የእስራኤል አገራዊ ምርጫ ሊካሄድ የአምስት ሳምንታት እድሜ ብቻ ቀርተውታል። በአሁኑ ወቅትም የምርጫው ተፋላሚዎች በይፋ ታውቀዋል። ቀጣዩ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርም ቤኒያሚን ኔታኒያሁ አሊያም ቤን ጋንቴዝ መሆናቸው እርግጥ ሆኗል። ከሁሉም በላይ የዘንድሮው ምርጫ ፍልሚያው ያለ ጥርጥር በታሪክ ከታዩት የተለየና ከባዱ እንደሚሆንም ዘገባዎች እያመለከቱ ናቸው።
ለዚህም ዋናው ምክንያት የፕሬዚዳንቱ ዋና ተቀናቃኝ የሚባሉት የቀድሞው የአገሪቱ ወታደራዊ ሃይል አዛዥ ቤን ጋንቴዝና የቀድሞው የፋይናንስ ሚኒስትር ያኢር ላፒድ በጋራ ተዋህደው ለመስራት መወሰናቸው ሆኖ ተገኝቷል።
ሁለቱ ፓርቲዎች በእስራኤል ብሄራዊ ሰንደቅ አላማ ሰማያዊና ነጭ የሚል መጣማርም የጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁና የቀኝ ዘመም ፓርቲያቸው (ሊኩድ) የአስርት ዓመታት የስልጣን ጉዞ ሊቋጨው እንደሚችል የሚተነብዩም ተበራክተዋል። የቢቢሲው ፖለቲካ ጉዳዮች ትንታኝ ቶም ቤትማንን ጨምሮ ሌሎችም የፖለቲካ ጉዳይ ትንታኞች፤ያለ ጥርጥር በታሪክ ከታዩት የተለየና ከባዱ ሲሉ በሚገልፁት የዘንድሮ ምርጫም የእስራኤል እጣ ፈንታ በሁለት የተለያየ ርዮተ ዓለም አቀንቃኝ ፖለቲከኞች ጫንቃ ላይ ወድቋል።
እኤአ በ1996 በአርባ ሰባት ዓመታቸው የመሪነቱን ስልጣን የያዙት ኔታንያሁ ከአራት ዓመታት በኋላ ስልጣናቸውን ለኤሁድ ባራክ ማስረከባቸው ይታወቃል። ኔታንያሁ ከአስር ዓመታት ቆይታ በኋላም እኤአ በ29 ለሁለተኛ ጊዜ የአገሪቱ መሪ በመሆን ያለፉትን አስራ ሶስት ዓመታት በስልጣን ላይ ቆይተዋል። በአገሪቱ የፖለቲካ ታሪክ በፍልስጤምና በኢራን ላይ ባላቸው ጠንካራ አቋም የሚታወቁት የስልሳ ዘጠኝ ዓመቱ ኔታኒያሁ፤ በአገራቸው የፖለቲካ በተለይም በደኅንነት ጉዳይ እጅ አይሰጡም። ለኢራንና ለፍልስጤም ያላቸው አይበገሬነት፣ ተጠራጣሪነትና ግትር አቋምም ከፖለቲካ ተቀናቃኞቻቸው ለየት ያደርጋቸዋል።
አገርን መምራት የሚለካው የአገርን ሉዓላዊነትና ደኅንነት በማስጠበቅ መሆኑን አጥብቀው የሚያምኑትኔታንያሁ፤ ይህ አቋማቸውም ከአረብ አገራት ጋር ሆድና ጀርባ ሆነው ዓመታትን እንዲዘልቁ አድርጓቸዋል። ተቀናቃኛቸው ግን ከዚህ የተለየ አቋም ነው ያላቸው። ቤን ጋንቴዝ እስራኤልን ከሀገሮች ጋር ማገናኘትና ልዩነቶችን በማጥበብ አብረው በመስራት በቀጣናው ያለውን ውጥረት ለማርገብ የፀና አቋም አላቸው።
ቤን ጋንቴዝ የፓርቲ ውህደት በይፋ ካሄዱ በኋላ፤ ለደጋፊዎቻቸው ባደረጉት ንግግር ይህን አጀንዳ እንደሚያቀነቅኑ አረጋግጠዋል። «በጠቅላይ ሚኒስትሩ አደገኛ የፖለቲካ ቁማር አጣብቂኝ ውስጥ የገባችውን አገራችንን የነገ እጣ ፈንታ ለመወሰን ተባብረን ልንሰራ ይገባል፤ ከልዩነት ይልቅ አንድነት፤ ብሄርተኛ ከመሆን ይልቅ አሳታፊነትን ብሄራዊ አንድነትን መምረጥ አለብን›› ሲሉም ተደምጠዋል። ይህም ሰውየው በአረቡ አገራት በኩል የሚከተሉት ለዘብተኛ አቋም የአብዛኞቹ ድጋፍ እንደሚቸራቸው ማረጋገጫን ሰጥቷል። ተጣማሪያቸው ላፒድም በሰውየው አቋምና አቅም ተማምነው ህብረት መፍጠራቸውን በመግለፅ፤ ፓርቲያችው አገሪቱን መምራት እንደሚችል አረጋግጠዋል።
በፓርቲዎቹ የጥምረት ስምምነት መሰረትም አብላጫውን ድምፅ አግኝተው ስልጣን ከተረከቡ እየተፈራራቁ ለማስተዳደር ወጥነዋል። በዚህም መሰረት ጋንቴዝ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ቦታ ከተረከቡ የመጀመሪያውን ሁለት ዓመት ከግማሽ በስልጣን ላይ የሚቆዩ ሲሆን፣ ከዚያም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ለሚጠብቋቸው ላፒድ ስልጣኑን የሚያስርክቡም ይሆናል። ኔታኒያሁ በአንፃሩ መቶ ሃያ መቀመጫዎች ባሉት የአገሪቱ ፓርላማ የሰማያዊና የነጭ ፓርቲው አብላጫውን ድምፅ እንዲያገኝና ፓርቲው በፓርላማው አብላጫውን ወንበር እንዲቆናጣጥ፤ ጠንካራ አጣማሪዎችን ከማሰናዳት አንስቶ አማራጮችን ከማስፋትና ከመቀመር አልቦዘኑም።
በግብፅና በአገራቸው ድንበር መካከል ስደተኞችን ለመቆጣጣር የግንብ አጥር ለመገንባት፣ የስራ እድል ለመከፈት፤ ከአረቡ ዓለም ጋር አዲስ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለመፍጠር፤ የኢራን የኒውክሌር ስምምነትና የእየሩሳሌምን የእስራሌን ዋና መዲናነት ለማስጠበቅ እንደሚሰሩም ሲናገሩ ተደምጠዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ማድረጋቸው በስልጣን ለመቆየት ያላቸውን እድል በእጅጉ የሚያሰፋው ቢሆንም፣ ሰውየው የተጠረጠሩባቸው የሙስናወንጀሎች በተለይ የቀኝ ዘመሙ ፓርቲ ደጋፊዎች ወደ ጋንታዝ ፊታቸውን እንዲያዞሩ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ታምኖበታል። የአሾሼትድ ፕሬሱ ጆሴፍ ፌዴርማን ግን ከሁሉም በላይ የፓርቲዎቹ ጥምረት ለአስርት ዓመታት ለቆየው የኔታኒሁ አስተዳደር ድንገተኛ እጅግ በጣም አስደንጋጭ ነው ብሏል።
ኔታኒያሁ፤ ጥንካራ ጎናቸውን እያነሱ በማወደስ የህዝብ ድምፅ ለማግኘት ቢጥሩም፤ ተቀናቃኛቸው በአንፃሩ የኔታኒያሁን ጠንካራ ሃይማኖታዊነትና ብሄርተኝነት በድክመትነት እንደሚጠቀሙበትም ይገልጻል። በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሙስና ጋር ተያይዞ እየተጠረጠሩ መሆናቸው በምርጫ ቅስቀሳቸው ላይ ከባድ ፈተና ይጋርጣል ብሏል። በእርግጥ በአሁኑ ወቅት ኔታኒያሁ እንዲሸነፉ የአብዛኛው የዓለም ህብረተሰብ በተለይ ደግሞ እንደ አሜሪካ ያሉ ሀያል ሀገራት ፍላጎትም ሆነ ምኞት አይደለም። አንዳንዶች በአንጻሩ ምንም ፓርቲ ይምጣ ማን ሰውየውን ከመንበራቸው የሚገፈትራቸው እንደማይኖር ማስተጋባት ጀምረዋል።
በዚህ ረገድ የባር ላን ዩኒቨርሲቱ የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሰሩ ሻሙል ሳንድለር ቻናል ኒውስ ኤሲያ በሰጡት አስተያየትም ‹‹ለአስራ ሶስት ዓመታት በስልጣን የቆዩትና ፖለቲካዊ እውቀታቸው ምጡቅ መሆኑ የሚመሰክረላቸው ኔታኒያሁ አሁንም የህዝቡ ምርጫ ስለመሆናቸው አትጠራጠሩ ብለዋል። ምንም እንኳን ገና ከወዲሁ አሸናፊውን መተንበይ አስቸጋሪ ቢሆንም በየኔታኒያሁ አሸናፊነት ላይ ጥርጣሬ የሌላቸው የመኖራቸውን ያህል፣ ጀርባ ሰጥተው የቆሙትም ጥቂት የሚባሉ እንደማይሆኑ የሚሞግቱም በርክተዋል።
ከሁሉም በላይ የዘንድሮውን ምርጫ የሚለየው የየፍላጎታቸውን ስልጣን ለማስያዝ የሚፈልጉ አገራት ጫና ምን ሊሆን ይችላል የሚለውን በቅጡ የሚመልስ አለመታየቱ ነው። እንዲያም ሆኖ ግን የኔታኒያሁ ወዳጅ እንደሆነች የሚነገርላት አሜሪካ በምርጫው እጇን ልታስገባ ትችላለች የሚለው ግምት ጎልቶ መደመጥ ጀምሯል። የዋሽንግተን ኤግዛማይነሩ ቶም ሮጋን ዋሽንግተን በመካከለኛው ምስራቅ ቀጠና ለወጠነቸው እቅድ ስኬታማነት የእስራሌን ሚና እጅጉን የገዘፈ መሆኑን በመጥቀስ፣ ይህም በኔታኒያሁ የስልጣን እጣ ፈንታ ላይ ወሳኝ እንደሆነ ይጠቁማል። ጉዳዩን በዚህ የእይታ መነፅር ለሚመለከቱም በእርግጥም ዋሽንግተን በምርጫው እጇን ልታስገባ ትችላለች ወደሚለው ሚዛን እንዲያጋድሉ ሊያስግድዳቸው እንደሚችል ተመላክቷል። ይህም ሁኔታ ከህዝብ በላይ በአንድ አገር መሪ ምርጫ እጣ ፈንታ ላይ የሚወስኑ የሳይበር ጥቃት ፈፃሚዎች መልካም አጋጣሚ እንደሆነ በመጥቀስ፣ በእስራኤል ምርጫ እጁን የሚያስገባ ማንም አይኖርም ብሎ መተማመን ከንቱ መሆኑን የሚጠቁሙም አሉ።
ለዚህም የአገሪቱ መንግስትና ማዕከላዊ የምርጫ ኮሚቴ የሂደቱን ደህንነት ለመጠበቅ ተግተው እንዲሰሩ የሚጠየቁ ባለሙያዎች ቁጥርን እንዲበራክቱ አድርጎል። ወቀሳው በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ይመለከታታል የተባለችው ዋሽንግተን በአንፃሩ ይህ ፈፀሞ ለጥርጥር መቅረብ እንደሌለበት አስታውቃለች። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማይክ ፖምፒዮምም አገራቸው በእስራኤል የምርጫ ሂደት ጣልቃ እንደማትገባና የህዝብ ውሳኔም ለሁሉም መልስ እንደሚሰጥ አስገንዝበዋል። አገራቸው ከውጤት በኋላም ከአሸናፊው መሪ ጋር የሁለቱን አገራት ህዝብ ጥቅም ለማስጠበቅ እንደምትሰራ ለሲኤን ኤኑ ጄክ ታፐር ተናግረዋል።
በመገናኛ ብዙሃንም ሆነ በፖለቲካ ጉዳይ ትንታኞች፤ የሚያዝያው የእስራኤል ምርጫ ሲነሳ ከሁሉም በላይ ለጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ ፈተና ሆኖ እንደሚደቀንና ምናልባትም በአሸናፊነታቸው ላይ ሳንካ ሊፈጥር እንደሚችል የተገመተው ስማቸው ከሙስና ወንጀል ጋር ክፉኛ በመጣመሩ ነው። በአሁኑ ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሶስት የሙስና ወንጀሎች የተጠረጠሩ ሲሆን፤ ያለፉትን ሁለት ዓመታትም የተለያዩ ምርምራዎች ሲካሄድባቸው ቆይቷል። ምንም እንኳን በተጠረጠሩበት ወንጀል ተጨባጭ ማስረጃ ማግኘት ባይቻልም፤ ፍንጮች ስለመኖራቸው ግን የሚናገሩም አልጠፉም።
ኔታኒያሁ ከደሙ ንፁህ ስለመሆናቸው በመግለፅ ወንጀላውም መሰረተ ቢስና ስልጣናቸውን ለመገዳዳር የተጠነሰሰ ሴራ እንደሆነ እያስገነዘቡ ናቸው። መገናኛ ብዙሃንና የፖለቲካ ተንታኞች በአንፃሩ፤ የምርጫውን ውጤት የመወሰን እቅሙ የገዘፈው ይህ የሙስና ጉዳይም ሀሰትነቱ ከተረጋገጠም የጠቅላይ ሚኒስትሩን አሸናፊነት ከግማሽ በላይ እንደሚጨምረው አትጠራጠሩ ብለዋል።
ይህ እውን ሆኖ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የምርጫ ፈተናቸውን ተሻግረው በስልጣን መቆየት ከቻሉ ግን አዲስ ታሪክ መፃፍ ይችላሉ። ከቀድሞው ዴቪድ ቤን ጉሪዮን በላይ በታሪክ የመጀመሪያና ብቸኛው እስራኤልን ለረጅም ዓመታት የመሩ ጠቅላይ ሚኒስትር የሚለውን ክብር መቀዳጃት ይቻላቸዋል።
አዲስ ዘመን የካቲት 26/2011
በታምራት ተስፋዬ