የኪነ ጥበብ ባለሙያዎቹ በአንድ የቪዲዮ የቀረፃ ሥራ ላይ ድንገት ተገናኙ። ባለሙያዎቹ ከዚያ ቀን በፊት ፈጽሞ አይተዋወቁም፤ ጥበብ ምክንያት ሆና ከያሉበት ጠርታ አገናኘቻቸው። በዚያ ሥራ ላይ ሳሉ የተመለከቱት ጥሩ ያልሆነ ገጠመኝ አንድ ነገር እንዲያስቡ አደረጋቸው። የኪነ ጥበብ ባለሙያ ስሜተ ስስ ነውና ባዩት ነገር ስሜታቸው ተነካ። ቀረፃው የነበረው እኩለ ሌሊት ላይ ነበርና በሴት እህቶች ላይ ከሙያዊ ሥነምግባር ያፈነገጠ ተግባር መቆም እንዳለበት አመኑ።
ያኔ ስለ ኪነጥበቡ እድገትም ስለ ሙያዊ ሥነምግባርም የቆመ ትልቅ ሃሳብ በውስጣቸው ተፀነሰ። እናም ተነጋገሩበት። የኪነጥበብ ባለሙያዎች በተለይ ተዋንያን በችሎታቸውና ባላቸው አቅም ወደ ኢንዱስትሪው እንዲቀላቀሉ ለመርዳት ብሎም ኪነ ጥበብን ጤናማ በሆነ መልኩ ለማሳደግ አለሙ። በዚህም መነሻነት የኪነጥበብ ባለሙያዎቹ አንድ ሙያዊ ማሕበር መሰረቱ። ስያሜውም ‹‹ኢትዮ ሀሌታ›› አሉት።
በሥራቸው እውቅናን ያተረፉ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች እድገትና መነሻቸው ሲጠየቁ አስቀድምው አካባቢያቸው ላይ የነበረ የኪነጥበብ ማሕበር አልያም ክበብ ይጠቅሳሉ። የኪነጥበብ ባለሙያዎችን በማፍራት ብሎም ለቁም ነገር በማብቃት የኪነጥበብ ባለሙያዎች ያህል ባይታወቁም ትልቅ አበርክቶ ያላቸው ክበባት ወይም ማሕበራት በየቦታው አሉ። እነዚህ ማሕበራት ለኪነጥበብ ባለሙያዎቹ መነሻ ወደ ጥበብ ዓለም ለመግባት ዋንኛ ማለፊያዎችም ናቸው።
ከመሰል የሙያ ማሕበራት ውስጥ አንዱ የሆነው ኢትዮ ሀሌታ ከመነሻው እሩቅ አስበውና በተለየ አንድ ዓላማ ለኪነ ጥበቡ እድገት ብሎም ለሙያዊ ሥነምግባር እውን መሆን ባለሙያዎች ተሰባስበው የመሰረቱት የኪነጥበብ ማሕበር ነው። ኢትዮ ሀሌታ በተለያየ ዘርፍ ያሉ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የተሰባሰቡበት በየዘርፋቸውም በንቃት የሚሳተፉበት በተመሰረተ አጭር ጊዜ ውስጥ እጅግ የላቁ እምርታዎችን ማስመዝገብ የቻለ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ስብስብ ማሕበር ነው።
ከሌላ ማሕበራት ለየት ባለ መልኩ የተቋቋመው ኢትዮ ሀሌታ ዘርፈ ብዙ የኪነ ጥበበብ ሙያተኞች የተሰባሰቡበትም ነው። ሁሉንም የኪነ ጥበብ ሙያዎች ባለቤት የሆኑ የኪነጥበብ ባለሙያዎች ሥራዎቻቸውን ይዘው በመቅረብ ከሌሎቹ ጋር ቅንጅት በመፍጠርና በማቅረብ የራሳቸውን ክህሎትና ፈጠራን ያሳድጋሉ፤ ሌሎችንም ለማስተማርና ለመማርም ጥሩ መንገድ ሆኗቸዋል።
ሁለገብ የኪነጥበብ ባለሙያዎችን ይዞ የሚንቀሳቀሰው ኢትዮ ሀሌታ ተዋንያን የቲያትር ባለሙያዎች ደራሲያን፣ የሙዘዚቃ ባለሙያዎችና ድምፃውያን እንዲሁም አማተርና አንጋፋ የኪነጥበብ ባለሙያዎች በመሰባሰብ ስለ ኪነጥበብ እድገትና ሙያዊ ሥነምግባሩ ትክክለኛ ዕድገትና የሚሰሩበት ማሕበር እንደሆነ የማሕበሩ ፀሀፊና ሁነት አስተባባሪ የሆነው አርቲስት መስፍን ኃይሉ ይናገራል።
አንጋፋና ወጣት የኪነጥበብ ባለሙያዎቹ በተለያዩ ጊዜያት እየተገናኙ ሙያዊ የልምድ ልውውጥ ከማድረጋቸው ባለፈ በዚያው በማሕበሩ አባላት የሚዘጋጁ የተለያዩ የኪነ ጥበብ ሥራዎች ለህዝብ በተለያየ መንገድ እንደሚያቀርቡና ይህም ለማሕበሩ አባላት ሙያው ላይ ያላቸውን የተሻለ ግንዛቤ እንዳሰፋው ልምድም እንደቀሰሙ አርቲስት መስፍን ያስረዳል። በተለይ ማሕበሩ በተመሰረተ አጭር ጊዜ ውስጥ ያገኛቸው ስኬቶችን በመጥቀስ የማሕበሩ ጥንካሬ ማሳያ መሆኑን የሚጠቅሰው አርቲስት መስፍን በማሕበሩ ጠንካራ እንቅስቃሴ የአዲስ አበባ መስተዳድር ከንቲባ በነበሩት ኢንጅነር ታከለ ኡማ የዋንጫና የሰርተፍኬት ሽልማት ማግኘቱን ይገልፃል።
የቲያትር፣ ፊልም፣ ሙዚቃ፣ ድርሰትና ሌሎች የጥበብ ሥራዎች በማሕበሩ አባላት እየቀረቡ እርስ በርስ በመማማር ሥራውን በማሳደግና ለሌሎች እንዲደርስ ያደርጋል። እንዲሁም ማሕበሩን እንደ አደዲስ የሚቀላቀሉ አባላትን ሙያዊ ድጋፍ በማድረግ የተለያዩ ሚዲያዎች እና ፊልሞች ላይ መሳተፍ እንዲችሉ እድሎችን የማመቻቸት ሥራንም ይሰራል።
ጅማሮው ላይ 8 አባላት ይዞ የተመሰረተው ኢትዮ ሀሌታ የኪነጥበብ ባለሙያዎች ማህበር ቁጥራቸው ከ200 በላይ የሆኑ የቲያትር፣ የፊልም፣ የሙዚቃና ሌሎች የኪነጥበብ አንጋፋና ወጣት ባለሙያዎች በአባልነት ያቀፈ ማሕበር ነው። ያለ ተጨማሪ ድጋፍ በአባላት መዋጮ ከሚያገኘው ገቢ ብቻ በርካታ ሥራዎችን የሰራው ይህ ማሕበር ከሙያ ማሕበሩ አባላት ሙያዊ እውቀትና ክህሉት የእርስ በርስ መማማርና ልምድ መቅሰም በተጨማሪም ማሕበራዊ ግንኙነታቸው ጠንካራ ይሆን ዘንድ ምክንያት ሆኗቸዋል።
የማሕበሩ ማሕበራዊ ተሳትፎ
የኪነጥበብ ባለሙያዎች ከሙያቸው ባለፈ አገራዊና ማሕበረሰባዊ ጉዳይ ላይ የሚያደርጉት ተሳትፎ የጎላ ነው። የኢትዮ ሀሌታ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ማሕበርም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የማሕበሩ አባላት በማስተባበርና በማሳተፍ የተለያዩ ማሕበራዊ ሃላፊነት በመወጣት ላይ ይገኛሉ። ከሚያደርጉት ልዩ ልዩ ተግባራት ውስጥም የአረጋዊና እና አቅመ ደጋሞች መደገፍ፣ ተማሪዎች በኢኮኖሚ ችግር ከትምህርታቸው እንዳይስተጓጎሉ መርዳትና ልዩ ልዩ መድረኮችን በመፍጠር ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ ይሰራሉ።
በተለይ የማሕበሩ አባላት በአገር አቀፍ ደረጃ በየጊዜው የሚካሄደውን የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር ላይ የላቀ ተሳትፎ በማድረግም ይታወቃል። በተጨማሪም በኮሮና ወረርሽኝ መጀመሪያ ሰሞን በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በመዞር ሕብረተሰቡ ለአደጋ እንዳይጋለጥ የማስተባበርና ስለ ኮሮና ወረርሽኝና የጤና አጠባበቅ ግንዛቤ የመፍጠር ስራንም ሰርቷል። በዚህ ከማሕበረሰቡ እውቅና መቀዳጀት ችሏል።
ማህበሩ የገጠመው ፈተና
በተመሰረተ አጭር ጊዜ ውስጥ ትልልቅ ተግባራትን በመከወንና የማሕበራቱን አቅም በማሳደግ ለኪነጥበቡ ትልቅ አስተዋፅዖ ያበረከተው ኢትዮ ሀሌታ የኪነጥበብ ባለሙያዎች ማሕበር ዛሬ ላይ የአጀማመሩ ያህል ጠንካራ እንቅስቃሴዎች እያደረገ አይደለም።
ለማሕበሩ ሥራዎች መቀዛቀዝ ዋንኛ ምክንያት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝና አገራዊ ሁኔታን የሚጠቅሰው አርቲስት መስፍን፤ ማሕበሩ እንዳሰበው ጠንካራና ብርቱ ሥራዎችን እንዳይሰራ እንቅፋት ፈጥሮበታል። ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መከሰት በፊት የማሕበሩ አባላት በየጊዜው እየተገናኙ አመርቂ ሥራዎችን በመስራት ከጊዜ ወደጊዜ ትልቅ መሻሻል ውስጥ የነበሩ መሆኑን የሚያስታውሰው መስፍን፤ ከዚያ ክስተት በኋላ የማሕበሩ እንቅስቃሴዎች ተዳክመው ቆይተዋል።
የማሕበሩ አባል የሆነው አርቲስት መኮንን ደባልቄ፤ ማሕበሩ በትንሽ ጊዜ እምርታን ያስመዘገበና ብዙ ሥራዎች የሰራ መሆኑን ገልፆ ከኮሮና ወዲህ የታዩ መቀዛቀዞች የማሕበሩ አባላት ያለሙትን እንዳይከውኑ እንዳደረጋቸው ያስረዳል። ማሕበሩ ከልዩ ልዩ ሙያ የተውጣጡ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የተሰባሰቡበት እንደመሆኑ ብዙ የእርስ በርስ መማማርና ክህሎት የማሳደግ አቅም መፍጠሩን የሚያስረዳው አርቲስት መኮንን የማሕበሩ አባላት ተጠቃሚ አድርጎ እደነበር ያስታውሳል። ወደፊት ብዙ ሥራዎች ለመስራት እቅድ እንዳላቸውና አሁንም በተለያየ መንገድ እየተገናኙ ሥራዎችን ወደፊት ለመስራትና እንቅስቃሴዎችን ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ መሆኑንም አስረድቷል።
የማሕበሩ ፕሬዚዳንት አርቲስት ኢሳያስ መለሰ፤ ማሕበሩ ከዚህ ቀደም ጠንካራ የሆኑ ሥራዎችን ሲሰራ እንደቆየና በተፈጠሩ አገራዊና ችግሮችና የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ሥራዎቹ ቢቀዛቀዙም መልሶ በተደራጀ መልኩ ሥራዎችን ለመስራትና የበፊቱን ጥንካሬ በማላበስ ለሥራ እየተዘጋጁ መሆኑን ያስረዳል። በሰራቸው ጠንካራ ሥራዎች እውቅናና ሽልማት ማግኘቱን የሚያስታውሰው አርቲስት ኢሳያስ፤ አባላቱን በማስተባበር የሰራቸው ማሕበራዊ ተሳትፎዎችም እንደ ኪነጥበብ ባለሙያዎች ማሕበርነቱ መልካም ተሞክሮ እደሆነ ገልጿል።
በተለያዩ መገናኛ ብዙኋን የማሕበሩ አባላት በኪነጥበብ ሥራዎቻቸው እየተሳተፉ መሆኑን የሚያስረዳው የማሕበሩ ፕሬዚዳንት አርቲስት ኢሳያስ፤ ማሕበሩ እንደ ኪነጥበብ ማዕከልነቱ የተለያዩ ሥራዎችን ለመስራትና አባላቱን ሥነምግባር በተላበሰና ብቁ የሙያው ባለቤት ይሆኑ ዘንድ ጠንክሮ ለመስራት እንደተዘጋጁና በቅርቡ ይህንን ለማድረግ የሚያስችል ሥራዎች እንደሚጀመር አሳውቋል።
መሰል እንቅስቃሴዎች መቀዛቀዛቸው በኢትዮ ሀሌታ የኪነጥበብ ባለሙዎች ማሕበር ብቻ እንዳልሆነ የሚናገረው አርቲስት መስፍን፤ ለኪነጥበቡ ዘርፍ ልዩ ድጋፍና ትኩረት ካልተሰጠ በምክንያች መብዛት የደበዘዘው ኢንዱስትሪ እድገቱ ላይ እንቅፋት መፈጠሩ አይቀርም በማለት ስጋቱን ይናገራል። በተለይም የሲኒማ ቤቶች ቀድሞ ይሰጡት የነበረው አገልግሎት በነበረበት አለመቀጠሉ፣ በኪነጥበቡ ዘርፍ ይሰሩ የነበሩ አዳዲስ ስራዎች መቀዛቀዛቸውና የአገራችን ሰላም ሁኔታ ስጋት አጠልሽቶበት መቆየቱ ለኪነጥበብ ዘርፍ ሥራዎች ዕድገት ላይ ትልቅ ተፅዕኖ ፈጥሮ ቆይቷል በማለት የማሕበራቸውም ሥራዎች መቀዛቀዝ ምክንያት መሰል ሁኔታዎች መሆኑን ያስረዳል።
በተለይ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝና በአገራዊ ጉዳዮች አለመረጋጋት ለዝቦ የቆየው የኪነጥበብ ዘርፍ እንዲነቃቃ የሚመለከተው አካል በጥናት ለይቶ ልዩ ድጋፍ ሊያደርግ እደሚገባ የሚገልጸው የማህበሩ ፀሀፊና የሁነት አስባባሪ አርቲስት መስፍን፤ ኪነጥበብ ለአገር የሚሰጠውን ከፍተኛ ጠቀሜታ ከግንዛቤ በማስገባት አፋጣኝ ድጋፍ መደረግ እንዳለበት ይጠቁማል።
ማሕበሩ ወደፊት ብዙ እቅዶች እንዳሉት የሚገልፀው መስፍን፤ በአሁኑ ሰዓት ከቀድሞ በተሻለ መልኩ ነገሮች እየተቀየሩ ስለሆነ ወደፊት የበፊቱን አይነት ጠንካራ እንቅስቃሴ ለማድረግ ዝግጅት ላይ መሆናቸውን ተናግሯል። ለሙያው ሥነምግባር መረጋገጥና ለኪነጥበብ እድገት ማሕበሩ ጥረቱን እንደሚቀጥል ያስረዳል። ነገር ግን ለኪነጥበብ ዕድገቱ ወሳኝ የሆነው ትኩረት መንፈግ ሊስተካከልና ድጋፍ ሊደረግ እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥቶ ይገልፃል።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሐሙስ መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም