በዘመናዊው የአማርኛ ሙዚቃ ውስጥ የምርጦቹ ዝርዝር ቢወጣ ከመጀመሪያዎቹ አስር ምርጦች መካከል አንዱ ሊሆን ይችላል። ስሙ በብዙዎች የፍቅር ታሪክ ውስጥ የሚቀመጥ የብዙዎች የወጣትነት ትውስታ አካል የሆኑ ስራዎች የሰራው ድምጸ መረዋው ኤፍሬም ታምሩ። ዛሬ በአጭሩ ስለ እሱ እናወጋለን።
የተወለደው ባህርዳር ከተማ ሲሆን የህይወት ታሪኩ ግን በይበልጥ ከደጀን ከተማ ጋር የተዛመደ ነው። አባቱ አቶ ታምሩ አመራ ሲባሉ እናቱ ደግሞ አትገኝ ብዙነህ ይሰኛሉ። አባቱ የፖስታ ቤት ስራ አስኪያጅ በመሆናቸው የተነሳ አንድ ቦታ ላይ ረግቶ የልጅነት ህይወቱን መግፋት ግን አልሆነለትም። አንደኛ ክፍል ባህር ዳር ከተማረ በኋላ ሁለተኛ ክፍልን የቀጠለው ደብረ ማርቆስ ነበር።
ከዚያም ሶስተኛ ክፍልን የያኔው ሲዳሞ ጠቅላይ ግዛት ዲላ ከተማ ተማረ። አራተኛ ክፍልን ደግሞ ወደ ሰሜን ተመልሶ ወሎ ጠቅላይ ግዛት ተማረ። አምስተኛ ክፍል ወደ መሀል ሀገር ተመልሶ አዲስ አበባ ተማረ። ከዚያ ግን አባቱ ከአመት በፊት በገጠማቸው የመኪና አደጋ ምክንያት ጤናቸው በመታወኩ ጡረታ ወጡ። ስለዚህም ወደ ትውልድ ሀገራቸው ወደ ደጀን ተመለሱ። ከዚያን በኋላ ለቀጣይ ጥቂት አመታት የቆየው ደጀን ውስ ጥ ነው።
የደጀን ህይወቱ ቀላል አልነበረም። ህይወቱን ቀላል ያላደረገው ግን ሌላ ምንም አልነበረም ፤ ብቸኛው ተግዳሮቱ ለሙዚቃ ያለው ፍቅር ነው። በልጅነቱ ገና የተለከፈባት ሙዚቃ እና የሚኖርበት አውድ አብረው አልሄዱም። የሚኖርበት ቤተሰብ ወግ አጥባቂ የሚባል ነው። ዘመኑ ሙዚቀኝነት የማይበረታታበት ነው።
አባቱ አቶ ታምሩ ደግሞ ጭራሽ ሙዚቃ የሚባል ነገርን የማይወዱ የቤተ ክህነት እና የመኳንንት ወገን ናቸው። ልጃቸው ኤፍሬም ግን ከዚህ በተቃራኒ ያለ ነው። እንዲያም ቢሆን ኤፍሬም በተለይ በትምህርት ቤት የስካውት እና የቴአትር ክበባት ውስጥ በንቃት ተሳታፊ ነው። ትምህርት ቤቱ ሜጋፎን የገዛ ጊዜም በርእሰ መምህሩ ትእዛዝ ሜጋፎኑ የተመረቀው በኤፍሬም ታምሩ ሙዚቃ ነበር። በዚህ መልኩ ዝናው ከቤቱ ውጭ የታወቀ ነበር።
አንድ ክረምት ላይ እሱ የሚኖረበት ከተማ ላይ ሙዚቃ ለማቅረብ አንድ ‹‹ባንድ›› ይመጣል። የኤፍሬምን ዝናም ይሰማሉ። የባንዱ መሪ ኤፍሬምን ድምጹን ይሰማል። አብሯቸው መሄድ ይችል እንደሆነም ይጠይቀዋል። ገናየ12 አመት ልጅ የነበረው ኤፍሬም የቤተሰቦቹን ፈቃድ ሳይጠይቅ ባንዱን ተከትሎ እብስ ይላል። ሁለት ወር ሙሉ ከሀገር ሀገር ባንዱን ተከትሎ እየዞረ ከሰራ በኋላ ወደ ቤቱ ተመለሰ።
ዘፈን የሚባል ነገር የማይወዱት አባቱ ጭራሽ በዚህ ተግባሩ አንጀታቸው እርር ብሎ ኖሮ ቤቱ ሲመጣ በደንብ ገረፉት፤ በብረትም ታሰረ። ይህ ሁኔታ ግን ኤፍሬምን ከሙዚቃ አልለየውም። በተቃራኒው በአመቱም ይህን ተግባር ደገመው። ከዚያም ባለፈ በወቅቱ በነበረ የአውራጃ ውድድር ላይ በዘመናዊ ሙዚቃ አሸናፊ በመሆኑ የደብረማርቆስ ‹‹ሀይስኩል ባንድ›› አባል ሆኖ ባንዱ ከሚያገኘው ገቢ 18 በመቶው የሚከፈለው ድምጻዊም ሆነ።
ሁለተኛ ደረጃ ሲገባ፤ ደጀን ከተማ ላይ ሁለተኛ ትምህርት ቤት ባለመኖሩ የሚዘፍንበት ባንድ ወደሚገኝበት ደብረ ማርቆስ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሄደ። ሙዚቃውና ትምህርት ቤቱ ተገናኙለት። ደብረ ማርቆስ እያለ ደግሞ ኮንሰርት ሊያቀርብ የመጣው ዝነኛው አያሌው መስፍን መጣ። አያሌውም የኤፍሬምን ተሰጥኦ አይቶ እንዲሁ አላለፈም። ከአያሌው ጋር የሙዚቃ ጉዞውን ለ5 ወራት ቀጠለ። ከዚያም ከአያሌው ጋር የነበረው ጉዞ ሲጠናቀቅ ወደ አዲስ አበባ መጣ። ምስራቅ አጠቃላይ ትምህርት ቤት ውስጥም ገባ። ከአያሌው መስፍን ጋር ይሰሩ ከነበሩ ሙዚቀኞች ጋር በመሆንም ዛምቤዚ የሚባል ክለብ መስራት ጀመረ።
ዛምቤዚ ከመግባቱ በፊት ግን አንድ ፈተና ያስፈልገው ነበር። ፈታኙ ደግሞ አንጋፋው አሊ ቢራ ነበር። ተፈተነ። አለፈ። በቀን ሦስት ብር ደሞዝም ተቆረጠለት። ከባንዱ ጋር ሆኖም ቬነስ ክለብ ፤ ሆቴል ዲ አፍሪክ፤ ጊዮን ሆቴል፤ ሂልተን ሆቴል፤ ራስ ሆቴል እና ሌሎች ቦታዎችም መዝፈኑን ቀጠለ። የመጀመሪያ ሙዚቃውም ገና ልጅ ነኝ ጋሜ በሚል ርእስ አወጣ። ዝነኛ የሆነበት ሙዚቃ ግን ነይልኝ ነበር። ነይልኝ ኤፍሬምን እና የኢትዮጵያ ህዝብን አስተዋወቀች። ሙዚቃውን የሰሩለት ይልማ ገብረአብ ነበሩ። ታዋቂ ከሆነበት ነይልኝ አንስቶ እስከ አሁንም በአስራዎቹ የሚቆጠሩ ከፍተኛ ተወዳጅነት ያተረፉ አልበሞችን አውጥቷል።
ኤፍሬም ከሙዚቃው በተጨማሪ በቁጥብ ህይወቱ የሚታወቅ ሲሆን አንዳንዶች እንዲያውም ከዘፋኝ ኩሩ ኤፍሬም ታምሩ የሚል ግጥም ገጥመነውበታል። ይሁንና እሱ ኩሩነቱ አንዳንዶች እንደሚሉት አይደለም ይላል። በአንድ ወቅት ከጋዜጠኛ ሰይፉ ፋንታሁን ጋር በነበረው ቆይታ እንዲህ ብሎ መልሶ ነበር። ‹‹ኩሩ ነኝ እንጂ ጉረኛ አይደለሁም፤ ቁጥብ ሰው ነኝ፤ ሰውን አከብራለሁ ነገር ግን ሰው መስመር እንዲያልፍ አልፈቅድም›› ብሏል። የቅርቡ ሰዎች ኤፍሬም ተጫዋች እና ተግባቢ ሰው እንደሆነ ይናገራሉ።
ኤፍሬም ከሚጠቀስባቸው ሁለት ታሪኮችን እዚህ ጋር እናንሳ። አንደኛው መድረክ ላይ የአንገት ሀብል የመለሰበት ነው። ነገሩ እንደዚህ ነው። ኤፍሬም በአንድ የሀይስኩል ምርቃት ላይ ሙዚቃውን ሊያቀርብ ነው። ከተመራቂዎቹ መሀከል ደግሞ አንዷ ከሱ ጋር ቅርርብ ነበራት። ነገር ግን በኢኮኖሚ ረገድ አነስ ካለ ቤተሰብ የተገኘች ልጅ ናት። ለኤፍሬም በጎ ስሜት አላት። ሌላኛዋ ደግሞ በኢኮኖሚ ሻል ካለ ቤተሰብ የተገኘች ልጅ ናት።
እናም ይህቺኛዋ ለኤፍሬም መድረክ ላይ የወርቅ ሀብል ልትሰጥ እና የኤፍሬም ወዳጅ የሆነችውን ጓደኛዋን ልታበሳጭ ብሎም ኤፍሬምን ልትቀማት ፈለገች። የኤፍሬም ወዳጅም ጓደኛዋ እንዲህ ያለ እቅድ እንደያዘች ትነግረዋለች። የተባለው አልቀረም መድረክ ላይ የባለጸጎቹ ልጅ መጥታ አንገቱ ላይ ወርቁን አጥልቃለት ሄደች። ከወረደች በኋላ ሁለቱ ጓደኛማቾች መጨቃጨቅ ያዙ። ሸላሚዋ ጓደኛዋን የድሀ ልጅ ስትል ኤፍሬም ጆሮ ውስጥ ጥልቅ አለ። ኤፍሬም ተበሳጨ። መድረክ ላይ ሸላሚዋን ጠርቶም ወርቁን መለሰላት። እስከዛሬም ነገሩ እንደ አፈታሪክ ሆኖ ይነገራል።
ሌላኛው ታሪክ ከኤፍሬም ተወዳጅ ሙዚቃዎች አንዱ የሆነው ጎዳናዬ አሰራር ነው። በዚያን ወቅት ዝነኛ ድምጻውያን ተሰብስበው በድርቅ የተጎዱ ኢትዮጵያውያንን ለማገዝ የሚውል የብሩህ ተስፋ እሸት የተሰኘ አልበም እንዲሰሩ መንግስት አዝዞ ነበር። ከነዚያ መሀከል አንዱ ኤፍሬም ነው። ነገር ግን መዚቃው ሳይሰራ በመቆየቱ ሹማምንት ዝነኞቹን አበበ መለሰ እና ይልማ ገብረአብን ጠርተው ማሳሰቢያ ሰጡ።
እነሱም ሰርተነዋል ኤፍሬም ሀገር ውስጥ ስለሌለ ነው አሉ። በተጨባጭ ግን ስራው አልተጀመረም ነበር። ኤፍሬም ሲመጣ በል ና ብለው በአስቸኳይ በአንድ ሌሊት አዲስ ሙዚቃ ማዋለድ ያዙ። ጠዋትም ጎዳናዬ ተሰርቶ አልቆ ለሳንሱር ቢሮ ደረሰ። ከአልበሙ ተወዳጅ ሙዚቃዎች አንዱ ሆነ።
ለበርካታ አስርት አመታት በአሜሪካ የኖረው ኤፍሬም ቤዛዊት ኤፍሬም የተባለች ልጅ ያለችው ሲሆን ኑሮውን በአብዛኛው በአሜሪካ ነው። የእረፍት ቀኑን በተመለከተ ሲናገር ‹‹ማንበብ ፤ ሙዚቃ ማድመጥ፤
እግር ኳስ ማየት፤ እወዳለሁ። ቀንደኛ የባርሳ እና ማንችስተር ሲቲ ደጋፊ ነኝ›› ይላል። ለአትሌቲክስ ስፖርት ያለው ፍቅርም እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ይናገራል። ሳቅ ወዳዱ ኤፍሬም የተዋናይ መኮንን ላእከም አድናቂ ነው። በሚዲያ ብዙም መታየት የማይወደው ኤፍሬም በአዲስ አልበም በቅርቡ እንደሚከሰት ተስፋ እናደርጋለን።
አቤል ገብረኪዳን
አዲስ ዘመን ታኅሳስ 24/2014