ባለፈው እሁድ ማታ ‹‹የኔ ትውልድ›› የተሰኘው የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ፕሮግራም ላይ አንድ የቴክኖሎጂ ባለሙያ ሲያብራራ (ወጣት ነው) ቀልቤን ሳበውና ሙሉውን ተከታተልኩ።
ስለማህበራዊ ገጾች ሳስብ ዘላቂነታቸው ያሰጋኛል። ከሆነ ዘመን በኋላ አሁን ያለውን ለዛ የምናገኘው አይመስለኝም። ምክንያቱም ከሰዋዊነት፣ ከማህበራዊነት፣ ከተፈጥሮነት… ወደ ሮቦትነት እየተለወጥን ነው። ከባለሙያው የሰማኋቸውን ትዝብቶች ላስቀድምና ወደራሴ ትዝብት እመለሳለሁ።
ባለሙያው የመተግበሪያዎችን ፈጣን አገልግሎት ሰጪነት፣ ሥራ አቅላይነት፣ ዓለምን አቀራራቢነት ካብራራ በኋላ፤ አሉታዊ ጎናቸው ግን ተፈጥሯዊ የሆነውን ‹‹ኢንተሌጀንት›› እየቀነሰብን መሆኑን ይጠቁማል። በአዕምሮ በማሰላሰል የምንሰራቸውን ሥራዎች ሁሉ መተግበሪያ ላይ ጥለናቸዋል። ምሳሌ ሲያስቀምጥም፤ በፊት ብዙ ቁጥሮችን ሁሉ እያሰብን እንደምር፣ እንቀንስ ነበር። አሁን ግን ከመቶ በታች የሆኑ ቁጥሮችን ሁሉ የምናሰላው ከስልካችን ላይ ያለውን የሂሳብ ስሌት መተግበሪያ ተጠቅመን ነው።
እነዚህን ነገሮች ለመታዘብ የባለሙያ ማብራሪያም አያስፈልገንም። በዙሪያችን ያለውን ነገር ልብ ማለት በቂ ማሳያ ነው። አሁን አሁን እያንዳንዷን ነገር በመተግበሪያ መጠቀም እየለመድን ነው። ለዚህም ነው ለትንሽ ደቂቃ ከስልካችን ስንለይ ከሕይወታችን አንድ ነገር የጎደለ የሚመስለን። በመተግበሪያዎች ምክንያት ተፈጥሯዊ የሆኑ ነገሮችን እየረሳን ነው።
ለምሳሌ፤ ዛሬ ቀን ስንት እንደሆነ፣ የዛሬ ሳምንት ስንት እንደሚሆን፣ የነገ ወይም የትናንት ሳምንት ስንት እንደሚሆን ወይም ስንት እንደነበር ለማወቅ የራሴ የምጠቀምበት ዘዴ ነበረኝ። አሁን ግን እየረሳኋቸው ነው። ማሰብና ማሰላሰል ሳያስፈልገኝ ከስልኬ ላይ ያለውን የቀን መቁጠሪያ መተግበሪያ አያለሁ። ቀን ለማወቅ እጄ ላይ ካለው ሰዓት አያለሁ።
ከምንም በላይ ግን የሚያሰጋኝ ማህበራዊ ገጾች ከዘመናት በኋላ የአሁኑን ለዛ እና ማራኪነት ማጣታቸው ነው። እርግጥ ነው ከዘመናት በኋላ አሁን የምንጠቀምባቸው መተግበሪያዎችም ሆኑ የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች አይነታቸው ሊቀየር ይችላል። ዳሩ ግን ምንም ይሁን ምን ሰዋዊና ተፈጥሯዊ የሆነውን ነገር ካጣን ሮቦታዊ ነው የምንሆነው።
በማህበራዊ ገጾች ምክንያት ማህበራዊ ህይወታችን እየሳሳ ነው። አካባቢን ማስተዋል እየቀረ ነው። ተፈጥሮ ላይ መመሰጥና በአዕምሮ ማሰላሰል፣ መመራመር እየሳሳ ነው። ይሄ ሆነ ማለት ደግሞ በሰው ልጅ አዕምሮ ታስበው የሚሰሩ ሥራዎች ይቀንሳሉ ማለት ነው። ረጃጅም ልቦለዶች አይጻፉም ማለት ነው። ይሄ ቢቀርም ቀላል ነው ብንል እንኳን ተፈጥሮ ላይ መመራመር ይቀንሳል ማለት ነው።
ለምሳሌ፤ ኢትዮጵያዊው ሳይንቲስት ዶክተር አክሊሉ ለማ በልብስ ማጠቢያ ማሽን ልብስ ቢያጥብ ኖሮ ያንን እንዶድ ይመራመርበት ነበር? እንዶዱን ልብ ብሎ ያየው ተፈጥሮ ውስጥ ስለነበር ነው። ልክ እንደዚያ ሁሉ፤ በየደረስንበትና በያረፍንበት ሁሉ ስልክ ላይ የምናተኩር ከሆነ እነዚያን በዙሪያችን ያሉ ተፈጥሮዎች አናስተውላቸውም ማለት ነው።
ማህበራዊ ገጾች አሁን ላይ ማራኪ የሆነ ለዛ፣ ቀልብ ሳቢ የሆነ ጽሑፍ የያዙት እስከ አሁን በነበረን የማህበራዊ ሕይወት ትሩፋቶች ነው። በማህበራዊ ገጾች ቋንቋ ‹‹ሜም›› የሚባሉ ቀልዶች አሉ። እነዚህን ቀልዶች ልብ ብላችሁ ካያችሁ ማህበራዊ ህይወታችን እና ግንኙነቶቻችን ላይ የሚያተኩሩ ናቸው። እሱ ሲረሳና ሲጠፋ እነዚህ ቀልዶች ላይኖሩ ይችላሉ ማለት ነው።
የማህበራዊ ገጾች በአገራችን ከ10 ዓመት የዘለለ ታሪክ የላቸውም። ስለዚህ አሁን ላይ ያለ ወጣት ከ10 ዓመት በፊት ተፈጥሮን ያስተውል ነበር፣ በማህበራዊ ህይወት ውስጥ ይሳተፍ ነበር፣ በአካባቢው የሚከወኑ ሁነቶችን በትኩረት አስተውሏል። ስለዚህ ዛሬ ላይ የሚጽፋቸውና የሚቀልዳቸው ሁሉ የዚያ ውጤት ናቸው።
ዛሬ ላይ ያለ አንድ የ10 ዓመት ህጻን ‹‹ስማርት›› ስልክ ያዘ እንበል። ይህ ልጅ 24 ሰዓት ከዚሁ ስልክ ጋር ቢቆይ፣ ጠዋትም ማታም ከትምህርት ቤት በመኪና የሚያመላልሱት ቢሆን፣ በአጠቃላይ አካባቢውንና ተፈጥሮን የማያይ ቢሆን፤ የተፈጥሮ ተመራማሪ መሆን ይችላል? የልቦለድም ይሁን የወግ ደራሲ መሆን ይችላል? የሕዝቡንና የአገሩን ችግር ተረድቶ የፖለቲካ ጉዳዮች ተሳታፊ መሆን ይችላል?
በዚህ ልጅ ምሳሌ ከሄድን፤ ዓለም ራሱ ከሆነ ዘመን በኋላ ከተፈጥሮ ውጭ ልትሆን ትችላለች። የውጭውን ዓለም (በተለይም የምዕራባውያንን) እና የኢትዮጵያን ካነጻጸርን ደግሞ ሰፊ ልዩነት አለው። እነርሱ ከማህበራዊ ገጾች መስፋፋት በፊትም ከቡድንና አብሮነት ይልቅ ተናጠላዊ ህይወታቸው ይበዛል። ባቡር ውስጥና ባስ ውስጥ ሁሉም ጋዜጣ ነገር እያነበቡ እንደሚሄዱ አገራቱን ያዩ ሲናገሩ ሰምተናል። ስለዚህ ማህበራዊ ህይወታቸው ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ጫና እንደ ኢትዮጵያ አይሆንም።
ቀደም ሲል እንዳልኩት የሚያሳጣን የማህበራዊ ህይወት ግንኙነታችንን ብቻ አይደለም፤ ዕውቀት አጠር እንድንሆንም ያደርገናል። ተፈጥሮንና አካባቢን አንመረምርም።
ብዙ ሰዎች ማህበራዊ ገጾች ለንባብ ልምድ መዳበር ጥሩ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ይናገራሉ። ዳሩ ግን ጥልቅ ንባብንና መረዳትን ያዳብራሉ ብሎ ማመን ይከብዳል። ምክንያቱም በባህሪው ፈጣን ነው፤ ብዙ ነገሮች በአንድ ጊዜ የሚታዩበት ነውና ቀልብን ወደ አጫጭር ነገሮች ይወሰውሳል።
በዚያ ላይ ማወቅ ማለት የግድ ከሚነበቡ ጽሑፎች ወይም ከሚታዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች ብቻ አይደለም። ተፈጥሮን እና አካባቢያችንን በማስተዋል ብዙ ማወቅ ይቻላል። የስልካችን መተግበሪያዎች ላይ ብቻ መሆናችን ያንን ነው የሚያሳጣን።
መገናኛ ከአንድ ፎቅ ላይ ካለ የካፌ በረንዳ ላይ የተቀመጠ ሰው ስልኩን አውጥቶ ይጎረጉር ይሆናል። በስልኩም ዓለምን ያያል። ዳሩ ግን በዙሪያው ብዙ ነገሮች እያለፉት ነው። ፌስቡክ ላይ የሚያነበው እኮ ከእነዚያ አካባቢያዊ መስተጋብሮች የወጡ ናቸው። እርሱ ግን የአካባቢውን ንቆ ፌስቡክ ላይ ያለው የተሻለ ስለሚመስለው ስልኩን ይጠቀማል። የሚያስቀውም፣ የሚያስለቅሰውም ትዕይንት ግን እዚያው መገናኛ ጎዳናዎች ላይ አለ።
በዓባይ በረሃ ወደ ጎጃም የሚሄድ፣ ወይም በጊቤ በረሀ ወደ ጅማ የሚሄድ፣ ወይም በደቡብ ለምለም አካባቢዎች እያቆራረጠ ወደ አርባ ምንጭ የሚሄድ ተጓዥ ስልኩ ላይ ተደፍቶ ቢሄድ ብዙ ነገር ነው የሚያመልጠው። የተፈጥሮን ምሥጢር ማየት አልቻለም ማለት ነው፤ በየመስመሩ ዳር ያሉ ማህበረሰቦችን ባህላዊ እንቅስቃሴዎችን ማየት አልቻለም ማለት ነው።
እነዚህ እንግዲህ እንደ አጠቃላይ እንደ ማህበራዊ ገጾች ካየነው ነው። በተለይ መተግበሪያዎችን ካየናቸው ደግሞ ዛሬውኑ ሮቦት ማድረግ ጀምረዋል። ሱቅ ውስጥ ትንንሽ ነገሮች ገዝተን ወይም ካፌ ውስጥ ምግብና ትኩን ነገር ተጠቅመን፤ እነዚያን ለመደመር ስልክ እናወጣለን። ‹‹አንድ አለኝ›› እያሉ መደመርን፣ ከዚያኛው ቁጥር እየተበደሩ መቀነስን፣ ቁልቁል ማካፈልን እና ማባዛትን እንደ አሰልቺ ነገር ስለምናየው በጽሑፍ አንሞክረውም ማለት ነው። ይሄ ደግሞ ከማሰብና ማሰላሰል እያራቀን ነው ማለት ነው። ስለዚህ፤ ከተፈጥሯዊ ማሰብና ማሰላሰል እንዳንርቅ አጠቃቀሙን እንወቅበት!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ሰኔ 29 /2014