ትውልድና እድገቱ አዲስ አበባ ነው። በሳንፎርድ እንግሊዝ ትምህርት ቤት ተምሯል። በእግር ኳስ ስፖርት መነሻው የቀድሞው ዝነኛ ክለብ አየር መንገድና ጥቁር አንበሳ ወጣት ቡድኖች ነበሩ:: ከነዚህ ክለቦች ጋርም ከልጅነቱ አንስቶ የጠበቀ ቁርኝት ኖሮት ነው ያደገው። የብሔራዊ ቡድን ተጫዋች በነበረው ዝነኛው ገረመው ዘርጋ ከልጅነቱ አንስቶ በሚገባ ተገርቶ አድጓል። ‹‹እግሮቹ ከመሮጥ የማይቦዝኑ ስኬታማና ሁለገቡ የስፖርት ሰው ነው›› ይሉታል እዮብ ተሰማን በቅርብ የሚያውቁት።
እዮብና ማራቶን
በትልቅ ደረጃ ለሚሮጡ እውቅ አትሌቶች የማራቶን ውድድርን ማሸነፍ መቻል ጀግንነት ነው። የማራቶን ሩጫን ተወዳድሮ አርባ ሁለት ኪሎ ሜትሮችን በብቃት ማጠናቀቅ መቻልም ለአንድ ተሳታፊ ትልቁ ስኬት ነው።በእርግጥ እንኳን ለአካል ብቃት፣ ለውጤት ለሚሮጡ አትሌቶችም ማራቶንን ማጠናቀቅ መቻል ቀላል ነገርአይደለም። ለዚህም ይመስላል የርቀቱ መክሊት ያላቸው ኢትዮጵያውያን ወይም ኬንያውያን አትሌቶች ከፊት በሚያጠናቅቁባቸው ውድድሮች የሌሎች በርካታ አገራት አትሌቶች መጨረሻ ሆነው ቢያጠናቅቁ እንኳን ውድድሩን በመጨረሳቸው ብቻ ደስታቸው ወደር ሲያጣ የምናስተውለው።
ታላላቅ አትሌቶች በጉብዝናቸው ወራት ማራቶንን በማሸነፍ አገራቸውን እንደሚያስጠሩት ሁሉ በርቀቱ በርካታ ጊዜ ሮጦ በማጠናቀቅም የአገርን ስም ከፍ ማድረግ ይቻላል። እንደ ኢትዮጵያ ላሉ በርካታ የዓለም ከዋክብት አትሌቶች ሁሌም የማይጠፋባቸው አገራት ይህን ቀለል አድርገው ይመለከቱት ይሆናል። ግን ቀላል አይደለም። ኢትዮጵያ በበርካታ ከዋክብት አትሌቶቿ በማራቶን ስኬታማ የመሆኗን ያህል በርካታ ጊዜ ተወዳድሮ በማጠናቀቅም የሚያስጠራት አላጣችም።
ባለፉት 40 ዓመታት ኑሮውን በአሜሪካን ሎስ አንጀለስ ካሊፎርኒያ ያደረገው ሁለገቡ የስፖርት ሰው እዮብ ተሰማ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ነው። ይህ ሰው ኑሮውን ባህር ማዶ ካደረገ በኋላ በዩኒቨርሲቲ ፣ በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያውያን ስፖርት ፌዴሬሽንና የብራዚል መለስተኛ ፕሮፌሽናል ቡድኖች ውስጥ በአጠቃላይ ለ19 ዓመታት እግር ኳስን አጠንክሮ ተጫውቷል። ሁለገብ የስፖርት ሰው ሲባልም በምክንያት እንደሆነ ከታሪኩ መረዳት ይቻላል። ይህን ስያሜ የሚያሰጠው በልጅነትና በወጣትነት ዘመኑ የነበረው የእግር ኳስ ሕይወት ብቻ አይደለም። ከእግር ኳስ ታሪኩ በኋላ ወደ አትሌቲክስ ስፖርት ጎራ ብሎ ባለፉት 28 ዓመታት የሰራቸውና እየሰራ ያለው ታሪክ አንድ የሚያስተምረን ነገር አለው። ታታሪነቱ፣ ከዓመት ዓመት አድካሚውን የማራቶን ሩጫ ለመወዳደር እድሜው ገፍቶ እንኳን ደከመኝ ሰለቸኝ ብለው የማይዝሉት እግሮቹ እንዲሁም ስኬቱ ለብዙዎች ተነሳሽነትን የሚፈጥር፣ትምህርትም የሚሆን ነው።
ከሃያ ስምንት ዓመታት በፊት ስኬታማ ወደሆነበት ‹‹የማራቶን ሩጫ ቤተሰብ›› ጎራ ያለው እዮብ በስፖርቱ ከምንም ተነስቶ የጀገነበትን ብዙ ታሪክ ጽፏል። ከዜሮ ጀምሮ ዛሬ የስኬት ማማ ላይ ያስቀመጠው የታላቅ ሙያ ባለቤትም ሆኗል። በ1995 የመጀመሪያውን ማራቶን ውድድሩን በሎስ አንጅለስ ማራቶን በመሮጥ የሚወደውን የአርባ ሁለት ኪሎ ሜትር የሩጫ ታሪኩን አንድ ብሎ የጀመረው ብርቱው ሰው በየዓመቱ በዚህ ውድድር ከሦስት አስርት ዓመታት ላላነሰ ጊዜ ወጥ በሆነ አቋም እየተሳተፈ በስኬት ማጠናቀቅ ችሏል። ይህን ታሪክ በመስራትም የሚስተካከለውን ማግኘት አዳጋች ነው።
ከሚኖርባት ከተማ ሎስ አንጀለስ ማራቶን ባሻገር፣ እንደ ዝነኞቹ የቦስተን፣ ኒው ዮርክ፣ ሺካጎ፣ በርሊንና የጃፓን ማራቶን ውድድሮች በመሳተፍም በርቀቱ በርካታ ጊዜ ሮጦ ማጠናቀቅ ችሏል። በሃምሳ ዓመት እድሜው ሃምሳ የማራቶን ውድድሮችን ሮጦ ማጠናቀቅ የቻለው ጠንካራው የስፖርት ሰው በአጠቃላይ ሰባ አራተኛ የማራቶን ውድድሩን ባሳለፍነው ሐምሌ ወር ሎስ አንጀለስ ዙሪያ በሚገኝ ማራቶን ውድድር አድርጎ ለሚቀጥለው ዓመት ቦስተን ውድድር ላይ እንዲወዳደር የሚያስችለውን መስፈርት አሟልቶ፣ በብቃትና በጥሩ ውጤት ፈጽሟል ቢባል የተጋነነ ሊመስል ይችላል። ግን እሱ አድርጎታል። ይህ ሰው በማራቶን ብቻ የሮጠውን ርቀት ብንደምረው 3108 ኪሎ ሜትር ሮጧል ማለት ነው።
‹‹የስፖርት ፍቅሬን፣ ስሜቴን፣ ጤንነቴንና የመንፈስ ጽናቴን ጠብቄ፣ አልበቃ ብሎኝ ነው እኩል ወደምወደውና እነሆ 28ኛ ዓመት ወዳስቆጠርኩበት የማራቶን ሩጫ ቤተሰብ ተሸጋግሬ እስከዛሬ ድረስ የቀጠልኩበት›› ይላል እዮብ በባህርማዶ ትልቅ ዝና ወዳተረፈበት የማራቶን ቤተሰብ ውድድር እንዴት እንደገባ ሲያስታውስ።
የማራቶን ውድድር እጅግ አድካሚና ትልቅ ጽናትን የሚሻ እንደመሆኑ የዓለማችን ታላላቅ አትሌቶች እንኳን በስፖርቱ በሚቆዩባቸው ዘመናት ሊሮጡ የሚችሉት ውድድር ብዛት የተወሰነ ነው። እዮብ ምናልባትም በዓለም በርቀቱ በርካታ ውድድሮችን በማድረግ ማጠናቀቅ የቻለ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ሰው ሊሆን ይችላል። ወደ ፊትም ተጨማሪ ውድድሮችን የማድረግ አቅምና ተነሳሽነቱ አሁንም ድረስ አብሮት እንዳለ ሲታሰብ ደግሞ ይህን ሰው የተለየ ያደርገዋል። ይህም በርካቶች እሱን እየተመለከቱ የአካል ብቃት እንቅስቃሴን እንዲያዘወትሩ ብርታትና ተነሳሽነት ሆኗቸዋል። የእዮብ ስኬትና ታሪክ ግን በማራቶን ብቻ የተወሰነ አይደለም። ሰማንያ ዘጠኝ የግማሽ ማራቶን ውድድሮችን ጨምሮ በበርካታ የአስርና አምስት ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ውድድሮችን አድርጎ ማጠናቀቅ ችሏል። በነዚህ ሁሉ ውድድሮችም የኢትዮጵያ ስም ከፍ ብሎ እንዲጠራ ሲያደርግ ኖሯል፣ አሁንም እያደረገነው።
እዮብ ከታላቁ ድል ጀርባ
እዮብ በቅርቡ በዩጂን፣ ኦሬገን ለ18ኛ ጊዜ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ ቻምፒዮና ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከምንጊዜውም የላቀ ውጤት ሲያስመዘግቡ ከልኡካን ቡድኑ ጎን ቆሞ የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት የቀደመው የለም። ውድድሩ ዩጂን ከተማ ይካሄዳል ሲባል የዘወትር የኢትዮጵያ ኩራት የሆኑትን ብርቅዬ አትሌቶች ቤቱ ቁጭ ብሎ በቴሌቪዥን መስኮት ብቻ ለመከታተል ልቦናው አልፈቀደም። 74ኛ ማራቶን ውድድሩን በጥሩ ውጤት ባጠናቀቀ ማግስት ውስጡ ያለው ከፍተኛ ስፖርታዊ ስሜት ገንፍሎ ወጣ። የአገርና የወገን ፍቅር ስሜቱ አላስችል ቢለው አረንጓዴ፣ቢጫና ቀይ ሰንደቅዓላማውን ታጥቆ፣ ቤተሰቡንና ሥራውን ትቶ፣ ለአንድ ሳምንት ያህል በከፍተኛ ወጪ በእንቁዎቹ አትሌቶች መንደር ኦሪገን ከትሟል። የኢትዮጵያ ኩራት የሆኑትን ከዋክብት አትሌቶችን ሩቅ መንገድ ተጉዞ በባዶ እጁ ለመቀበልም አልፈለገም ነበር:: የሎስ አንጅለስ ማራቶን ውድድርን ለ27 ተከታታይ ዓመታት በጤና፣ በትጋትና ለተለያዩ የኢትዮጵያ ማህበራዊና ሌሎች በጎ አድራጎት ድርጅቶች “ተወካይ አምባሳደር ሯጭ” በመሆን ያፈራውን እውቅና በመጠቀም አንድ ነገር ለማድረግ ወሰነ። “ለምወዳቸው፣ለማደንቃቸውና ለማከብራቸው ወንድሞቼና እህቶቼ ለሆኑት የኢትዮጵያ ስፖርት ልኡካን(ስፖርተኞች፣ አሰልጣኞች፣ ባለሙያዎችና አመራሮች በጠቅላላ) መተዋወቂያ ናሙና የሚሆን 60 በልዩ መልክ የተዘጋጁ መታሰቢያ ካናቴራዎች (ቲ-ሸርቶች) በሻንጣዬ ሰንቄ፣ በእህቴ ኮማንደር ደራርቱ ቱሉ በተመቻቸልኝ መድረክ ላይ ለማበርከት በቅቻለሁ” ሲል እዮብ ቡድኑን እንዴት እንደተቀበለ ይናገራል።
ውድድሩ ለአንድ ሳምንት በቆየባቸው ቀናት በየእለቱ የኢትዮጵያን ልኡካን ቡድን በማግኘት፣ በግል ጀግኖቻችንን በመተዋወቅና ሙያዊ ምክር በመለገስ ያላሰለሰ ድጋፍና ፍቅሩን ሲገልጽ ሰንብቷል። ባካባቢው ከነበረው የኢትዮጵያ የዳያስፖራው ማህበረሰብና ደጋፊዎች ጋር በመሆንም ትልቅ የሞራል ድጋፍ አድርጓል። ‹‹ድምጹ እስከሚዘጋ ድረስ በከፍተኛ ፍላጎት ሲጨፍርና ሲጮህ ነበር›› ይላሉ ውድድሩን በአካል ተገኝተው በመመልከት ወደ አገር ቤት የተመለሱ የስፖርት ቤተሰቦች እዮብ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በኦሪገን ተአምር ሲሰሩ የነበረውን ድባብ ሲያስታውሱ። ከድጋፉ ጎን ለጎን አልፎ አልፎ በአሜሪካውያን ተመልካቾችንና ታዛቢዎች ኢትዮጵያንና አትሌቶቹን በተመለከተ ይቀርቡ ለነበሩ ጥያቄዎች የተለያዩ ምላሾችና ማብራሪያዎችን በመስጠት በገጽታግንባታ ረገድ ሲያበረክት የነበረው አስተዋጽኦም ቀላል አልነበረም። ከሶስት አስርት ዓመታት በኋላ በአካል ያገኛትና “እህቴ” የሚላት እንቁዋ አትሌትና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት ኮማንደር ደራርቱ ቱሉ እንዲሁም በልኡካን ቡድኑ መሪ አቶ ተፈራ ሞላ አማካኝነትም እዮብ ጠርቀም ያለውንና አጠቃላይ ይዘት ያለውን የረጅም ጊዜ ሙያዊ ችሎታውንና ልምዱን ለቡድኑ ማካፈል ችሏል። ይህንን ሙያዊ ድጋፉን ወደ ፊትም በነጻ ለማበርከት ዝግጁ መሆኑን በመግለፅ፣ ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጋር በቅርቡ የሥራግንኙነት ለመፍጠር ፍላጎቱን እንደገለጸላቸው ይናገራል። የልኡካን ቡድኑ በዩጂን በነበረው ቆይታ ባደረገው አስተዋጽኦ ግን የረካ አይመስልም። ‹‹በውድድሩ ወቅት ለኢትዮጵያ ልኡካን ቡድን ያደረኩት አስተዋጽኦና ድጋፍ እጅግ በጎላ መንገድነው ብዬ ባላምንም፤ እንደ መነሻና መተዋወቂያ ይሆናል ብዬ በማሰብ የበኩሌን ለማድረግ ሞክሬያለሁ፣በዚህምተደስቻለሁ›› ይላል።
እዮብ በስኬት ጎዳና
እኤአ በ2004 “በካሊፎርኒያ ግዛት እጅግ አነቃቂው ሯጭ” የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል። ይህም ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ እንደ ሶኮኒ፣ ናይኪ፣ ኤሲክስ፣ ኬ ስዊስ፣ ስኬቸርስ፣ ሆካና ከሌሎችም ዓለም አቀፍ እውቅና ካላቸው ታላላቅ ኩባንያዎች እውቅና አግኝቶና ድጋፍ ተደርጎለት በጋራ ለመስራት አስችሎታል። በደቡብ ካሊፎርኒያ ግዛት በሚካሄዱ በርካታ የጎዳና ላይ ውድድሮች ብዙዎች ተሳታፊ እንዲሆኑ የ”ሌጋሲ ራነርስ” መስራች የሆነው እዮብ በትልልቅ መገናኛ ብዙሃን ትኩረት የሚሰጠው ሰው ነው። የሎስ አንጀለስ የስፖርትና አካል ብቃት መጽሄት ሰፊ ሽፋን የሰጠው ሲሆን፣ ኬኤንቢሲ ቻናል 4 ስፖርትስ፣ኬቲኤልኤፍ ቻናል 5 ቴሌቪዥን በእንግድነት ካቀረቡት መካከል ተጠቃሽ ናቸው። ከነዚህ በተጨማሪም ማህበረሰብ አቀፍ በሆኑ በሌሎች በርካታ የመገናኛ ብዙሃን ፕሮግራሞች ላይም በተደጋጋሚ በክብር እንግድነት መቅረብ ችሏል። እኤአ በ2014 የካሊፎርኒያ ግዛት ምክር ቤት እውቅና የተቸረው ሲሆን፣ የሎስ አንጀለስ ከተማ ምክር ቤት እንዲሁም ከንቲባው ኤሪክ ጋርሴቲ እዮብ ለሃያ ዓመታት በማህበረሰብ ስፖርት እንቅስቃሴ ውስጥ ላበረከተው አስተዋጽኦ እንዲሁም በነዚህ ዓመታት በሃምሳ ዓመት እድሜው ሃምሳ የማራቶን ውድድሮችን ማሳካት በመቻሉ እውቅና ሰጥተውታል።
እዮብና በጎ አድራጎት
እዮብ በማህበረሰብ ስፖርት ውስጥ ከሚያደርገው ሰፊ እንቅስቃሴ ጎን ለጎን ከበርካታ በጎ አድራጎት ድርጅቶች ጋር የሩጫ አምባሳደር ሆኖ በመስራት የተለያዩ ድጋፎችን በማሰባሰብ አንቱታን አትርፏል። ከነዚህም መካከልኸርሽበርግ ፓንክሬቲክ ካንሰር ሶሳይቲ፣ ወርልድ ቪዥን፣ የልብ ህሙማን ማህበር፣ ፍሬገነት የህጻናት ትምህርት ፋውንዴሽን እና በሎስ አንጅለስ የኢትዮጵያውያን ማህበረሰብ ድርጅት (ኢሲኤልኤ) ጋር በተያያዘ ከተለያዩ በጎአድራጎት ድርጅቶች ጋር ገቢ በማሰባሰብ ይሰራል።
እዮብ በሌላኛው የሙያ ገጽ
እዮብ የሎስ አንጀለስ የአካል ብቃት አማካሪ ቡድን (LA ENDURANCE SPORTS CONSULTING GROUP) መስራችም ነው። በዚህ ተቋምም ስር ከአካል ብቃትና ከስፖርት ጋር በተያያዘ ለማህበረሰብ ጠቃሚ የሆኑ በርካታ አገልግሎቶችን ይሰጣል። የአትሌቲክስ አሰልጣኝና አማካሪ ሆኖም ይሰራል። በአካል ብቃትና በስፖርቱ ዓለም በየጊዜው እየተጋበዘ አነቃቂ ንግግሮችን ለአማርኛም ሆነ ለእንግሊዝኛ አድማጮች በማድረግ ይታወቃል።
ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት የሆነው እዮብ፣ የተለያዩ አትሌቶች ማኔጀርና ተወካይ በመሆንም ይሰራል።በዚህም የተለያዩ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለይም በሎስ አንጀለስ ማራቶን እንዲወዳደሩ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ይታወቃል። ከነዚህም መካከል ባለፈው መጋቢት በተካሄደው 37ኛው የሎስ አንጀለስ ዓመታዊ የማራቶን ውድድር ላይ እንዲሳተፉ መንገዱን የጠረገላቸው ሶስት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ብርሃኑ በቀለ በርጋ፣ግዛቸው ሃይሉ ነጋሽና በላይነሽ ሽፈራ ይገዙ ተጠቃሽ ናቸው።
ቦጋለ አበበ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 15 /2014