የጠላትነት ስዕል ፈጥሮና ይሄንኑ በሰነድ አስደግፎ ሕዝብን በተዛባ ትርክት እየሸነገሉ ለማሳመንና ከጎኑ አሰልፎ ጋሻ ለማድረግ የመስራት የግማሽ ምዕተዓመት ልምድ ያለው አሸባሪው ሕወሓት፤ ዘንድሮም እንደ ደደቢት ጥንስሱ የጥፋትና የጠላትነት ትርክትን የከተበ ምስጢራዊ ሰነድ አዘጋጅቶ “የማጠቃለያ ምዕራፍ አካሄድና ስትራቴጂ” በሚል የዳቦ ስም ሰጥቶ የአገር ክህደት ጉዞውን መቋጫ ለመስጠት ማቀዱን መረዳት ተችሏል። ሰነዱን የጥፋት ቡድኑ ዋና ዋና የፖለቲካና የጦር መሪዎች ያዘጋጁት ሲሆን፤ ይሄንኑ ሰነድ በምስጢር ይዞና በዚሁ ተመርቶ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን ለመበታተን የሚያስችላቸውን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ቀውሶች በማባባስ፤ ብሎም ከአጋር የሽብር ኃይሎች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት የተባባሰውን ችግር በሽብር አቀጣጥሎ ሥርዓቱን በመነቅነቅ አገር የማፍረስ ከፍ ያለ ሕልም መሰነቃቸውን ያሳያል። መቐለ ላይ ቁጭ ብለው ያዘጋጁት እና ነሃሴ 8 ቀን 2014 ዓ.ም ወደስራ እንዲገባ የወሰኑትን ይሄን ምስጢራዊ ሰነድ በወፍ በረር ለመመልከት እንሞክር።
ነገረ ሕወሓት _ ሰላም ጠል ጉዞው
የሽብር ቡድኑ ሲሻው ፋሽስት፣ ሲፈልግ ደግሞ አሃዳዊው መንግሥት ብሎ የሚጠራው በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የሚመራውን መንግስት የወሰደውን የተናጠል ተኩስ አቁምና የሰላም አማራጭ ተስፋ የሌለውና በቡድኑ ተቀባይነት እንዳልነበረው በሚያረጋግጥ ነው ጽሑፉ የሚጀምረው። በመግቢያው ክፍል “መንግስት ያዘጋጀው የሰላም አማራጭ ከመጀመሪያውም የማይሆንና የትግራይን ሕዝብ ጥያቄ ፈፅሞ የማይፈታ መሆኑ ቀደም ብሎም የታመነበት ነው፤” በማለት ነው ቡድኑ ፈጽሞ ሊቀበለው እንደማይችል ያውቀው እንደነበር ያረጋገጠው። ከዚህም ባለፈ በአፍሪካ ሕብረት አደራዳሪነት ላይ እምነት እንደሌላቸው በሰነዱ በግልጽ ያስቀመጡ ሲሆን፤ ችግሮች በሰላም ሳይሆን በጦርነት ብቻ እንደሚፈቱ የሚያስበው ይህ ቡድን “ለሁለንተናዊ የመጨረሻ ምዕራፍ ዘመቻ ልንዘጋጅ ግድ ይላል” ሲል ለዓላማው ተከታዮች ያሳስባል።
በአደራዳሪነት የተመረጡት የአፍሪካ ህብረት ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ፣ ምንም እንኳን ባካበቱት ልምድና በገነቡት ስም የምናከብራቸው ቢሆንም፤ …የሕዝባችን ዘላቂ የሰላም ዋስትና የሚረጋገጠው በዐቢይ የሰላም አማራጭ ሳይሆን፣ በክንዳችን ብቻ መሆኑን በፅኑ እናምናለን። የትግራይ ሕዝብ የሚበጀውም ጦርነቱ የጠየቀውን ያክል የሕይወት መስዋእትነት ከፍለን አዲስ አበባ የሚገኘውን ፋሺስቱን ዐቢይ መንጥረን ሕዝባዊ መንግሥት ማቋቋም ስንችል ብቻ ነው።
በዚህ ሂደትም ዓለማቀፉን ማህበረሰብ በማስመሰል የፕሮፖጋንዳ አሰራራቸው መሰረት ከጎናቸው ማሰለፍ እንደሚገባቸው በአግባቡ በሰነዱ ያስቀመጡ ሲሆን፤ ይሄንኑም “በጦርነት ሂደት ውስጥ የመረጃ ልዕልና ለማግኘት እና በርካታ ኃይሎችን ከጎንህ ለማሰለፍ ከሚያስችሉ ሁኔታዎች አንዱ፣ ለዓለም አቀፉ ማህብረሰብ ችግሮችን በሰላም ለመፍታት ቁርጠኝነት እንዳለህ አስመስለህ እራስህን ማቅረብ መሆኑ ሊረሳ አይገባም፤” በሚል በግልጽ አስፍረውታል።
ለዚህ ደግሞ የራሳችንና የአጋሮቻችን ዝግጁነት ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለ ሁኔታ ይገኛል። የውስጥ ትግላችን በማገዝ የሚንቀሳቀሱ እንደ ኦነግ የመሳሰሉ አጋሮቻችን እንዲሁም በተለያዬ የዓለም መአዘናት የሚገኙ የትግራይ ዲያስፖራና ዓለም አቀፍ አጋዦቻችን በዚህ ጊዜ የተሳካ ጥምረት በማድረግ ወደ አዲስ አበባ በምናደርገው እንቅስቃሴ ከጎናችን መሆናቸውን የሚያረጋግጥ መሆኑን የክልላችን ዋና ስራ አስፈፃሚ በዝግ ባደረገው ውይይት አረጋግጧል። ስለሆነም ይሄ ፅሁፍ ከአጋሮቻችን ጋር የምንከተለውን ስትራቴጂ አስመልክቶ በየደረጃው ለሚገኝ አመራር ግብአት እንዲሆን የቀረበ ነው” ሲል ወደ ዋና ጉዳዩ ያንደረድራል።
የሕወሓት ስልታዊ “መንታ ገጽ”ነት
አሸባሪው ሕወሓት የአማራ ሕዝብን በጠላትነት ፈርጆ ትግል ከመጀመሩም በላይ፣ በ27 ዓመታት የስልጣን ዘመኑ አማራ ጠልነቱን በተግባር ያሳየ ኃይል ነው። በዚህም በርከት ያሉ አማራ ጠል ተረኮችን ከማዘጋጀትና ከማኖር ባለፈ፤ በልዩ ሁኔታ የአማራው ሕዝብ ተረጋግቶና ራሱን አደራጅቶ እንዳይኖር አድርጎት ቆይቷል። በኋላም ከስልጣን ተወግዶ መቐሌ ከመሸገና በአገር መከላከያ ሰራዊት ላይ ጥቃት ፈጽሞ የአገር አፍራሽነት ተልዕኮውን ባረጋገጠ ማግስት፤ በአማራ ሕዝብ ላይ ሂሳብ አወራርዳለሁ ብሎ በፈጸመው ወረራ እልፍ አማራዎችን በጅምላ ጨፍጭፏል፤ ሃብት ንብረታቸውን ዘርፏል፣ አቃጥሏል፤ አውድሟል፤ ለማይሽር የአካልና ሥነልቦና ጉዳትም ዳርጓል። በተመሳሳይ ይሄንኑ የእርኩሰት ተግባር በአፋር ሕዝብ ላይ ፈጽሟል።
ሕወሓት በተለይ በአማራ ህዝብ ላይ ያለው የማይወላውል የጥላቻና የጠላትነት ስዕል እንዳለ ቢሆንም፤ እንደ ጊዜና ሁኔታው የአማራን ሕዝብ የጠላትነት ደረጃና ወሰን ከፍና ዝቅ እያደረገ፣ አንዳንዴ ልሒቁን ከአርሷደሩ ለመነጠል፤ ሌላ ጊዜ የጥምር ኃይሉን ከሕዝቡ ለመነጠል፤ አንዳንዴም ሙሉ ሕዝቡን ወዳጅ አድርጎ የመሳል፤ ከፍ ሲልም የታጠቀውን ጥምር ኃይል ሳይቀር በፌዴራል መንግስቱ ተታልሎ የገባበት እንጂ የአማራ ሕዝብ ሕዝባችን ነው፤ ከእነሱ ጋር ጠብ አንፈልግም፤… ሲል መደመጡ የተለመደ ሆኗል። በዚሁ ሰነድም እንደቀደሙት ሁሉ ተመሳሳይ የሆነ የአስልቶ አራጅነት ስልታዊ የጠላትነት ገጽ መፍጠር የታየበት ነው።
በዚህ ረገድ በሰነዱ እንዲህ አስፍረውታል፡- የአማራ ተስፋፊ ሃይል ከፋሽስት ዐቢይ በሚሰጠው ትዕዛዝ መነሻ እና በቆየ የትምክህት ታሪኩ፣ ተስፋፊነቱና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል ለመጫን የሚያደርገው እንቅስቃሴ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ …በአማራ ክልል ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ ሃይሎች ጦርነቱ በፈጠረላቸው አጋጣሚ ተጠቅመው በርካታ ገንዘብ ያገኙ ሲሆን፤ ይህም ራሳቸውን በትጥቅ ያደራጁ ፅንፈኛ ተስፋፊ የአማራ ሃይሎች እንዲፈለፈሉ አድርጓል። ይሄ ሁኔታ የተፈጠረው በሌሎች ክልሎች ቢሆን ኖሮ ለትግላችን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነበር። ነገር ግን ይሄ ሁኔታ የተፈጠረው በአማራ ክልል መሆኑ… ከዚህ ቡድን ጋር ወዳጅነት ሊኖረን አይችልም፤ ይልቁንም ከሁኔታው በመነሳት ቡድኑን በጠላትነት እንፈርጀዋለን።
ይሄ ፅንፈኛ የአማራ ተስፋፊ ሃይል… በክልሉ ያገኘውን ሕዝባዊ ተቀባይነት ሽፋን በማድረግ እና ጠንካራ ቅንጅት በመፍጠር ከአማራ ክልል መንግሥት የሚስተካከል አቅም መፍጠር በመጀመሩ እና ይሄ ሃይል ራሱን “ፋኖ” ብሎ በመጥራቱ የዐቢይ አስተዳደር በወሰደው ርምጃ በተወሰነ መልኩ መዳከም ታይቶበታል። …ይሄ ሁኔታ የትግራይ ሰራዊት እንደ ጥሩ አጋጣሚ ሊጠቀምበት የሚገባ ሲሆን፤ …ይህንን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ሰፊ የፕሮፓጋንዳ ስራ በመስራት የተፈጠረውን መሻከርና ክፍተት የበለጠ እንዲከር ማድረግ ይገባል።…
በአማራ ክልል በተወሰነ መልኩም ቢሆን ፊቱን ወደ ልማት ያዞረ ገበሬ እየታየ ነው። …ይህ ሃይል የእርሻ ውጤቱን ወደ ቤቱ እንዲያስገባ ልንፈቅድለት አይገባም። …ለጦርነት ባልተዘጋጁበትና በዐቢይ የሰላም ጥሪ በተዘናጋበት ጊዜ አስፈላጊ የሚባል ርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል። …ከወታደራዊ ዘመቻዎቻችን ጎን ለጎን የቅማንት የወሰንና ማንነት ጉዳዮችን በሚመለከት እዛ አካባቢ ከፍተኛ ሕዝባዊ ጥያቄ እንዲነሳና አካባቢውን ወደማያባራ ፖለቲካዊ ማህበራዊ ችግር ሊለውጥ የሚያስችሉ ስራዎች መስራት አስፈላጊ ነው።
ተደማሪ የጠላትነትና አጋርነት ትንተናዎች
የሽብር ቡድኑ በአማራ ሕዝብ ላይ ከያዘው የጠላትነትና የስልታዊ የለውጥ ጉዞው ባሻገር፤ የአፋር፣ የሶማሌ እንዲሁም ኦሮሚያ አካባቢ አሉብኝ የሚላቸውን ሥጋቶች፤ አሉኝ የሚላቸውን እድሎችና አጋሮች በሰፊው ተመልክቷል፤ በምስጢራዊ ሰነዱም በግልጽ አስፍሯል። ለምሳሌ፣ በአፋር ያለውን ስጋትና ተስፋ ሲያስቀምጥ፤ “የዓፋር መንግሥት… ከዐቢይ አስተዳደር በሚሰጠው አድናቆትና ቁጥር የሌለው የትጥቅ እገዛ አይኑ የታወረ፣ ጆሮው የተደፈነ በመሆኑ፣ ትግላችን በሚያግዙ የዓፋር የነፃነት ታጋዮችና ቤተሰቦቻቸው አፈናና ግድያ እየፈፀመባቸው ይገኛል” በማለት ነው። በተመሳሳይ፤ “በሱማሌ ክልል ያለው የሙስጠፌ ዑመር አምባገነን አስተዳደር… የአሸባሪውን አልሸባብ እንቅስቃሴ ለመግታት በሚል ምክንያት በርከት ያለ ወታደራዊ ትጥቆች የታጠቀ እና ዝግጅት ያለው ሲሆን፣ የዐቢይ ሰራዊት በትግራይ ሰራዊት ላይ ባደረጋቸው ዘመቻዎች በንቃት የሚሳተፍ የትግራይ ሕዝብ ጠላት በመሆኑ፣ በክልሉ ከሚንቀሳቀሱ እና የጋራ ጠላታችንን ከሚታገሉ የአልሸባብ ሴሎችና ከኦጋዴን ታጋዮች ጋር የመረጃ ልውውጥ እገዛ እና ስትራቴጂ ሥራዎቻችን ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል” ሲል አስቀምጧል።
ከዚህ በተጨማሪ በኦሮሚያ ክልል ስለሚንቀሳቀሰው እና ቀደም ብለው “ያልተቀደሰውን ጋብቻ” ለሽብር አብሮ የመስራት ትብብራቸውን ይፋ ባደረጉት ሸኔ ላይ ያለውን ተስፋ እና ተስፋውን እውን በማድረግ ሂደት እያጋጠሙ ያሉ ፈተናዎቹን ከመፍትሄዎቻቸው ጋር አሰናስሎ ያቀረበበት ሃቲት ተጠቃሽ ነው። ሃቲቱም በሰነዱ በሚከተለው መልኩ ተቀምጦ ይገኛል፡- በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሰው የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት የትግላችን አጋር መሆኑን በግልጽ ማሳወቃችንን ተከትሎ እንዲሁም በክልሉ ያለው ይዘት እየሰፋ በመምጣቱ የተነሳ ፋሺስቱ ዐቢይ ከሰሜን ግንባር በማያንስ የተጠናከረ ኦፕሬሽን እያካሄደ እንደሚገኝ የፋሺስቱ የመንግሥት መገናኛ ብዙሃን እየተቀባበሉት ይገኛሉ። ከዚህ በተጨማሪ ግንባር ላይ የሚገኙ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት አመራሮች እንደሚነግሩን ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰባቸው እንዳለና የትግል ስልት መቀየር ግዴታ እንደሆነባቸው ማየት ተችሏል። …ይሁን እንጂ መንግስትን በማዳከም ወደ አዲስ አበባ የሚደረገው የመጨረሻ የትግል ምዕራፍ ላይ የቅርብ አጋዦች እነዚህ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት በመሆናቸው ሊስተካከሉ የሚገባቸው እና ባለፈው ግምገማ የታዩ ክፍተቶች ታርመው ወደ መጨረሻው ምዕራፍ እንዲዘጋጁ ማድረግ አስፈላጊ ነው።
ለማጠቃለያው ምዕራፍ ራስን ማዘጋጀት
የሕወሓት የሽብር ቡድን ጦርነትን እንደ ሕልውና ማስቀጠያ አድርጎ እንደመያዙ፣ ለዚህ ጦርነት የሚውለውን የሰው ሃይልም ሆነ ሎጀስቲክስ ማሰባሰብ ትልቁ የቤት ሥራው ነው። ለዚህ ሥራው ደግሞ ቢችል ቀድሞ በፈጠረው የጠላትነት ሥዕል ታግዞ ፍላጎቱን ማሟላት፤ ሳይችል ደግሞ በሰብዓዊ ርዳታ መያዣነት የሰው ሃይሉን ማጠናከር፤ ካልሆነም በቅርቡ ሲያደርግ እንደነበረው ከጎኑ ያልተሰለፈ ቦታ እንደሌለው አስፈራርቶ በመንገር የሕዝብ ማዕበል መፍጠር ስትራቴጂካዊ መንገዶቹ ናቸው። የሎጀስቲክስ ጉዳዩም ቢሆን፣ ምግብን ከሰብዓዊ ድርጅቶች በመዝረፍና ሕዝቡን በማስገደድ፤ ትጥቁንም በመንግስትነት ዘመኑ ደብቆ ካከማቸውና ከዘረፈው፣ እንዲሁም ከታሪካዊ የኢትዮጵያ ጠላቶች በሚያገኘው የሚያሰባስበው ነው። ይሄው እውነት በተለያዩ ጊዜያት ሲገለጽ የቆየ ሲሆን፤ በዚህ ምስጢራዊ ሰነድ የተመላከተውም ይሄው ሃቅ ነው።
በሰነዱ ባሰፈሩት መሰረትም፤ እስከ ቀበሌ ያሉ አደረጃጀቶችን ተጠቅመው ባካሄዱት ስራ ባለፉት ወራት ብቻ በርከት ያሉ ወጣቶች ወደ ታጣቂ ቡድኑ እንዲገቡ በማድረግ የተሳካ ስራ ሰርተዋል። ለዚህም የትግራይ ወጣቶችን አሁን የሚደረገው ትግል ወደ አዲስ አበባ የመግባት የመጨረሻ ምዕራፍ ትግላቸው እንደሆነ በማሳመን የሕወሓት አመራር ካለፈው ዘመቻ ራሱን ገምግሞ የነበሩበትን ክፍተቶች በሙሉ በመዝጋት ለመንቀሳቀስ ቆርጦ መነሳቱና ድል አይቀሬ መሆኑን መላው የትግራይ ወጣትና ሕዝቡን ለማሳመን የሚያስችል የሚዲያ ሥራ እየተሰራ ይገኛል።
ከዚህ በተጨማሪ፣ “የመሳሪያና ትጥቅ አቅም አለማጠናከር ባለፉት ዘመቻዎቻችን የነበረብን ክፍተት እንደሆነ ተገምግሟል። ይህንን ግምገማ በማየት በውጭ ያሉ አጋዦቻችን በአስቸጋሪ እና አጣብቂኝ ጊዜ ውስጥም ቢሆን ችግሩን አልፈው ዘመናዊ ትጥቆች እንድንታጠቅ አድርገውናል። ይህም ሆኖ የዚህ ዘመቻ ምዕራፍ መራርና በርካታ መስዋእትነት የሚጠይቅ በመሆኑ አሁንም ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ዘመናዊ ትጥቅ ለመከላከያ ሃይላችን እንዲያቀርቡልን የሚያስችሉ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ከውስጥና ከውጪ ተባባሪዎቻችን ጋር ያለንን ስራ አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል፤” ሲል ያስቀምጣል።
የስንቅ አቅርቦቱን አስመልክቶም፤ “የታጋዮቻችን ትጥቅና ስንቅ የሟሟላት ስራ በዋናነት በነፃነቱ የማይደራደረው ሕዝባችን ተግባር ይሆናል፤ በትግራይ የሚገኙ የዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች ሰብአዊ ድጋፍ ማከማቻ መጋዘኖች ፋሽስቱን ለማስወገድ በምናደርገው ትግል የስንቅ አቅርቦት እንዳይጓደል በቁጥጥራችን ስር ልናደርጋቸው ይገባል። ይሄም ከዓለም አቀፍ የእርዳታ አስተባባሪዎች አወንታዊ የሆነ ግንኙነቶች በማጠናከር ረሃብና ተረጅነት ከሕዝባችን ትከሻ ላይ ለማውረድ ለምናደርገው ትግል ደጋፊ እንዲሆኑና ከጎናችን እንዲቆሙ ልናደርግ ይገባል፤” በማለት ነበር ከጫካ ጀምሮ የኖረበትን አሰራር ዛሬም አለመልቀቁን ያረጋገጠበትን እውነት ያሰፈረው።
የመረጃ ልውውጥና ፕሮፖጋንዳ ስልት
ቡድኑ በውስጥም በውጪም ካሉ ተባባሪ ሃይሎች የመረጃ ቴክኖሎጂዎችን የማግኘትም ሆነ የሃሰት ፕሮፖጋንዳዎችን ተቀናጅቶ የማሰራጨት ልምዱ ቀደም ባሉት የአገር ማፍረስ ስምሪቶቹ ተስተውሏል። አሁንም በዚህ ምስጢራዊ ሰነዱ ይሄው እውነት እንዲህ ተሰድሮ ይገኛል፡- አንዱና ዋነኛው የውስጣችን ጥንካሬ መገለጫ ውስጣዊ አቅማችንና የአሸናፊነት ስነልቦና በመሆኑ ይሄን ከፍ የሚያደርጉና የሚያነቃቁ ስልጠናዎችና የዶክመንተሪ ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል። ከሠራዊታችን በተጨማሪ፣ መላው የትግራይ ሕዝብና በኢትዮጵያም ሆነ ከኢትዮጵያም ውጪ ለሚገኙ የትግል አጋሮቻችን ድላችን እንደማይቀር እያበሰርን እስከ መጨረሻ መዳረሻችን አብረውን እንዲጓዙ የሚያስችል ስራዎች፣ ስልጠናዎች፣ የመረጃ ልውውጥና ፕሮፖጋንዳ ልዩ ትኩረት ይሰጠዋል።
በተመሳሳይ በጠላት ላይ ሽብር፣ ፍርሃትና የስነ ልቦና ጫና መፍጠር አስፈላጊ በመሆኑ፣ ሽብር የሚያስፋፉ እና በመሀል አገር ያለው ሕዝብ ሳይቀር በመንግሥት አቅም ላይ ያለው እምነት እንዲሸረሸር የሚያደርጉ መረጃዎች በአገር ውስጥና በውጪ ሚዲያዎች በሙሉ ማዳረስ ያስፈልጋል። …ከአገር ውጪ የሚገኙ የኦሮሞ ፖለቲከኞችና የሌሎች ብሄር ብሄረሰቦች ልሂቃን የሚመሯቸው በውጪ አገር ያሉ ሚዲያዎች፣ የጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ፀጋይ ርእዮት ሚዲያ፣ የጋዜጠኛ ኤርሚያስ ለገሰ ኢትዮ 360 እና ሌሎች በትግራይ ተወላጆች የሚመሩ ሚዲያዎች ተከታታይነት ያላቸውና በዋነኝነት ፋሺስት ዐቢይ ላይ ያነጣጠሩ የማዳከምና የመበተን ስራዎች ሊሰሩ ይገባል። ይሄም በፓርቲያችን የፕሮፖጋንዳ ክፍል በሚቀረፁ መልዕክቶችና ይዘቶች የሚመራና በላይኛው አመራሮች ክትትል የሚደረግበት ይሆናል።
ከዚህ በተጨማሪ ወደ አማራ ክልል በተፈናቃይና በተጓዥ ስም የሚገባ ሃይል ሊዘጋጅና ሥራውም በከፍተኛ ጥንቃቄ ሊፈፀም ይገባል። ይህ ወደ ክልሉ የሚገባ ሃይል በተቻለው መጠን የትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቅሞ ወደ አዲስ አበባ ዙሪያም ሊጠጋ ይገባል። አስርገን የምናስገባው ሃይል በየደረሰበት አካባቢዎች መረጃና ሁኔታ የሚጠቁምዋቸው አመራሮች ይኖራሉ። ይህ ስራ ከዚህ በፊት እንዳጋጠመን ታጋያችን ለተልዕኮ ዝቅተኛ ትኩረት በመስጠት በማያስፈልግ የምዝበራና ዘረፋ ተግባር እንዳይሳተፍ ከፍተኛ የሆነ የዲስፕሊን አቅጣጫ ይሰጣል።
ሕዝብን እረፍት የመንሳት ሴራ
የሽብር ቡድኑ አንዱና የሚታወቅበት ሴራ፣ ሕዝብ በአንድ ሃሳብ ሆኖ በአንድነት እንዳይቆም የተለያዩ አጀንዳዎችን በማቀበል ረፍት እንዳያገኝ በማድረግ ከመንግስት ጋርም ሆነ እርስ በእርሱ እንዳይናበብ ማድረግ ነው። ይሄ የህዝብ አለመናበብና በተለያዩ ጉዳዮች ተጠምዶ አንድነቱን እንዲያጣ የማድረግ ሴራው ደግሞ ሕብረት በሌለው ሕዝብና መንግስት ውስጥ በቀላሉ ሰርጎ ለመግባትና የሚፈልጉትን ነገር ማግኘት ይቻላል የሚል እምነት በማሳደራቸው ነው። በርግጥ ይሄ ሕልማቸው የሚሳካ ባይሆንም፤ ይሄን አካሄዳቸውን ግብ በሚከተለው መልኩ ነው ነድፈው ያኖሩት፡-
በግንባር ላይ ከሚገኘው ድል ባልተናነሰ፣ የጦርነት ነጋሪት በመጎሰምና የተሳካ የፕሮፖጋንዳ ስራ መስራት ብቻውን የሚያደርሰው ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ችግሮች ጠላትን ከፍተኛ ዋጋ ያስከፍሉታል። ስለሆነም ፋሺስት የዐቢይ መንግሥት በችግር ጊዜ አሳክቼዋለሁ የሚላቸው የእርሻ ዘርፍም ሆነ የኢኮኖሚ ልእልና በማደናቀፍ ወደ ኋላ መመለስ ከተቻለ በስርዓቱ ላይ ከፍተኛ ኪሳራ ማድረስ ይቻላል። …የእርሻ ዘርፉ እንዲደናቀፍ በየአካባቢው ግጭት በመቀስቀስ እና ግጭት ለመቀስቀስ የሚያስችሉንን ሃይሎች በማገዝ እረፍት በመንሳት፣ የልማት ስራዎችን ትቶ እሳት ማጥፋት ላይ እንዲጠመድ ማድረግ በረዥም ጊዜ የዐቢይ መንግሥትን ለማዳከም የሚያግዝ ሲሆን፤ ባጭር ጊዜም ደግሞ ለሚካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ የጠላት አቅም እንዲዳከም ትልቅ ጥቅም አለው።
ፖለቲካዊ አጀንዳዎች በተለይም የማንነት ጥያቄዎች በጥንቃቄ ሊፈቱ የሚችሉበት እድል ከተፈጠረ የዐቢይ አገዛዝ ጎልቶ የሚወጣበት እድል እንደሚኖረው ቀደም ብሎ ከተፈቱ የማንነት ጥያቄዎች ማየት ይቻላል። ስለሆነም፣ ማንኛውንም አይነት ማህበራዊና ፖለቲካዊ አጀንዳዎችን ሳንንቅ ወደ አደባባይ እንዲመጡ በማድረግ፣ ጥያቄዎቹ ሕዝባዊ ቁመና እንዲላበሱ ማድረግ አስፈላጊ ነው። እነዚህ ጉዳዮች ተገቢ ትኩረት እንዲያገኙ ሚዲያዎች፣ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች አጀንዳውን የማቀጣጠል ሚናቸውን በሚገባ እንዲወጡ በማገዝ የፋሺስት ዐቢይን ውድቀት ሊያፋጥኑ ይገባል። ለዚህም አሃዳዊውን የዐቢይ አገዛዝ ከሚቃወሙ ፌደራሊስት ሃይሎች ጋር በተጠናከረ መንገድ ግንኙነታችንን በማደስ፣ በደቡብ ክልል እየታየ ያለውን የክልልነት ጥያቄ በደንብ እንዲጠናከር በማድረግ እንዲሁም ተመሳሳይ የክልልነት ጥያቄዎች በተጠናና በተናበበ መልኩ በሌሎች አከባቢዎች እንዲነሱ ማድረግ ይገባል።
በሌላ በኩል፤ ኢትዮጵያዊያን በተለይም የከተማ ነዋሪዎች፣ መንግሥትን የሚቃወሙት በተለያየ የፖለቲካ አጀንዳዎች አይደለም፣ ከፖለቲካ አጀንዳዎች ይልቅ በቀጥታ ከዕለት ኑሯቸው ጋር የተያያዘው የኑሮ ውድነት ዋና መንግሥትን የሚቃወሙበት አጀንዳ መሆኑ ግልፅ ነው። በርከት ያሉ ዜጎች የኑሮ ውድነቱን መቻል አቅቷቸዋል። ከባድ ፈተና ውስጥ እንዳሉ ብዙ ማሳያዎች አሉ። ስለሆነም የኑሮ ውድነቱን የሚያባብሱ ኢኮኖሚያዊ አሻጥሮችን በተቀናጀ መንገድ መፈጸም አስፈላጊ ነው። …ስለሆነም የተመረጡ አምራች ድርጅቶችንና መጋዝናቸውን ማጥቃትና ማፍረስ፣ ከእርሻ እስከ ገበያ ባለው ሂደት የዕለት አስቤዛ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ እንዲኖረው ማድረግ፣ ከውጪ የሚገቡ ሸቀጦች እና ነዳጅ እንዲስተጓጎል ዋና ዋና የማስገቢያ ኮሪደሮች በመቆጣጠርና ሌሎች እርምጃዎችን በመውሰድ በአገሪቱ የኢኮኖሚ ችግር እንዲፈጠር እና እንዲባባስ ማድረግ ዋናው ትኩረታችን እናደርገዋለን።
ማሙሻ ከአቡርሻ
አዲስ ዘመን ጳጉሜን 3/2014