የኩፍኝ በሽታ ለሕፃናት ህመም፣ የአካል ጉዳትና ሞት ምክንያት ከሆኑት በሽታዎች አንዱ ነው። መነሻው የኩፍኝ ቫይረስ የሚባል ረቂቅ ተህዋስያን ሲሆን፤ በቀላሉ ከሰው ወደ ሰው የሚዛመት የበሽታ ዓይነት ነው። በሽታው ከሰው ወደ ሰው የሚተላለፈው የኩፍኝ በሽታ ከያዘው ሰው አፍንጫና ጉሮሮ በሚወጡ ፈሳሾች ንክክኪና በትንፋሽ አማካኝነት ነው።
በኩፍኝ በሽታ የተያዙ ሰዎች የበሽታው ምልክቶች መታየት ከጀመሩ በኋላ ባሉት ቀናትና ምልክቶቹ ከመታየታቸው ከበርካታ ቀናት በፊት ጭምር በሽታውን ወደ ሌሎች ሰዎች ሊያስተላልፉ ይችላሉ። ሆኖም የበሽታው አምጪ ተህዋስ ወይም ቫይረስ በከፍተኛ ሁኔታ የመሰራጨት አቅም የሚኖረው የበሽታው ምልክቶች መታየት በሚጀምርበት ወቅት እንደሆነ የዘርፉ ምሁራን ያስረዳሉ።
ሕፃናት በሚሰባሰቡበት ቦታ ማለትም በትምህርት ቤቶች፣ በጤና ተቋማት እና በሌሎች ቦታዎች በተለይም በሽታው በቀላሉ ሊዛመት ይችላል። በኩፍኝ በሽታ የተያዘ ሰው (ሕፃን) የሚያሣያቸው ዋና ዋና ምልክቶች ከፍተኛ ትኩሳት፤ ከራስ ፀጉር ጀምሮ ወደ ሌሎች የሰውነት ክፍሎች የሚዛመት ሽፍታ፣ የዓይን መደፍረስ ወይም መቅላት፣ ከአፍንጫ የሚወጣ ፈሳሽ መብዛት፣ የዓይን እንባ ማዘልና ሣል ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑ በዘርፉ ጥናት ያደረጉ ምሁራን ይናገራሉ።
ምልክቶች በማንኛውም ሕፃን ላይ ከታዩ ሕፃኑን በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋማት መውሰድ እንደሚያስፈልግ የሚጠቁሙት የዘርፉ ምሁራን፤ የኩፍኝ በሽታ መከላከል የሚቻለው ሕፃናትን በመደበኛ ክትባት መርሐ ግብር እና በዘመቻ መልክ የሚሰጠውን የክትባት አገልግሎት መጠቀም ሲቻል ነው። በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት ሕፃናት ከዘጠኝ ወር ጅምሮ በክትባቱ መሳተፍ አለባቸው። መደበኛ የክትባት መርሐ ግብሩንም ያለማቋረጥ መውሰድ ይገባቸዋል ሲሉ ይመክራሉ።
በኢትዮጵያ በተለያዩ ወቅቶች የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ ይከሰታል። በመሆኑም የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት በዘመቻ መልክ መስጠት አስፈላጊ ነው። እንደአገርም ተግባሩ በጊዜውና በወቅቱ እንደሚከወን በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሚወጡ መረጃዎች ያሳያሉ። ይህንን የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ ችግር በከፍተኛ ደረጃ ለመቀነስ ብሎም በዘላቂነት ለመፍታት በየዓመቱ በአገር አቀፍ ደረጃ እድሜያቸው ከዘጠኝ ወር በላይና ከአምስት ዓመት በታች ለሆኑ ሕፃናት እንዲሁም በተመረጡ አካባቢዎች ደግሞ ከዘጠኝ ወር በላይና ከ 15 ዓመት በታች ለሆኑ ሕፃናት የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት በዘመቻ መልክ ይሰጣልም።
የክትባት ዘመቻ የሚሰጠው በቋሚነት በተመረጡ ጤና ጣቢያዎች ፣ ጤና ኬላዎች ፣ ትምህርት ቤቶች እና በጊዜያዊ የክትባት መስጫ ጣቢያዎችም ነው። ምክንያቱም በዘመቻው ወቅት ማንኛውም ወላጅ ወይም አሳዳጊ በአካባቢው በሚገኝ የክትባት መስጫ ጣቢያ ሳይቸገር እንዲሄድና ሕፃናትን እንዲያስከትብ ያግዛልና ነው። በዚያ ላይ በአንድ ስፍራ ብዙ ሰው እንዳይሰበሰብና እንዳይጠጋጋ ስለሚያደርግ በሽታው ከአንዱ ወደ አንዱ እንዳይተላለፍ ለማድረግም ይረዳል።
የኩፍኝ በሽታው ሁኔታ ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ መምጣቱን ዓለምአቀፍ መረጃዎች ያመላክታሉ። ክትባቱ ቢኖርም መከሰቻ አጋጣሚው ብዙ በመሆኑ ሁኔታው አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱንም የዓለም ጤና ድርጅት ጭምር ይገልጻል። እንደውም የኮሮና ተሐዋሲ መላ ዓለምን ሲያምሳት በአፍሪካ እንደ ኮንጎ አይነት አገራት ትልቅ አደጋ ውስጥ እንደነበሩም ተጠቁሟል።
ኮንጎ በዓለም ላይ ከተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ሞት የበለጠ ዜጎቿን በአንድ ቀን ውስጥ በኩፍኝ ወረርሽኝ ገብራ እንደነበርም ተዘግቧል። አዘጋገቡም እንደ አፍሪካ የተዘነጉ የመሰሉ በሽታዎች የሰዎችን ሕይወት መቅጠፍ ጀምረዋል ተብሎ ነበር። ይሁን እንጂ ይህም ሆኖ ትኩረቱ አናሳ ነበር።
በአንድ ወቅት በዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪቃ የድንገተኛ መከላከል ክፍል ኃላፊው ሚኬል ያኦ ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት እንደገለጹት «በርካታ ሕጻናት ከተወለዱበት ጊዜ አንስቶ በሕይወታቸው ሙሉ አንዳችም ክትባት አላገኙም፤ ይሄም ነገሮችን እጅግ አስቸጋሪ ያደርጋል» ብለዋል። በእርግጥ በኩፍኝ ተሐዋሲ የሚያዙ ሕጻናት ቁጥር ከበፊቱ አንጻር መቀነስ ይታይበታል። ግን ክትባቱ የማይወሰድ ከሆነ አደጋው የከፋ እንደሚሆንም አንስተዋል።
እድሜያቸው ከአምስት ዓመት እስከ 16 ያሉትን ልጆች ለመከተብ የገንዘብ እና የክትባት እጥረት ከፍተኛው ተግዳሮት መሆኑን የጠቆሙት ሚኬል፤ ያልተከተቡ ልጆች ቁጥር መጨመር እና የክትባት እጥረት ምናልባትም ወረርሽኙ ይበልጥ እንዲስፋፋ ሊያደርግ ይችላል ሲሉም ስጋታቸውን ገልጸዋል።
የዓለምጤና ድርጅት እንዳስታወቀው፤ የኩፍኝ በሽታ በ79 በመቶ ጨምሯል። ሶማሊያ፣ የመን አፍጋኒስታንና ናይጀሪያም የችግሩ ሰለባ ናቸው።
በተያዘው ዓመት ማለትም 2022 ከጥር ወር ጀምሮ ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ ብቻ ከ19 ሺህ በላይ የኩፍኝ በሽታች ተከስቷል። በዚህም በዓለም አቀፍ ደረጃ በኩፍኝ በሽታ የተጠቁ ሰዎች ብዛት ከአምናው ተመሳሳይ ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ79 በመቶ እንዲጨምር አድርጎታል።
ድርጅቱ በድረገጹ እንዳብራራው፤ የኩፍኝ በሽታ እንደ አዲስ አገርሽቷል። ለዚህ ደግሞ መንስኤው የኮሮና ቫይረስ እና ግጭቶች እንዲሁም የሰዎች መፈናቀል እና የጤና መሰረተ ልማት በጦርነት መውደማቸው ነው። በኢትዮጵያ ባለፉት 12 ወራት ውስጥ 3 ሺህ 39 ሰዎች በኩፍኝ በሽታ የመጠቃታቸው ምስጢርም ይኸው ነው። 58 በመቶዎቹ ደግሞ የመጀመሪያ ዙር ክትባት ማግኘታቸው ተገልጿል።
በአብዛኛው ሕጻናትን የሚያጠቃው የኩፍኝ በሽታ ተላላፊ በሽታ ስለሆነ ተገቢው የሕክምና ክትትል ስላልተደረገለት ችግሩን በቀላሉ መግታት እንዳልተቻለም ተነስቷል። በበሽታው ላለመጠቃት አስቀድሞ ክትባት መውሰድም ይመከራል። ነገር ግን ተገቢውን የህክምና ክትትል ስላላገኘ የከፋ ጉዳት እስከማድረስ እየዘለቀ ነው። በሽታው በደንብ መታከም ካልቻለ ከመግደል ጀምሮ ዘላቂ ለሆነ የአዕምሮ ጉዳት፣ ለሳንባ ምች፣ ያለጊዜው ጽንስ መውለድ፣ ለመስማት ችግር እና ለሌሎች ጉዳቶች የሚያጋልጥ እንደሆነም መረጃው ያመላክታል። በፈረንጆቹ 2020፣ 20 ሚሊዮን ሕጻናት የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት መውሰድ እያለባቸው ያልወሰዱ በመሆናቸው አሁን ለተከሰተው የኩፍኝ በሽታ የራሱ አስተዋጽኦ ማድረጉንም ድርጅቱ በመግለጫዎቹ አስቀምጧል።
ክትባቱ ባለመሰጠቱ ምክንያት 73 ሚሊዮን የዓለማችን ሕጻናት የኩፍኝ ወረርሽኝ ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉ ያስጠነቀቀው የዓለም ጤና ድርጅት፤ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ የክትባት ኩባንያዎች ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጡም አሳስቧል።
የኩፍኝ በሽታ መከሰቻ አጋጣሚዎቹ ከላይ እንዳነሳነው በተለይ መፈናቀልና ግጭቶች ናቸው። ኢትዮጵያ ደግሞ አሁን ያለችበት ሁኔታ በብዙ መልኩ ይታወቃል። እናም ሰሞኑን የወጣው መረጃ ደግሞ ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው። የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ እንዳለው፤ በሽታው በስፋት እየተሰራጨ መጥቷል። በተለያዩ ክልሎችም ወረርሽኙ ተከስቷል።
የኩፍኝ ወረርሽኝ በተለያዩ ክልሎች መከሰቱን ያነሱት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ድጉማ ሲሆኑ፤ በ2014 ዓ.ም 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎች በወረረሽኙ ተይዘዋል ብለዋል። ወረርሽኙ ባለፉት ሁለት ወራት ውስጥ ብቻ 10 በመቶ እንደጨመረም ተናግረዋል። ወረርሽኙ በአምስት ክልሎች ማለትም በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ሕዝቦች፣ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች እንዲሁም በሶማሌ ክልል በ45 ወረዳዎች ላይ መከሰቱንም አስረድተዋል። ይሁን እንጂ በእነዚህ አካባቢዎች በተሰሩ ፈጣን ምላሽ ሥራዎች አብዛኞቹን መቆጣጠር መቻሉን ገልጸዋል።
በአሁኑ ጊዜ በ 11 ወረዳዎች ወረርሽኙ መስፋፋቱን ያነሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ በኢትዮጵያ በተከሰቱ የተለያዩ ምክንያቶች የኩፍኝ ክትባት ሽፋን ዝቅተኛ በሆነባቸው አካባቢዎች የተከሰተውን የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ የጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከክልል ጤና ቢሮዎች እና አጋር አካላት ጋር በመተባበር ፈጣን ምላሽ የመስጠት ስራዎች እየተሰሩ ናቸውም ብለዋል።
ኩፍኝና መሰል ተላላፊ በሽታዎች በአገር ደረጃ የሉም የሚያስብላቸውን ሁኔታ ይዘው እንደነበር የሚያነሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ጠንካራ ክትትልና ሥራም ስለነበረ ለረጅም ዓመታት በሽታው ችግር ሳይሆን ቆይቷል። አሁን ግን በተለይም መከሰቻ አጋጣሚው ሰፊ በመሆኑ የመጨመር አዝማሚያ አሳየ እንጂ ይህንን መመከት አይቻልም አልተባለም። እናም በተጠና መልኩ ጠንካራ ክትትልና ሥራ ተደርጎበት መፍትሄ እንዲያገኝ እንደሚደረግም አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ ውስጥ የተላላፊ በሽታዎች ህክምናን የሚፈታተኑ 10 ምልከታዎችን የሚዘረዝረውን ‹‹የጤና ወግ›› በሚል ርዕሰ ጉዳይ በዶክተር ትንሳኤ አለማየሁ የተጻፈውን አንድን ጽሁፍ እናስቃኛችሁና ጽሁፉን እንቋጭ። የመጀመሪያው ያለ ሀኪም ትእዛዝ መድሃኒት ገዝቶ መጠቀም ሲሆን፤ ብዙ ባለሙያዎች ባደረጉት ጥናት መሰረት ሕብረተሰባችን ያለ ሀኪም ትእዛዝ መድሃኒት የመጠቀም ልምዱ ከፍተኛ እንደሆነም ይናገራል።
ሌላው በባለሙያዎች መሀል ያለ የግንዛቤ እጥረት ሲሆን፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ 33 የህክምና ት/ቤቶች የተላላፊ በሽታዎች እና የፀረ ተህዋስያን መድሃኒቶች የድህረ-ምረቃ ሥልጠናን ለሀኪሞች የሚሰጠው የጥቁር አንበሳ የህክምና ት/ቤት ብቻ መሆኑንም ያስቀምጣል። እናም የሁለቱ አካላት ልዩነት ለጉዳት ሰለባ ከሚያደርጉ መካከል እንደሆነም መረጃው ያነሳል።
ሦስተኛው የመድሃኒት ዝውውር ቁጥጥር መላላት ሲሆን፤ የሀገራችን የመድሃኒት ዝውውር ቁጥጥር በቂ አይደለም። በሕገወጥ መንገድ የሚዘዋወሩ የፀረ ተህዋስያን መድሃኒቶች በአብዛኛው በሚመከረው መንገድ (ሙቀታቸው ተጠብቆ፣ የአገልግሎት ዘመናቸው ሳያልፍ ወ.ዘ.ተ.) ከአምራቹ ወደ ተጠቃሚው አይደርሱም። ስለዚህም ውጤታማ አይሆኑም።
አራተኛው የሚዲያው ለፀረ ተህዋስያን መድሃኒቶች መላመድ እና ውጤታማነት መቀነስ ትኩረት አለመስጠት ሲሆን፤ የፀረ ተህዋስያን መድሃኒቶች መላመድ በዓመት ውስጥ ከማንኛውም ህመም የበለጠ ታካሚዎች ይገድላሉ። ነገር ግን ሚድያዎች ይህንን ለማህበረሰቡ አያሳውቁም በሚባል ደረጃ ላይ ናቸው።
አምስተኛው ከፀረ ተህዋስያን ህክምና በፊት መሟላት ያለባቸው ምርመራዎች ትኩረት ሰጥቶ እንዲሟሉ አለማድረግ ሲሆን፤ እንደማንኛውም ህክምና የተላላፊ በሽታዎች ህክምና ከመሰጠቱ በፊት ለህሙማን ስላስከተለው ተህዋስ ተገቢው መረጃ በምርመራ መደረግ ይገባል። ነገር ግን በኢትዮጵያ ያሉ ሆስፒታሎች የፀረ ተህዋስያን መድሃኒቶች ግዢን እንጂ ምርመራ ላይ ትኩረት አያደርጉም። ይህ ደግሞ ለበሽታው ይበልጥ መስፋፋት መንስኤ ሆኗል።
መረጃው በስድስተኝነት የሚያነሳው የውሃ አቅርቦት አለመኖር ወይም መቆራረጥን ሲሆን፤ የተላላፊ በሽታዎች ህክምና እና መከላከልን በእጅጉ የሚፈትነው መሆኑን ይጠቁማል። “በሽታ ለመከላከል እጃችሁን በሳሙና እና በውሃ ታጠቡ” የዘወትር የህክምና ባለሙያዎች ምክር ቢሆንም ያን ለማሟላት በተለይ በህክምና መስጫ ተቋማት መቼም የማይቆራረጥ ውሃ መሟላት ግደታ ነው። ነገር ግን ብዙ ጊዜ የለምና ችግሩ ይሰፋል።
ሰባተኛው የጤና መድህን አገልግሎት አለመስፋፋት ነው። በዝቅተኛ ገቢ የሚተዳደረው ሕብረተሰብ በሚታመምበት ሰዓት ሁለት አማራጮችን ይጋፈጣል። የመጀመሪያው ሆስፒታል በመሄድ ምርመራ አድርጎ መድሃኒት ገዝቶ መታከም ሲሆን፤ ሁለተኛው ቀጥታ ፋርማሲዎችን በመጎብኘት ያለ ሀኪም ትዕዛዝ መድሃኒት ገዝቶ መጠቀም ነው (ቢያድንም ባያድንም)። እናም ከገቢ ውስንነት የተነሳ ተላላፊ በሽታን መከላከል የማይቻልበት ምክንያት ይህ እንደሆነም ይነሳል።
ስምንተኛው የህክምና ባለሙያዎች እና የሚድያ መራራቅ ሲሆን፤ በሙያው የተሰማሩ ሰዎች በተለያዩ የሚድያ መድረኮች እየቀረቡ (በራሳቸው ተነሳሽነት) ሕብረተሰቡን አያስተምሩም። የተላላፊ በሽታዎች ህክምና በሀሰተኛ መረጃዎች ስህተት ከሚፈጠሩ በሽታዎች አንዱ በመሆኑ ይህንን እንዳያክሙም ያደርጋቸዋል።
የህክምና መስጫ ተቋማት ቁጥራቸው በበዛ ታካሚዎች እና አስታማሚዎች መጣበብም ሌላውና በዘጠነኛነት የሚነሳው ጉዳይ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ የህክምና መስጫ ተቋማት ብዙ ታካሚዎች ያስተናግዳሉ። በተጨማሪም ቁጥራቸው በበዛ አስታማሚዎች ይጣበባሉ። ይህ ደግሞ ከታማሚው የተላላፊ በሽታዎች እና ተህዋስያን ወዳልታመሙ ሰዎች እንዲሄድ እና ታማሚውም ለሌሎች ህመሞች እንዲጋለጥ ያደርጋል።
የመጨረሻውና አስረኛው ከሀገሪቱ ነባራዊ የፀረ ተህዋስያን ህክምና ጋር ተዛማጅ የሆኑ ምርምሮች እጥረት ነው። ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጋር ተዛማጅ የሆኑ የፀረ ተህዋስያን ህክምና ምርምሮች እጥረት አለ። ያሉትም ጥቂት ተመራማሪዎች በቂ ድጋፍ እና ማበረታቻ ያንሳቸዋል። እናም የተላላፊ በሽታዎች ህክምና ፖሊሲን መሰረት አድርገው እንዲሰራባቸው አይሆኑም። ይህ ደግሞ የበሽታው ተስፋፊነት ላይ የጎላ ሚና እንዲኖረው ያደርጋል።
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ሐምሌ 23 ቀን 2014 ዓ.ም