በኮሪደሩ ላይ ወዲህ ወዲያ ትላለች እኔም ሁኔታዋ ቀልቤን ስለሳበው ጠጋ ብዬ ሰላምታ ከሰጠኋት በኋላ ምነው አሞሽ ነው? ስል ጠየኳት “አይ አይደለም ከአንድ ቀን በፊት በቀዶ ህክምና ወንድ ልጅ ተገላግዬ ነው አሁን የህክምና ባለሙያዎቹ እንቅስቃሴ ማድረግ አለብሽ ስላሉ ለእሱ ነው እየተንቀሳቀስኩ ያለሁት” አለችኝ። ወይዘሮ ማስተዋል የተባለች አንዲት ሴት።
ወይዘሮ ማስተዋል ኑሮዋ አባዶ አካባቢ ሲሆን ለወሊድ የመጣችው ደግሞ በደጓ እናት አበበች ጎበና ስም ወደተሰየመው የአበበች ጎበና የእናቶችና ህጻናት ህክምና ማዕከል ነው። የህክምና ተቋሙን ለመምረጧ ደግሞ የምታነሳቸው ብዙ ምክንያቶች አሏት። ከክትትል ጀምሮ ለእናትም ለጽንሱም የሚሰጠው ትኩረት ከምክንያቶቿ መካከል ተጠቃሹ ነው።
ሁለተኛ ልጇን የተገላገለችው ወይዘሮ ማስተዋል ከዚህ ቀደም የወለደችበት ሆስፒታል የዚህን ያህል ትኩ ረትና ክትትል አለማየቷን ትናገራለች። ይህ ሆስፒታል የመንግሥት ሆስፒታል መሆኑን ራሱ እስከምትጠራጠር ድረስ በጣም አስደሳችና እናትና ልጅን ጤነኛ የሚያደርግ ተግባር ማየቷንም ትመሰክራለች።
“እኔ በምጥ ያልወለድኩት ልጁ በትክክለኛ አመጣጥ ባለመምጣቱ ብቻ ነው። በቀዶ ህክምና ስገላገልም በጣም በቀላሉ ብሎም ለእኔም ለልጄም ጤና አስተማማኝ በሆነ መልኩ ነው። በዚህም በጣም ደስተኛ ነኝ። ሌሎች እናቶችም ይህ እድል እንዲገጥማቸው እመኛለሁ”። ትላለች።
በሆስፒታሉ መንታ ህጻናትን በሰላም የተገላገለችው ሌላዋ ወይዘሮ ዘሃራ ሱሌማን እንደምትለውም መንታ ህጻናት ልጆቿን ከወለደች አምስት ያህል ቀናት ሆኗታል። ልጆቹ ያለቀናቸው የተወለዱ በመሆኑ ተጨማሪ ህክምናን እንዲያገኙ በሆስፒታል አቆይተዋቸዋል።
እናት ዘሃራ እንደምትለው የእርግዝና ክትትሏ ሌላ ቦታ ነበር ሆኖም ለተጨማሪ ህክምና ወደ ሆስፒታሉ ተልካ ነው የመጣችው ነገር ግን መጥታ ያገኘችው የህክምና አገልግሎት ኋላም ልጆቿ እየተደረገላቸው ያለውን ክትትል እንዳስደሰታት ትናገራለች።
ከመውለዴ ከአንድ ሳምንት በፊት ነው ወደህክምና ተቋሙ ገብቼ አልጋ የተሰጠኝ የምትለው ወይዘሮ ዘሃራ እየተደረገላት የነበረው የህክምና ክትትል ጥሩ በመሆኑ ቀኗም ደርሶ ባይሆንም በሰላም በጤና ልጆቿን ለማግኘት መብቃቷን ትናገራለች።
ነገር ግን ወይዘሮ ዘሃራ ልጆቿ ወደ ማሞቂያ እሷም የህክምና ክትትል ወደሚደረግላት ክፍል እንድትገባ ተደረገ። በመካከል ግን የነበረው የክፍሎች ርቀት እንዳስቸገራትና አሁንም መመላለሱ ከቁስሏ ጋር ስላልተመቻት የእሷን ህክምና አቋርጣ ልጆቿ ጋር መቆየትን መምረጧን ትናገራለች። ይህ ባይሆንና እናትና ልጅ በአንድ ላይ የህክምና አገልግሎቱን የሚያገኙበት ሁኔታ ቢመቻች መልካም መሆኑንም ሃሳብ ታቀርባለች።
እናቶች እንደሚሉትም በአበበች ጎበና ስም በተሰየመውና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ በየካቲት 12 ሆስፒታል ስር የሚተዳደረው ሆስፒታል የሚሰጠውን አገልግሎት ሁሉም እናቶች ያግኙ የሚል ነው።
አዎ በአገራችን በወሊድ ወቅት የደም መፍሰስ አሁንም ለእናቶች ሞት ምክንያት ሆኖ መቀጠሉ ይነገራል። የጨቅላ ሕጻናት ሞትም እንዲሁ ልናልፈው ያልቻልነው ችግራችን ነው። አሁን ላይ በመላው አገሪቱ ሕፃናት ሆስፒታል ውስጥ እየተወለዱ ቢሆንም የመሞት መጠናቸው ግን ከፍ ያለ ስለመሆኑ መረጃዎች ያሳያሉ።
አንዳንድ ባለሙያዎች እንደሚሉት የችግሮች ሁሉ መነሻ ለአዋላጅነት ሙያ የተሰጠው ትኩረትና የግንዛቤ መጠን ሲሆን በሌላ ጎኑም በሙያው የሚሰማሩ ሰዎች በሥራው ላይ የመቆየት ፍላጎት ማጣት፣ የግብዓት እጥረት፣ ቸልተኝነትና ሌሎችም እንደ ምክንያት ይነሳሉ።
በአበበች ጎበና ስም የተሰየመው የእናቶችና የህጻናት ሆስፒታል ግን ይህንን ነገር ሁሉ ለመቅረፍ ብሎም በእናቶችና ህጻናት ጤና ላይ አዎንታዊ አሻራውን ለማሳረፍ ቆርጦ የተነሳ ይመስላል።
“እናት ደህና ልጅም ጤና “ የሚለውን ለማሳካትም እየሰራ ስለመሆኑ የግቢው እንቅስቃሴ ይመሰክራል። ሁሉም ነገር በስርዓት በአግባቡና በባለሙያ እንደሚሰራም የአይን እማኞች ነን።
ይህንን አገልግሎቱን ያስጎበኙን የሆስፒታሉ የኳሊቲ ኦፊሰር አቶ ሸጋዬ ዘሌ እንደገለጹልን ሆስፒታሉ ከድንገተኛ ክፍሉ ጀምሮ እናቶችን ተቀብሎ ተንከባክቦ ለማስተናገድ ዝግጁ ሆኖ ነው የሚጠብቀው። እኛም አንዳየነው ድንገተኛ ክፍሉ የራሱ የሆነ ላብራቶሪ እንዲሁም መድኃኒት ቤትና ማረፊያ ክፍልን ይዟል።
ቀጥሎ ባለው በሰፊው አዳራሹም ከሌላ ሆስፒታል ለተጨማሪ ህክምና የተላኩ እናቶች ክትትል የሚያደርጉበት እዛው ሆስፒታልም ወልደው ችግር ያጋጠማቸው ካሉ በዚህ አዳራሽ የተለያዩ ክትትሎችን ያገኛሉ። በዚህ ሆስፒታል ውስጥ ምንም ዓይነት የወረቀት ዝውውር የሌለ ሲሆን ሁሉም ነገር የሚካሄደው በቴክኖሎጂ በታገዘና ሲስተም ነው።
ማዋለጃ ክፍሉም በባለሙያዎች የታገዘ አገልግሎት ከመስጠቱም በላይ በርከት ያሉ የማዋለጃ አልጋዎችን እንዲሁም የቅድመና የድህረ ወሊድ ማረፊያ ክፍሎችን አካቶ የሚገኝ ነው። በሆስፒታሉ በጽኑ የታመሙ ምናልባትም የመተንፈሻ መሳሪያ የሚያስፈልጋቸው እናቶች ሲኖሩ በተመቻቸ ሁኔታ አገልግሎቱን ያገኙ ዘንድ በዘመናዊ መሳሪያ የታገዙ ክፍሎችም ተዘጋጅተዋል።
ያለቀናቸው የተወለዱ ብሎም ከተወለዱ በኋላ በሚፈጠሩ ኢንፌክሽኖች የተያዙ ህጻናት ክትትል የሚያደርጉበት የጨቅላ ህጻናት የህክምና ክፍሉም በበቂ ባለሙያዎችና የህክምና መሳሪያዎች የተደራጀ ሆኖ አይተነዋል። ልጆቻቸውን በክፍሉ ያስተኙ እናቶችም በየኮሪደሩ ላይ እንዳይንገላቱ የተመቻቸ የመቆያ ክፍል ተዘጋጅቶላቸዋል።
እናቶች በተለይም ከእርግዝና ጋር ተያይዞ የሚገጥ ማቸውን የደም ግፊትና የስኳር እንዲሁም የደም መፍሰስ ህመሞችን አስተኝቶ በማከም እናትም ጽንሱም ደህና እንዲሆኑ በማድረግ በኩልም ሆስፒታሉ ሰፋፊ ሥራዎችን እንደሚሰራ ተመልክተናል።
በሌላ በኩልም እናቶች ከወለዱ በኋላ በተለያዩ ምክንያቶች ቢታመሙና ወደ ጽኑ ህመም ቢደርሱ ወደ ሌላ ሆስፒታል ሳይሆን የሚላኩት እዛው በተዘጋጀው የጽኑ ህሙማን ክፍል ተኝተው እንዲታከሙ ይደረጋል። ከዚህም ባለፈ የመተንፈሻ መሳሪያና ሌሎች አጋዥ መሳሪያዎች ቢያስፈልጓቸውም ከጽኑ ህሙማን ከፍ ያለ በዘመናዊ የህክምና መሳሪያ የተደራጀ በባለሙያዎች ከፍተኛ ክትትል የሚደረግበት ክፍለም ተዘጋጅቷል
ሆስፒታሉ ከቅጥር ግቢው ጀምሮ እንደለመድናቸው የመንግሥት የጤና ተቋማት እዛም እዚህም የተኛ በሽተኛ አይታይም፤ ሁሉም አገልግሎት ቦታና ስርዓቱን የያዘ ነው። ” የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ…..” እንዲሉ ግቢው በጥንቃቄ በተያዙ አትክልቶች አምሯል ይህ ደግሞ በምጥ ተይዞ ለመጣ አይደለም ለሌላውም ሳቢ ነው። ሆስፒታሉም አሁን ለይ ይበል በሚያሰኝ የሥራ እንቅስቃሴ ውስጥ ስለመሆኑም የአይን እማኞች ነን።
ሆስፒታሉ ሪፈራል ይጠይቃል ፤ለዚህ ደግሞ ዋናው ምክንያት አገልግሎቱን በጥራት ለማዳረስ ነው የሚሉት የሆስፒታሉ የኳሊቲ ኦፊሰር አቶ ሸጋዬ ዘሌ ናቸው።
አቶ ሸጋዬ እንደሚሉት ሪፈራል ይባል እንጂ አንዲት እናት ሪፈራልም ባይኖራት ከመጣች አትመለስም፤ በመሆኑም በመጣችበት ሁኔታ በተሻለ ባለሙያ የህክምና መሳሪያ ብሎም ሳቢ በሆነ መስተንግዶ አገልግሎቱን አግኝታ ትሄዳለች። በነገራችን ላይ ማንኛውንም አይነት ድንገተኛ የህክምና አገልግሎቶችን እንሰጣለን በማለትም ይናገራሉ።
በወር ከ 850 እስከ 1ሺ እናቶችን የማዋለድ አገልግሎት ይሰጣል የሚሉት አቶ ሸጋዬ እነዚህ እናቶችም ሆኑ ጨቅላ ህጻናቶቻቸው በሚገባቸው ልክ አገልግሎቱን አግኝተው እንዲሄዱ የተቻለንን ሁሉ እናደርጋለን።
አገልግሎቱ ሰፊ ብሎም ማራኪ ነውና በዚሁ እንዲቀጥል የምታደርጉት ጥረት ምን ይመስላል? ተብለው ለተጠየቁት ሲመልሱም “በየጊዜው የሥራ ኦዲት ይደረጋል፤ ይህ የሚሆነው ደግሞ በየሥራ ክፍሉ ሁሉም በደረጃው ነው። በዚህ ደግሞ ለእናቶችም ሆነ ለሚወልዱት ህጻን ብቻ ሳይሆን መረጃ አያያዛችን በራሱ ትልቅ ክትትል ይደረግበታል። የ24 ሰዓቱ ሥራ ደግሞ በየቀኑ ይገለጻል። በዚህም በሰራው ልክ ይመሰገናል ፤ባልሰራው ደግሞ ይጠየቃል፤ ሌላው ደግሞ የእናቶች የህክምና እርካታ ነጻ ሆነው እንዲሰጡም ይደረጋል። በዚህም ሰፊ ግብዓት ይሰበሰባል ችግሮች ይለያሉ የመፍትሔ መንገዶች ይቀመጣሉ” በማለት ይገልጻሉ።
አቶ ሸጋዬ በጤና ተቋሙ ላይ የሚድ ዋይፈሪና የነርሶች እጥረት በተወሰነ መልኩ ይታያል። ከሁሉም በላይ ግን የጽዳትና የጥበቃ ጉዳይ በኤጀንሲ መምጣታቸው በሥራው ላይ ከፍ ያለ ችግር እያስከተለ ስለመሆኑ በመግለጽ ምክንያቱ ደግሞ ሆስፒታሉ በጽዳትም ሆነ በጥበቃ በኩል የራሴ ሰራተኞች ናቸው ብሎ የተለያዩ ስልጠናዎችን ገለጻዎችን አድርጎ ለራሳቸውም ሆነ ለሌላው ጤና በሚጠቅም መልኩ እንዴት መስራት እንዳለባቸው አመላክቶ ወደ ሥራ ካስገባቸው በኋላ ሆስፒታሉ በማያውቀው ሁኔታ ሰራተኞቹ ይቀየራሉ። ይህ ደግሞ በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ ከፍ ያለ ችግር እያስከተለ ስለመሆኑ ይናገራሉ።
በአበበች ጎበና ስም የተሰየመው የእናቶችና ህጻናት ሆስፒታል ዳይሬክተር ዶክተር አናንያ ሰለሞን እንደገለጹት፤ ሆስፒታሉ ከአንድ ዓመት በላይ ለሆነ ጊዜ ለእናቶችና ሕጻናት የተለያዩ ሕክምና አገልግሎቶችን ሲሰጥ ቆይቷል። በዚህ ዓመት ውስጥም አሥራ ሁለት ሺ ለሚሆኑ እናቶች የማዋለድ አገልግሎት ሰጥቷል።
ሆስፒታሉ ለእናቶችና ሕጻናት የሚሰጠው የሕክምና አገልግሎት እንደተጠበቀ ሆኖ በየወሩ ከአንድ ሺ በላይ ለሚሆኑ እናቶች የማዋለድ አገልግሎት ይሰጣል ያሉት ዶክተር አናንያ፤ ከዚህም ባለፈ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠትን መርሁ አድርጎ እየሠራ ይገኛል። ኢትዮጵያ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ የያዘችውን ግብ ለማሳካት የበኩሉን በጎ ተጽዕኖ ለማሳረፍ በትኩረት እየተሠራ መሆኑንም አመልክተዋል።
አገልግሎቱን ቀልጣፋ ለማድረግ ከሚሠራው ሥራ ጎን ለጎን የአገልግሎቱን ጥራት ማስጠበቅ የተቋሙ ቀዳሚ አጀንዳ ነው ያሉት የሆስፒታሉ ዳይሬክተር፤ የሚሰጠውን የአገልግሎት ጥራት የሚከታተል የጥራት ቡድን መቋቋሙንና በየዕለቱ ዳሠሣ በመሥራት ለሚስተዋሉ ችግሮች መፍትሔ እንደሚቀመጥ ተናግረ ዋል።
በየሦስት ወሩ ደግሞ የደንበኞች አጠቃላይ የአገልግሎት እርካታ ምን ይመስላል የሚለው የሚ ለካበት የዳሰሳ ጥናት እንደሚከናወንም አክለዋል።
ሆስፒታሉ ከሚሰጠው የእናቶችና ሕጻናት ሕክምና አገልግሎት በተጨማሪ የማስተማር አገልግሎት ይሰጣል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ እስካሁን ድረስ የቅድመ ምረቃ ሕክምና ተማሪዎችንና የሕክምና ስፔሻሊቲ ተማሪዎችን እያስተማረ ነው። በቀጣይነትም በዘርፍ ላይ የተለያዩ የሰብ ስፔሻሊቲ የትምህርት ክፍሎችን በመክፈት ተማሪዎችን ተቀብሎ ያስተምራል ይላሉ።
ሆስፒታሉ ወረቀት አልባ አገልግሎት መስጠቱ ከሌሎች ሆስፒታሎች እንደሚለየው የጠቀሱት ዶክተር አናንያ፤ በተጨማሪም በእናቶችና ሕጻናት ሕክምና አገልግሎት ከፍተኛ የልህቀት ማዕከል መሆን፣ ለእናቶችና ህጻናት ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት በመስጠት በአገሪቱ ቀዳሚ ተቋም የመሆንና በዘርፉ ከፍተኛ የጥናትና ምርምር ማዕከል መሆን ራዕዮቹ መሆናቸውን በመግለጽ ይህንን ለማሳካት እየተጋ እንደሚገኝም ነው ያብራሩት።
ሆስፒታሉ በየካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ስር የሚተዳደርና 400 የመተኛ አልጋዎች፣ ሰባት የሚሆኑ የቀዶ ጥገና አገልግሎት መስጫዎች እና 12 የማዋለጃ አልጋዎችን አካቶ በእናቶችና ሕጻናት ሕክምና ዘርፍ ሰፊ አገልግሎት እየሰጠ የሚገኝ ግዙፍ ተቋም ነው።
እኛም ይህ የእናቶችንና የህጻናትን ጤና የሚጠብቅ ብሎም እንደ አገር የተያዘውን የእናቶችን ሞት የመቀነስ ስትራቴጂ ግብ እንዲመታ የሚያደርገውን ጥረት ሆስፒታል በጥሩ አግባብ እየተገበረው ይገኛል። ሌሎች ሆስፒታሎችም የዚህን ሆስፒታል ልምድ መቀመር ቢችሉ በዘርፉ ትልቅ ለውጥ ይመጣልም የሚል እምነት አለን።
እፀገነት አክሊሉ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 2 ቀን 2014 ዓ.ም