ልጆች እንዴት ናችሁ? ረዘም ላለ ጊዜ አልተገናኘንም አይደል? መቼም የአያቴ ታሪኮች እንደናፈቋችሁ አልጠራጠርም። እኔም ታሪኮቹን ለእናንተ ለመንገር ሁሌም እጓጓለሁ። ታዲያ ዛሬ ከታሪኮቹ መካከል ስለ ምን የምነግራችሁ ይመስላችኋል? መልካም፤ ዛሬ ጊዜው ስለፈቀደ አንድ ቆንጆ ታሪክ ይዤላችሁ ቀርቤያለሁ። ጥሩ የንባብ ጊዜ ይሁንላችሁ።
የሦስተኛ ክፍል ተማሪ በነበርኩበት ወቅት አስተማሪያችን «ለችግሮቻችን እንዴት መፍትሄ ማግኘት እንደምንችል የሚያሳይ አንድ ታሪክ ፅፋችሁ ኑ» ሲል የቤት ሥራ ይሰጠናል። እኔም አያቴ ብልሀተኛ እና ጥሩ ታሪክ አዋቂ መሆኗን ስለማውቅ፤ ከሷ ለመጠየቅ እና ለመሥራት ወሰንኩ።
ከትምህርት ቤት እንደመጣሁ አያቴን የተለመደው ቦታዋ ላይ ቁጭ ብላ ጥጥ ስትፈትል አገኘኋት። ጥጥ መፍተል ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ አይደል ልጆች? አዎ፤ ጥጥ መፍተል ማለት በባህላዊ መንገድ እንዝርት በሚባል ቀጭን የእንጨት መሳሪያ፤ ጋቢ፣ ነጠላ እና የሀበሻ ቀሚስ ለመስሪያ የሚሆን ክር(ድውር) ማዘጋጀት ነው። እናም አያቴ ጋር እንደደረስኩ አስተማሪያችን የሰጠንን የቤት ሥራ ነገርኳት። እሷም መክሰሴን ከበላሁ በኋላ ታሪኩን እንደምትነግረኝ ገለፀችልኝ።
መክሰሴን በልቼ ትንሽ እንዳረፍኩኝ አያቴ ጋር ታሪኩን እንድታጫውተኝ ሄድኩ። እሷም የምትሠራውን ሥራ ለጊዜው አቁማ እንዲህ የሚል ታሪክ አጫወተችኝ።
ከብዙ ዓመታት በፊት በአንድ መሥሪያ ቤት ውስጥ ያሉ 30 ሠራተኞች ነበሩ። እነዚህ ሠራተኞች ወጣት ከመሆናቸውም በላይ፤ ታታሪ እና የሥራ ተነሳሽነታቸው እጅግ የሚያስደስት ነበር። ከዚህም ሌላ ወጣት ሠራተኞቹ አዳዲስ ሀሳቦችን ቶሎ ለመቀበል እና ለመማርም ዝግጁ ነበሩ።
ታዲያ በመሥሪያ ቤቱ ውስጥ ያሉት ኃላፊዎች እነዚህን ሠራተኞች እንዴት ለችግሮች መፍትሄ ማግኘት እንደሚችሉ ሊያስተምሯቸው ይፈልጋሉ። በመሆኑም ሀሳቡን ይነግሯቸዋል። እነዚህ ታታሪ ሠራተኞችም በሀሳቡ ይስማሙ እና የሥልጠናው ቀን ይወሰናል።
ሥልጠናው በሚሰጥበት እለት ሠራተኞቹ በአንድ አዳራሽ እንዲሰባሰቡ ይደረጋል። እዚህ አዳራሽ ውስጥም አንድ ጨዋታ እንደሚጫወቱ ይነገራቸዋል። እነዚህ ሠራተኞችም ትምህርት ነክ ስብሰባ እንጂ ጨዋታ ለመጫወት እንደተጠሩ ስላልገመቱ፤ በነገሩ በጣም ይገረማሉ። ሁሉም ወደዚህ ስፍራ ሲመጡ የየራሳቸውን ግምት ይዘው ነበር።
አዳራሹ በጣም በሚያምሩ ቀለማት የተዋበ እና የተለያየ የልጆች መጫወቻ የያዘ ነበር። በዚህ ስፍራ አየር የተሞላበት ፊኛ ወይም «ባሎን» በሁሉም ቦታዎች ይገኛል። አዳራሹ ስብሰባ ከማስተናገድ ይልቅ ለጨዋታ በጣም የሚመች ሆኖ ነበር የሚታየው። ሁሉም በነገሩ ስለተገረሙ እርስ በእርስ መንሾካሾክ እና መነጋገር ይጀምራሉ።
በዚህ አዳራሽ ውስጥ በተለየ መልኩ በትልቅ ካርቶን አየር ተሞልቶበት የተቀመጠ ፊኛ ነበር። ፊኛዎቹ የተለያዩ ቀለማትንም የያዙ ነበሩ። ሁሉም ወደ አዳራሹ ገብተው ከተረጋጉ በኋላ የቡድን አስተባባሪው ሁሉም አንዳንድ ፊኛ ከካርቶኑ ውስጥ እንዲወስዱ ይነግራቸዋል። ከዛም ሁሉም እንዲያፈነዱት ይጠይቋቸዋል።
እነዚህ 30 ሠራተኞች በታዘዙት መሰረት የያዙትን አየር የተሞላ ፊኛ ያፈነዱታል። ሁኔታው በጣም የሚያስገርም እና አዝናኝም ነበር። በዚህ ጊዜ ሠራተኞቹ እየተሳሳቁ እና ደስተኛ እየሆኑ ነበር። በድጋሚ የቡድን አስተባባሪ ተመሳሳይ ፊኛ እንዲያነሱ እና በያዙት እስኪርቢቶ እላዩ ላይ ስማቸውን እንዲፅፉ ይጠይቃቸዋል። ፊኛው እንዳይፈነዳም ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ይነግራቸዋል።
ሁሉም የጨዋታው ተሳታፊዎች በያዙት ፊኛ ላይ ስማቸውን በጥንቃቄ ለመፃፍ ይሞክራሉ። ሆኖም ግን ፊኛው በአየር በጣም ስለተወጠረ አብዛኛው ይፈነዳል። ስማቸውንም ሳይፅፉ ይቀራሉ። የቡድን አስተባባሪው አሁንም ፊኛው ለፈነዳባቸው ሠራተኞች በድጋሚ እድል ይሰጣቸዋል። ለሁለተኛ ጊዜ እድል ቢሰጣቸውም ግን ከ30 ሠራተኞቹ ውስጥ አምስቱ እድለኛ ሳይሆኑ አሁንም ይፈነዳባቸዋል። በዚህም 25 ሠራተኞች ለሁለተኛው ዙር ጨዋታ ያልፋሉ። በድጋሚ እድል ተሰጥቷቸው ስማቸውን መፃፍ ያልቻሉት ደግሞ በጨዋታው ህግ መሰረት ከውድድሩ ይሰረዛሉ።
በሁለተኛው ዙር የቡድን መሪው ስማቸው የተፃፈበት ፊኛን በመሰብሰብ፤ በአንድ ክፍል ውስጥ ያስቀምጠዋል። ከዛም ለሁለተኛው ዙር ያለፉትን ሠራተኞች እንዲህ የሚል ትእዛዝ ይሰጣቸዋል «ሁላችሁም ፊኛውን ባስቀመጥንበት ክፍል ትገቡና ሰማችሁ የተፃፈበትን ፊኛ ታነሳላችሁ። በዚህ ጊዜ ፊኛዎቹ መፈንዳት የለባቸውም» በማለት ያስጠነቅቃቸዋል።
25ቱም ሠራተኞች ፊኛው በሚገኝበት ክፍል ውስጥ ይገባሉ። የራሳቸው ስም የተፃፈበትን ፊኛ ለማግኘትም በጥንቃቄ መፈለግ ይጀምራሉ። በግርግር ወቅት ፊኛው እንዳይፈነዳም ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይጀምራሉ። ክፍሉ ጠባብ እና በፊኛ የተሞላ በመሆኑም የራሳቸው ስም የተፃፈበትን ለማግኘት አስቸጋሪ ነበር።
በክፍሉ ውስጥ የራሳቸውን ስም ለማግኘት ብዙ ጥረት አደረጉ። በሚያደርጉት ጥንቃቄ የተሞላበት እንቅስቃሴ ረጅም ደቂቃ ወሰደባቸው። ሆኖም ግን ስማቸው የተፃፈበትን ፊኛ ለማግኘት አልቻሉም ነበር። በዚህ ጊዜ የቡድን አስተባባሪው ስማቸው ያለበትን ፊኛ ለማግኘት የሚያደርጉት ጨዋታ ጊዜ እንዳለቀ ይነግራቸዋል።
ሁሉም ጨዋታውን እንዲያቆሙ ያስጠነቀቀው የቡድን መሪ፤ ሦስተኛ ዙር ጨዋታ እንደሚቀርም ይገልፅላቸዋል። ሠራተኞቹ ቀጣዩ የጨዋታ ህግ ምን እንደሚሆን ለማወቅ ጉጉት አደረባቸው። ቡድን መሪው እንዲህ አላቸው « አሁን ሁላችሁም ክፍል ውስጥ ትገቡና ያገኛችሁትን ፊኛ በማንሳት ስሙ ለሚመለከተው ሰው ትሰጡታላችሁ» አላቸው።
ሁሉም ሠራተኞች በክፍል ውስጥ ይገባሉ። ከፊት ለፊታቸው ያገኙትንም ፊኛ በማንሳት የተፃፈውን ስም ተመልክተው ለጓደኛቸው ይሰጣሉ። በዚህ ጊዜ ፊኛዎቹን በፍጥነት ለሁሉም ደረሱ። ሁሉም በሁለት ደቂቃ ውስጥ የራሳቸው ስም ያለበትን ፊኛ ማግኘት ቻሉ። በነገሩም በጣም በመደነቅ እርስ በርስ እየተነጋገሩ መሳሳቅ ጀመሩ።
የቡድን አስተባባሪያቸው ጨዋታው ማለቁን አሳውቆ «ይሄ ማለት ለችግሮቻችን ትክክለኛውን መፍትሄ የምናገኝበት ነው። ሁላችንም ነገሮችን ሳናገናዝብ በራሳችን ጥረት መፍትሄ እንፈልጋለን። አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር፤ እርስ በርስ በመረዳዳት እና ነገሮችን በመጋራት፤ ለችግሮች መፍትሄ ማምጣት እንችላለን» በማለት ለሥራ ባልደረቦቹ አስተማራቸው።
ሁሉም ሠራተኞች በሁኔታው ስለተገረሙ እና ትክክለኛውን መፍትሄ ስላገኙ ተደሰቱ። ለቡድን መሪያቸውም ሞቅ ያለ ጭብጨባ ከመቀመጫቸው በመነሳት አደረጉ። ከዛን ጊዜ በኋላ በመሥሪያ ቤታቸው በመደጋገፍ እና በጋራ መሥራት ጀመሩ። ድርጅቱም ትርፋማ ሆነ።
አያቴ ይህን ጣፋጭ ታሪክ አወራችኝ። እኔም በነገረችኝ ወቅት በደብተሬ ላይ አስፍሬው ነበር። በሚቀጥለው ቀን አስተማሪያችን ሁላችንም ወጥተን እንድናነብ ጋበዘን። ታሪኩን አንብቤ እንደጨረስኩ አድናቆቱን ሰጠኝ። ሌሎቹም ተማሪዎች ጥሩ ጥሩ ታሪክ በክፍሉ ውስጥ አንብበው ነበር።
እናንተስ ልጆች ከዚህ ታሪክ ምን ተማራችሁ? በጋራ መሥራት ችግሮችን እንደሚያቀል እንደተረዳችሁ እርግጠኛ ነኝ። መልካም! ለዛሬ እንሰነባበታለን። በሚቀጥለው ጊዜ ደግሞ በተመሳሳይ ቆንጆ ታሪኮችን ይዤላችሁ እቀርባለሁ። ጥሩ የትምህርት ጊዜ ይሁንላችሁ።
አዲስ ዘመን መጋቢት 29 /2011
ዳግም ከበደ