በቅርቡ የጉማ ሽልማት ተካሂዶ ነበር። ሽልማቱ በተለይ በፊልሙ ዘርፍ በ2013 ጥሩ ስራዎችን ያቀረቡ የጥበብ ሰዎች የተሸለሙበት እና በማህበራዊ ሚዲያም የብዙዎች መወያያ የነበረ ፕሮግራም ነበር። በዚህ የሽልማት መርሀ ግብር ላይ ወርቃማውን ዋንጫ ይዘው ወደቤታቸው ከሄዱ የጥበብ ሰዎች መሀከል አንዱ የዛሬው እንግዳችን ነው። በጉማ አዋርድ ላይ ማን ያዘዋል በሚለው ፊልሙ በ11 ዘርፎች ታጭቶ በሶስቱ ዋንጫውን የወሰደው እና ከሶስቱ ሽልማቶቸ መሀከል ደግሞ ሁለቱ የግሉ የሆኑለት በዚህም የተነሳ የ2013 የአመቱ ምርጥ ደራሲ እና ዳይሬክተር የተሰኘው ወጣቱ ጥበበኛ ኑር አክመል ዛሬ አብሮን ይቆያል።
የተወለደው እዚሁ አዲስ አበባ በተለምዶ አስኮ ጨረታ በሚባለው አካባቢ ነው። ቀኑ ጳጉሜ 3 አመቱም 1989 አ.ም ነው። አሁን 25ኛ አመቱ ላይ ነው ማለት ነው። አባቱ አቶ አክመል ሰማን እና እናቱ ወ/ሮ ብርሀኔ ተፈሪ አራት ልጆች ያሏቸው ሲሆን ከነዚህ 4 ልጆች ኑር የመጨረሻው ነው። የአቶ አከመል ቤተሰብ ለየት ያለ ነው። ኑር የቤተሰቡን ታሪክ “ፊልም ይወጣዋል” ይላል። ምናልባትም ስልጡን እና ዴሞክራሲያዊ ቤተሰብ ነው ልንለው እንችላለን። ከአራቱ ልጆች ኑር እና ወንድሙ ሙስሊም ሲሆኑ ሁለቱ ሴቶች ደግሞ ኦርቶዶክስ ናቸው። በቴዲ አፍሮ ሙዚቃ እንደተባለው አንቺም በሀይማኖትሽ እኔም በሀይማኖቴ ፤ መኖር እንችላለን አይጠበንም ቤቴ የተባለበት ሁሉም ተዋድዶ እና ተስማምቶ የሚኖርበት ቤት ነው የአቶ አክመል ቤት።
ኑር እድሜው ለትምህርት ሲደርስ መጀመሪያ የገባው እዚያው ቤታቸው አቅራቢያ የሚገኘው ቃሌ አጸደ ህጻናት ነበር። ከዚያም ከአንድ እስከ ስምንት ጉለሌ ፋና አንደኛ ደራጃ ሲማር ሁለተኛ ደረጃውን ደግሞ አስኮ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አጠናቀቀ። የመሰናዶ ትምህርቱን ደግሞ መድሀኔአለም ሁለተኛ ደረጃ ተማረ።
ኑር በተማሪነት ዘመኑ እንደ ብዙሀኑ ተማሪ ለትምህርት የተለየ ፍቅር የሌለው እና እንዲሁ ሲጫወት እና ወዲያ ወዲህ ሲል ቢውል የሚወድ ልጅ ነበር። ሙሉ ትኩረቱን ትምህርት ላይ አለማድረጉ ግን ወደ ኪነ ጥበብ አልመራውም። እንዲያውም የሱ ልብ ያለው ስፖርት ላይ ነበር። ቀንደኛ የማንችስተር ዩናይትድ ደጋፊ ነው። ስለዚህም እሱም ሆነ ቤተሰቦቹ ምናልባት ወደፊት ጋዜጠኝነትን ተምሮ የስፖርት ጋዜጠኛ ይሆናል እንጂ ወደ ጥበብ የሚወስደው መንገድ ይኖራል ብለው አላሰቡም። ህይወት ግን ለኑር ሌላ የራሷ የሆነ መንገድ ቀይሳ እየጠበቀችው ነበር።
በየጊዜው ከክፍለ ሀገር ወደ አዲስ አበባ የሚመጣ በጸጋው የሚባል የነ ኑር ዘመድ አለ። ሲመጣ ኑርን ሲኒማ ይዞት ይገባል። ያኔ ኑር የመሰናዶ ትምህርት ቤት ተማሪ ነበር። ወቅቱ ደግሞ እነ ረቡኒ እና መሰል ምርጥ ፊልሞች በሲኒማ ቤቶች የሚታዩበት ወቅት ነበር። ኑር እነዚያን ፊልሞች ሲያይ ከመዝናናት በላይ ፊልም የመስራትን ምኞት ፈጠሩበት። ከዚያ ደግሞ አንድ ቀን ወንድሙ የሚራክል የፊልም ትምህርት ቤትን ማስታወቂያ በራሪ ወረቅት ይዞ ቤት መጣ። ኑር ለመማር ወሰነ። በወቅቱ የመሰናዶ ትምህርቱን ጨርሶ ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ አካውንቲንግ ተማሪ እንዲሆን ተመድቦ የነበረ ቢሆንም እሱ ግን እዚሁ አዲስ አበባ ለመማር ነው የወሰነው። እናም የፊልም ትምህርት ቤቱ ገብቶ ተማሪ ሆነ። አንጋፋው የጥበብ ሰው የክብር ዶክተር ተስፋዬ አበበ (ፋዘር) የሚያስተምሩበት በተለምዶው ፋዘር ቤት የሚባለው ትምህርት ቤትም ተቀላቀለ። እዚያ ብዙ እሱን የሚመስሉ እና ከሱም የሚበልጡ የጥበብ ሰዎችን አገኘ። ከዚያም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በማታው ክፍለ ጊዜ የቴአትሪካል አርት ተማሪ ሆኖ ተመዘገበ። በወቅቱ የጋዜጠኝነት ተማሪ ይሆናል ብለው አስበው የነበሩት እናቱ በውሳኔው ቢደናገጡም ነገር ግን የልጃቸውን መሻት እሳቸውም ሆነ ጋሽ አክመል ሊገቱት አልፈለጉም። ”መጀመሪያ ራሱ ያሰኘውን ይሞክርና በኋላ እንሞክርበታለን ብለው ነው መሰለኝ እድል ሰጥተውኛል” ይላል።
ትምህርቱ ተጀመረ። ኑር ትምህርቱን እየተማረ ረፍት አልነበረውም። የተማረውን በተግባርም ይሞክር ነበር። ስክሪፕቶችን ይጽፋል ፤ ባለሙያዎች እንዲያዩለትም ይሰጣል። በእጅ የተጻፈ እሷ ናት የተሰኘ 120 ገጽ ስክሪፕት በእጁ ጽፎ ነበር። ሌሎችም ተጨማሪ ሁለት ሶስት ስክሪፕቶችን ጽፏል። ከዚያ የመጀመሪያ ስራው የሆነውን አቶ እና ወይዘሮ ጻፈ። እንዲያዩትም ለአንጋፋዎቹ ሰለሞን ሙሄ እና ቃልኪዳን ጥበቡ ሰጣቸው። ያኔ ገና የ20 አመት ጎረምሳ ነበር። ልጅ ነው ብለው ሳይንቁ ስክሪፕቱን አዩ ፤ አደነቁለትም። ወደ ስራ ተገባ። ባለሙያ ተመረጠ ፤ ዝግጅቶችም ተጠናቀቁ። የቀረው አንድ ነገር ብቻ ነው፡ ፡ ገንዘብ። ሊያውም 150ሺ ብር።
ቤት ሄደ። ፊልም ስለማየት እንጂ ፊልም ስለመስራት ምንም ግንዛቤው ለሌላቸው ቤተሰቦቹ ሀሳቡን አስረዳ። ብዙም ስላልገባቸው ባይቃወሙትም ገንዘብ ለመስጠት ግን አልደፈሩም። ስለዚህም አዲስ እና ለየት ያለ የቅስቀሳ ዘዴ ይዞ መጣ። ዝናብ ሲዘንብ የጣሪያው ፍሳሽ ተሰብስቦ የሚወርድበት አሸንዳ ስር ሄዶ ተቀመጠ። ይህን ያየችው አንደኛዋ እህቱ ጥያቄው ምን ያህል ጽኑ እንደሆነ ስታውቅ ለክፉ ቀን ብላ ያስቀመጠችውን ወደ 70ሺ ብር ገደማ ልትሰጠው ወሰነች። ወትሮም ቢሆን ልቧ የማይጨክነው እናት ወ/ሮ ብርሀኔም ለቁርጥ ቀን ይሆናል ብላ ያስቀመጠችውን ብር አውጥታ ልትሰጥ ወሰነች። ብሩ ተገኘ። ፊልሙም ተሰራ። የምርቃቱ ቀን ቤተሰቦቹ ሁሉ እንዲያውም ምን ጉድ ሰርቶ ይሆን ብለው ነበር የተገኙት። ፊልሙ ታየ። ህዘብ ወደደው። ተነስቶ አጨበጨበለት። እናትና እህት ገንዘባቸውን ውሀ እንዳልበላው አዩ። ከሁሉ በላይ ግን የጋሽ አክመል ቤተሰብ ልጃቸው ፊልም ውስጥ እንዲገባ መፍቀዳቸው ስህተት እንዳልነበር አዩ።
በመጀመሪያ ፊልሙ ስኬት የተነቃቃው ኑር ሁለተኛ ፊልም ሊሰራ ተነሳ። ባለቤት የሚል ፊልምም ሰራ። አንጋፋው ፈለቀ የማርውሀ ነበር ተዋናዩ። ስኬታማ እንደሚሆኑ እርግጠኛ ሆነው ነበር የጀመሩት። ነገር ግን ፊልሙ እንደታሰበው በህዝብ ዘንድ አልተወደደም። እሱና አብሮት የሰራው ወዳጁ የግማሽ ሚሊየን ብር ኪሳራ ተከናንበው ቁጭ አሉ። በወቅቱ የነበውን ስሜት ሲያስታውስ “ለወር ገደማ ከቤት አልወጣሁም” ይላል ኑር። ፊልሙ በወቅቱ በሲኒማ ቤት ተመልካቾች ተወዳጅነት አያግኝ እንጂ በኋላ ላይ ግን ተወዳጅ እንደሆነ እና ብዙ ገንቢ አስተያየቶችም እንደመጡ በተለይም ፊልሙ ከትዳር ጋር የተያያዘ በመሆኑ ብዙ ባለትዳሮች ትምህርት እንደቀሰሙበት እንደነገሯቸው ኑር ይናገራል።
ቀጠለ። ካደረበት ጉዳት ለማገገም መፍትሄ ያስፈልጋል። መፍትሄው ደግሞ ሌላ ፊልም መስራት ነው። ኮሜዲ ፊልም ለመስራት ተነሳ። ስቄ ልሙት የሚል ኮሜዲ ፊልም ሰራ። ይሄኛው ደግሞ ተወደደለት። እንደገና አገገመ። ወደ መስመሩ ተመለሰ። ቀጣዩ ፊልም ታሰበ። አንድ ቀን ቡና እየጠጡ ጓደኛው የነገረውን ታሪክ ፊልም ሊያረግ ወሰነ። ማን ያዘዋል የሚል ፊልም ተሰራ። ፊልሙ ተሰርቶ ፤ ማስታወቂያ ለህዝብ ተነግሮ ለህዝብ ሊቀርብ ሲል ግን ያልታሰበ ችግር መጣ። ኮሮና ገባና ሲኒማ ቤቶች ተዘጉ። ምንም ማድረግ ስለማይቻል ኑር እና ጓደኞቹ እጃቸውን አጣጥፈው ቁጭ አሉ። ያኔ ለማንበቢያ እና ለማሰቢያ ጊዜ አገኘ። ከዚያም ወደ ክሊፕ እና ማስታወቂያ ስራዎችም ገባ። በወቅቱ ከሰራቸው የሙዚቃ ክሊፖች መሀከል የመሳይ ተፈራ ደሞ ደሞ ፤ የሀሌሉያ ካንተ ጋራ ፤የኩኩ ሰብስቤ ድማማ ፤የ ህብስት ጥሩ ነህ ቀረ እንዴ ተጠቃሽ ናቸው። ከዚያ ኮሮናው ጋብ ሲል እና ሲኒማ ቤቶች ሲከፈቱ ፊልሙ ለእይታ በቃ። እነሆ ከሳምንታት በፊትም የአመቱ ምርጥ የፊልም ሰውም ተባለበት።
በአሁኑ ወቅት ለሌላ ፊልም ዝግጅት ላይ ያለው ኑር በዲኤስ ቲ ቪ ሁለት ጉልቻ የተሰኘ ከደቡብ አፍሪካው አንሜሪድ የተሰኘ ፊልም የተቀዳ ተከታታይ ድራማ እያዘጋጀም ይገኛል። ስለ ሽልማቱ ሲያስብ በብዙ ታላላቅ እና ለሲኒማው ዘርፍ ማደግ ብዙ መስዋእትነት የከፈሉ ሰዎች ፊት ሽልማት መቀበሉ ትልቅ ኩራት እንደፈጠረለት ይናገራል። ኑር የፊልም ዘርፉ እንዲያድግ ዲሲፕሊን እና ጠንካራ ስራ ያስፈልገናል ይላል። ”ጠዋት ዝም ብላ ከቤት የወጣች ልጅ ከሰአት ቤቷ ስትመለስ ተዋናይ ሆና ከመጣች ጥሩ አይደለም። ሀገራችን ብዙ ህዝብ አላት ፤ ከዚህም መሀከል ብዙሀኑ ወጣት ነው። ይህ የሚፈጥረው ብዙ እድል አለ። ናይጄሪያን ፤ ህንድን ማየት ትችላለህ። አሁን ወደ እኛም እየመጡ ያሉ አዳዲስ ትልልቅ እድሎችም አሉ። እነሱን ለመጠቀም ካስፈለገ ደግሞ በዚያ ልክ ራሳችንን ማዘጋጀት አለብን” ይላል። ከዚህም ባለፈ ኑር “ፊልም ለማየት አንድ ሰው ወደ ሲኒማ ሲመጣ ሊከፍል የሚገባው 5 ብር ብቻ ነው ብዬ አምናለሁ ይላል። የሚያስፈልገው ከአንድ ሰው ለአንድ ፊልም መቶ ብር መቀበል ሳይሆን ፊልሙ ለተመልካች ተደራሽ የሚሆንበትን እድል ማስፋት ነው ብዬ አምናለሁ” ይላል።
ኑር ኳስ ይወዳል። ስራውም መዝናኛውም ፊልም ቢሆንም እንኳ ከዚያ ውጭ ያለውን ጊዜ የሚያሳልፈው እግር ኳስ በማየት እንደሆነም ይናገራል። በመጨረሻ በዚህ በጉርምስናው ወራት ለስኬት እንዲበቃ ላገዙት ሰዎች ምስጋናውን እንዲቀርብ እድል ሰጠነው። ”በመጀመሪያ እዚህ ቦታ ላይ እንድደርስ በሁሉም መንገድ ላገዙኝ ቤተሰቦቼ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ፤ በመቀጠል በስራዬ ለሚያግዙኝ የነፍስ ሰዎቼ የስራ ባልደረቦቼ ምስጋና አቀርባለሁ። በመጨረሻም ይህ ሙያ እዚህ እንዲደርስ መስዋእትነት ለከፈሉ ሰዎች ምስጋናዬን አቀርባለሁ” ብሏል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ሰኔ 5 ቀን 2014 ዓ.ም