የዘመናዊ የኢትዮጵያ ሙዚቃ ላይ የሚታይ አሻራ ካላቸው አካላት መካከል ዋነኛው በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የግል ባንድ የሆነው ሶል ኤኮስ ባንድ ነው። ይህ ባንድ በኦርኬስትራዎች ብቻ የተዋቀረውን የኢትዮጵያ የሙዚቃ መልክአ ምድር ሰብሮ የገባ የግል ባንዶች በኩር ሲሆን፣ ለዝነኞቹ ሮሀ እና አይቤክስ ባንድም ወላጅ ነው።
የዚህ ባንድ መስራች ደግሞ ታላቁ ሙዚቀኛ ተሾመ ምትኩ ነው። በዛሬው የዝነኞች ገጽ አምዳችን ከአገር ከወጣ ግማሽ ክፍለ ዘመን ገደማ የቀረበውን ይህን ግዙፍ የሙዚቃ ሰው እንዳስሳለን። ይህንንም በተለያዩ ጊዜያት ያደረጋቸውን ቃለመጠይቆች አሰባስበን እንደሚከተለው ታሪኩን በአጭሩ ጽፈናል።
ከዚያ በፊት ግን አንባቢ ተሾመ ምትኩ ማን ነው ብሎ ግራ እንዳይጋባ ዛሬም ድረስ እንደ አዲስ እየተደመጡ እና እየተዘፈኑ ካሉ ሙዚቃዎቹ ጥቂቶቹን እናስታውስ፤- ጋራ ስር ነው ቤትሽ ፤ ሞት አደላድሎኝ ፤ ሀሳቤ ፤ ሱሰኛሽ ፤ የመቃብር እጮኛዬ ፤ ቼ በለው ከሙዚቃዎቹ መካከል ይጠቀሳሉ።
ተሾመ የተወለደው እዚህ አዲስ አበባ ቀበና አካባቢ ነው። ወቅቱም በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1942 ዓ.ም ገደማ ነው። ስወለድ ጀምሮ ነው ከሙዚቃ ጋር በፍቅር የወደቅኩት የሚለው ተሾመ፣ ስለ እድሜ ልክ ወዳጁ ስለሙዚቃ ሲያወራም ሆነ ተወዳጅ ሙዚቃዎቹን ሲጫወት በጥልቅ ስሜት ውስጥ ሆኖ ነው።
የሙዚቃ ፍቅሩን የጀመረው ከእናቱ ድምጽ በመስማት ይመስላል። የተሾመ እናት እንደ ብዙሀኑ የኢትዮጵያ እናቶች ስራ እየሰሩ ለስለስ ያለ ልብ የሚነካ እንጉርጉሮ የሚንጎራጉሩ ሲሆን፣ የተሾመ ጆሮም የተቃኘው በዚያ ነው።
ሙዚቃን መጫወት የጀመረው ገና የ0 ክፍል ተማሪ በነበረበት ወቅት ነው። በዚያን ወቅት 0 ክፍል የሚባል የነበረ ሲሆን፣ እዚያ ክፍል ላይ ለትምህርት መሰረታዊ የሆኑትን እንደ ፊደል መቁጠር ያሉ ነገሮች ተምሮ ያለፈ ብቻ ነበር አንደኛ ክፍል የሚገባው።
ተሾመ ከ0 ክፍሉ በፊት ቄስ ትምህርት ቤት ገብቶ ፊደል ቆጥሮ ዳዊት የደገመ ስለነበረ ኮከበ ጽባህ ገብቶ 0 ክፍልን ሲማር አልከበደውም፤ ተማረ። ትምህርት ቤት ሲሄድ ግን ብዙ ጊዜ አርፋጅ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ ጠዋት ከእንቅልፉ እንደተነሳ በሬዲዮ ሙዚቃ እየሰማ ብዙ ደቂቃዎችን ስለሚያልፍ ነው። የሙዚቃ ፍቅሩ በዚያ ልክ ነበር። በተለይም ክራር እና በገና ያለባቸው ሙዚቃዎችን በጣም ይወድድ ነበር። አንዳንዴ እንደውም ዋሽንት የሚጫወት ሰው ካየ ትምህርት ቤቱን እርግፍ አድርጎ ቁጭ ብሎ ሊሰማ ሁሉ ይችላል።
0 ክፍልን ጨርሶ አንደኛ ክፍል ሲገባ በሚማርበት ትምህርት ቤት የሙዚቃ ትምህርት ተጀመረ። የሙዚቃ መምህሩ ደግሞ ዴንማርካዊው ፖል ባንክ ሀንሰን ናቸው። መምህሩ ተማሪዎችን የሙዚቃ ምት አጠባበቅ፤ አዚያዚያም ወዘተ ላይ ስልጠና ይሰጣሉ። ከዚያም ይፈተናሉ። ተሾመም ተፈተነ ፤ አለፈ። መምህሩ ያቋቋሙት የሙዚቃ ቡድን አባል ሆነ። ከእሱ ጋር በኋላ ላይ ሶል ኤኮስን ያቋቋሙት ወንድሙ ቴዎድሮስ ምትኩ ፤ ተስፋዬ መኮንን እና ታምራት ፈረጃም የቡድኑ አባል ሆኑ።
ሙዚቃ አፍቃሪው ተሾመ ከመምህሩ ሚስተር ሀንሰን ቤት አንድ የተለየ ድምጽ የሚያወጣ የሙዚቃ መሳሪያ የመምህሩ ባለቤት ሚስስ ማርጋሬት ሲጫወቱ አየ። የሙዚቃ መሳሪያው ፒያኖ ነው። በድፍረት እንዲያስተምሩት ጠየቃቸው። ወይዘሮዋ ተገረሙ። ግን ፈቃደኛነታቸውን ገለጹለት። እሺ አስተምርሃለሁ፤ ግን አንድ ነገር ቃል መግባት አለብህ። በየቀኑ ከ10 እስከ 11 ሰዓት ሳታረፍድ ሳትቀር መምጣት አለብህ አሉት፤ ተስማማ።
ትምህርቱ ተጀመረ። ወ/ሮ ማርጋሬት ለአዲሱ ተማሪያቸው ከረሜላ ፤ ብስኩት ፤ ለስላሳ እየጋበዙ ያስተምሩት ጀመር። በፒያኖ የተጀመረው ትምህርት ትራምፔት ቫዮሊን እና ድራምንም ጨመረ።
ተሾመ ሙዚቀኛ ሆነ። አባቱ አቶ ምትኩ ልጃቸው ሙዚቃ መማሩ ባይከፋቸውም ነገር ግን ከመሳሪያዎች ሁሉ ግን ትራምፔትን አልወደዱትም። ምክንያታቸው ደግሞ በልጃቸው ሳንባ ላይ ጉዳት ያመጣል ብለው ማሰባቸው ነው። ቢሆንም ተሾመን ማስቆም አልቻሉም።
በየቀኑ ጠዋት 12 ሰዓት ተነስቶ የመጀመሪያ ስራው ትራምፔትን መጫወቱን ተያያዘው። ጎረቤትም የሚነቃው በተሾመ ትራምፔት ድምጽ ነው። ከዚያም 1 ሰዓት ሲል ትምህርት ቤት ደርሶ ሰንደቅ አላማውን ይሰቅላል። ማታም እንደዚሁ የሰቀለውን ሰንደቅ አውርዶ ይመለሳል።
እንዲህ እንዲህ እያለ ያደገው የሙዚቃ ሕይወት ቀጣዩ ደረጃ ባንድ መመስረት ሆነ። ተሾመን ፤ ወንድሙን ቴዎድሮስ ፤ ታምራት ፈረጃ ፤ ተስፋዬ መኮንንን እንዲሁም በኋላ ላይ ተወዳጁን ድምጻዊ ሰይፉ ዮሀንስን እና ጊታር ተጫዋቹን አሉላ ዮሀንስን የያዘው ሶል ኤኮስ ባንድ ተመሰረተ።
ሶል ኤኮስ በወቅቱ ካሉት የቴአትር ቤት ኦርኬስትራዎች ውጭ የሆነ የመጀመሪያው ባንድ ሲሆን አጨዋወቱም ለየት ያለ ነበር። ተሾመ በግሉ ‹‹ሸግዬ ሸግዬ ሸግዬ ሸጊቱ›› በሚለው ሙዚቃው የምናውቀው የአሰፋ አባተ ተጽእኖ እንዳለበት የሚናገር ሲሆን፣ ባንዱ ደግሞ በወቅቱ በጣም ተወዳጅ የነበሩት ጥቁር አሜሪካዊ ድምጻውያን ጀምስ ብራውን ፤ ማርቪን ጌይ ፤ አሪታ ፍራንክሊን እና ሌሎች ተጽእኖ ያለበት ነበር። ኢትዮጵያዊውን ሙዚቃ ከነዚህ ድምጻውያን የአጨዋወት ስልት ጋር እያዳቀሉ ነበር እንደ ጋራ ስር ነው ቤትሽ እና መሰል ለየት ያሉ ተወዳጅ ሙዚቃዎች የሰሩት።
የተሾመ እና የሶል ኤኮስ ባንድ ዝና መናኘት ጀመረ። እነሱ ይገኙበታል የተባለ ቦታ ሁሉ በታዳሚ መሞላት ጀመረ። በተለይም ወጣቱ በጣሙን ወደዳቸው። እነሱ ተወዳጅ የሆኑበት ያ ወቅት ደግሞ ኢትዮጵያ እንደ አገር ፖለቲካዊ ውጥረት ውስጥ የነበረችበት ወቅት ነበር።
ዘውዳዊ ስርአቱን ለመገርሰስ በተማሪዎች የሚመራው እንቅስቃሴ ተጧጡፏል። ወጣቱ በተለይም የሁለተኛ ደረጃ እና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በአንድ ጎን የለውጥ ሀይሎች በሌላ ጎን የነተሾመ ሙዚቃ አድናቂዎች ነበሩ።
አንድ ቀን እነ ተሾመ በሺ የሚቆጠር ተማሪ በታደመበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ልደት አዳራሽ ሙዚቃ ሊያቀርቡ ተገኙ። ሰይፉ ዮሀንስ ሶስት ሙዚቃዎችን አቅርቦ ወረደ። ተረኛው ተሾመ ነው። ወደ መድረክ ሲወጣ ተማሪው በሙሉ ‹‹ፋኖ ተሰማራን ›› ካልዘፈንክልን ብሎ አስጨነቀው። በተማሪው ዙሪያ ክቡር ዘበኛ እና ፖሊስ መሳሪያቸውን ታጥቀው ተኮልኩለዋል። ተሾመ ግራ ገባው። እምቢ ቢል ተማሪዎቹን ማሳዘን ሆነ። እሺ ቢል መንግስት ጥርስ ውስጥ ሊገባ ነው። የጸጥታ ኃላፊውን ጠየቀው። የተማሪዎቹ ጥያቄ እንደማይቆም ያወቀው ኃላፊ ዝፈን አለው፤ ዘፈነ። ያቺ ዘፈን ግን የተሾመን የሕይወት መስመር የምትቀይር ሆነች።
ከዚያ በኋላ የመንግስት የጸጥታ ሀይሎች እነ ተሾመን መከታተል እና ማዋከቡን ስራ አድርገው ያዙት። ክስ እና ምርመራ ተደጋጋሚ ሆነ። እንዲያውም በአንድ ወቅት 350 ሺ ብር ታክስ መክፈል እንዳለበት ተነገረው። ሌላ ቀን ደግሞ ዙላ ክለብ የሙዚቃ ዝግጅቱን ሊያቀርብ ዝግጅት ላይ እያለ ያለ ምንም ምክንያት ታሰሮ የዝግጅቱ ቀን ካለፈ በኋላ በዋስ ተለቀቀ።
ይህ ነገር ከቀጠለ ለሕይወቱም እንደሚያሰጋው ያወቀው ተሾመ ከአገር ለመውጣት ወሰነ። የዴንማርክ እና የስዊድን ቪዛ ነበረውና ወደ ኮፐንሀገን ከዚያም ወደ ስዊድን ሄደ። ኮፐንሀገን እንደደረሰ ከአውሮፕላን ወርዶ ታክሲ ሲሳፈር የመጀመሪያ ጥያቄው ሙዚቃ ወዳለበት ቦታ ውሰደኝ የሚል ነበር። ሹፌሩ ወደ አንድ ፐብ ወሰደው። ሆቴል ገብቶ ልብሱን ከቀየረ እና ጥቂት እረፍት ካደረገ በኋላ ወደ ቡና ቤቱ ተመለሰ። ጥብስ አዘዘ ፤ ውስኪም ተጎነጨ።
ከጥቂት ቆይታ በኋላ ባንዱ ሙዚቃ ጀመረ። የባንዱን መሪ ጠርቶ ፒያኖ ልጫወት ሲል ጠየቀው። ሰውየው ግራ ገባው። ቆይ ባለቤቷን ላናግር አለ። ባለቤቷ ስታየው ተሾመ ከነገስታት ወገን መሰላት። በእርግጥም በወቅቱ ኮፐንሀገን ላይ እንኳን የጣልያን ሱፍ ለብሶ የተጠበሰ ስጋ ከውስኪ ጋር የሚመገብ ቀርቶ መደበኛው ጥቁርም ብዙ አይታይም ነበርና ነው የገረማት። ፈቀደችለት። ተጫወተ። ወደደችው። ከባንዱ ጋር እንዲሰራ ጠየቀችው። ተስማማ ፤ ሰራ።
ከሶስት ወር በኋላ ግን ለሙዚቃ ትምህርት ከኮፐንሀገን ይልቅ ስዊድን እንደምትሻል ሰማና ወደ ስዊድን ተሻገረ። ስዊድን ከሙዚቀኝነቱ ይልቅ የአባቱ ምኞት የነበረውን ትምህርት ብዙ የገፋበት አገር ናት። ለበርካታ አመታት በዚያ ከቆየ በኋላ ወንድሙን ሊጎበኝ ወደ አሜሪካ ሄደ። እዚያ ደግሞ ብዙ ኢትዮጵያውያንን ሲያይ ደስ አለው። ስለዚህም ቀጣይ ኑሮው አሜሪካ መሆን እንዳለበት ወሰነ። አሁንም እዚያው ነው የሚኖረው።
ተሾመ የራሱን ሙዚቃዎች አብዛኛውን ራሱ የጻፋቸው ናቸው። መመሰጥ እና ጊዜ ወስዶ ማሰላሰል ይወዳል። እንዲያውም እናቱ እንዲህ ቁጭ ብሎ ሲያሰላስል ሀዘን የገባው ይመስላቸውና ምን ሆንክ ምን እየሰራህ ነው ብለው ይጠይቁታል። ለምሳሌ ያህል በአንድ ወቅት ይሰራበት ከነበረበት ክለብ ባለቤቶች ጋር አለመስማማት ተፈጥሮ ቤት ቁጭ ብሎ በሚያሰላስልበት ወቅት ይህንኑ ጥያቄ ጠይቀውት እያሰብኩ ነው ሲላቸው ‹‹አይዞህ ሁሉም ነገር መልካም ይሆናል›› ብለው አጽናንተውታል።
ለእናቱ የተሾመ የሀሳብ ምንጭ ስራ አጥነቱ የመሰላቸው ቢሆንም ተሾመ ግን የሚያስበው ሀሳብ ሙዚቃን እና ለሙዚቃ የሚሆነውን ሀሳብ ብቻ ነው። ዛሬም ድረስ የምንወዳቸው ሙዚቃዎቹ የተገኙትም በዚህ መሰል ተመስጦ ነው። በዚህ የሀሳብ መንገድ ከተፈጠሩት ሙዚቃዎች መሀከል አንዱ ‹‹ጋራ ስር ነው ቤትሽ›› ተሾመ ስራ በፈታበት ሰሞን የሚኖርበትን ሰፈር በደንብ ካስተዋለ በኋላ የደረሰው ሙዚቃ ነው። ሙዚቃውን መጀመሪያ ሲደርሰው ቀበና ስር ነው ቤትሽ በሚል ርእስ ነበር። የነተሾመ ሰፈር (ቀበና) ከራስጌ ኮረብታ ያለው ሲሆን ፣ ከስር ደግሞ የቀበና ወንዝ ይፈስበታል። ሙዚቃውም የተሰራው በዚህ መልክአ ምድራዊ እይታ ቀስቃሽነት ነው።
የተሾመ ሙዚቃዎች ዛሬም በአዲሱ ትውልድ እንደ አዲስ የሚዘፈኑ ናቸው። ይህ በእንዲህ እንዳለ የአዲሱ ትውልድ አካል የሆነችው ልጁ ኤሚሊያ ተሾመም ታዋቂ ድምጻዊ ናት። ብዙዎች በአንድ ወቅት ከፍተኛ ተደማጭነት አግኝቶ በነበረው ቢግ ቢግ ወርልድ በተሰኘ ሙዚቃዋ ያውቋታል። በአንድ ወቅት ወደ አገር ቤት መጥታ አያቷን /የተሾመን እናት/ ጎብኝታ ለአባቷ የተወለደበትን ቤት ፎቶ ይዛለት ሄዳለች።
ከሚወድህ ሕዝብ ከተለየህ በኋላ ግማሽ ሰው ነህ የሚለው ተሾመ ኢትዮጵያ አሁንም ልቡ ውስጥ ናት። የአገሩን ናፍቆት የሚወጣው በእኩለ ሌሊት ተነስቶ ፒያኖ በመጫወት እንደሆነም ይገልጻል። በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ለኢትዮጵያ ኪነ ጥበብ እድገት አስተዋጽኦ ያደረጉ ጠቢባንን እውቅና በሰጡበት ወቅት በሙዚቃው ዘርፍ እውቅና ከሰጧቸው ድምጻውያን መካከልም ተሾመ አንዱ ነው።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 9/2014