ይህ የአንድ የፊልምና ድራማ ደራሲ ገጠመኝ ነው። ጽሑፉ ‹‹ለክብርት ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ›› በሚል በማህበራዊ ገጾች ሲዘዋወር አይቼ፣ ጽሑፉን ያነበብኩት ዕለት እኔም ተመሳሳይ ገጠመኝ ማስተዋሌ ነው ትኩረት እንድሰጠው ያደረገኝ ። የታዘቢውን ገጠመኝ ላስቀድም።
‹‹…. ዛሬ ከባድ ዝናብ እየዘነበ ዝናቡን ሽሽት አንድ መንደር ውስጥ ያለ ስጋ ቤት ተጠልዬ ነበረ። የስጋ ቤቱ አስተናጋጆች በመላው አዲስ አበባ እየተለመደ የመጣውን ‹‹ከፓንት ትንሽ የረዘመ›› ቀሚስ ለብሰዋል። ብርዱ እንኳን በዚህ አለባበስ ይቅርና ጋቢ ለለበሰም ይከብዳል።
በዚህ መሀል አንዷ አስተናጋጅ ከስር ታይት አድርጋ ስትመጣ ከባለቤቱ ጋር ተጣሉ። ባለቤቱ ታይቷን እንድታወልቅ ሲያዛት እሷም ማህፀኗን እንደሚያማትና ዝናቡ እስኪያልፍ ድረስ ታይቱን እንድትለብስ እያለቀሰች ብትለምነውም በጄ ሊላት አልፈቀደም። ታይቱን እንድታወልቅ ካልሆነ ስራውን እንድትለቅ ነገራት።
ሰውየውን በሰዓቱ አነጋግሬ ከነታይቷ እንድትሰራ ካልሆነ እንደምከሰው ነግሬው ባስቆመውም ይህ ግን በአሁኑ ሰዓት የመላ ከተማው ገፅታ እየሆነ በመምጣቱ በኔ ብቻ ሊፈታ የሚችል ጉዳይ ስላልሆነ በቀጥታ ለእርስዎ ደብዳቤዬን ፃፍኩ…›› በማለት ጉዳዩን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትኩረት እንዲሰጠው ተማጽኗል።
በተመሳሳይ የዚያኑ ዕለት ማታ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ጉርድ ሾላ አካባቢ ከሚገኝ አንድ አነስተኛ ሆቴል ገባን፤ ሥጋ ቤትም ያለው ነው ። በዕለቱ ዝናብ ሙሉ ቀን ሲዘንብ ውሎ በዚያን ሰዓትም እየዘነበ ነበር:: እንደተለመደው የሥጋ ቤቱ አስተናጋጆች ከጭናቸው ሥር የተጣበቀች አጫጭር ቀሚስ ለብሰዋል ።
የተቀመጥነው ወደ በሩ በኩል ጠጋ ብሎ ነበር። ከጣሪያ ላይ የሚወርደው ፍሳሽ በበሩ በኩል ወደ ውስጥ እየገባ ነው ። ያቺኑ ጭኗ ሥር የተጣበቀች ቀሚስ የለበሰች አንደኛዋ አስተናጋጅ ወደ ውስጥ እየገባ ያለውን ውሃ በመጥረጊያ ወደ ውጭ ትረጫለች ። ከላይ ያለው ዝናብ እንዳለ ሆኖ ከሥር ወደ ውጭ የምትረጨው ውሃ ነጠብጣቦች በቀጥታ ሰውነቷ ላይ ነው የሚያርፉት ።
ምግብ ቤት ውስጥ እንደዚያ አይነት አጭር ቀሚስ የሚለብሱ አስተናጋጆች ትኩረት ሰጥቼ ያየሁት ያቺን ልጅ ብቻ ነው ። የሆቴሉ ተስተናጋጆችም ሆኑ አላፊ አግዳሚው ሁሉ ከእግር ጥፍራቸው እስከ ራስ ፀጉራቸው ድረስ ተከናንበዋል ። እንደዚያም ሆኖ ያልተቻለውን ብርድ ግን እነዚህ ልጆች ሙሉ ራቁት ሊሆን ምንም ባልቀረው አለባበስ የዝናብና ብርድ ማረፊያ ሆነዋል ።
ሥጋ ቤቶች የራሳቸው የአለባበስ ሕግና ደንብ እንደሚኖራቸው ግልጽ ነው ። ብዙ የሥራ ቦታዎች የራሳቸው የአለባበስ ሕግ አላቸው ። ምክንያቱ ለምን እንደሆነ ባይገባኝም የሥጋ ቤቶች ደንብ ደግሞ የሴት ልጅን ገላ የሚያራቁት ሆነ ።
ወደውና ፈቅደው የሚያደርጉት ብዙ ናቸው፤ ያ ግን በፍላጎት ነው ። የሚደረገውም በእንዲህ አይነት ብርድ ሳይሆን ለዝግጅት ነው ። በአዘቦት የሚያደርጉትም የራሳቸው መኪና ያላቸው ናቸው፤ የተሻለ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ናቸው ። ብርድ ላይ ቆመው የሚውሉ አይደሉም ። እንግዲህ የሥጋ ቤቶችም ሆነ ሌሎች ሆቴሎች የአለባበስ ሕግ ነውና ለምን እንዲህ አደረጉ ማለት አንችል ይሆናል ። ምክንያቱም ‹‹ሕጋችን ነው›› ነው የሚሉት ።
ዳሩ ግን አንዳንዴ ሕሊና ከሕግ በታች ይሆናል ። ወደሰውየው ገጠመኝ እንመለስና፤ ለምሳሌ ልጅቷ የማህፀን ህመም አለባት ። በዚያ ብርድ ላይ ህመም ሲጨመርበት ልጅቷ ለዘላቂ በሽታ ተዳረገች ማለት ነው ። ጤናዬ ይበልጥብኛል ብላ ትታው እንዳትሄድ የዕለት እንጀራዋ ነው ። ሥራ ቶሎ አታገኝም፤ ሥራ አላገኘችም ማለት ደግሞ የዕለት ጉርሷን እና የቤት ኪራይ የምትከፍለው አታገኝም ማለት ነው ። እንዲህ ዙሪያው ገደል ሆኖባት ነው ያለቀሰችው ።
ባለገጠመኙ ባለቤቱን ባይቆጣውና ‹‹እከስሃለሁ›› ባይለው ኖሮ ልጅቷ ተባራ ነበር፤ ላለመባረር ብላ እያመማት ብትሰራ ኖሮ ደግሞ የማህፀኗ ህመም ተባብሶ የአልጋ ቁራኛ ትሆን ነበር ማለት ነው ። የእኔ ትዝብት፤ አንዳንድ ጊዜ ሕሊና ሕግን ቢገዛ ምን ችግር አለው? ያቺ ልጅ ዝናቡ እስከሚለቅ እንኳን ከሥር ‹‹ታይት›› የሚባለውን ብታደርግ ሆቴሉ ምን ኪሳራ ይደርስበታል? እሷ እንደዚያ በመልበሷ የሚመለስ ደንበኛ ይኖር ይሆን? የሆነውስ ሆነና ግን ‹‹የሴት መብት ተሟጋች ነን›› የሚሉ ሴቶችስ የእንዲህ አይነት ሴቶችን በደል ያስተውሉት ይሆን?
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቤተ መጻሕፍት ውስጥ አንዲት ሴት አጭር ቀሚስ ለብሰሽ አትገቢም ተብላ በሴት መብት ተሟጋቾች ዘንድ ተነስቶ የነበረውን ከፍተኛ ቅሬታ አስታውሳለሁ ። በቴሌቭዥን ሁሉ መወያያና መከራከሪያ ሆኖ ነበር ።
ታዲያ አጭር ቀሚስ መልበስ መብት እንደሆነው ሁሉ በብርድ ወቅት ብርድን ሊከላከል የሚችል ልብስ መልበስስ ምናለ መብት ቢሆን? ሥጋ ቤቶች ሙሉ ልብስ የሚከለክሉ ከሆነ ቤተ መጽሐፉ ደግሞ አጭር ቀሚስ ሊከለክል ይችላል ። ስለዚህ ለአጭር ቀሚስ ተከልካዮች የተደረገው የመብት መሟገት ልብስ መልበስ የሚከለከሉትም የመብት ተሟጋች ያስፈልጋቸዋል ። ለዚያውም ለሕመም እየተዳረጉ ።
ሥጋ ቤት ምግብ ቤት ነው ። ጭፈራ ቤት ወይም መዝናኛ አይደለም ። ምግብ ቤት ውስጥ የሚገባው ለመብላት እንጂ ለመዝናናት አይደለም ። ስለዚህ የምግብ ቤት እንደዚያ አይነት አለባበስ ለምን ግዴታ ሆነ? እዚያ የሚገባው ሰው የምግቡ ጥራት ነው መመዘኛው ወይስ የአስተናጋጆቹ ጭን መታየት?
ገጠመኞችን ያነሳናቸው እንደ ማሳያ ነው ። በትዝብት ደረጃ ሕጋቸውን ይቀይሩ አንልም ። ዳሩ ግን በየትኛውም ሥራ ቦታ ቢሆን የሰዎችን ችግር መረዳት ባለሀብትን አያከስርም፤ የህሊና እርካታ ነው የሚሰጥ ። የሰዎችን ችግር መረዳት ሰዋዊነት ነው ።
እንኳን እነዚህን ተራ እና ቀላል ነገሮች ሕሊና ካለ ሕግንም ይበልጣል ። ሕግ የሚያስፈልገው በሕሊና መተማመን አልኖር ሲል ነው ። ሰዎች ወደ ክስ እና የፍርድ ቤት ውጣ ውረድ የሚሄዱት አለመግባባትና አለመተማመን ሲፈጠር ነው ። ሕሊና ከቀደመ እና ለሕሊናችን ተገዢ ብንሆን መተማመን ይኖራል፣ መተሳሰብና መተዛዘን ይኖራል ። ስለዚህ ሰዎች ሕግ አያስፈልገንም ነበር ማለት ነው ።
ሕግ አያስፈልግም እያልኩ አይደለም፤ ወይም ሕግ መከበር የለበትም እያልኩ አይደለም ። እያልኩ ያለሁት ሕግ የሚያስፈልገን ከአግባብ ውጭ የሆነ ስናደርግ ነውና እዚያ ድረስ መሄድ የለብንም ነው ። መተሳሰብና መተማመን ካለ ነገርየው በባለጉዳዮች ብቻ ያልቃል። ለምሳሌ አሰሪና ሰራተኛ ከተማመኑና ከተሳሰቡ ክስ እና ክርክር አያስፈልግም ። ስለዚህ በፈቃዳችን ለሕሊና ተገዢ እንሁን፤ አለበለዚያ በግዴታ ለሕግ ተገዢ እንሆናለን!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 13/2014