አበው ሲተርቱ ‹‹የሚያድግ ልጅ አይጥላህ የሚያልፍ ዝናብ አይምታህ ›› ይላሉ። ተረቱ ሁሉም በጊዜው መስመር ሊይዝ እርምጃህን በወግ አድርገው ለማለት ይመስላል›› ድንገቴው የሰሞኑ ዝናብ ግን እንደአባባሉ ቶሎ ያልፍ አይመስልም። ዘንቦ ባባራ ቁጥር ክፉ ዜናዎችን ያሰማን፣ ያሳየን ይዟል።
በአምና ካቻምና ተሞክሮ ዝናቡ ይህን ጊዜ እንደወጉ ደርሶ፣ እንደዓመሉ አድርሶ ይመለስ ነበር። ብዘዎች እንደሚሉትም በዚህ ወቅት የሚመጣ ዝናብ ለበልጉ እርሻ እጅግ ተፈላጊና ተስማሚ ነው። ዘንድሮ ግን የአመጣጡ ጉዳይ ከዓመል መለወጥ ጋር ሆኗል። በበጋው ጸሀይ መሀል እንግዳ ሆኖ የከረመው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ዋጋ እያስከፈለ ነው።
ከሰሞኑ በከተማችን አዲስ አበባ አምርሮ የሚጥለው ከባድ ዝናብ ጎርፍ አስከትሎ ህይወትን ቀጥፏል። ንብረት አውድሞ መንገድ ድልድዮችን ሰብሯል። የድንገቴው ከባድ ዝናብ ጉዳይ ማባራትን ተከትሎ ወደጆሮ የሚደርሱ ክፉ ዜናዎች ደግሞ የጉዳዩን አሳሳቢነት ያመላክታሉ። በቅርቡ አገር አማን ብለው ከታክሲ ገብተው ጉዞ የጀመሩ መንገደኞች ያላሰቡት ገጥሟቸዋል። የመንገደኞቹ ጉዞ በምሽት ነበር። እዚሁ መዲናችን አዲስ አበባ።
ታክሲው ተሳፋሪዎቹን እንዳጨቀ መፍጠኑን ይዟል። ሰዓቱ እየገፋ፣ ጊዜው እየጨለመ ነው። በውስጡ ያሉት ተሳፋሪዎች የዝናቡን ማጉረምረም እያስተዋሉ ከቤታቸው ለመግባት ተጣድፈዋል። ለሾፌሩ መንገዱም ሆነ መንገደኞቹ አዲሶች አይደሉም። በየዕለት አጋጣሚው እነሱን መሰል ተሳፋሪዎች ይዞ መጓዙ የተለመደ ነው።
መንገዱ ቀጥሏል። በየወንበሩ ከልክ በላይ የጫነው ታክሲ የእግር ማሳረፊያ ይኩት የለውም። በታክሲው ተቀምጠዋል ከተባለ ከመሬት ኩርምት ያሉ መንገደኞች ጭምር ተካተዋል። ሾፌሩ አንድ ከተባለ በውስጡ ሀያ አንድ ሰዎች ተቆጥረው ታጭቀዋል።
ታክሲው ቀስ እያለ የማዝገሙን ጉዳይ ተሳፋሪው የወደደው አይመስልም። ሁሉም ‹‹መጣሁ›› ካለው ከባድ ዝናብ አምልጦ ቤቱ መግባትን ይፈልጋል። ጉዳዩ እንደታሰበው አልሆነም። ዝናቡ እየጨከነ፣ ክፉኛ እያመረረ ነው። ጉልበቱን በከባድ ወጨፎው ተገልጾ እያሳወቃቸው ነው።
በዚህ ብቻ አልበቃውም። ጥቂት ቆይቶ ወጨፎው በሀይለኛ ዝናብ ተተካ። ሆዱን ሞልቶ ጉዞ የጀመረው መኪና ጭንቅ ያዘው። ከውስጥ ያሉት ሰዎች እየሆነባቸው ያለውን ጉዳይ አምነው መቀበል አልቻሉም።
አሁን የታክሲው ግማሽ ወገብ በደለልና በጎርፍ ተውጧል። አንድም ሰው በቀላሉ ወርዶ ማምለጥ አይችልም። የታክሲው ውስጥ ሰዎች አይቀሬውን ገጠመኝ ሊጋፈጡት ግድ ሆነ። ራሳቸውን ከችግሩ የታደጉ የመሰላቸው ጥቂቶች መላ ያሉትን ዘየዱ። ፈጥነው ከታክሲው አናት ኮፈኑ ላይ ወጡ። መፍትሄ የለም። ዝናቡ ያለማቋረጥ ቀጥሏል። ጭንቀቱ ያለቅጥ በርትቷል።
ከላይ ዝናብ፣ ከስር ጎርፍና ደለል ባስጨነቀው ታክሲ ያሉ ሰዎች ‹‹ድረሱልን›› እያሉ ነው። ሰሚ የለም። ከነዚህ መሀል ዘጠኙ ሴቶች ናቸው። ማንም ከአፍታ በኋላ የሚሆነውን አያውቅም። ጊዜው በተስፋም ያለተስፋም እየሄደ ነው። የበረቱ ስልካቸውን ይደውላሉ፣ ወደ ወዳጅ ቤተሰብ፣ ጓደኛና ጎረቤት ዘንድ። ውሀው ወገባቸውን አልፎ ከትከሻቸው የደረሰ ተሳፋሪዎች አሁንም ተጨንቀዋል። ለእርዳታ ከሚደውሉ ስልኮች መሀል በድንገት አንደኛው መስመር ተነሳ። የአዲስ አበባ እሳትና ደንገተኛ አደጋዎች ክፍል ነበር።
መልዕክት ተቀባዩ ስልኩን እንደዘጋ ጊዜ አላባከነም። ጥቆማ በደረሰው ቦሌ አካባቢ አስፈላጊውን ቡድን አሟልቶ በፍጥነት ገሰገሰ። የአደጋ ጊዜ ተጠሪዎች በስፍራው ሲደርሱ ሀይለኛው ዝናብ እንደቀጠለ ነበር። እንዲህ መሆኑ እርዳታውን ፈጥኖ ለመከወን አዳጋች አደረገው።
ሀያ አንዱን ተሳፋሪዎች እስከ አንገታቸው ከዋጣቸው ጎርፍ አውጥቶ ታክሲውን ከገባበት የደለል ማጥ ለማንቀሳቀስ ሁኔታው ከባድ ሆኖ ቆየ። በመጨረሻም በአደጋ ጊዜ ባለሙያዎች ብርታትና በሌሎች ሰዎች እገዛ ሕይወት ሳይጠፋና የከፋ ጉዳት ሳይደርስ ችግሩን መታደግ መቻሉን ከሚመለከተው ክፍል መረጃው ተላለፈ።
በዚህ ቀን በደረሰው ተመሳሳይ ክስተት በዝናቡ ሰበብ መንገድ ጥሶ የገባ ድንገቴ ጎርፍ በመኖሪያ ቤቶችና በርካታ ንብረቶች ላይ ጉዳት አድርሷል። ይህ የበጋ ዝናብ ጉዳይ በእንዲህ አይነቱ ገጠመኝ ብቻ አልተቋጨም። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ‹‹ማንጎ ጨፌ›› ከሚባል ስፍራ ድንገቴው ዝናብ ከወንዝ አብሮ የአራት ሰዎችን ህይወት ቀጥፏል።
መረጃዎች እንደጠቀሙት ጎርፉ ከሌላ አካባቢ ተጠራርጎ አካባቢውን ያጥለቀለቀ ነው። በአካባቢው ቤቶችን እየጣሰ፣ ግድግዳ እየገመሰ ጉዳት አድርሷል። በድንገቴው ዝናብና አደጋውም አንዲት እናት ከሶስት ልጆቿ ጋር ህይወቷን አጥታለች።
የአጋጣሚው መከሰት አንድ ጉዳይ ሆኖ ለአደጋው መባባስ መንስኤ የሚሆኑ ሰበቦችን መገመት ይቻላል። በቅድሚያ በታክሲው የተከሰተው ድንገቴ ጉዳይ እንቃኝ ብንል ከመጠን በላይ ሀያአንድ ሰዎችን የማሳፈሩን ስህተት ነቅሶ ማየቱ ተገቢ ነው።
በእርግጥ ታክሲው በተፈቀደለት ቁጥር ልክ መጫኑ ብቻ ከአደጋ አያድነውም ሊባል ይችላል። በወቅቱ በልክ ማሳፈሩ ግን ሊደርስ የሚችለውን የአደጋ መጠን ሊቀንስለት እንደሚችል ልብ ይሏል። ምንአልባት የከፋ አደጋ አጋጥሞ ህይወት ቢያልፍና አካል ቢጎዳ ቁጥሩ በግማሽ መቀነሱ የጉዳት መጠኑን የተሻለ ያደርገዋል።
ሰሞኑን እየሆነ ያለውን ክስተት መነሻ በማድረግ በአንዳንድ አካባቢዎች ያለውን እውነታ እንፈትሽ። ተደጋግሞ እንደሚባለው ድንገቴው ዝናብ የሚያስከትለው የጎርፍ አደጋ መንስኤ በየስፍራው የሚደፈኑ የውሀ መፋሰሻ ቱቦዎች ያለልክ መደፈን ነው። ለዚህ ደግሞ የቆሻሻ አወጋድ ልማዳችንን ተጠቃሽ ማድረጉ ብቻ በቂ ይሆናል።
አንዳንዴ ሰዎች በአንድም ይሁን በሌላ ጉዳይ በራሳችን ላይ ለሚከሰት ችግር ተጠያቂ የምንሆንበት አጋጣሚ ይኖራል። ሙዝ በልቶ ከጎዳና ላይ ጥሎ ያለፈ መንገደኛ ሲመለስ በጣለው ልጣጭ ተንሸራቶ ቢወድቅ ለስብራቱ ማንንም ተወቃሽ ሊያደርግ አይገባም። ‹‹እጄን በእጄ›› ይሉት ነውና ጉዳቱ መልሶ ራሱን የሚጎዳው ይሆናል።
አብዛኞቻችን በ‹‹አዩኝ አላዩኝ›› ስሜት ዛሬን ከቱቦ የምንወረውረው ቆሻሻ ውሎ አድሮ ዋጋ ያስከፍለናል። ለውሀ የተባለው መፋሰሻ በቁስ ጥርቅም በተዘጋ ጊዜ ውጤቱን ለማየት ቀን መቁጠር፣ አልያም ክረምቱን መጠበቅ አይኖርብንም። እንዲህ እንደሰሞኑ ክስተት በገዛ እጃችን አጥብቀን በምናስረው ገመድ ተጠልፈን ለመውደቅ የተመቸን እንሆናለን።
ችግሩ ከደረሰብን በኋላም በሌሎች ላይ ጣት ለመቀሰርና ኃላፊነቱን ላለመውሰድ ፈጣኖች ነን። ይህ እንዳይሆን ጥንቃቄ ከራስ ሊጀምር ግድ ይላል። ዛሬ በእኛ ሰበብ በሚፈጠረው ግዴለሽነት ነገን በስጋት ለሚያድሩ ወገኖች ሰበብ ልንሆን አይገባም።
ዛሬ የወንዝ ዳር ቤቶች ዕንቅልፍ የላቸውም። ዳምኖ ባካፋ ቁጥር የሚሆነውን አያውቁምና ስጋታቸው ያይላል። እንዲህ እንደ ሰሞኑ በጸሀይ ተዋዝቶ፣ በዳመና ተሸፍኖ ‹‹መጣሁ›› የሚለው የዝናብ እንግዳ በማን ላይ ምን እንዳሰበ መገመቱ ከባድ ነው። ትንሽ ነው የተባለ ካፊያ በአፍታ የበረዶ ክምር ሲሆን ያስደነግጣል። ምክንያቱም ያለንበት ምድር ኢትዮጵያ እንጂ አውሮፓና አሜሪካ አይደለም።
‹‹ግባ›› አይሉትን ድንገቴ ደራሽ ከበር ለመሸኘት አስቀድሞ መዝጊያን ማጠንክር፣ ተግባርንም ማጥራት ግድ ይላል። ዛሬ በእኛ ምክንያት ለሌሎች መጎዳት ሰበብ ልንሆን አይገባም። ሁሌም ለአደጋ መንስኤ በመሆን ከመተባበር እንጠበቅ፣ ‹‹ነግ በኔ›› ስንል ስለራሳችን እንጠንቀቅ።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን መጋቢት 16/2015