ ግንብ የወህኒውም የውስጥ ግድግዳ ስለሆነ ትንንሽ መስኮቶች በግንቡ ዙሪያ ይታያሉ። …ወታደሮች በየቀኑ እስረኞቹን ከክፍላቸው እያወጡ በግፍ እየደበደቡና እያዳፉ ወደ ተለያየ የጉልበት ሥራ የሚያሰማሩበት ትልቅና ሰፊ ክፍት ሜዳ ግቢው መሃል ይገኛል (ገጽ 170)።
ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ የአንድ አገር ሕጋዊ መንግሥት ሥልጣኔን ተቀናቅኖኛል፣ አድሞብኛል፣ ወይንም የመንግሥቴን ክብር አቃሏል ወዘተ. ተብሎ የተጠረጠረን የራሱን ዜጋ ወይንም የመንግሥትን ሹመኛ በቅጣት መልክ ራቅ ወዳለ ዳር አገር በመላክ በጥብቅ ክትትልና ጥበቃ ሥር ሆኖ ለተወሰነ ጊዜ እንዲቀጣ ማድረግም የተለመደ “መንግሥታዊ ተግባር” ነበር። ግዞተኛው የተወሰነበትን የቅጣት ጊዜ ሲያጠናቅቅ ወይንም በወሰነው አካል ምህረትና ይቅርታ ሲደረግለት ከግዞቱ ቦታ ወደ ቀድሞ ሕይወቱ ተመልሶ የተለመደውን ኑሮውን ሊኖር ይችላል።
ለኢትዮጵያ ፊውዳላዊ ሥርዓተ መንግሥታት ግዞትና ግዞተኝነት የባህል ያህል ለፖለቲካ አካሄዱ ቤትኛ እንደነበር በተለያዩ ታሪኮቻችን ውስጥ ተጽፎ እናነባለን። ለምሳሌ፡- “አቤቶ እያሱ አጤ ምኒልክ ታመው አልጋ ላይ በዋሉበት ጊዜ ሥልጣነ መንግሥቱን ይቀናቀናሉ ተብለው የጠረጠሯቸውን እቴጌ ጣይቱንና ወይዘሮ ዘውዲቱን (በኋላ ንግሥተ ዘውዲቱ) በግዞት መልክ ጣይቱን እንጦጦ ይገኝ በነበረው ቤተ መንግሥት፣ ዘውዲቱን ደግሞ ሙሎ ወረዳ ፋሌ በሚባለው አካባቢ ርስታቸው ላይ ከሥልጣን ወንበሩ ፊት ገለል በማድረግ ለተወሰነ ጊዜ አርቀዋቸዋል። ልጅ እያሱም እንዲሁ ዕድል ፊቷን አዙራባቸው ቀን ከጣላቸው በኋላ ኩረማሽ፣ ፍቼ እና ሀረርጌ (ጋራ ሙለታ) ባለጊዜ አሸናፊዎቹ ከቦታ ቦታ እያዟዟሩ የግዞትን ዋንጫ እንዲጎነጩ አድርገዋቸዋል።
እጅግ በርካታ መጻሕፍትንና የቴያትር ሥራዎቹን ያወረሰን ታዋቂው የሥነ ጽሑፍ ሰው አቤ ጉበኛ በድርሰት መጻሕፍቱ አማካይነት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ሥርዓተ መንግሥት ክፉኛ ይተች ስለነበር በቀድሞው የኢሉባቦር ጠቅላይ ግዛት ጎሬና ሞቻ ውስጥ ተፈርዶበት የግዞት ኑሮ እንዲገፋ ተደርጓል። በግዞት ላይ እያለም በሚከተሉት አጫጭር ሰም ለበስ ስንኞች ቁጭቱን ይገልጽ ነበር።
“አውሬ መስያቸው ፈሩኝ ዘመዶቼ፣
ድንገት ቢያዩኝ ጊዜ ከጎሬ ወጥቼ።
ሰሙ፡- ከተሸሸግሁበት ጉድጓድ (ከጎሬ) ውስጥ ወጣሁ የሚል ሲሆን፤ በወርቅ የሚመሰለው ፍቺ ደግሞ “ጎሬ ተግዣለሁ” ማለት ነው።
የምትፈልጉኝ ወዳጅ ዘመዶቼ ስሙልኝ ሮሮ፣
ተስፋ እንዳታደርጉ ሞቻለሁ ዘንድሮ። ”
ስለ ሞቻ የተጠቀሰው ግጥም በትክክል ስለመታወሱ እርግጠኛ ባልሆንም የመልእክቱን ሃሳብ ግን በሚገባ ይገልጻል። ሰሙ ለሞት ተዳርጌያለሁ (ሞቻለሁ) ሲሆን ወርቁ ደግሞ “ሞቻ ውስጥ በግዞት ተጥያለሁ” ማለት ነው።
በግዞትና በግዞተኝነት ጉዳይ ላይ ይህንን ያህል በሰፊ ትንተና ከተንደረደርኩ ዘንድ ወቅታዊና ዐውዳዊ አገራዊ እውነታችንን በተመለከተ በአስተሳሰብ ግዞተኝነት ጉዳይ ላይ ጥቂት ሃሳቦችን ልፈነጣጥቅ።
“ግዞተኛ አስተሳሰብ በድፍን ቅል ይመሰላል”
የአስተሳሰብ ግዞተኝነት ከአካላዊ ግዞት እጅግ የከፋና የሚያስከትለው ውጤትም በቀላሉ የሚታይ አይደለም። አካላዊ ግዞት ጠባሳ አኑሮ የሚያልፈው በአንድ ግለሰብ ወይንም በቅርብ ዘምዶችና ወዳጆች ላይ ብቻ ሊሆን ይችላል። የአስተሳሰብ ግዞተኛ ሆኖ አእምሮን በተለያዩ ቁልፎች ቆልፎ ማሕበረሰብን ለመምራትና ለማገልገል መሞከር ግን ውሎ አድሮ የከፋ ውጤት ማስከተሉ አይቀርም።
የአስተሳሰብ ግዞተኝነት በልማድ፣ በወግና በቋንቋ፣ በብሔርና በጎጥ፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ ሥርዓቶችና በማሕበራዊ ተራክቦ ውስጥ ተጠናክሮ ሲንሰራፋ አገር እያነሰና የዕድገት ምኞትና ተስፋ ቁልቁል እንደ ካሮት ሥር እየሰደደ ሄዶ አደጋ ላይ መውደቅ አይቀሬ ነው። የመጀመሪያው የጋና ጠቅላይ ሚኒስትርና ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶ/ር ፍራንሲስ ክዋሚ ንክሩማ ከቅኝ ገዢዎች የተላቀቀችውን አገራቸውን በነፃነት ዋዜማ የገለጹት እንዲህ በማለት ነበር። “Ghana got a flag and anthem in 1957. But, it didn’t get real independence.”
ጋናን ብቻ ሳይሆን የአፍሪካውያንን የአስተሳሰብ ግዞተኝነት በተመለከተ ከልጆቿ ቁጭት ውጭ እጅግ የጠነከሩ የምጸት፣ የትችትና የማዋረድ አገላለጾች በምእራቡ ዓለም ጸሐፍት፣ ምሁራንና ተንታኞች እንደ ጉድ ሲዘንቡ እንደኖሩ በሚገባ ይታወቃል። “አፍሪካ ራሷን ከመለወጥ ይልቅ በታሪክ ኩራት ተለክፋ የኖረች አህጉር ነች – Africa is a continent to be history’s permanent victim” የሚለው ገለጻ በብዙ የታሪክ መጻሕፍት ውስጥ ተደጋግሞ ተጠቅሷል።
መሰል ገለጻዎችን በመደርደር አፍሪካን ማሰስም ሆነ ሩቅ ተጉዞ ማሳበብ ሳያስፈልግ የአገራችንን ጉዳይ ብቻ መፈተሹ በቂና ከበቂ በላይ ማስተማሪያ ሊሆን ይችላል። በተለይም ዛሬ የተዘፈቅንባቸውን አገራዊ ሁኔታዎችና ግራ አጋቢ ጉዳዮቻችንን ጫንና ጠንከር ብለን እንድንፈትሽ ግድ የሆነበት ወቅት ላይ የደረስን ይመስላል።
ፖለቲከኞቻችን በአዲስ አስተሳሰብና አመለካከት ተቃኝተው ራሳቸውን ከግዞተኝነት በማላቀቅ ነፃ እንዳይወጡ ዛሬም ተራራ የመውጣት ያህል ወኔያቸውና ጉልበታቸው ከድቷቸው ሲንፏቀቁ እያስተዋልን ነው። እንደ እኛ እንደ ኢትዮጵያውያን በግል አስተሳሰብ ለለውጥ ግትር በመሆን እኔነትን የሙጥኝ ብሎ የሚኖር ሌላ አገር ስለመኖሩ እርግጠኛ መሆን ያዳግታል። አለ ከተባልንም ዝርዝሩ ይገለጽልንና ራሳችንን እየፈተሽን እንማርበታለን።
ለምሳሌ፡- የሶሻሊዝም ሥርዓት ሞቶና ተገንዞ መቃብር መውረዱ ተረጋግጦ እያለ እንኳን አንዳንድ ፖለቲከኞቻችን መቃብሩን ቆፍረው በድኑን በማውጣት የአበባ ጉንጉን አንገቱ ላይ ሊያጠልቁ ሲያላዝኑ ስንመለከት “ይብላኝላችሁ!” ማለታችን አልቀረም። የሚያሳዝነው ነገር ይህ የአስተሳሰብ ግዞተኝነት የሚስተዋለው “ተቃዋሚ” በሚል ፍረጃ በተለዩት የፖለቲካው ቤተሰቦች ዘንድ ብቻም ሳይሆን አገር እመራለሁ የሚለው የገዢው ፓርቲ በርካታ ካድሬዎችም ዛሬም ድረስ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ዐይነ ጥላ ሊገፈፍላቸው ስላልቻለ ሞቶ ለተቀበረው ውል አልባ ፍልስፍና ሙሾ አውራጆች ሆነው ሲያረግዱ መመልከት በእጅጉ ለትዝብት ይዳርጋል።
በሰፌድ ላይ እንደሚበጠር ጥሬ አገራችንን እያንቀረቀበ አሳሯን በማብላት ላይ የሚገኘውና ጥቂቶችን ብቻ ተጠቃሚ ያደረገውን የፅንፈኝነት ፖለቲካ “እንዳትነኩብን” በሚሉ የአስተሳሰብ ግዞተኞች አማካይነት አገሬ አሳሯን እየገፈገፈች ትገኛለች። ዓለም ባከበረው ታሪክ መስማማት ተስኖን፣ በየራሳችን ጎራ ፀጋችን በሆኑት ቋንቋዎችና ባህሎች ተከባብረን፣ ተደናንቀንና ተቀባብለን አብረን ከማደግ ይልቅ “የእኔ ካንተ ይሻላል፣ ከቅርቡ የጋራ ቅርሳችን ይልቅ የሩቁ ይበልጥብናል” እየተባባልን እንደ መመከቻ ጋሻና በጉራጌዎች አገላለጽ እንደ የወፎች ማስፈራሪያ “አውከሬ” በነተበ አስተሳሰብ ግዞተኝነትን መርጠን “ይዋጣልን!” እያልን መፋለም ጀግንነት ሳይሆን ድኩምነት ነው። የንጹሐን ደምን በማፍሰስ ጀግንነትን ለማሳየት መሞከርም ሽንፈት ብቻ ሳይሆን ሰማያዊ ቅጣት የሚያስከትል የእሳት ፍም በራስ ላይ ከመሸከም የሚተናነስ አይደለም።
በአስተሳሰብ ግዞት አእምሯቸውን ባጠሩ ጥቂት ቡድኖች ወይንም ጀብደኛ የዕለት ተዕለት ተግባር ግለሰብ ዜጎች በነፃነት ከቦታ ወደ ቦታ እንዳይንቀሳቀሱ ማገድና መገደብ ስያሜ የሌለው የግፍ ድርጊት ነው። የአገራችን የአስተሳሰብ ግዞተኝነት ተኮትኩቶ የበቀለው በውጭ አካል ተጽእኖ ሳይሆን እኛው ራሳችን ዘርተን በማሳደጋችን መሆኑ ለክርክር አይጋብዝም።
የአስተሳሰብ ግዞተኝነት ከሌሎች ሰዎች እውቀትንና ጥበብን፣ በጎ ተሞክሮዎችንና ልምምዶችን ከመቅሰም ይልቅ በራስ አስተሳሰብ ታጥሮ መኖርን የሚያበረታታ አመለካከት ነው። የሌሎች መልካምና በጎ ሃሳብ ለግዞተኛ ሰው አይጥመውም። እርሱ ካለው ውጭ አንዳች ነቁጥ ተግባራዊ ከሚሆን ይልቅ “ሰማይና ምድር ቢያልፉ ይመርጣል።
”እንደ ሰፈር በጠበበችው ዓላማችን እውቀት እንደ ንፋስ በተዘራበት ዘመን የአስተሳሰብ ግዞተኞች “ጎሬያቸው ውስጥ መሽገው” አናይም፣ አንሰማም፣ አናስተውልም ብለው መወሰናቸው መብታቸው ቢሆንም፤ የቆለፉበት አእምሯቸውና አስተሳሰባቸው ተፈትቶ ነፃ እስካልወጡ ድረስ ተገንዘው ሲቀበሩ የሚደረደርላቸው የሙሾ ግጥም “ተኖረና ተሞተ” እየተባለ መሆኑን ሊረዱት ይገባል።
እንደነዚህ ዓይነት የራስ አስተሳሰብ ግዞተኞችን አሊክ ሻሃዳድ የተባለ በመወለድ ጀርመናዊ፣ እድገቱ በካሬቢያን፣ ኑሮውን በአሜሪካና በእንግሊዝ ያደረግ የፓን አፍሪካ አቀንቃኝ ሙዚቀኛና የፊልም ባለሙያ ስለ አስተሳሰብ ግዞተኞች እንዲህ በማለት ተናግሮ ነበር።
“ጥማቸውን እንዲያረኩ ንጹሕ ውሃ በብርጭቆ ብትሰጧቸው እየዋኘን ካልሰመጥንበት ብለው ለያዥ ለገራዥ ያስቸግራሉ። እንደ ተራራ የገዘፈውን የራሳቸውን ችግር በአሸናፊነት እንዲወጡ የመወጣጫ ”ገመድ” ብታቀብሏቸው ካልተሰቀልንበት ብለው ይወራጫሉ። ” ለሰብእና ክብር ደንታ በሌላቸው ጉልበተኞችና “ዘመን ባገነናቸው ምን ግዴዎች” ተጽእኖ ሥር ወድቀው የአስተሳሰብ ግዞተኛ ሆኖ ከመኖር ይልቅ፤ አንድ ቀን ነፃ መውጣቴ አይቀርም እየተባለ ተስፋ በሚደረግበት አካላዊ ግዞት መቀጣት በብዙ ይሻላል። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 16/2015