የትውልድ ስፍራው ጎንደር አዘዞ ነው። ወቅቱም ሚያዝያ 10 ቀን 1970 ዓም። ወይዘሮ ሀገርነሽ ዋሴ እና አቶ አፈወርቅ መንግሥቱ ወንድ ልጅ ወለዱ። ስሙንም ተገኔ አሉት፤ “ጠበቃዬ ፥ ጋሻ መከታዬ ማለት ነው። ልጃቸውን በወለዱ በሦስተኛው ወር ግን የልጃቸው እትብት የተቀበረባትን አዘዞን ትተው ወደ ትውልድ ቦታቸው ደብረ ታቦር ሄዱ። ይህ ልጅ በኋለኛው ዘመን በኢትዮጵያ ሙዚቃ የሚጠቀስ ስም ካፈሩ ድምጻውያን መካከል አንዱ የሆነው ማዲንጎ አፈወርቅ ነው።
የማዲንጎ ቤተሰብ ለመንፈሳዊ ዓለም ቅርብ ነው። አባቱን ጨምሮ አብዛኛው ቤተሰቡ የቤተ ክህነት አገልጋይ ነበሩ። ምናልባትም የዜማ ተሰጥዖው ከዚያው የመነጨ ሳይሆን አይቀርም። በልጅነቱ የሙዚቃ ፍቅር እንዳደረበት እና ገና በ9 ዓመቱ በቀበሌ ኪነት ውስጥ ማይክ እንደጨበጠ ይናገር የነበረው ማዲንጎ፥ የሰባተኛ ክፍለ ጦር የ603 ኮር የሙዚቃ ቡድን ልምምድ ሲያደርግ ከተመለከተ በኋላ ግን ልቡ ሙዚቀኛ ለመሆን ቆረጠ። ድምፃዊ መሆን እችላለሁ በማለት እድል እንዲሰጡት ጠየቀ። እናም በወቅቱ እድሉን አግኝቶ የድምፃዊ ኤፍሬም ታምሩን ” ና ተላክ ልቤ ፥ ልላክህ ልስደድህ ልቤ” የተሰኘውን ሙዚቃ ተጫውቶ አድናቆት ተቸረው። ተቀባይነትን አግኝቶም በዛው በወታደር ቤት ሙዚቃውን የቀጠለ ሲሆን፥ “ማዲንጎ” የሚለው ስሙም የወጣለት እዚያው ነው።
ማዲንጎ ከጦሩ ከወጣ በኃላ በ1982 ዓም አካባቢ ገና በ12 ዓመቱ በባህር ዳር የሙዚቃ ሥራዎችን በማቅረብ አንድም ድምፃዊ የመሆን ሕልሙን መስመር ያስያዘበት በሌላ በኩል ገቢ በማግኘት እራሱንና ቤተሰቦቹን ማገዝ የቻለበትን ሁኔታ መፍጠር ችሏል። በወቅቱ 120 ብር ይከፈለው ነበር። በመቀጠልም ወደ አዲስ አበባ ከተማ በመምጣት እርጎዬዎችን እና ላፎንቴኖችን ጨምሮ የተለያዩ የሙዚቃ ባንዶችን በመቀላቀል የታዋቂ ሙዚቀኛ ስራዎችን በማቀንቀን ተወዳጅነትን አገኘ።
በ1991 “ስያሜ አጣሁላት” የተሰኘውን እና እሱ የልጅነቴና ከሰው ጋር አስተዋወቀኝ የሚለውን አልበሙን ለሕዝብ ጆሮ አደረሰ። ከጥቂት ዓመታት በፊት ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ ስለ መጀመሪያ አልበሙ እንዲህ ብሎ ነበር “የመጀመሪያው አልበሜ የልጅነት ሥራዬ ነው። ያኔ ጠቆር ያልኩ ነበርኩኝ፤ እንዳሁኑ አልገፈፍኩም ነበር። አሁን እንደ እባብ ቆዳ ቀይሬያለሁ። የሆነ ሆኖ ‘ስያሜ አጣሁላት’ በልጅነት ዕድሜ ከሕዝብ ያገናኘኝ ሥራ ነው። ወቅቱ የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ነበር። ታዲያ ‘ስያሜ አጣሁላት’ እና ‘አማን ነው ወይ ጎራው’ የተሰኙት ሁለት ዘፈኖች በተለየ መልኩ ተወደውልኝ ነበር።”ይላል።
በዚህም አድናቆትን እና የሕዝብ ፍቅርን ሲያገኝ ከዓመታት በኋላ በ1997 “አይደረግም” የተሰኘውን ሁለተኛ አልበሙን ለሕዝብ በማድረስ ተወዳጅነቱን ከፍ አደረገ። ይህ አልበሙም አይደረግም፣ የአፋሯ ቆንጆ፣ ሰው የለኝም፣ ማህሌት፣ ሞኙ ልቤ እና ሌሎች ተወዳጅ ዜማዎችን ያካተተ ነው። በተለይም በዚህ አልበሙ ላይ የተጫወተው የአራት ታላላቅ ድምፃውያንን የትዝታ ዜማ አንድ ላይ ያዋሀደው ትዝታ የማዲንጎን የመዝፈን ችሎታ በሚገባ ያሳየ ነበር።
ከዚያም “አይደረግም” የተሰኘውን ሁለተኛውን አልበሙን ካወጣ ከስምንት ዓመት በኋላ “ስወድላት” የተሰኘውን ሦስተኛ አልበሙን በ2007 ዓ.ም ለአድማጮቹ እንካችሁ አለ። በዚህ የሙዚቃ አልበሙ ውስጥ ላላተርፍ፣ ስወድላት፣ አቅሜን፣ አይሆንልኝም፣ እባክሽ ታረቂኝ፣ ከተለያየን ፣ ውሰጃት፣ ዳኛ፣ ጎዳናው፣ ማተቧ፣ ማርማር የተሰኙና ሌሎች ሙዚቃዎች ተካተዋል። በስወድላት አልበምም በተለያዩ የሙዚቃ ውድድሮች እጩ እንዲሁም “ምርጥ የፍቅር አልበም“ ተብሎ ለመሸለም ችሏል።
እንዲሁም ከአልበሞቹ በተጨማሪ “በላይ”፣ ከብርሃኑ ተዘራ ጋር የተጫወተው “ሰላም ያገር ሰው”፣ ለ“ዓባይ ወይስ ቬጋስ” ፊልም የሰራው ማጀቢያ ሙዚቃ ከሥራዎቹ ውስጥ ግንባር ቀደም ሆነው ይጠቀሳሉ። “በማንኛውም ሙያ ውስጥ ያላችሁ ወጣቶች፥ በጥረት እንጂ ከመሬት ተነስቶ የሚመጣ ነገር የለም፤ በድንገት የሚመጣ ነገርም ጠቃሚ አይደለም” በማለት ያስተላለፈው መልዕክትም የሚታወስ ነው።
አርቲስት ማዲንጎ አራተኛ አልበሙን ለአድማጮች ለማድረስ በመሥራት ላይ እንደነበርም ነው የተሰማው። አይቀሬው ሞት ድንገት ፈጥኖ ቀደመው እንጂ። ከሶስተኛው አልበም መውጣት በኋላ ከሰይፉ ፋንታሁን ጋር ባደረገው ቆይታ በቀጣይ በስምንት ዓመታት ውስጥ ሶስት አልበሞችን ለማውጣት አቅዶ እንደነበር የተናገረው አርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ በወጣትነቱ እና ብዙ መሥራት በሚችልበት ዕድሜው ባደረበት ድንገተኛ ሕመም ምክንያት መስከረም 17 ቀን 2015 ዓም ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ። ከወይዘሮ ሮዛ ይግዛው ጋር በነበረው ትዳርም ዲቦራ የተሰኘች ሴት ልጅ አፍርቷል።
ማዲንጎ በማኅበራዊ ሕይወቱ እና በበጎ አድራጎት ሥራው ተጠቃሽ ነው። ስለ በጎ ሥራው ከሚመሰክሩ ሰዎች መካከል አንዱ አርቲስት አለልኝ መኳንንት ጽጌ ነው። አለልኝ እንዲህ ይላል “መጽሔተ ጥበብ” የሬድዮ ፕሮግራማችን ላይ የተቸገሩ፣ በክፉ ደዌ ተይዘው መታከሚያ ያጡ፣ ሰው መሐል ሆነው ሰው የራባቸው እና የሰው ያለህ የሚሉ ሰዎችን አድማጮቻችንን በማስተባበር የምንረዳበት”የፍቅር ቃል” በተሰኘው ዝግጅት ላይ ስማቸው እንዳይጠቀስ አደራ ብለው ከሚረዱ ከሚደግፉ በጎ አድራጊዎች አንዱ ወንድሜ ማዲንጎ አፈወርቅ ነበር” ብሏል።
በዘንድሮው የበጎ ሰው ሽልማት መርሐ ግብር ላይም በበጎ አድራጎት ሥራ የተሸለመው ወጣት ሄኖክ ፈቃዱም እንዲሁ ለዚህ በጎነቱ ምስክር ነው። ”ከአምስት ዓመት በፊት በአንድ ማለዳ ለአርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ ስልክ ደወልንለትና ለባይሽ ኮልፌ በጎ አድራጎት ብቸኛ እናቶቻችን አስቤዛ ለመግዛትና ለበዓል እንዲሆን ጫማ መጥረግ ፕሮግራም አለንና እባክህ ተገኝ አልነው፤ ‘ኮንሰርት አለኝ ዛሬ ወደ አሜሪካ እበራለሁ፣ ይህ በረከት ከሚያልፈኝ ለምን አሁን መጥቼ እኔ ጫማ አልጠርግም’ አለን። እንዳለውም ጓደኛችን አብርሽ ያለበት ቦታ በአምስት ደቂቃ ውስጥ ደርሶ ዝቅ ብሎ ጫማ በመጥረግ ሌሎች የምንወዳቸው ደጋጎች እንዲሳተፉ መነሳሳትን ፈጥሮልናል” በማለት ያስታውሳል። ለሙያ አጋሮቹ ድጋፍ በማድረግም ማዲንጎን የሚቀደመው ማንም እንደሌለ ብዙ አርቲስቶች ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።
ማዲንጎ ሀገር ወዳድ አርበኛም ነው። በተለይም ኢትዮጵያ በተፈተነችበት ወቅት እያመመው ግንባር ድረስ በመሄድና በማሰልጠኛ የሚገኙ ምልምል ወታደሮችን በማነቃቃት የራሱን ታሪክ የሠራ ብርቅዬ አርቲስት ነበር። ግንባር ድረስ በመዝመትም ማዲንጎ አፈወርቅ በወርቃማ ድምጹ አገር ወዳድ ወጣቶችን ሳይሰስት አዝናንቷል። ለዚህም በቅርቡ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እጅ እውቅና እና ሽልማት ተበርክቶለታል።
የማዲንጎ ዜና ዕረፍት ከተነገረ በኋላም ብዙዎች የተሰማቸውን ኃዘን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ገልጸዋል። ፕሬዚዳንት ሣሕለወርቅ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ፥ “ታዋቂው ድምጻዊ ማዲንጎ አፈወርቅ ገና በአፍላ ዕድሜ ላይ እያለ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየቱ በጣም አዝኛለሁ። ለቤተሰቡ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹና ለአድናቂዎቹ መጽናናትን ብርታትን እመኛለሁ” ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በበኩላቸው ባስተላለፉት የኃዘን መልእክት “አርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ በማረፉ የተሰማኝ ኀዘን ከባድ ነው። ለሀገሩ በአጭር እድሜው ብዙ የሠራ ከያኒ ነው። ሀገር በተደፈረች ጊዜ ሕመሙን እየቻለ ግንባር ተገኝቶ ሠራዊቱን አጀግኗል። ሠልጣኞችን አበርትቷል። ነፍሱ በሰላም ትረፍ።”ብለዋል።
የመከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል፣ የማዕድን ሚኒስትር ታከለ ኡማ፣ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል ከፋለ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል ተመስገን ጥሩነህ በአርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ ሕልፈተ ሕይወት የተሰማቸውን ኃዘን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ገልጸዋል። በአዲስ አበባ የሚገኘው የሩሲያ ኤምባሲም ኃዘናቸውን ከገለጹት መሀከል ተጠቃሽ ነው።
የሙያ አጋሮቹ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት በወዳጃቸው ሞት ልባቸው መሰበሩን ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል ድምጻዊት ሐመልማል አባተ ባስተላለፈችው መልዕክት “በሰማሁት ነገር እጅግ ደንግጫለሁ። ያለ እድሜህ ቀድመህ ብትሄድም አንረሳህም። ጓደኛዬ ነፍስህ በሰላም ትረፍ” በማለት ኃዘኗን ስትገልጽ ጎሳዬ ተስፋዬ በበኩሉ “ከሞያ ባልደረባነት አልፎ የልብ ወዳጅ ወንድሜ ማዲንጎ አፈወርቅን በህልፈተ ሕይወት ማጣቴን ማመን እስኪያቅተኝ ድረስ ኃዘኑን መቋቋም ከብዶኛል :: የመልካምነትህን ዋጋ እግዚአብሔር አምላክ ነፍስህን በአፀደገነት ያኑራት !!!” ብሏል። ተወዳጁ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) በበኩሉ ባስተላለፈው የኃዘን መግለጫ መልእክት “በዝነኛውና በተወዳጁ ወንድሜ አርቲስት ማዲንጎ አፈወርቅ ድንገተኛ ህልፈተ ሕይወት የተሰማኝን ኃዘን ስገልጽ እጅግ በተሰበረ ልብ ነው” ብሏል። ማዲንጎ ቅን ሰው ነበር ያለው አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ድምጻዊውን “ባለ ዕጹብ ተሰጥዖ” ሲልም አሞካሽቶታል።
አብዛኞቹም በዚህ ሰሞን የነበራቸውን የመድረክ ሥራ ሰርዘዋል። ሐሙስ መስከረም 19 ቀን 2015 ዓም የማዲንጎ ሥርዓተ ቀብር የተፈጸመበት እለት ነበር። በዚህ ዕለትም የታላቁ አርቲስት አስከሬን ከሙያ አባቱ ጥላሁን ገሰሰ አጠገብ አርፏል። በቀብሩ ሥነ ሥርዓት ላይ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ማትያስን ጨምሮ በርካታ ታላላቅ ሰዎች እና በብዙ ሺ የሚቆጠር ሕዝብ በቦታው ተገኝቶ ነበር። በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ከተደረገው ሥርዓተ ቀብር ቀደም ብሎ በወዳጅነት አደባባይ በተደረገው የሽኝት መርሐ ግብር ላይ ብዙዎች ስለ አርቲስቱ ያላቸውን ስሜት አጋርተዋል።
ከነዚህም መሀከል ልጁ ዲቦራ ማዲንጎ አንዷናት። “ማዲንጎ ልዩ አፍቃሪና ትሁት ሰው ነበር። እናንተ የምታውቁት እንደ አርቲስት ነው። የኔ ግን አባቢ ነው። ደስታ የሚሰማኝ በአጭር ጊዜ ሀገር የሚያኮራ ሥራ በመሥራቱ ነው” በማለት በሞቱ ብታዝንም በሥራው እንደምትኮራ ገልጻለች። አንጋፋው ድምፃዊ መሐሙድ አሕመድ “ዛሬ ልጄን አጥቻለሁ፤ አይዞህ ባይ ደጋፊዬን ምን ጎደለህ ባዬን አጥቻለሁ” በማለት የኃዘኑን ጥልቀት ተናግሯል። የመከላከያ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው ኮሎኔል ጌትነት አዳነ “ማዲንጎ ከመጣና ከሄደ ሥርዓት ጋር ሳይሆን ከሀገር ወዳድ ጀግኖች ጋር መሆኑን ለሠራዊቱ ግንባር ዘልቆ ፍቅር አሳይቷል። ሀገር መውደድ ማለትም ደመራው ወዴት ይወድቃል ብሎ የሚደረግ ሳይሆን እንደዚህ በጽናት የሚደረግ መሆኑን አሳይቷል” ብለዋል።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትሩ አቶ ቀጀላ መርዳሳ በበኩላቸው “ሞት የተፈጥሮ ሕግ ቢሆንም እንደ ማዲንጎ ያሉ የሀገር ተቆርቋሪዎች ሲያልፉ ያሳዝናል። ድምጻዊው በሁሉም ማኅበረሰብ ዝና እና ተቀባይነት ያለው ነው። ሁለት ዓይነት ሞት አለ፤ ተራ ሞትና እንደ ማዲንጎ ያለ የጀግና ሞት። በወያኔ ምክንያት አንዳንዶች በልባቸው ተሸነፍን ሲሉ እሱ ግን በልበ ሙሉነት ደፍሮ ሀገሩን ለማገልገል ወደ ግንባር ዘምቷል” በማለት ጀግንነቱን አስታውሰዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በበኩላቸው “ድምፃዊ ማዲንጎ አፈወርቅን በቅርብ አውቀዋለሁ። ሀገሩን የሚወድና እራሱን ለሀገሩ የሰጠ መልካም አርቲስት ነበር። ሀገራችን ጭንቅ ሲገጥማት ራሱን የሰጠ ሰው ነው። በሥጋ ቢያልፍም ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎችን ትቶ ነው ያለፈው” ሲሉ ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል ፤ ኪነ ጥበብ እና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊውና የሙዚቃ ሀያሲው አቶ ሠርጸ ፍሬስብሐት “ድምጻዊው ዜማን ዜማ እስከማይመስል ድረስ ከራሱ ጋር አዋህዶ የሚቀልጽ ሰው ነበር፤ አርቲስቱ በአጭር ጊዜ ዘመን አይሽሬ ሥራዎችን በመሥራት የሁላችንም ምሳሌ የሆነ ሰው ነው” በማለት የማዲንጎን የሙዚቃ አቅም ዘክረዋል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን መስከረም 22/2015