ስለ ሰላም ብዙዎች ዘምረዋል። በርካቶች አዚመዋል። ጥቂት የማይባሉ ጽፈዋል። አያሌዎች ህይወታቸውን ሰውተዋል። ሚሊየኖችም ሰላምን ለመሻት ከአገር ከቄያቸው ተሰደዉ ተንከራተዋል:: የሰውነትን ስብእና እና ክብር አጥተዋል።
ሰላም ሁሉ አቀፍ ተፈላጊነት አለው። ሁሉም በተግባር ይፈልገዋል። ይፈቅደዋል። የተለየ ዋጋ ይሰጠዋል። በሁሉም ባህሎችና እምነቶች እንዲሁም ሕዝቦች ዘንድ ሰላም ከፍተኛ ዋጋ አለው። ሰላምን የማያስተምር እምነትም የለም።
በየቤተ እምነቱ በሚደረጉ ፀሎቶችም ሰላም ከቀዳሚ ርዕሶች የመጀመሪያው ነው። ህዝብን እንደ የእምነቱ ፈጣሪን እለት እለት በሰላም ያሳደርከኝ በሰላም አውለኝ ከማለት አልፎ፤ ለአገሩ፣ ለህዝቡ ሰላም መሆን ይመኛል። ይፀልያል።
ዩናይትድ እስቴትስ ተወዳጅ ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን፣ ‹‹ሠላም ማለት ግጭቶችን በሠላማዊ መንገድ መፍታት መቻል ማለት ነው›› ይላሉ። እርግጥም ሠላምን በጉልበት ማስጠበቅ አይቻልም። ሠላምን ማሳካት የሚቻለው በመግባባት ብቻ ነው። ልዩነትን ማቀራረብ ወይም ቅራኔን ማርገብ የሚቻለው በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ እንጂ፣ ‹‹የምፈልገውን አስፈጽማለሁ›› በሚል ጀብደኝነት አይደለም።
በተለይ በፖለቲካው ዓለም ፉክክርና የትግል ተሳትፎ ሁለንተናዊ ሰላም እውን ይሆን ዘንድ በተለይ ከአገርና ከሕዝብ በፊት ሥልጣንን ማስቀደም፣ ከራስ ክብርና ዝና በላይ ለሌላው አለመጨነቅና ዕብሪት አሽቀንጥሮ ማስወገድ የግድ ይላል።
ሰላም የሚረጋገጠው በሠለጠነ አስተሳሰብ እንጂ ዘመን ባለፈበት አስተሳሰብና በጠመንጃ አምላኪነት አይደለም። ለአገር የሚበጅ ሥርዓት ዕውን ሊሆን የሚችለው በሕዝብ ይሁንታ እንጂ በጀብደኝነት አይደለም። ሆኖም አያውቅም። በኋላ ቀር አስተሳሰብ ተቸክሎ ጠመንጃ መወልወልም ሆነ ውረድ እንውረድ ተባብሎ ጦር መስበቅ፣ በየትኛውም መመዘኛ በጣም የሚያስንቅ አስነዋሪ ድርጊት ነው።
ሰላምን በጉልበት የማምጣት ሙከራዎችም በአብዛኛው ትርፋቸው መከራ ነው። በጉልበትና በጠመንጃ የሚጠበቅ ሰላም ቀኝ ጠብቆ ፍርክርኩ መውጣቱ አይቀሬ ነው። አንዳንድ ፀሃፍት እንዳውም በጉልበት የተገኘ ድል ከሽንፈት እኩል ያነፃፅሩታል። ምክንያታችን የሚሉት ደግሞ ጊዜያዊ መፍትሄ መሆኑን ነው።
ኢትዮጵያ ታሪክ አንድ ችግር ሲያጋጥና ሰላም ሲደፈርስ ተነጋግሮ መፍትሔ ለማፍለቅ ከመትጋት ይልቅ ዱላ መምዘዝ የተለመደ ነው። በዚህም ምክንያት ግጭትን ወይም ጦርነትን ሙጥኝ በማለት ዓላማን ለማስፈጸም ጥድፊያው ሲበረታም ይታያል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጦርነት ባስከተለው ሁለንተናዊ ቀውስ ከባድ መንገራገጮችን ውስጥ ቆይታለች። በውጫዊም ሆነ በውስጣዊ ምክንያቶች የሰላም አየር ናፍቆት ቆይታል። ችግሩ እንዳይከሰት ብዙ የሰላም አማራጮች ተሞክረዋል፤ ሳይሳኩ ቀርተው ጦርነት ውስጠይ ገብተን ቆይተናል።
በጦርነቱ ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ሞተዋል። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩት ደግሞ ከአካላዊና ከሥነ ልቦናዊ ጉዳት በተጨማሪ ተፈናቅለው ሜዳ ላይ ወድቀዋል። ግምቱ እጅግ በጣም ከፍተኛ የሆነ የህዝብ እና አገር ሀብት ወድሟል።
የሰሜን ጦርነት ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጦርነቱ ኢኮኖሚውን እያደቀቀ የዜጎችን ኑሮ ከማክፋቱና የሚሊዮኖችን ደኅንነት ከማቃወሱም በላይ ኢትዮጵያ ብዙ ሴራ ተሸርቦባታል። በርካታ መሰናክሎች አሳልፋለችል። ተወንጅላለች። በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማትና ሚዲያዎች ሆን ተብሎ ገጽታዋ እንዲጠቁር ተደርጓል። ተስፋ ቢስ እንደሆነች ተደርጋም ተስላለች።
በመጨረሻው አሁን ችግሩ በሰላም ስምምነት መስመር መያዥ እየጀመረ ነው። ከቀናት በፊትም በአፍሪካ ኅብረት ጥላ ሥር በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ በፌዴራል መንግሥትና በ ሕወሓት መካከል የሰላም ንግግር እውን ሆናል። የኢትዮጵያን ጥቅምና ክብር ባስጠበቀ መልኩ ሰላምን እውን ለማድረግ ከስምምነት ተደርሷል።
ይህም የሰላም መንገድ ለኢትዮጵያ ትልቅ ድል ነው:: በሰላም እንጂ በጦርነት ያተረፈ አገር አለመኖሩን በመረዳት ግጭትና ጦርነት ይብቃን መባሉ እጅግ የሚደገፍና የሚያስደስት ነው:: ከምንም በላይ ለህዝባችን ትልቅ እፎይታ ነው።
በሠለጠነ መንገድ ሰላም መንገድ ማራመድም ትሩፋቱ በርካታ ነው። በተለይ ኢትዮጵያ የታሪካዊ ጠላቶቿ መቀለጃና መፈንጫ እንዳትሆን ያደርጋል። በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ እጃቸውን አስረዝመው እያስገቡ ያሉ የውጭ ኃይሎች ፍላጎት እንዳይሳካ ግዙፍ ሚና ይጫወታል።
በዚህ የሰላም መንገድ ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካ አገሮች ከምእራባውያን ይልቅ በራሳቸው አቅም ያለማንም ጣልቃ ገብነት ከቅኝ ግዛት እሳቤ ተላቀው የራሳቸውን ችግር በራስ መፍታት እንደሚችሉ በተጨባጭ ማመላከት ተችላል።
ሰላም በመገኘቱ የሚከስር ህዝብም ሆነ የህዝብ አጀንዳ የለም። ይሑንና ከሰላም ይልቅ ጦርነት ምርጫቸውና የደስታቸው ምንጭ የሆነ አንዳንዶች መኖራቸው የሚደበቅ አይደለም። ትናንት ‹‹የትግራይ ሕዝብ መንገድ ተዘጋበት፣ የእርዳታ እህል እየደረሰው አይደለም፣ ስልክ፣ መብራት፣ ወዘተ ወዘተ ተከለከለ። በከበባ ውስጥ ሆኖ ዘሩ ሊጠፋ ነው›› ሲሉ የነበሩ ሰዎች ዛሬ ጦርነቱ ለምን ቆመ ብለው ነጠላ ዘቅዝቀው፣ ደረት እየደቁ ናቸው።
በኢትዮጵያ ምድር የሰላም አየር መንፈስ እንዲቀጥል ታዲያ መሰል የሰላም መንገድ ለመዝጋት የሚታትሩ እና እንደ ጎልያድ መንገድ የሚዘጉን አይቶ እናዳላየ ሰምቶ እንዳልሰማ በጥንቃቄ ማለፍ ከፍ ሲልም ገሸሽ ማድረግ የግድ ይላል።
በኢትዮጵያ ምድር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የጦርነት ምዕራፍ ተዘግቶ ሰላም እንዲሰፍን፣ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ከዳር እስከ ዳር በአንድነት መንቀሳቀስ ይጠበቅባቸዋል። የአገር ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ወገኖች በሰላማዊና በሕጋዊ መንገድ ተቀራርበው መነጋገር ይጠበቅባቸዋል።
የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎችም ሆኑ ሌሎች የአገር ጉዳይ የሚመለከታቸው ወገኖች፣ ኢትዮጵያ ከግጭት የፀዳች አገር እንድትሆን ቁርጠኝነታቸውን በተግባር ማሳየት ይጠበቅባቸዋል። ለዚህ ስኬት ደግሞ ብሔራዊ ምክክር አስፈላጊ ነው። ጦርነቱ ሲጠናቀቅ ኢትዮጵያ ዳግም ወደ ጦርነት እንዳትመለስ ተደርጎ መሆን ይኖርበታል።
አንድ መታወቅ ያለበት አብይ ጉዳይ የሰላም ሽግግር ስክነትና ብስለት ይፈልጋል። ከቂምና በቀል በመፅዳት ይጠይቃል። የሰላምን መንገድ ስንራመድም ይሕ መፈክራችን ሊሆን የግድ ይላል። ኢትጵያ በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች እድገት ለማስመዝገብ መጀመሪያ ሊኖራት የሚገባው ሃብት ሰላም ነው።
የሰላም ዋጋው የይቅርታ ብቻ በመሆኑ በይቅርታ ላይ የተመሰረተ የሰላም ባህል ማበልጸግ ይገባናል። ጦርነት ብዙ አውዳሚ እንደመሆኑ በዚህ ጦርነት የተጎዱትን የሶልሶ ማቋቋም እና መደገፍ የመንግስት ኃላፊነት ብቻ ሳይሆን የሁላችንንም ርብርብ ሊሆን የግድ ይላል።
የሰላምን መንድ ስንራመድ ሰላም እውን እንዳይሆን የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች የተዳፈነው እሳት እሳቱን ለማራገብ አድፍጠው እንደሚተጉም ለአፍታ መዘንጋት የለበትም። በሰላም ንግግሩ የሚፈለገው ውጤት ላይ ቢደርስምም እንኳን ምዕራባውያኑ በኢትዮጵያ ላይ የሚያደርጉትን ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ጫና ይቆማል ብሎ ማሰብም አይቻልም። ይሕ እንደመሆኑም አንድነታችንን ይበልጥ ሊጠናከር ይገባል።
እንደ አገር የተደረሰውን የሰላም ስምምነት ተቀብሎ ለአፈጻጸሙ በአግባቡ ሊዘጋጅና ስለ ሰላም ሃያልነት መንገር ቋሚ መልዕክቱ ሊሆን ይገባል። በዚህ ሂደት በአንድ አፍ ስለሰላም እየዘመሩ በሌላ አፍ ጦርነትን የሚደግፉ የፖለቲካ ተዋንያንም ሆኑ አክቲቪስቶች፣ የሰላም መንገዱ እንዲዘጋና ጦርነቱ እንዲያገረሽ ከሚያደርጉ ፕሮፓጋንዳዎች እንዲታቀቡ ማድረግ የግድ ይላል።
ሰላምን መንገድ በመራመድ ጠላትን በጋራ በመመከት የምናስመዘግባቸው ድሎች በሌሎች ዘርፎችም ሊደገሙ ይገባል። ይህን ማድረግ ኢትዮጵያ በእድገት ጐዳና ላይ ያራምዳል። የተሻለች አገር ለቀጣዩ ትውልድ እንድናስረክብ ያግዛል።
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ሰኞ ጥቅምት 28 ቀን 2015 ዓ.ም