እንደ መግቢያ
“ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲዖልም ቢሆን እንገባለን” ሲል በመጨረሻው የጥፋት ጉዞው ዋዜማ ላይ ቆሞ የመፈጠርና መኖሩን ምክንያት ግልጽ ያደረገው የሕወሓት ቡድን፤ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ሌሊት በተፈጸመው የአገር ክህደት አገር አፍራሽ ተልዕኮ ተሸካሚነቱን ለሁሉም ግልጽ አድርጓል፡፡ ከዚህ የክህደት ተግባሩ ማግስት ጀምሮም በኢትዮጵያ በተለይም በሰሜኑ ክፍል በዚሁ ቡድን አማካኝነት ተደጋጋሚ ጦርነት ተስተውሏል፡፡ አገር አፍራሽነቱን ከሂሳብ አወራራጅነት ስሜቱ ጋር አቀናጅቶ ወደ አፋርና አማራ ክልሎች ለወረራ በተሰማራባቸው ወራትም ከሰው ልጅ የማይጠበቅ ሰይጣንን ያስቀና አረመኔያዊ ተግባራትን ፈጽሞ ጉዞውን በሽንፈት ደምድሞ ተመልሷል፡፡ ክስተቱ ታሪክ የማይዘነጋው በርካታ ሰብዓዊም ቁሳዊም ውድመት አስከትሏል፡፡
ዛሬም ይሄው የጥፋት ተልዕኮ ኑረቱ(የጥፋት አዙሪቱ) አገርሽቶበት በመንግስት በኩል የተዘረጋውን የሰላም እጅ ባለመቀበል ለሦስተኛ ጊዜ በአማራ እና አፋር ክልሎች በኩል ጦርነት ጀምሯል፡፡ ይሄን ተከትሎም ቀድሞ በመከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ የፈጸመውን ጥቃት “በአርባ አምስት ደቂቃ ውስጥ መብረቃዊ ጥቃት ፈጽመናል” ብሎ በራሱ ሰዎች አምኖም ጭምር ጥቃት ተከፈተብኝ ሲል እንደነበረው የክህደት ግብሩ ሁሉ፤ አሁንም በበቂ ዝግጅትና እቅድ የጀመረውን ጦርነት “በመንግስት በኩል ወረራ ተፈጸመብኝ፤ ጥቃት ተከፈተብኝ” በሚል የማደናገሪያ ቅጥፈቱ ጥፋተኝነቱን ለመሸፋፈን በብርቱ እየጣረ ነው፡፡ እኔም ይሄን የሽብር ቡድኑን ቅጥፈት በመሰረቱ ለመረዳት ያስችላሉ ያልኳቸውን ጉዳዮች “ዓባይን በጭልፋ” ቢሆንም ጥቂት ለማነሳሳት ፈለግሁ፡፡
አሸባሪው ሕወሓት ምን ይዞ ጦርነት ጀመረ?
መንግስት የሕወሓትን ሁለተኛ ዙር አገር የማፍረስ ወረራ በቀለበሰ ማግስት ያደረገውን የተናጠል ተኩስ አቁም እና ተደጋጋሚ የሰላም አማራጭ ጥሪን ጆሮ ነፍጎ የቆየው ይህ የሽብር ቡድን፤ በእነዚህ ጊዜያት የሰላም ውይይት ሂደቶችን የሚያደናቅፉ ትርጉም አልባ ምክንያቶችን እየደረደረ ከሰላም ይልቅ ስለ ጦርነት እያሰበና እየተዘጋጀ ቆይቷል፡፡ ይሄንን እንዴት ሊያደርግ ቻለ? የሚል ጥያቄ ቢነሳም፤ የሚከተሉትን ጥቂት ማሳያዎች በማንሳት መመልከትና መረዳቱ ተገቢ ይሆናል፡፡
የመጀመሪያው ጉዳይ፤ መንግስት የሽብር ቡድኑን የጥፋት ጉዞ ከሰሜን ሸዋ ገትቶ ወደ ነበረበት ዋሻ በመለሰው ማግስት ስለ ትግራይ ሕዝብ ሲባል ጦርነት አቁሞ የሰብዓዊ ድጋፍ እንዲገባ ማድረግ እና የሰላም ንግግር መጀመርን ነበር ታሳቢ ያደረገው፡፡ ይሁን እንጂ የሽብር ቡድኑ የሰብዓዊ ድጋፍ መድረሱም ሆነ የሰላም ንግግር ማድረጉን ፈጽሞ አይፈልገውም ነበርና ሁለቱም እንዳይሳኩ በብዙ ለፍቷል፡፡ የሰብዓዊ ርዳታ ኮሪደሮችን በታጣቂዎቹ እንዲዘጋ፤ የሰላም አማራጩም በተደጋጋሚ ትንኮሳ እንዳይሳካ ጥሯል፡፡ ይሄን ተከትሎም መንግስት የትግራይን ሕዝብ ሰብዓዊ ርዳታ እንዲደርሰው ባደረገው ያላሰለሰ ሥራ የሰብዓዊ ርዳታ ማስገቢያ ኮሪደሮች ከሽብር ቡድኑ እንዲጸዱ በማድረግ ከተባባሪ ዓለማቀፍ ግብረሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር በአየርም፤ በየብስም ድጋፍ እንዲደርስ ማድረግ ችሏል፡፡
በዚህም ባለፉት ወራት ብቻ ከአምስት ሺህ 600 በላይ በመኪና /በየብስ ትራንስፖርት/፣ ከ270 በላይ በረራ /በአየር ትራንስፖርት/ ታግዞ የሰብዓዊ ድጋፍ ወደ ክልሉ እንዲገባ ተደርጓል፡፡ ሆኖም የሰብዓዊ ድጋፉ ለሕዝቡ እንዲደርስ ማድረግ እንዳልተቻለ የተለያዩ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ይህ ለምን ተብሎ ሲጠየቅ ደግሞ፤ ድጋፉን ወደ ሕዝቡ ለማድረስ የሚያስችል ነዳጅ የለም የሚል ምክንያት ይቀርብ ነበር፡፡ ይሄንንም አለም ቀፍ ድርጅቶች ጭምር ሲያስተጋቡት ተስተውሏል፡፡ የሚባለው ነዳጅ ከገባ ቦኋላ ግን ቀጣይ የነበረው ዜና “አሸባሪው ሕወሓት ከዓለም ምግብ ፕሮግራም መጋዘን ነዳጅ ዘረፈ” የሚለው ነው፡፡
ይሄንንም በመንግስታቱ ድርጅት ዋና ጸሐፊ የአንቶኒዮ ጉተሬስ ቃል አቀባይ ስቴፋን ዱጃሪክ በኩል “ሕወሓት መቐለ ከሚገኘው ከዓለም ምግብ ፕሮግራም መጋዘን 12 ታንከር (570 ሺህ ሊትር) ነዳጅ ዘርፏል፤ በቦታው የነበሩ የመንግስታ ድርጅት እርዳታ ሰጪዎች ዝርፊያውን ማስቆም አልቻሉም፤ የነዳጅ ክምችቱም ምግብ፣ ማዳበሪያን እና አስፈላጊ የሰብአዊ እርዳታ ቁሳቁሶችን ለማጓጓዝ የሚውል የነበረ ሲሆን፤ የነዳጁ በሕወሓት ቡድን መዘረፍ ለአካባቢው ማህበረሰብ የሚሰጠውን ሰብአዊ ድጋፍ ይጎዳዋል፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም ለሰብዓዊ ስራ ሊውል የነበረው ነዳጅ ላይ የተፈፀመውን ዝርፊያ አጥብቆ ያወግዛል፤” ሲሉ ነበር በራሳቸው አንደበት ያስደመጡት፡፡
ምንም እንኳን በመግለጫው ይሄን ቢባልም፤ ይሄን መሰል ዘረፋና ቅጥፈት ለሽብር ቡድኑ አዲስ ያልሆነና በመንግስትነት ዘመኑ ጭምር ሲፈጽመው የኖረው ነው፡፡ ይሄኛው ድርጊቱ ግን ቡድኑ ምን ያህል በተጠናና በታቀደ መልኩ በውስጥም በውጭ ኃይሎችም እገዛ ለጦርነት ሲዘጋጅ እንደነበር ግልጽ ያደረገ ተግባር ነበር፡፡ ለምሳሌ፣ ይህ ቡድን የሰብዓዊ ድጋፍ ጭነው ወደክልሉ ከገቡ ተሽከርካሪዎች ውስጥ ከአንድ ሺህ በላዩን እዛው ሲያስቀር በፌዴራል መንግስት በኩል ለተነሳው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የደፈረ አልነበረም፡፡ ይልቁንም የደርሶ መልስ ነዳጅ ሞልተው የሄዱ ተሽከርካሪዎች “በነዳጅ እጥረት ምክንያት ነው ያልተመለሱት” የሚለውን የሽብር ቡድኑን ነጭ ቅጥፈት ለማስተጋባት ተሞክረዋል፡፡ በዚህም ሰብዓዊ ድጋፍ ጭነው ወደትግራይ ክልል የገቡ ተሽከርካሪዎች እዛው እንዲቀሩ ሆኗል፡፡ ይሄም ተሽከርካሪዎቹን ለጦርነቱ ማሳለጫ የማዋል የራሱ ምክንያትና ዓላማ ነበረው፡፡
ይህ ብቻም አይደለም፡፡ ሕወሓት በህዝቡ ስም ወደክልሉ የሚገቡ የሰብዓዊ ድጋፎች በቀጥታ ለሕዝቡ ከማድረስ ይልቅ ሰብዓዊ ድጋፍን የታጣቂ መመልመያ መንገድ አድርጎ የመጠቀሙን መረጃ ከፌዴራሉ መንግስት በቀር ሊናገረውም፣ ሊያወግዘውም የደፈረ አልነበረም፡፡ ይሄም የሽብር ቡድኑ ለጦርነት ለሚያደርገው ዝግጅት ሰዎች ወድደው ሳይሆን ተገድደው የቤተሰቦቻቸውን ሕይወት ለማትረፍ ሲሉ ወደ ቡድኑ ታጣቂዎች እንዲቀላቀሉ እና የሰው ኃይሉን እንዲያጠናክር እድል እንዲያገኝ ሆን ተብሎ የተሰራ ነበር፡፡
በዚህ መልኩ እህልን በሰው ለውጦ ሃይል በማሰባሰብ ስልታቸው የሚፈልጉትን ያህል የሰው ሃይል ያስገኘላቸው አልነበረም፡፡ እናም ልጅን በሰብዓዊ ድጋፍ እንዲለውጥ ከማስገደድ ባሻገር ሕዝቡን ወደማስፈራራት ገብተዋል፡፡ በዚህም ሕወሓት በሚያካሂደው አገር የማፍረስ ጦርነት የማይሳተፍ ሰው በትግራይ ውስጥ ቦታ የለውም ሲሉ የሽብር ቡድኑ መሪ ደብረጽዮን በአደባባይ ሲያስፈራሩና ሲፎክሩ ተደምጠዋል፡፡ ይሄም ሕዝቡ ተስፋ ቆርጦ አብሯቸው እንዲሆን እና በጦርነት ሂደት የሕዝብ ማዕበልን እንደ አንድ የጦር ስልት ለመጠቀም ያላቸውን እቅድ ለማሳካት የሚያስችል የሰው ሃይል ለማሰለፍ እንዲችሉ ሆን ተብሎ የተሰራ ነበር፡፡ አሁን ላይ ሕጻናትና አረጋውያን ሳይቀሩ በሕዝብ ማዕበል እየተገፉ የሚገቡበትን አካሄድ ለተመለከተም የዚሁ ሥራቸው ውጤት መሆኑን መረዳት አያዳግተውም፡፡
ይህ ሁሉ የሆነው ግን በእቅድና ለታለመ ጦርነት ለሚውል ዝግጅት በሚል መሆኑ ግልጽ የወጣው ሕወሓት ሦስተኛ ዙር ጦርነት መክፈቱን ተከትሎ ነው፡፡ ምክንያቱም አሸባሪው ሕወሓት ተደጋጋሚ የሰላም ጥሪዎችን ሲገፋ እና ምክንያት ሲደረድር የኖረው የተራዘመ ጦርነት ውስጥ የመግባት እና ሦስተኛውን ዙር ጦርነት የመቀስቀስ ድብቅ ምኞቱን ለማሳካት ጊዜ እንዲያገኝ በማሰብ ነበር፡፡
ከዚህ ጋር አያይዞ ቡድኑ ምን ይዞና ተማምኖ ይሄንን ጦርነት ጀመረ? የሚለውን ለመመልከት አራት ነገሮችን ማንሳቱ በቂ ነው፡፡ አንደኛ የሰው ሃይሉን አደራጅቷል፡፡ ለዚህ ደግሞ ቀድሞውንም የሱን እኩይ ዓላማ እንዲሸከሙ የተደረጉ ሃይሎች በወዶ ገብነት ተመልምለው በቂ ስልጠና ተሰጥቷቸው ተዘጋጅተዋል፤ በመቀጠልም ለቤተሰቦቻቸው ሕልውና ሲሉ በሰብዓዊ ርዳታ ምግብ ተለውጠው ለእኩይ ዓላማው የተመለመሉና የተዘጋጁ ኃይሎች አሉ፤ በሶስተኛ ደረጃ፣ በትግራይ ውስጥ ቦታ እንዲኖራቸው ሲሉ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ተገድደው በገፍ እንዲቀላቀሉ የታጩ ቡድኖች አሉ፡፡ የእነዚህ ድምር ውጤት ቡድኑ በሰው ሃይል ተደራጅቶ ጦርነት እንዲጀምር አድርገውታል፡፡
ሁለተኛው ዝግጅቱ ለታጣቂዎቹ የሚያውለው ምግብ ነው፡፡ ይሄም በሰብዓዊ ድጋፍ ስም ወደክልሉ የገባው ምግብና መድሃኒት ለህዝቡ ሳይደርስ በመጋዘን እንዲቆይ በመደረጉ በቀጥታ ለታጣቂው ሬሽን አውሎታል፡፡ ሌላው የተማመነበት አቅም ሎጀስቲክስ ነው፡፡ ይህ ትጥቅና መጓጓዣን ይመለከታል፡፡ በዚህ ረገድ ከአንድ ሺህ በላይ ርዳታ ጭነው የገቡ ተሽከርካሪዎች እዛው እንዲቀሩ አድርጓል፤ ለእነዚህ ማንቀሳቀሻ የሚውል ነዳጅም ደብቆም፣ ዘርፎም አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ በኩልም በቀላሉ ያሰባሰባቸውን ታጣቂዎች ለማንቀሳቀስ የሚያስችለውን በቂ ዝግጅት አድርጓል፡፡ በትጥቅ በኩል ደግሞ፣ አንድም በመንግስትነት ዘመኑ በየዋሻውና በመሬት ውስጥ የቀበራቸው፤ ሁለተኛም ከሰሜን እዝ ላይ የወሰዳቸውና በኋላም በወረራው ወቅት የሰበሰባቸው ከነፍስ ወከፍ እስከ ሜካናይዝድ ትጥቆች አሉት፡፡
ከዚህ ባለፈም በተለያየ ጊዜ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በመጋፋት ጭምር መሳሪያ ሊያቀብሉ የሞከሩ ታሪካዊ ጠላቶች አሉ፡፡ ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ በአየር ኃይል ተመትቶ የወደቀው ትጥቅ የጫነ አንቶኖቭ ነው፡፡ በዚህ መልኩ በትጥቅ በኩል አቅም ፈጥሯል፡፡ የመገናኛና ቴክኖሎጂ ውጤቶችንም በዚሁ አግባብ ተለግሷል፤ የፕሮፖጋንዳና የሚዲያ ጦሩንም በውጪም፣ በውስጥም አስቀድሞ አሰማርቷል፡፡ በመሆኑም ቡድኑ የሰላም ጥሪውን በምክንያት እየገፋና ጊዜ እየገዛ ከርሞ በዚህ መልኩ በሰው ሃይልም በሎጀስቲክስም ራሱን በማደራጀት ነው ሶስተኛውን ዙር ጦርነት የጀመረው፡፡
ለምን ዓላማ ጦርነቱን ጀመረ?
ይህ ጦርነት ለማንም የማይጠቅም ይልቁንም ለሀገርም ሆነ ለህዝብ ከፍ ያለ ኪሳራን የሚያስከትል መሆኑ ቢታወቅም፤ የሽብር ቡድኑ ግን ሕልውናዬ በጦርነት ውስጥ ይረጋገጣል ብሎ ስላመነ፤ እንዲሁም የጥፋት ተልዕኮውን ለመፈጸም ሲል ጀምሮታል፡፡ ምክንያቱም በአንድ በኩል በዘመናት ሂደት ውስጥ በወንጀልና ሌብነት፣ እንዲሁም የትግራይን ወጣት ላልተገባ እልቂት እየዳረገ የኖረ በመሆኑ ከትግራይ ሕዝብ የሚነሳበትን ጥያቄ የመመለስ አቅም የሌለው በመሆኑ፤ በሌላ በኩል ከተለያዩ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች የተሰጠውን ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን የመበታተን ተልዕኮ በወጉ ሰርቶ ባለማጠናቁ ይሄንኑ የማድረግ ግዴታ የገባ በመሆኑ ነው፡፡ ሃሳቡን ግልጽ ለማድረግ አንዱን ማሳያ ላንሳ፡፡
እንደሚታወቀው የትግራይ ሕዝብ ለሃምሳ ዓመታት የሚጠጋ ጊዜን በነጻነትና ልማት ስም በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ልጆቹን ገብሯል፤ ዛሬም በነጻነት ስም እየገበረ ይገኛል፡፡ ሆኖም በእነዚህ ዓመታት ልጆቹን ለሞት ከመዳረግ የዘለለ የሚጠበቀው ነጻነትም ሆነ ልማት እውን አልሆነለትም፡፡ ይባስ ብሎ እንደ መዥገር ተጣብቆ ደሙን እየመጠጠ የራሱን ህልውና የሚያዘልቅ ቡድን ሰላሙን፣ ነጻነቱን፣ በሕይወት የመኖር ሰብዓዊ መብቱንና በልቶ የማደር ሕልውናውን ነጥቆታል፡፡ እንደ አገር በተለይም በትግራይ ክልል ሰላም ከሰፈነ የትግራይ ሕዝብ ዛሬ ልጆቼ የት አሉ? ነጻነቴስ? በልቶ የማደር ዋስትናዬና በሕይወት የመኖር ሰብዓዊ መብቴ ወደየት ሄዱ? ብሎ መጠየቁ አይቀርም፡፡
ይሄ ከሆነ ደግሞ ሕወሓቶች ለሕዝቡ የሚሰጡት መልስ ስለሌላቸው ሕዝቡ ለተቃውሞ መነሳቱ፤ ቡድኑንም ተጠያቂ ማድረጉ አይቀርም፡፡ ስለዚህ ይህ ከመሆኑ በፊት ሕዝቡን አስጨንቆና በዙሪያው የጠላት ምስል ፈጥሮ በጦርነት ውስጥ እንዲኖር፤ በልቶ የማደር ሕልውናው በቡድኑ ላይ እንዲመሰረት፤ ለማያባራ ጦርነት ልጆቹን እየገበረ የሰቀቀንና ሃዘን ኑሮን እንዲገፋ ማድረግን መርጦለታል፡፡
ቡድኑ በአንድ በኩል ከትግራይ ሕዝብ ጥያቄ ለመዳን፤ በሌላ በኩል ከተልዕኮ አቀባዮቹ የላቀ ክብርና ሞገስን የሚያስገኝነትን ኢትዮጵያን የማፍረስ ሕልሙን ለማሳካት ሲል የትግራይን ታዳጊዎች በሕዝባዊ ማዕበል ለእሳት ለመማገድ ባልጠነከረ ክንዳቸው ብረት በማሸከም ከህዝቡ ላይ የዕለት ጉርሱን ነጥቆ ጦር ሰብቆ እሳት ለኮሷል ፡፡ ዳግም አገርን የማፍረስ፣ ወገንን የማጎሳቆል፣ ሃብት ንብረት የማውደምና የመዝረፍ፣ ሴቶችን በቡድን የመድፈር፣… የአውሬነት ፍላጎቱን ሁሉ ለመፈጸም ያስችለኛል ያለውን ጦርነት ጀምሯል፡፡
ለማስታወስ ያህል
ይህ ቡድን የትግራይ ወጣቶችን ጭዳ አድርጎ ከጫካ አራት ኪሎ ቤተመንግስት ሲገባም ሆነ በ27 ዓመታት የመንግስትነት ቆይታው ዓላማው ኢትዮጵያን ከፍ አድርጎ ማስተዳደር፤ ኢትዮጵያውያንን በአንድነት ሰንሰለት ማስተሳሰር አልነበረም፡፡ ይልቁንም የቡድን ፋላጎቱን አግዝፎ፣ የተልዕኮ አስፈጻሚነቱን አስቀድሞ በዘረፋ፣ በሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ በሴራና አፈና ተግባር ላይ ተጠምዶ የኖረ ነው፡፡
አፈናና ጭቆና የመረረው ሕዝብ ከስልጣን ካወረደው በኋላም፤ ቡድኑ እኔ ያልመራኋት አገር ልትኖር አይገባም በሚል ወደ ትግራይ ክልል ተመልሶ ለሌላ ጥፋት ራሱን ሲያደራጅ፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲኦልም ቢሆን እንወርዳለን ብሎ ይሄንኑ ብሂሉን እውን ለማድረግ በመከላከያ ሰራዊት የሰሜን እዝ ላይ በውድቅት ከጀርባው ጥቃት የፈጸመ የባንዳ ስብስብ መሆኑ በተግባር አረጋግጧል፡፡
ይህ የጥፋት ቡድን ሂሳብ አወራርዳለሁ፣ ኢትዮጵያንም አፈርሳለሁ ብሎ በአፋርና አማራ ክልሎች በኩል ወረራ ፈጽሞ እስከ ሰሜን ሸዋ ሲዘልቅ መልከ ብዙ ነበር፡፡ በአንድ በኩል በደረሰበት ሁሉ ሃብት ንብረት ሲያወድም፣ ሲዘርፍና ሲያቃጥል፤ ንጹሃንን በግፍ ሲገድል፣ በጅምላ (በማይካድራ፣ ንፋስ መውጫ፣ ጋሊኮማ፣…) በጅምላ ሲጨፈጭፍ፣ አካል ሲያጎድል፣ የስነልቡና ጥቃት ሲፈጽም፣ ሴቶችን (ከህጻን እስከ አዛውንትና መነኮሳትን ሳይቀር) በቡድን ሲደፍር፣ ቤተ እምነቶችን ሲያቃጥልና ሲያወድም፣ ትምህርት ቤቶችንና ጤና ተቋማትን ጨምሮ ሲያቀጥልና ሲያወድም፣ የዓለም የምግብ ፕሮግራም መጋዘኖችን ሲዘርፍ፣… ወረራው ዓላማ የለሽና የጥፋት መሆኑን በተግባር ገልጿል፡፡
በሌላ በኩል ድል የቀናው መስሏቸው የሚፈጽመው ግፍና ጥፋት እንኳን ሳይታያቸው፣ ይልቁንም ግፍና ጥፋቱን በሚሸፍንለት መልኩ በዲፕሎማሲውም፣ በሚዲያ ፕሮፖጋንዳውም፣ በፈጠራ ዜናውም፣… ሲደግፉት የነበሩ በርካታ የውስጥም የውጭም አገር ጠሎች፣ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ነበሩ፡፡
ይህ ህልማቸው ቅዠት ሆኖ ሲቀር እና ኢትዮጵያውያን በተባበረ ክንዳቸው ወረራውን ቀልብሰው ስለ ሰላም የማይደክም እጃቸውን ዳግም ዘርግተው የሰላም ውይይት እናድርግ ማለታቸው፤ ሕልምና ምኞቱ አገር ማፍረስ፣ በጦርነት ውስጥ ተደብቆ ከትግራይ ሕዝብ ተጠያቂነት ማምለጥ ለሆነው የሕወሓት ቡድን የሚመች አልሆነም፡፡እናም ዘርፎም አስፈራርቶም ለተልዕኮው የሚሰጠውን ምንዳ ቃርሞም ራሱን በሙላት አደራጅቶ የተዘረጋውን የሰላም እጅ ገፍቶ ሦስተኛውን ዙር ወረራና ጦርነት ጀምሯል። ይህ ሃቅ እንዳለ ቢሆንም ዛሬም አሸባሪው ሕወሓት ጦርነት ከፍቶ ተከፈተብኝ፣ ወርሮ ተወረርኩኝ፣ ዘርፎ ተዘረፍኩኝ፣… የኖረ የቅጥፈት ትርክቱን ማስተጋባቱን አላቆመም፡፡
እንደ መውጫ
የእብሪት መጨረሻው ውድቀትና ጥፋት ነው፡፡ የአሸባሪው ሕወሓት እውነትም ይሄው ነው፡፡ በእብሪት አገር ለማፍረስ ሲዖል እወርዳለሁ፣ በአማራ ላይ ሂሳብ አወራርዳለሁ፣… ብሎ ለወረራ ተሰማርቶ መጨረሻው ምን እንደሆነ ታይቷል፡፡ አሁንም በመሰል እብሪት ሌላ ጦርነት ከፍቷል፤ በዚህም መጠነ ሰፊ ጥቃትና ወረራ ለመፈጸም አቅዶ የተነሳ ቢሆንም የሚፈልገውን ማግኘት እንደማይችል ከወዲሁ የተገነዘበ ይመስላል፡፡ እናም በአንድ አፍ ሁለት ምላስ ሆኖ “ከአማራ የማወራርደው ሂሳብ አለ”፣ “ከአማራ ሕዝብ የሱዳን ሕዝብ ይሻለኛል”፣ ኢትዮጵያ ስትፈርስ ማየት ሕልማችን ነው”፣… ሲል የነበረ አንደበታቸው፤ ዛሬ ላይ የአማራ ወንድም ሕዝብ፣ የኢትዮጵያ ወገኖች፣… የሚል የቅጥፈት መደለያ ቃላትን ማዥጎድጎድ ይዘዋል፤ የገፉትን የሰላም መድረክ ዳግም ለማግኘት የፈለጉ በመምሰል ሌላ የማሰቢያና የዝግጅት ጊዜ ለማግኘት ለሰላም ዝግጁ ነን ትርክት ማሰማት ይዘዋል፡፡
ይሄን መሰል እርስ በእርሱ የተምታታ መግለጫና አቤቱታ የሽብር ቡድኑ የኖረበት ባህሪው ነው፡፡ ርግብ ለቅቆ መተኮስ፣ አቅፎ መውጋት፣ ስሞ መንከስ፣ የታመነ መስሎ መክዳት፣… የኖረበት ግብሩ ሆኖ በዘመናት ውስጥ ታይቷል፡፡ አሁንም ሦስተኛውን ዙር ጦርነት በአማራ እና አፋር ክልሎች በኩል ሲጀምር ይሄንኑ የጥፋት፣ የክፋትና የክህደት ጥሙን ለማርካት እንጂ ሌላ ምንም መልካም ነገር ኖሮት አይደለም፡፡
በመሆኑም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ይሄን ተገንዝቦ በየተሰማረበት መስክ ሁሉ ስለ ኢትዮጵያ ዘብ ሊቆም፤ ስለ ኢትዮጵያ ሊታገልና ኢትዮጵያ አሸናፊ ሆና እንድትወጣ የሚቻለውን ሁሉ ማበርከት ይኖርበታል፡፡ የትግራይ ሕዝብም ቢሆን በዚህ ቡድን ምክንያት ግማሽ ምዕተ ዓመት ልጆቹን ሲገብር፣ ሲራብና ሲጨቆን የኖረበት ጊዜ ይበቃዋልና ከዚህ በኋላ የሽብር ቡድኑን በቃህ ብሎ ከኢትዮጵያውያን እህት ወንድሞቹ ጎን በመሆን ልጆቹን ከጉያው ሳይነጥል የሚያሳድግበት፣ ነጻነቱን አግኝቶና ሰላሙን አረጋግጦ ልማቱን የሚያፋጥንበት ጊዜ እውን እንዲሆን የድርሻውን መወጣት ይኖርበታል፡፡
ማሙሻ ከአቡርሻ
አዲስ ዘመን ሰኞ ነሐሴ 30 ቀን 2014 ዓ.ም