ኢትዮጵያዊነት ኢትዮጵያውያን በጋራ የጻፉት የጋራ ታሪካቸው ነው። ኢትዮጵያዊነት ለዘመናት ጠብቀንና ተንከባክበን ያዘለቅንው የጋራ ትውፊታችን ነው። ይሄ የጋራ ታሪካችን አሁን ላይ መልኩንና ቀለሙን እያጣ የመጣበት ሰሞን ላይ ነን። ኢትዮጵያዊነት ለምን በዚህ ልክ ዝቅ አለ ብለን ስንጠይቅ የምናገኛቸው ብዙ መልሶች አሉ። ከመልሶቹ መካከል ፖለቲካችንና ፖለቲከኞቻችን የአንበሳውን ድርሻ ይይዛሉ።
አሁን ላይ የተፈጠሩ አብዛኞቹ ችግሮቻችን በትናንት የፖለቲካ ሸር ነፍስ የዘሩ ናቸው። የፖለቲከኞቻችን ሃሳብ ምንም ይሁን ማረፊያው ሀገርና ሕዝብ ነው። ሕዝብ ከትናንት እስከዛሬ የፖለቲከኞቻችን ዱላ ገፈት ቀማሽ ነው። ይሄ ችግር እንዲያባራ ሕዝቡም ሆነ ፖለቲከኞቻችን በመተማመን ላይ የተመሰረተ የጋራ ሃሳብ ያስፈልጋቸዋል።
በእርቅና በምክክር ትንሳኤዋን የምታይ ሀገርን ለመፍጠር ሁሉም ዜጋ፣ ሁሉም ፖለቲከኛ ሊተባበር ይገባል። የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በመርህና በእቅድ ደረጃ ለያዘው የለውጥና የስብዕና ግንባታ ተልዕኮ የበኩላችንን በማዋጣት ሀገር በመፍጠር ሂደት ላይ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ ያስፈልጋል።
የብቻ ታሪክ የለንም። ታሪኮቻችንን የፈጠርናቸው በጋራ ሰርተን፣ በጋራ አስበን ነው። ዛሬም የጋራ ታሪክ ለመስራት በጋራ ማሰብና በጋራ መስራት ግድ ይለናል። ፖለቲካው የፈጠራቸው ማሕበራዊ ቀውሶቻችን የሚታከሙት በመነጋገር ብቻ ነው። ልብ ማፍቀር ሲጀምር መጀመሪያ የሚተወው ጥላቻን ነው።
አእምሮ ማሰብ ሲጀምር መጀመሪያ የሚተወው ስሜታዊነትን ነው። በፍቅርና በእውቀት አእምሮና ልባችንን አቀናጅተን ልትፈርስ ያዘመመች ሀገራችንን መገንባት ያስፈልገናል። ማፍቀር ከልክለነው እንጂ ልብ ለማፍቀር ነበር የተፈጠረው..ግን በከበበን ሴይጣናዊ ሃሳብ ልባችንን ፍቅር ከልክለን ጥላቻን አለመድነው።
አእምሮ በጎ ለማሰብ ነበር ህያው የሆነው ግን በከበበን ነውረኛ ድርጊት እኩይ አድርገን ፈጠርነው። እስኪ እንዋደድ.. ያለምክንያት እንድንወድ ነው ሰው የሆነው። ፖለቲከኞቻችን መነጋገር ቢችሉ፣ ችግሮቻችንን በይቅርታ ማለፍ ብንችል ያኔ የሚያቆመን አንዳች ሃይል አይኖርም ነበር።
ኒልሰን ማንዴላ በሮቢን ደሴት ላይ ለሃያ ሰባት ዓመታት ሲታሰር በዙሪያው ያሉ ክፉ ሰዎችን ሁሉ በይቅርታ ነበር ያሸነፋቸው። ከእስር ወጥቶ ያሰቃዩትን ሰዎች አላሳደደም፣ ለበቀል አልተነሳሳም በመተው ማሸነፍን ነው የመረጠው። እኛም ልባችንን ፍቅር፣ አእምሯችንን እውቀት አስተምረን ስለሀገራችን ስንል አንድ መሆንን ነው ማስቀደም የለብን።
ተነጋግሮ ለችግሮቻችን መፍትሄ ከመፈለግ ይልቅ ችግሮቻችንን ተንከባክበን ሌላ ችግር እንዲፈጥሩ ማድረግ የሚቀናን ነን። ባጭሩ መቅጨት እየቻልን ግን ደግሞ እሹሩሩ ብለን ያሳደግናቸው ብዙ ችግሮች አሉብን። ዛሬ ላይ አድገውና ጎልምሰው ጣጣ እያመጡብን ያሉት እነዛ ችግሮች ናቸው። ልንዋጋቸው ይገባል።
በጋራ የጻፍናቸውን ኢትዮጵያዊ ታሪኮቻችንን እንዳይንዱብን መፍትሄ ልንሰጣቸው ይገባል። በጋራ ያቆምናቸውን፣ በጋራ የቀለምናቸውን አለለ መልኮቻችንን እንዳያደበዝዙብን ሀይ ልንላቸው ይገባል። በየትኛውም የዓለም ሀገራት ታሪክ ውስጥ ደምቀው የተጻፉ ሕዝባዊ ታሪኮች የአንድነት ታሪኮች ናቸው። ሀገር የሚተሳሰቡ፣ የሚከባበሩ ሕዝቦች ካሏት የሚጻፍ ታሪክ አታጣም።
ሀገር በመነጋገር የሚያምኑ ዜጎች ካሏት ሥልጣኔ አይርቃትም። ታሪክ እውቀትን መሰረት ያደረገ ነው። ሰው በእውቀትም በድንቁርናም ታሪክ መጻፍ ይችላል። የአባቶቻችን ታሪክ በእውቀት የተጻፈ ሲሆን አሁን እኛ እየጻፍን ያለነው ብሄር ተኮር ታሪክ ደግሞ እውቀት የማይጠይቅ የድንቁርና ታሪክ ነው። በእውቀት ከፍ እንበል። በምክንያትና በአመክንዮ እንራመድ። በመነጋገርና በመተማመን ሃይል እናብጅ።
ሀገር መልካም ዜጋ ካላት ሁሌም ታሪክ አላት። ሀገር መልካም ዜጎች ካሏት ሁልም ሰላም አላት። ቤት ሲሰራ የቤቱን ህልውና ከሚያስጠብቁ ግብዓቶች ውስጥ ዋናዎቹ ዋልታና ማገር ናቸው። ቤት ያለ ዋልታና ማገር ዘመን ሊቆጥር አይችልም። ልክ እንደ ቤቱ ሁሉ የሀገርም ህልውና ዜጎቿ ናቸው። ዜጎች እርስ በርስ ካልተከባበሩ፣ እርስ በርስ ካልተባበሩ ሀገር መተማመኛ አይኖራትም።
እንዲህ እንደዛሬው ሰው በዘመን ላይ ሰይጥኖ ታሪክ ከማበላሸቱ በፊት ታሪኮቻችን በጋራ የተጻፉ ነበሩ። እሴቶቻችን ኢትዮጵያዊ ነበሩ። አሁን ሁሉም ነገር ወደ ቡድንና ወደ ግለኝነት ዞሯል። እያባላን ያለውም ይሄ ኢትዮጵያዊነትን የሻረው የእኔነት መንፈስ ነው። መነጋገር አለብን። የጋራ ታሪክ ለመጻፍ ራሳችንን ማዘጋጀት አለብን። የአባቶቻችንን አይነት ታላቋን ዳግማዊ ምድር ለመፍጠር ከዝምታ ወጥተን መነጋገር መቻል አለብን።
ተመልካች ከመሆን ወጥተን እኔም ያገባኛል ስንል ለውይይት በራችንን ክፍት ማድረግ ይጠበቅብናል። መሰረት የሌለው ያልሆነ ወሬ እያወሩ ሕዝብ ከማደናገር የድርሻችንን አንድ እንጨት በማዋጣት ኢትዮጵያን መስራት እንችላለን። ብዙዎች በተገነባ ሀገር እየኖሩ የእኛን ሀገር ለማፍረስ ቀን ከሌት የሚለፉ ናቸው። የእኛን ተለያይቶ መቆም የእኛን መነካከስ የሚፈልጉ እዛም እዚህም አሉ። እኚህን ሀገራት፣ እኚህን ግለሰቦች የምናሸንፈው ለአንድ ዓላማ በአንድ ስንቆም ብቻ ነው።
ወደሚጠቅመን መሄዱ ያዋጣናል። የሚጠቅመን ልዩነታችንን ትተን አንድ ሀገርና አንድ ሕዝብ መፍጠር ነው። የሚጠቅመን ያለ ልዩነት የኖሩትን አባቶቻችንን መምሰል ነው። የሚጠቅመን ከጥላቻና ከመለያየት ወጥቶ ወደሚደነቅ ሀገራዊ ልማት መሄድ ነው። ከማንም በፊት ሕዝብ ነበርን። ከማንም በፊት ሀገር ነበርን። ከማንም በፊት ስልጡን ማሕበረሰብ ነበርን። ከማንም በፊት የሥልጣንና የጀግንነት መሰረቶች ነበርን።
አሁንስ ምንድንነን? ራሳችንን፣ ፖለቲካችንን መፈተሽ ያስፈልጋል። ፍቅር ካለን፣ አንድነት ካለን አሁንም ቢሆን ትልቅ ሀገር መፍጠር እንችላለን። ከዛ በፊት ግን ለራሳችንም ለሌላውም ሰው እንሁን። በሰይፍ ሳይሆን በፍቅር፣ በትግል ሳይሆን በሃሳብ ሌሎችን ማሸነፍ እንልመድ። ውስጣችን የተዘራውን ተዘርቶም የበቀለውን በቅሎም መቶና ስልሳ ያፈራውን እኩይ የጥላቻና የመለያየት የሞት በለስ ነቅለን እንጣል።
ባላየንውና ባልሰማንው ፤በማናውቀውም ታሪክ መባላት ትተን በሰለጠነ አእምሮ ሀገር የሚጠቅሙ የጋራ እውነቶችን እንገንባ..ያኔ ሰው እንባላለን። ያኔ ኢትዮጵያ ታመሰግነናለች። ያኔ ትውልድ ያከብረናል።
የአባቶቻችን ኢትዮጵያ የተገነባችው በአንድነት መሰረት ላይ ነው። የአባቶቻችን ታሪክና ሥልጣኔ ዘመን የተሻገረው በአንድ ዓላማ በቆሙ ልቦች ነው። የእኛም ኢትዮጵያ ከዚህ ውስጥ የምትወጣ ናት። ኢትዮጵያችሁን በንጹህ ልባችሁ በንጹህ ነፍሳችሁ በንጹህ አሳባችሁ ውስጥ እናብቅላት። ይሄ ትውልድ ቀላል አይደለም። በአንድነት ከተነሳ የአባቶቹን እውነት መድገም የሚችል ነው። በአንድነት ከቆመ ዳግማዊ አድዋን የሚፈጥር ነው። ኢትዮጵያን ለመስራት ጊዜው የእኛ ነው።
በግዜአችን ለነገ ዋስትና የሚሆን መልካም ነገር እንስራ እንጂ እንጂ የሚጸጽተንንና የሚያስቆጨንን ነጋዊ ድርጊት በስሜት እንዳንከውን እንጠንቀቅ። ዛሬ ላይ ብዙ ነገራችንን እያጣን ያለንው ትናንት ላይ በሰናቸው ስህተቶቻችን ነው። በዙሪያዬ ያሉ ልክ እንዲሆኑ እኔ ልክ መሆን አለብኝ። የእኔ ልክ ሆኖ መቆም ለአዲሷ ኢትዮጵያ ትልቅ ዋጋ አለው።
የእያንዳንዳችን ወቅታዊ ሁኔታ አዲስ ለምንፈጥረው ሀገርና ሕዝብ የላቀ ዋጋ አለውን ከጥፋትና ከስህተት ርቀን ራሳችንን ልክ በሆነ ቦታ ላይ እናቁም ። ያኔ የሁላችን ኢትዮጵያ በሁላችን ልክነት ውስጥ ትፈጠራለች። ያኔ እንደ አባቶቻችን ትልቅ እንሆናለን። ያኔ የብርሃን ዘመን ይሆንልናል።
እኛ በባህልና በወግ የታነጹ ርህራሄን ለዓለም ያሳዩ የጋራ እሴቶች ያሉን ሕዝቦች ነን። የትኛውም ዓለም የሚደነቅበት ባህልና ትውፊት ያለን ትውልዶች ነን። ግን በዚህ ሁሉ በረከት ውስጥ የፍቅርን ስፍራ ተንጠራርተን አልደረስንበትም። እየኖርን ያለነው በአባቶቻችን ሀቅ ነው። ወጥተን የምንገባው በዚያ ትውልድ ታሪክ ነው። አሁን ላይ የብዙዎቻችን ሩጫ የብቻ ሀገርና የብቻ ታሪክ ለመፍጠር ነው።
መቶ ሃያ ሚሊዮን የሕዝብ ብዛት ባላት ሀገር ላይ፣ ከሰማኒያ በላይ ብሄር ብሄረሰቦች ተሰባጥረው በሚኖሩባት ምድር ላይ በምንም አይነት መልኩ የብቻ ሀገርና የብቻ ታሪክ የማይታሰብ ነው። ኢትዮጵያን የሰሯት ሰማንያና ከዛ በላይ የሆኑ ብሄር ብሄረሰቦች ናቸው። ኢትዮጵያን ያደመቋት የነዛ ብሄር ብሄረሰብ መልክና ቀለም፣ ቋንቋና ዘዬ፣ ባህልና ወግ፣ ስርዐትና ትውፊት ነው።
አሁንም ቢሆን ያለነዛ ብዙ እጆች፣ ያለእነዛ ብዙ ልቦች፣ ያለእነዛ ብዙ ሃሳቦች ኢትዮጵያን ሙሉ አድርገን መስራት አንችልም። ለኢትዮጵያ አሁን ያለነው ሁላችንም እናስፈልጋለን። ኢትዮጵያ መልኳ ፤ ሰማንያና ከዛ በላይ የብሄር ብሄረሰቦችን ቅይጥ መልክ፣ ቅይጥ ታሪክ፣ ቅይጥ ባህል ነው።
ሁላችንም የዚህ ሁሉ ብሄር ብሄረሰብ ቅይጥ መልኮች ነን። ተጋብተን ተዋልደናል። ተዋልደን አንድ ሆነናል። ኦሮሞ ሆነን አማራነት የተጋባብን፣ አማራ ሆነን ኦሮሞነት የተላለፈብን፣ ጉራጌ ሆነን እንደ ትግራዋይ የሆንን፣ ትግሬ ሆነን እንደ ጉራጌ የቆምን፣ ሲዳማ ሆነን ወላይታነት፣ ወላይታ ሆነን ሲዳማነት የተላበስን፣ ጋሞ ሆነን ሌላውን ብሄር የምንመስል ብዙ ነን።
ራሳችንን ብንመረምር በኢትዮጵያ ደግ እጆች ያልታቀፍን፣ በኢትዮጵያ ቅን ልቦች ያልተፈቀርን አንገኝም። ተጠጋግተንና ተነካክተን እስከኖርን ድረስ ሁላችንም አማራም፣ ኦሮሞም፣ ትግሬም ሌላውንም ብሄርብሄረሰብ ነን። ኢትዮጵያዊ ስንባል በዚህ ሁሉ የብሄር ስብጥር ውስጥ አልፈን ነው። ማናችሁ ስንባል ኢትዮጵያዊ ነን ምንለው የክብር ሸማ ባለበሱን ብሄር ብሄረሰቦች ተመጻድቀን ነው። በዚህ ሁሉ ውስጥ በቅለን፣ በዚህ ሁሉ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ሆነን ታዲያ ምናችን ነው የብቻ? የብቻ ኢትዮጵያዊነት የለም።
ከዚህ ሁሉ አንድነት ውስጥ፣ ከዚህ ሁሉ ድብልቅልቅ ውስጥ ራስን ማውጣት ፍጹም የማይቻል ነገር ነው። ከዚህ አንድ አይነት ፈትል ውስጥ፣ ከዚህ የጋራ ታሪክ ውስጥ የራስን አንድ ታሪክ መዞ ማውጣት ኢትዮጵያዊነትን ማጉደል ነው። ከዛ ሁሉ የብሄር ብሄረሰብ ቅይጥ ታሪክ ውስጥ የራስን አንድ ታሪክ ለመምዘዝ መሞከር ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው።
የኢትዮጵያ ቀሚስ የተሰፋው በእኔና በእናተ ባህልና ወግ፣ ልማድና ሥርዓት፣ ቋንቋና ዘዬ ነውና ከዛ ሁሉ ብዙ አይነት መርፌና ክር ውስጥ የራስን ብቻ መፈለግ ኢትዮጵያን ርቃኗን ማስቀረት ነውና ልብ ልንል ይገባል። ለኩራት ሲሆን የምንለብሰው፣ ለጥላቻ ሲሆን የምናወልቀው ኢትዮጵያዊነት የለም። ኢትዮጵያዊነት የትም መቼም ለብሰነው የምንዞረው የኩራት፣ የጽናትና የጀግንነት መንፈስ ነው።
ዛሬ ላይ እንደ ሀገር ግራ የተጋባንው ይሄን የአንድነት ካባ ሲሞቀን እያወለቅን ሲበርደን መደረባችን ነው። በብርዱም በጸሀዩም፣ በክረምቱም በበጋውም ኢትዮጵያዊነት ሁልጊዜም አንድ አይነት ነው። ሲመቸን የምንለው ዜግነት የለም። በችግሯም በደስታዋን ለሀገራችን ታማኝ መሆን አለብን።
ኢትዮጵያዊነት ትርጉም የሚኖረው እንደ አሁኑ ባለው አስቸጋሪ የፈተና ጊዜ ላይ ከጎኗ ስንቆም ነው። በነፈሰበት መንፈስ ሳይሆን ለሀገርና ሕዝብ ህልውና ሲባል ሰላምን፣ አንድነትን ማስቀደም ነው። በሃይል ሳይሆን በጥበብ፣ በአፈሙዝ ሳይሆን በመልካም አንደበት ተነጋግሮ መግባባት ያሻናል። እንዳይፈታ ሆኖ የተገመደውን አንድነታችንን እያሰብን፣ እንዳንለያይ ሆኖ የተሳሰረውን ታሪካችንን እያሰብን መጥፎ ነገሮችን መጸየፍ አለብን። ይሄ ሀገራችንን ከጦርነት ወደ ሰላም፣ ከእኔነት ወደ እኛነት፣ ከብሄር ፖለቲካ ወደ ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ የምንመልስበት ጥበብ ነው።
በአንድ ቀለም፣ በአንድ ሰሌዳ ላይ ኢትዮጵያን መስለው የተሳሉ አንድ አይነት ነፍሶች ልዩነት ፈጥረው ሲገፋፉ እንደማየት የሚያሳዝን ነገር የለም። የጋራ ታሪክ፣ የጋራ ባህል፣ የጋራ እሴት ያለው ሕዝብ በማይመጥነው ትንሽ አጀንዳ አንድነቱን ሲያጣ እንደማየት የሚያሳዝን ነገር የለም።
በሀገር ፍቅር እሳት፣ በሞታቸው ዋልታና ማገር በሆኑ በአባቶች ደምና አጥንት የተገነባች ሀገር በሰላም እጦት መከራዋን ስታይ እንደመስማት ምንም የሚያም የለም። የሀገራችን መጻኢ እድል በእኛ እጅ ውስጥ ነው። ከኋላችን ተፈጥረው ሀገርና ሕዝብ የሆኑ ምዕራባውያንና አውሮፓውያን እንዳያላግጡብን በምክክር የችግሮቻችንን ምንጭ ማድረቅ አለብን።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን መስከረም 2 / 2015 ዓ.ም