የአፍሪካ የፋሽን ኢንዱስትሪ እያደገ ያለ ዘርፍ ነው። ፈጣን የህዝብ ቁጥር እድገት እየታየባት እና በወጣቶች እየተሞላች ያለችው አፍሪካ፣ ለፋሽን ኢንዱስትሪው ከየትኛውም አህጉር በላይ የተመቸች ናት። በአህጉሪቱ መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ ዜጎች እየጨመሩ ያለበት ሁኔታም ሌላው ለኢንዱስትሪው እድገት ትልቅ ፋይዳ ያለው ነው።
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2020 የአፍሪካ ህዝብ ብዛት ከ1 ነጥብ 3 ቢሊየን ዘሏል፤ ይህ አሀዝ የህዝብ ብዛቱ በዓመት በ2 ነጥብ 5 በመቶ የሚያሻቅብ ነው። አንዲት አፍሪካዊት እናት በአማካይ 4 ነጥበ 7 ልጆች የምትወልድ ሲሆን፣ በአህጉሪቱ እየቀነሰ የመጣው ከወሊድ ጋር የተያያዘ የሚከሰት የህጻናትም ሆነ የእናቶች ሞት የህዝብ ቁጥሩ እድገት እንደሚቀጥል ያመላክታል።
ከጠቅላላው የአህጉሪቱ ህዝብ ከ60 በመቶ በላይ የሚሆነው እድሜው ከ25 ዓመት በታች መሆኑም ለኢንዱስትሪው ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል።
እነዚህ ቁጥሮች ሲገጣጠሙ የሚመጣው ትርጉም በወጣቶች የተሞላችው አህጉር በፋሽን እና ጨርቃጨርቅ በኩል ቀጣይ ጊዜዋ ብሩህ እንደሚሆን የሚያመላክት ቢሆንም፣ ፈተናዎችም የተጋረጡበት ነው። በተለይ የልባሽ ጨርቆች በገፍ ወደ አህጉሪቱ መግባት ለፋሽን ኢንዱስትሪው አሳሳቢ ሁኔታን ጋርጧል።
የአፍሪካ እድገት እና የገበያ እድል (አጎአ) ገጸ ድር ‘Global business of secondhand clothes thrive in Africa’ በሚል ርዕስ ባወጣው ጽሁፍ ልባሽ ጨርቆች ገበያ እንዴት የአፍሪካን የጨርቃጨርቅ እና ፋሽን ዘርፍ እየጎዳ እንደሆነ አትቷል።
እስከ ፈረንጆቹ 1980 ድረስ የአፍሪካ ሀገራት በከፍተኛ ታሪፍ ከውጭ የሚገቡ ልብሶችን እየተቆጣጠሩ ሀገር በቀል አልባሳትን ያሳድጉ እንደነበረ መረጃው አስታውሶ፣ ከዚያ በኋላ ግን በነጻ ገበያ ስም ብዙዎቹ በዓለም ባንክ እና ሌሎች አበዳሪ ተቋማት በደረሰባቸው ጫና ገበያቸውን እንዲከፍቱ ተገደዋል ይላል። ይህ ሁኔታም በርካታ የአፍሪካ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ፉክክሩ እየከበዳቸው የከሰሙ ሲሆን፣ ሁኔታው የፋሽን ዘርፉ በፍጥነት እንዳይመነደግ አድርጓል።
ጽሁፉ እንዳብራራው፣ የአፍሪካ ሀገራት በአውሮፓ እና አሜሪካ ጥቅም ላይ ውለው ከዚያ ለበጎ አድራጎት የተሰጡ አልባሳትን በገፍ ይገዛሉ። ለምሳሌ ያህል ጎረቤታችን ኬንያ በዓመት እስክ 100ሺ ቶን የሚደርስ ልባሽ ጨርቆችን ታስገባለች። ሌሎችም እንደዚሁ ያደርጋሉ። ብዙዎቹ መንግስታት ከዚህ ንግድ በቀረጥ በኩል ገቢ የሚያገኙ ቢሆንም፣ ይህ ቀረጥ የሚያስገኘው ገቢ ግን ከስራ ውጪ እየሆኑ ከሚገኙት የጨርቃጨርቅ እና ፋሽን ኢንዱስትሪዎች አንጻር ሲታይ ኢምንት ነው ።
በተቃራኒው በምዕራቡ ሀገራት እነዚህን ያገለገሉ አልባሳት በእርዳታ መልክ የሚቀበሉ የእርዳታ ድርጅቶች የተወሰነውን ብቻ አስቀርተው ሌላውን በኪሎ እስከ 90 የአሜሪካ ሳንቲም በሚደርስ እየሸጡ ወደ አፍሪካ ሀገራት ይልካሉ። በኪሎ 90 ሳንቲም የተሸጠው ልብስ ከነጋዴ ነጋዴ፤ ከአስመጪና ላኪ እስከ አከፋፋይ ቅብብሎሽ እየተደረገበት ቆይቶ ሁሉም የቻሉትን ያህል ትርፍ ከሰበሰቡበት በኋላ መንግስታትም ቀረጥ ቀርጠውበት በአፍሪካ ጎዳናዎች ይቸረቸራል።
እንዲያም ሆኖ እነዚህ ልባሽ ጨርቆች በአፍሪካ ጎዳናዎች ለገበያ ሲቀርቡ ዋጋቸው ርካሽ በመሆናቸው በብዛት ይቸበቸባሉ። ኤስኤልኤ /SLA/ የተባለ የፋሽን ድረ ገጽ በአፍሪካ የፋሽን ኢንዱስትሪ ላይ መዋዕለ ነዋይን የማፍሰሻው ጊዜ አሁን ነው /Its time to Invest in the African Fashion Industry/ በሚል ርዕስ ባሰፈረው ጽሁፍ ላይ አስተያየቷን የሰጠችው ዩጋንዳዊቷ የፋሽን ዲዛይነር ሲልቪያ ኦዎሪ ከልባሽ ጨርቆች ገበያ ጋር መፎካከር ከባድ መሆኑን አስታውቃለች።
”ከሀገራችን ህዝብ 90 በመቶው የሚለብሰው ልባሽ ጨርቆችን ነው፤ ታዲያ እንዴት አድርገን ከዚህ ጋር መፎካከር እንችላለን?” ስትልም ትጠይቃለች።
መረጃዎች አንደሚጠቁሙት፤ ይህን ያልተመጣጠነ ፉክክር ለመግራት እና ሀገር በቀል የአልባሳት ምርቶችን ለማሳደግ አንዳንድ መንግስታት ሙከራ አድርገው ነበር። ለምሳሌ ያህል የሩዋንዳ መንግስት ልባሽ ጨርቆች ወደ ሀገሪቱ እንዳይገቡ በማገዱ ከአሜሪካ ጋር መፋጠጥ ውስጥ ገብቶ ነበር። በውሳኔው ያልተደሰተችው ዋሽንግተን ሩዋንዳን ከአጎአ ተጠቃሚነት እንድትታገድ አድርጋለች።
የአፍሪካ የጥጥ እና ጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ፌዴሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ራጂቭ አሮራ እንደሚሉት፤ ከ1990 ዎቹ ጀምሮ በኬንያ 85 በመቶ የጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች ተዘግተዋል። በሌላ መልኩ ፋብሪካቸውን የዘጉት የአፍሪካ ሀገራት ለምዕራቡ አለም ፋብሪካዎች ዋነኛ የጥጥ እና ሌሎች ጥሬ እቃዎች ማቅረባቸውን ቀጥለዋል። በምላሹ ደግሞ በብዙ ሺ ኮንቴነሮች ልባሽ ጨርቆችን እየሸመቱ ወደ ሀገራቸው ያስገባሉ።
በሌላ መልኩ መልከ መልካሞቹ የአፍሪካ ሴት እና ወንድ ልጆች በአሜሪካ እና አውሮፓ የፋሽን ትርኢቶች ላይ በሞዴልነት ደምቀው ቢታዩም፣ የሚለብሱት ግን አፍሪካውያን ወንድም እና እህቶቻቸው የሰሩትን ሳይሆን፣ በምዕራባውያን ዲዛይነሮች የተሰራውን ነው።
ያሉት ጥቂት ዲዛይነሮች በበኩላቸው የዓለምአቀፉን የፋሽን ኢንዱስትሪ ገበያ ሰብረው ለመግባት ጥረት እያደረጉ ነው። ከነዚህ ታጋዮች መካከል ደግሞ አንዷ የኛዋ ቤተልሄም አለሙ ናት። የሶል ሬብልስ ኩባንያ ባለቤቷ ቤተልሄም ለኤስ ኤል ኤ /SLA/ በሰጠችው አስተያየት “አሁን ዓለምአቀፉ ገበያ ተነቃቅቷል። የባለቤቶቹ እውነተኛ እና ፈጠራ የታከለባቸው ሀሳቦች በፋሽኞች ውስጥ ማየት ይፈለጋል” ትላለች። እንደ ቤተልሄም አባባል ከሆነ ተጠቃሚው በአፍሪካውያን አእምሮ እና እጆች የተሰሩ ልብሶችን እንጂ በአውሮፓ፤ አሜሪካ እና ቻይና ፋብሪካዎች የተሰሩ የአፍሪካን የሚመስሉ አልባሳትን መፈለግ እየተወ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አሁን ባለው ሁኔታ የአውሮፓ እና አሜሪካ ዲዛይነሮች ከአፍሪካውያን ዲዛይነሮችን ይወስዳሉ፤ አንዳንዴም ይሰርቃሉ። አፍሪካውያኑ ሀሳባቸው ሳይዘረፍ በተግባር ላይ እንዳያውሉት ደግሞ የአቅም ማነስ አለባቸው።
የጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎቿን በምትዘጋ እና ልባሽ ጨርቆችን /ሰልቫጅ/ በምትሸምት አህጉር የራስን ምርት ዲዛይን አድርጎ በራስ ፋብሪካ ለማምረት ይከብዳል። ስለዚህም የመንግስትን ድጋፍ ያስፈልጋል። ከሚፈለጉት ድጋፎች መካከል ደግሞ አንዱ እና ዋነኛው መንግስት የልባሽ ጨርቆች ገበያውን ያዝ ማድረግ ነው።
ለምሳሌ ያህልም የአፍሪካ ልማት ባንክ ሪፖርት እንደሚያሳየው፤ የሩዋንዳ መንግስት የሀገር ውስጥ ጨርቃጨርቅ ምርቶችን እና የፋሽን ኢንዱስትሪውን ለማሳደግ ፋውንዴሽን አቋቁሟል። ሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ተመሳሳይ እርምጃ መውሰድ አለባቸው። በዚህ መልኩ አፍሪካውያን የራሳቸውን ዲዛይነሮች፤ ሰፊዎች እና ነጋዴዎች ማበረታታት ይችላሉ። በእዚህ እርምጃ ውጤት ለማምጣት ደግሞ ጊዜው አሁን ነው።
ዩሮሞኒተር ኢንተርናሽናል የተባለ ተቋም እንዳሳወቀው፤ አፍሪካውያን ለአልባሳት እና ጫማዎች የሚያወጡት ወጪ 31 ቢሊየን ዶላር ገደማ ይደርሳል። ይህ ገበያ ደግሞ እየሰፋ እና እየጠነከረ የሚሄድ ነው። አፍሪካውያን ይህን ገበያ እንዲቆጣጠሩት ማድረግ ያስፈልጋል።
የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪው በዚህ መልኩ ከሰራ በሺ ለሚቆጠሩ ወጣቶችም የስራ እድል ይፈጥራል። ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈም የጨርቃጨርቅ እና ፋሽን ኢንዱስትሪው ማደግ ማህበራዊ ፋይዳም አለው። በፋሽን ውስጥ ዓለም ስለ አፍሪካውያን ያለውን የተዛባ አመለካከት ማስተካከልም ይቻላል። በተጨማሪም ከአውሮፓ እና አሜሪካ በሚጎርፉ ልባሽ ጨርቆች ውስጥ የሚሰራጨውን የነጭ የበላይነት አመለካከት ለመግራትም አፍሪካዊ ፋሽን እና አለባበስን ማዳበር ወሳኝ ነው።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 29/2014