በኢትዮጵያ የሙዚቃ ኢንደስትሪ ውስጥ የማይሞት ስም ካላቸው ድምጻውያን መካከል ይጠቀሳል፡፡ እሱ ካለፈ ዓመታት ቢቆጥሩም ሙዚቃዎቹ ዛሬም ድረስ እንደ አዲስ የሚደመጡ ሙዚቃዎች ናቸው፡፡ ብዙ የሙዚቃ ልሂቃንም የእሱ የዜማ መንገድ እና ሙዚቃዎች ዋጋቸው በጣም ከፍ ያለ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ የዛሬው ትውስታችን ታላቁ ድምጻዊ ታምራት ሞላ ላይ ያተኮረ ነው፡፡
አርቲስት ታምራት ሞላ በ1936 ዓም ከአባቱ ከፊት አውራሪ ሞላ ዘለለው እና ከእናቱ ከወይዘሮ አበራሽ የኔነህ፤ በጎንደር ከተማ ተወለደ። በ1953 ዓም የ17 አመት ጎረምሳ ሲሆን ከጎንደር ወደ አዲስ አበባ ከአጎቱ ጋር በመምጣት በክቡር ዘበኛ የልጅ ወታደር በመሆን የሙዚቃውን አለም ጉዞውን አሃዱ ብሎ ጀመረ።
በ1955 ዓም አብዛኛውን የሙዚቃ ህይወቱን ያሳለፈበትን የምድር ጦር ሰራዊትን የተቀላቀለው አርቲስት ታምራት፤ ሃገራዊ፣ ማህበራዊ እና ፍቅርን መሰረት ያደረጉ ሙዚቃዎችን ከመጫወቱ ባለፈ ድራማ እና ቴአትርን ምክንያት አድርጎ መድረክ ላይ መቆም መቻሉን ታሪኩ ያስረዳል። በተለይም ትግላችን በሚል ቴአትር በመሪ ተዋናይነት ከመጫወቱም ባለፈ፥ የበርካታ ዜማዎች ድርሰትን ቀምሮ ለህዝብ አቅርቧል። በሃገር ፍቅር ቴአትር ቤት ለረጅም ጊዜ በድምጻዊነት ያገለገለው አርቲስት ታምራት፥ ከ50 ዓመታት በላይ ባስቆጠረው የሙዚቃ ህይወቱ ከአድማጭ ጆሮ የማይጠፉና የማይረሱ ሙዚቃዎችን ተጫውቷል።
ታምራት ከተጫወታቸው ሙዚቃዎች መካከል አብዛኞቹ ዛሬ ላይ በምሽት ክበቦች ወጣት ድምጻውያን ይጫወቷቸዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ታምሜ ተኝቼ ፤ ስንዋደድ ፤ የሾላ ፍሬ ነሽ ፤ በምን ቃል ላስረዳሽ ፤ ማን ነበረ ቆንጆ እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ አርቲስት ታምራት በተለያዩ ሃገራዊ ተሳትፎዎች ላይ ኪነ ጥበቡን በመወከል በሙያው ሃገሩን አገልግሏል። በተለይም በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ከሙያ አጋሮቹ ጋር በመሆን በአውደ ውጊያው ተገኝቶ የጦር ሰራዊቱን ሲያበረታታ ነበር። በወቅቱ
እናት ኢትዮጵያ ሀገራችን
ያላንቺ ምን አለን ህይወታችን
ብዙ ሺ ዘመናት ተከብረሽ የኖርሽው
በጀግኖች አባቶች አጥንት የታጠርሽው
በእኛም ደም ውስጥ አለ ያባቶች ጀግንነት
ፈጽሞ አይናጋም የኢትዮጵያ አንድነት
ታምራት ተጫውቶት በህዝብ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ ከሆኑት ሙዚቃዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ ዛሬም ድረስ በህዝብ ዘንድ ተወዳጅ ከሆኑት መካከል ታምሜ ተኝቼ የተሰኘው ሙዚቃም ተጠቃሽ ነው፡፡ ይህ ሙዚቃ በቅንብሩ ለዳንስ የተመቸ በመሆኑ በወቅቱም ዛሬም እየተደነሰበት ይገኛል፡፡
ታምሜ ተኝቼ ትላንትና ሌሊት
በህልሜ መጥተሽብኝ ዓይኔ ሲንከራተት
እኔም ወዳንቺ እመለከትና
ይፈሳል ዕምባዬ ሆዴ ይባባና
አልጋዬንም ዘልቆ ትራሴን በሙሉ
በዕምባ ወንዝ ራሰ አንድም ሳይቀር ሁሉ
ታምሜ ተኝቼ ትላንትና ሌሊት
በህልሜ መጥተሽብኝ ዓይኔ ሲንከራተት
በቅንብሩ እጅግ የላቀውና ከዝነኛው የሮህ ባንድ ጋር በመሆን የተጫወተው ፍቅሬ በምን ቋንቋም እንዲሁ ሌላኛው ተወዳጅ ሙዚቃው ነው፡፡ ይሄ ዘፈን የወጣው በደርግ ዘመን በ1977 ዓ ም በድርቅ ለተጎዱ ወገኖች ገቢ ማሳበሰቢያ እንዲሆን ተብሎ በተሰራው ‹‹የብሩህ ተስፋ እሸት›› የሚል ርዕስ በተሰጠው አልበም ውስጥ ከሌሎች ታላቅ ድምጻውያን ሙዚቃ ጋር በጋራ በመሆን ነበር፡፡
ፍቅሬ በምን ቋንቋ በምን ቃል ላስረዳሽ
አብሮሽ ኗሪው ልቤ አንቺን እንዳልከዳሽ
እያለ በዚያ ልብን በሚሰረስር ዜማ ሲጫወተው ስሜቱ የማይነካ ሰው የለም፡፡ አንዳንድ የታምራት ሙዚቃዎች ደግሞ መሰረታዊ የህይወትን ሀቅ የሚያስታውሱ ናቸው፡ ፡ በእርግጥም ወርቃማ ሙዚቀኛ የሆነው በነዚህ ዜማዎቹ ነው፡፡ ለዚህም ጥሩ ማሳያ ስንዋደድ ነው
ስንዋደድ ከልባችን
መሞት ኑሯስ ለካ መሀላችን
በማለት ስብከት የሚመስለውን መሰረታዊ የህይወት ሀቅ በቆንጆ ሙዚቃ ለህዝብ አድርሷል፡፡ ታምራት በሙዚቃዎቹ ለሀገሩ የሚመኘውን ነገርም እንዲሁ በዜማው ገልጧል፡፡ በእድገት በህብረት ዘመቻ ወቅት የተጫወተው ሙዚቃ ለዚህ ምስክር ነው፡፡
‹‹በህይወት ግቡ በህይወት
ዘመቻ የምትሄዱ ለእድገት በህብረት
እውቀት የጠማውን- ከርታታ ገበሬ
እንድትመግቡት -የጥበብን ፍሬ
እዚህ ላይ ነውና -የለውጡ ቁምነገር
ደንቆሮ እንዲሰማ -ዲዳው እንዲናገር
አድባር ትቀበላችሁ- ወገን ይደግፋችሁ
በደስታ በሆታ -እንደሸኘናችሁ
በሳቅ በፈገግታ- እንቀበላችሁ….!
በህይወት ግቡ በህይወት..
ዘመቻ የምትሄዱ ለእድገት በህብረት
ወንዞች ለጋረዱት ገጠሬው ባላገር
ድልድዩን ስሩና -እንደልቡ ይሻገር
እሰፈሩ ድረስ- በፍጥነት ሂዱና
ደረስንልህ በሉት- ከተፍ በሉና!..››
ዶ/ር ጥላሁን ገሠሰ ስለ ታምራት ሞላ ምን ብሎ ነበር?
“ስለ ታምራት ብጠየቅ የቱ ነው ጫፉ የቱስ ነው መጨረሻው በአጠቃላይ ፍቅር ነው። እንደማስታውሰው ታምራትና አለማየሁ እሸቴ የ1954 ዓም የክቡር ዘበኛ ቅጥረኞች ናቸው። ታምራት በትርፍ ሰዓቱም አዲስ አበባና ሹፌሮች ሆቴል ይሰራ ነበር። ሁላችንም አሪዞና ክለብ እንሰራ ነበር። በዚህ ወቅት አንድ የመንግስት ሰራተኛ የሆነ ሰው ሌላ ቦታ መስራት ሰለማይችል በጣም እየተሳቀቅን እርስ በርሳችን በመሸፋፈን ነበር የምንሰራው። ሌላው የማይረሳው በዚሁ ወቅት ታምራት ደሞዜ ወደ 347 ብር ተቆራርጦ እንዲደርሰኝ ተከራክሮ ያስጨመረልኝ እሱ ነው። ታምራት ለኔ ብቻ አይደለም ለሁሉም ወንድሞቹ ተቆርቋሪ የሆነ ወንድም ነው። እኔማ ደሞዝ ይጨመርልኝ ስል አለቆቼ የጠየቁኝ ዲግሪ ነው። እባካችሁን እንደውም በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ ሁለት ስንኝ ጽሁፍ እንድጽፍ ይፈቀደልኝና ዲግሪዬን ህዝቡ ይሰጠኝ ብዬ በተናገርኩ እስር ቤት ገብቼ ነበር። በዚህ ሰዓት ታምራት እኔን ለማስወጣት ያልገባበት ቦታና ያልቆፈረው ጉድጓድ ያልሄደባቸው ባለስልጣናት ጋር አልነበሩም።
ኮሎኔል ሞላልኝ አማቹ ስለበሩ፤ እንዴት እንደዚህ ያደርጉታል ብሎ በአማርኛ ለመስደብ “ግርማዬ ተገፎ ካሳን ጠራሁኝ ሞላጎደል ሆኖ እያበሳጨኝ” እያልን ወደ ንፋስልክ አካባቢ ባትሪሲዮን ቦታ ላይ እንጫወት ነበር። ኮረኔል ሞላልኝ በመነጽራቸውና በባርኔጣቸው ተሸፋፍነው መጥተው ያስተውላሉ። በኋላም በጥፊ. . . በርግጫ. . . ፍዳችንን አሳይተውን ነበር። እንዲህ እንዲህ እያልን እሱ ሲያዝ እኔ ስሰራ እኔ ስያዝ እሱ ሲሰራ ብዙ ነገር አሳልፈናል። አንድ ሰሞን መኪና የገዛሁ አካባቢ መኪናዬ ውስጥ ትራስ ፣ አንሶላና ፍራሽ ነበር ይዤ የምዞረው። ምክንያቱም ተደብቄ ነበር የምሰራው ትርፍ ስራ እንደሆነ በአደባባይ መስራት አንችልም። ምናልባት ለምን ሃብታም አልሆናችሁም? እንባል ይሆናል። ችግራችንን ግን እኛው እራሳችን ነን የምናውቀው።
ለአሁኖቹ ትውልዶች ቀደምትና ፈር ቀዳጆች ነን ብንል የተሳሳትኩ አይመስለኝም። ከተሳሳትኩም እታረማለሁ። በኋላም መከረኛው ታህሳስ ሲመጣ ልንለያይ ሆነ። ከጦሩ ጋር ወደ ኦጋዴን ሊልኩት ሆነ። በዚህ ወቅት ነበር ከሻለቃ ወንድሙ ዘውዴ እና ሻለቃ ተስፋዬ መኩሪያ እንዲሁም እኔም ጭምር በመሆን ኮሎኔል አሽኔንና ሻለቃ ደስታን መክረንና አሳምነን ከጦሩ ውስጥ እንዲቀር ተደረገ። እግዚአብሔር ይስጣቸው፤ እኔና ታምራት አብረን ብዙ ክፉና ደግ ቀኖችን አሳልፈናል። መጠጥ የሚባል እንኳን አያውቅም። የሱ መጠጥ ውሃ ነው። ይቅርታ አድርጉልኝና እኔ ብቻዬን በጣም ብዙ እጠጣ ነበር። እንዲህ ያለ ጥንቃቄ የሚወስድ ሰው እንኳን ያመዋል ብዬ አላስብም ነበር። ለካ ወንድሜ ተይዞ ነበር። ሌላው እሱም ወታደር ነበር እኔም ለሁለት ዓመት ወታደር ነበርኩ። ታምራት በጦር ሜዳውም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ ከወንድም ወንድ እና ሞራል ያለው ሰው ነው። ለወገኖቹም ተቆርቋሪ ጥሩ አርቲስት ነው። እኔ ለታምራት እችኑ ያለችህን አንድ ሃገር ፈጣሪ ፍቀድልኝና ልግዛህ ቢለኝ አሜን ብዬ የምቀበል ሰው ነኝ። ታምራት ለኔ ልጄም ወንድሜም ጓደኛዬም ነው። ይሄው ነው ብዬ ሚዛን ላይ ማስቀመጥ አልችልም። በአጠቃላይ መለኪያዬ ነው።”
ማህሙድ አህመድስ ምን ብሎ ነበር?
«ስለታምራት ለመጀመር ቢከብድም እኔ መቼም ሁላችሁም እንደሰማችሁትና በታሪክም እንደምታውቁት አሪዞና ክለብ ውስጥ ወጥ ቤት እሰራ ነበር። በ1954ዓም ነው አባታችን ፣ ወንድማችን ፣ የጉሮሮ መክፈቻችንና አምባሰደራችን የሆነው ጥላሁን ገሰሰን ጨምሮ ታምራት ሞላ፣ አባይ በለጠ ፣ እሳቱ ተሰማ ፣ ተፈራ ካሳ ፣ አሰፋ ሚካኤልና የመሳሰሉት በመሆን እየመጡ በሚጫወቱበት ወቅት ነው የተዋወቅነው። በኋላም ክቡር ዘበኛ በምንቀጠርበት ወቅት በነ ታምራትና በሌሎቹም ዘፋኞች ስራ በመዝፈን ነበር ያለፍኩት። ከዛን ጊዜ ጀምሮ ይሄው እስከ ዛሬ ወዳጆች ሆነናል። ታምራት በጣም ጠንካራ ሰው ነው። ነገርን በትክክል በጭንቅላቱ አስቦ የሚመልስ መካሪ ፣ እስኪ እንነጋገር የሚል ሰው አክባሪ ነው። ሌላው ይቅርና እርስ በርሳችንም ብንሰዳደብና ብንኮራረፍ ገበናችን ግን ወደ ውጪ አይወጣም። ትንሹም ትልቁም ለታምራት እኩል ናቸው። መቼም ወታደር ቤት ያለን ሰዎች ሲቪሎችም ብንሆን ወታደር ነን። ለትንሹም ለትልቁም «አቤት ጌታዬ ነው» እርስ በርሳችንም ቢሆን መሃሙድዬ ሲለኝ «አቤት ጌታዬ» ታምራትዬ ስለው “አቤት ጌታዬ” ነው የሚለኝ። ይህንን ለልጆቻችን ሁሉ ሳይቀር አውርሰነዋል።” ብሏል።
ለኢሳት ቴሌቪዥን አስተያየቱን የሰጠው አርቲስት ዳምጠው አየለ እርሱ በሚቀጠርበት ጊዜ የሙያ ገምጋሚው አርቲስት ታምራት እንደነበር ገልጾ፣ ለ30 አመታት ያክል ሳይለያዩ በምድር ጦር አገልግሎት መስጠታቸውን አውስቷል። እኛ የምንሰራው ለአገር፣ ለሙያ ፍቅር እንጅ ለሌላ አልነበረም ያለው አርቲስት ዳምጠው፣ አርቲስት ታምራት ሞላ ኩሩ፣ ሽቅርቅር ፣ ንጹህ እና ከሰዎች ጋር መኖር የሚችል ነበር ብሎአል። ምድር ጦርን ምድር ጦር ካሰኙት አርቲስቶች መካከል ታምራት አንዱ እንደነበርም ተናግሯል፡፡
ታምራት ያረፈው በተወለደ በ69 አመቱ ሲሆን ካጋጠመው የካንሰር ህመም ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ማገገሙን አንጋፋው ድምጻዊ በአንድ ቃለመጠይቅ ወቅት አሳውቆ የነበር ሲሆን ህመሙ አገርሽቶበት ከዚህ አለም በሞት ተለይቷል። የአርቲስት ታምራት የቀብር ስነስርአት የካቲት 03/2005ዓም በቅድስት ስላሴ ካቴደራል ተፈጽሟል። አርቲስት ታምራት ባለ ትዳር እና የ3 ወንድ እና የ2 ሴት ልጆች አባት ነበር።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ኅዳር 18/ 2015 ዓ.ም