የካፍቴሪያው ደንበኞች ቦታ ቦታቸውን ይዘው ጉዳያቸውን እየከወኑ ነው። ጠረጴዛውም የተለያየ ባለጉዳይ አለበት። አንዱ ጠረጴዛ አብሮ ንግድ ስለመሥራት የሚያወሩ፤ አንዱ ደግሞ ፍቅረኛሞች በስስት እየተያዩ ስለሚጋቡበት የትዳር ሕይወት ይማከሩበታል። አለፍ ሲባልም በጦፈ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ስለትላንት ታሪክ አውጥተው የሚጥሉ ወጣቶች ተሰይመዋል። ሁሉም እንደየጉዳዩ በሃሳብ ፈረስ ተሟል። የቤቱ ባለቤት በጡረታ እድሜ ላይ የሚገኙት አባት በተለመደችው ቦታቸው ላይ ብቻቸውን ተቀምጠው የታሪክ መጽሐፍ እያነበቡ ናቸው።
የታሪክ መምህር የነበሩ ጡረተኛው አባትም የዘውትር ተግባራቸውን እየከወኑ ናቸው። ልጆቻቸው አዋጥተው ሥራ ያስጀመሯት ካፍቴሪያ ለእርሳቸው እንደ ቢሮም ሆና ታገለግላለች። ለጽሁፍ ሥራቸው ወደ ቢሯቸው ሲገቡ ለደቂቃዎች ያህል በትኩረት የሚመለከቷቸው ሁለት ካርታዎች አሉ። የዓለም ካርታና የኢትዮጵያ ካርታ። ካርታውን ተመልክተው ወደ ኋላ ሄደው ከታሪክ ትምህርታቸው ያገኙትን እውቀት ተጠቅመው አገራቱን መርምረው፤ ከአሁናዊ ሁናቴ ጋር አስታርቀው እለታዊ ጽሁፋቸውን ይጀምራሉ። በታሪክ የሚሠራ ታሪክን ፍለጋው ካደረገ የብዕር ሥራቸው።
“ታሪክ” የሚለው ቃል ሁለት ጊዜ የተደገመበትን ርእስ ይዘን ስንነሳ በዝርዝሩ ውስጥ ታሪክ ሰፊውን ቦታ ሊይዝ እንደሚቻል አንባቢው መገመቱ ስህተት ላይ አይጥለውም። የዲጂታሉ ዓለም ይህን ያህል ሁሉም ነገር ከመሆኑ በፊት በፎቶ አማካኝነት የቤተሰብ ታሪክ ተሰንዶ ይቀመጣል። እንግዳ ሲመጣ ብድግ ተደርጎ የሚሰጠው የፎቶ አልበምም ነበር። ዘመነኛ ስቱዲዮዎች ለፍጽምና የደረሰ ፎቶን አዘጋጅተው በአልበም መልክ አድርገው ማቅረባቸው አሁንም ያለ ቢሆንም የቀደመውን ያህል ግን አይሆንም። የቀደሙት ዘመናት ፎቶዎች እውነተኛ መልክን፣ ከባቢ ሁኔታን ወይንም ድባብን የሚያሳዩ ነበሩ። አሁነኛው የፎቶ ክምችት በብዙ አብረቅራቂ ነገሮች የታጀበ ሆኖ እውነተኛው መልክና በፎቶ ወረቀት ላይ ያለው ለየቅል ሆነው የድሮውን እንድንናፍቅ እያደረገንም ይገኛል።
በድሮ የትምህርት ስርዓት ውስጥ ተካተው ከነበሩ ታሪኮች መካከል ስለ ፎቶ የሚናገር ምንባብን እናስታውሳለን። ፎቶ ያለውን ስሜትን የማስቀረት አቅሙን የሚያደንቅ ንባብ ነበር። ለእዚያም ይመስላል የበረከቱ የታሪክ መጽሐፍት ፎቶ ጣልጣል አድርገው ዘገባዎቻቸውን የማቅረብ ልምድ ያካበቱት። የታሪካችን ጥቅል መልክ ግን እንደ ዘመኑ የዲጂታል ፎቶዎች የባለታሪኮቹን ፍጥምና የሚያሳዩ ሆነው ከትምህርት ቤትነታቸው ይልቅ የተወሰኑትን ማምለኪያነት የዋሉ ይምስላል። ታሪክ የማያውቃቸውን ባለታሪኮች እናንሳና እናዝግም።
ታሪክ የማያውቃቸው ባለታሪኮች
“ትውልድ አይደናገር እኛም እንናገር” በተሰኘው መጽሐፋቸው እውቁ የፖለቲካ ሰው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ታሪክ ስለማያውቃቸው ባለታሪኮች ተሟግተዋል። ታሪክ የታሪክ አጻፊዎቹ መሆኑን፤ እነርሱም ድላቸውን ብቻ አስመዝግበው የሚያልፉ መሆናቸውን አንስተው ነገርግን ከጀርባቸው ስላለው የበዛው ሕዝብ የሚለው አለመኖሩ ጸሐፊውን አሳስቧቸዋል። ከአንድ የጦር ውሎ ገድል ጀርባ እንዴት የኩሽናው ሰዎች ገድል ይረሳል፤ እንዴት ለጌታቸው ታማኝ ሆነው ከፊት የተዋደቁት ተራ ወታደሮች ታሪክ ይረሳል፤ እንዴት እያሉ በብዙ እየጠየቁ ጉዞ ቢያደርጉ መድረስ የማይችሉበት ርቀት እንዳለ ሙግቱ ያሳያል።
ታሪክ የማያውቃቸው ባለታሪኮች ዋጋ ዛሬ በምናየው አለም ውስጥ ትልቁን ድርሻ ይይዛል። ታሪክ መሪዎቹን ያውቃል። ታሪክ ጎልተው የወጡት የሠሩትን ገድል በብርቱ ይዟል። ታሪክ መሪዎቹ የሄዱበትን የስህተት መንገድ እንዳላየ አልፎ በፍጽምና ዋዜማ ላይ የሆኑ ሰዎች አድርጎ የመጨረሻው ገጽ ላይ ይደርሳል። ታሪክ የማያውቃቸው ባለታሪኮች ግን እድሜያቸው ጉልበታቸው ሁሉነገራቸው በውዴታም ይሁን በስርዓት ግዴታነት ለተከተሉት መሪ ግብዓት ሆነው ያልፋል።
ግብዓት የሆኑት እንጨቶች ግን አይታወቁም፤ የሚነደው እሳት በእሳትነቱ ትርጉም ይሰጠዋል እንጂ። እሳትነቱም በሰፊው ይዘገባል። እሳቱ ያጠፋው ደን፤ እሳቱ የገደላቸው ብዛት፤ እሳቱ ያደረገው አያሌ ጀብዱ ጎልቶ ይዘከራል። እሳቱን የፈጠሩት እያንዳንዱ እንጨቶች ግን ታሪካቸው በእሳቱም ሆነ በአመዱ ውስጥ የለም። እንዲያው በዝምታ ያለፉ፤ ድምጽየለሽ እንጨቶች ብቻ ይሆናሉ እንጂ።
እውነት ስንነጋገር ይህ ችግር ዛሬም በእያንዳችን ጓዳ የሚገኝ መሆኑን እንረዳለን። ዛሬስ ድካማቸው ያልተቆጠረላቸው በዙሪያችን የሚደክሙ የሉም? ትላልቅ ትልሞች ወደ መዳረሻቸው እንዲደርሱ የምናደርገው ጥረት ውስጥ የተዘነጉ አቅሞች የሉም? ሁሉም በየቤቱ ቢያይ ታሪክ የዘነጋቸውን ታሪክ ሰሪዎችን እናገኛቸዋለን።
እየሱስ ክርስቶስ ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዩሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ በመንግሥተ ሰማያት ግን ከሁሉ የሚያንሰው ይበልጠዋል።›› የሚለው አነጋገሩ በከፍታው ላይ የሚታዩ ግለሰቦች የታሪክ ማህደርን የሚያጨናንቁት በምድር ላይ መሆኑን የሚያስረግጥ ነው። በዚያኛው አለም ሚዛን በአግባቡ የሚመዝንበት በመሆኑ ታሪክ የማያውቃቸው ባለታሪኮች ከፊት መሆናቸው አይቀርምና።
ስለ አገሩ የተዋደቀ ወታደር በሀዘን ወደ መቃብር ሲወርድ፤ መምህሩ እንደ ጠመኔው ሰልሎ የጡረታው በራፍ ላይ ሲደርስ፤ ከገንዘብ ይልቅ ማህበረሰብን አስቀድመው በማህበረሰብ ውስጥ ኑሮቸውን ያደረጉ የህክምና ሰዎች በቅጡ ሳይታዩ ሲቀሩ፤ በአራቱም አቅጣጫ ከገንዘብ ባሻገር ባለ ስሌት አገልጋይነትን አስበው የተሰለፉትን ማየት ሳንችል ስንቀር እንዴት ጤንነታችን የምር ይሆን?
በቀለ ወልደኪዳን “ጣልቃ እየገባ” የተሰኘው መጽሐፋቸውን በሚያስመርቁበት መርሃግብር ላይ የምስጋና ቃላትን ባቀረቡበት ንግግራቸው ወቅት ከተለመደው የአደባባይ የምስጋና ቃላት የተለየውን አሰሙ። ልብሳቸውን በማጠብ፤ ምግባቸውን በማብሰል የምታገለግላቸውን ሴት በአደባባይ አመሰገኑ። ከእርሳቸው ውብ ብእር ውስጥ አስገራሚ ሆኖ ከወጣው “ጣልቃ እየገባ” መጽሐፍ ስኬት ውስጥ ምስጋና የተገባቸው ዝርዝር ውስጥም ተካተተች። ታሪክ የማያውቃቸው ባለታሪኮች ከቤተክህነት እስከ ቤተመንግሥት አሉ። ቀልባቸው ከልባቸው ጋር የሆነ፤ ቀልባቸው ከእያንዳንዱ እርምጃቸው ጋር ያደረ፤ ድካማቸው አንዳች ፍሬ እንዲኖረው አስበው ከሚሰሩ ባለታሪኮች ጀርባ አይጠፉም።
በታሪክ የተበላሸው ዛሬ
መቼስ እንደ ዛሬ ያለ ድንቅ ሃብት መኖሩ ያጠራጥራል። ስለ ነገ ብዙ እናስብ ይሆናል፤ ዛሬ ግን በተጨባጭ በእጃችን የሚገኝ ትልቁ ሃብታችን ነው። ዛሬ ትርጉም እንዲኖረው ማድረግ የሕይወት ስኬት መሰረት ተደርጎ ቢቆጠር ማጋነን አይሆንም። ነገ በተራው ዛሬ ስለሚሆን። ትላንት ግን ያው ትላንት ነው ዛሬ ላይ ለመድረስ በራሱ የማይችል። እኛ ጎትተን ካመጣነው ብቻ ዛሬ ላይ ጥላውን የሚያጠላ፤ በአሉታዊነቱ። ለአዎንታዊ ተግባር ከጠራነው እንዲሁ የሚያገለግል።
በዚህ ወቅት በዓለማችን አራቱም አቅጣጫ ያሉትን ግጭቶች እንመልከት። ምልከታችንን አጥብበን ወደራሳችን በማዞርም መሆን አለበት። ወደ ኋላ ዓመታትን ሄደን ምልከታችንን በዓመታት ውስጥ ደግሞ እናስፋ። አንድ ነገር ላይ እንደርሳለን። በታሪክ የተበላሹ ቀናትን፣ በታሪክ ውስጥ አልፈን ሌላ የተሻለ ታሪክ ከመስራት መዘግየታችንን የሚያሳዩ እንመለከታለን። ዛሬም እንዲሁ!
በታሪክ የተበላሹ ዛሬዎች ሲብላሉ ቆይተው በስተመጨረሻ አንገት የሚያስደፋ እልቂት ውስጥ ሲጨምሩን በታሪካችን መዛግብት ውስጥ ይገኛል። ዛሬም እንዲያው ነው። መፍትሄው በዛሬ ትርጉም ውስጥ ብቻ የሚገኝ መሆኑን አንዘንጋ፤ አዎን በዛሬ የታከመ ትርጉም ውስጥ። የቻይናው ቀርክሃ ምሳሌነቱ በብዙ ጉዳዮች ላይ ይነሳል። እዚህ ጋር በታሪክ ስለተበላሸው ዛሬ እናንሳው። ይህ ልዩ የሆነው ቀርክሃ ከሌሎች ዛፎች የሚለይበት ባህሪው የዛፉ የዛሬ ትርጉም ከሌሎች የተለየ መሆኑ ነው። ሌሎች ዛፎች በእያንዳንዱ ጊዜ ውስጥ እድገታቸው በሚገባ የሚስተዋል ነው። በየወቅቱ እያደጉ ይታያሉ። በየወቅቱ በቁመት እየጨመሩ ይታያል። በዝግታ ውስጥ ሊሆን ስለሚገባ እድገት አስተማሪዎችም ሆነው ይቀርባሉ።
ልዩው ቀርክሃ ግን እንደዚያ አይደለም። ለአምስት አመታት ይኑር አይኑር የማይታወቅ ውስጥ ለውስጥ የሚኖር። በየጊዜው ውሃ በማጠጣት የሚጠብቀው ካገኘ ግን በአምስተኛው ዓመት በመጀመሪያዎች ስድስት ወራት ውስጥ የመቶ ሜትር ሩጫ ይመስል ተመዘግዝጎ የሚወጣ ነው። በእያንዳንዱ ቀን እየተመዘዘ ይሄዳል። በቀን እስከ 39 ኢንች ድረስ ያድጋል። ውስጥ ለውስጥ የተብላላው የአምስት ዓመት ታሪክ በስተመጨረሻ ይዞት የሚመጣው ታላቅ የምስራች ነውም። ይህ ቀርክሃ ጎጂ ቢሆንስ ብለን እናስብ። ትላንት እየጠጣ የመጣው አድፍጦ የቆየው የውስጥ የጥላቻ እድገት በስተመጨረሻ የሚደረስበት ጥፋት ምን ሊመስል እንደሚችል መረዳት ቀላል ይሆናል።
በታሪክ የተበላሸው ብልሽት ዛሬ በጊዜ ሂደት ውስጥ ውድመት ሲሆን አይተናል። ከቁጥጥር ውጭ የወጣ ጥፋትን ሲያስከትልም እንዲሁ። የደም ጎርፉ መስፈሪያ እስኪታጣለት ድረስ። ዛሬ የተጀመረው ነገ ሲያልቅ የዛሬው ጅምር ላይ ተመስርቶ መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ሊሆን እንደሚገባው በሚገባ የሚያስረዳ። ዛሬም እየሆነ ያለው ይህ ነው። መንገድ ስተናል። በታሪክ የተበላሸው ዛሬ ታሪክ መስሪያ ጊዜያችንን አባክኖታል።
በታሪክ የሚሰራ ታሪክ
ወቅታዊው የኢትዮጵያ መሰንበቻ ደሴን የትኩረት ማዕከል አድርጓታል። ደሴን በደሴነቷ መልክ ያላት ትሆን ዘንድ ከደከሙት መካከል ከታሪክ ማህደር ማስታወሻ ስንፈልግ አጼ ዮሐንስን እናገኛቸዋለን። “ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት ስለእርሳቸው በጥናታቸው ጽፈዋል ብሎ አዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስነበበው ደሴ፣ ደብረታቦር፣ ጎንደር እንዲሁም አድዋ ከአጼ ዮሐንስ አንጻር በተገለጹበት ጽሑፍ ውስጥ አልሚነት የሚታይበት ነው። ዛሬ በገባንበት የጎራ አሰላለፍ ግን በተቃራኒው መንገድ ውስጥ እንገኛለን። ያለፈውን ታሪክ ዛሬ ላይ ሌላ ታሪክ መሥራት በሚያስችል ሁኔታ እንጠቀምበት ቢባል አስተዋይነት የጎደለው ሆኖም የሚታይ ይመስላል።
በሌላው ገጽ ግን ታሪክን ለመገዳደያነት እንጠቀም ቢባል ልንመዝ የምንችለው ብዙ አለን፤ እስከአሁን እየተጠቀምንበት ስለሆነ። ታሪክ የትላንት ድርሳን መሆኑን እያወቅን። ታሪክ የተዘጋ ምዕራፍ ሆኖ ሳለ ጎትተን ዛሬ ውስጥ በማይጠቅም ሁኔታ ስንጨምረው በታሪክ የሚሰራ በጎ ታሪክን ከመፈለግ ይልቅ በተቃራኒው እየተራመድን እንገኛለን።
አጼ ዮሐንስ በተደጋጋሚ ግብጽን ድል በማድረግ የተጻፈላቸው ታሪክ የሚነግረንን አንስተን የዛሬዋን ኢትዮጵያ ሁናቴ ስናጤን ስብራታችን መጠኑ የጠለቀ እንደሆነ እንረዳለን። በታሪክ የሚሰራውን ታሪክ ፍለጋ ምሁራኖቻችን የሄዱበትን ርቀት ቆመን መጠየቅ ያለብን ወቅት ላይ እንደምንገኝ አጠያያቂ አይደለም። ከእዚህ በላይ ጥፋት እንዴት ልንሸከም እንችላለን? እንዴትስ ሞት በመካከላችን ነገሰ ልንባባልም ይገባል? በመካከላችን የተዘራው አረም እንዴትስ የጠለቀበት ጥልቀት ይህን ያህል እረዘመ ማለት አለብን?
የሦስት ሺህ ዓመታት ታሪክ አገር በታሪክ ውስጥ አልፈን የተሻለውን ዛሬን ከመገንባት እንዴት ባለበሌለ መሳሪያችን እንጠፋፋለን? ዛሬ ኢትዮጵያ አዲስ የታሪክ መስመርን ፈልጋ ማግኘት ያለባት ወሳኝ ወቅት ላይ ትገኛለች። የማህበረሰባዊ ተቋሞቻችን፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች ልምዳችንን እንዴት ገፈን አብረን ሕይወትን መፈለግ እንዳለብን ሊያነሱ ይገባል። በታሪክ ውስጥ አልፈን ታሪክ ከመሥራት ውጭ አማራጭ እንደሌለንም ሊያስገነዝቡን። ታሪካችን ውስጥ የበዛ ለዛሬ ሊመነዘር የሚችል አቅም አለ። ታሪካችን እንደ ትምህርትቤት ስርዓት አበጅተንለት በሕይወት ወደ መጠቀም መስመር ለመመጣት መፍጠን አለብን።
አሁንም አንድ የታሪክ ገጽ ለመምዘዝ ወደ ሰኔ 14፣ 1973 ዓ.ም እንሂድ። በብዙ አሉታዊ ውሳኔዎቹ መጽሐፍቶቻችን በሚጠሩት በደርጉ የስርዓት ዘመን የሆነውን ለመመልከት። አፄ ዮሐንስ ከደርቡሽ ጋር በተዋጉበት ስፍራ ደርግ ለአጼ ዮሐንስ መታሰቢያ አቁሟል። ይህ ሲታሰብ ደግሞ በታሪክ ስለሚሠራ ታሪክ አብረን እንድናስብ እንሆናለን። ይህንን እያሰብንም በካፍቴሪያው ውስጥ ስለተነሳው ጸብ እንመልከት።
የካፍቴሪያው ጸብ
የዚህ ጽሁፍ መንደርደሪያ ያደረግነው የምናብ ካፍቴሪያ ውስጥ ጸብ ነው። ጡረተኛው ባለቤትም ከጽሑፍ ሥራቸው ወጥተው ብቅ አሉ። ስለ ፖለቲካ ሲጨቃጨቁ የነበሩት ወጣቶች ግብግብ ጀምረዋል። ሽማግሌውም በመነጽራቸው ውስጥ አሻግረው የሚሆነውን ተመልክተው ተገረሙ። ካፍቴሪያው በአንድ እግሩ ቆሟል። ሁሉም ሰው ተረብሿል። ቦታ ቦታቸውን ይዘው በጉዳያቸው መስመር ይተሙ የነበሩት ደንበኞችም ትኩረታቸው ተወስዷል። ሰላም ሲጠፋ ሁሉም መረበሹ እውን ነውና። ጡረተኛው ሊያገላግሉት የሚችሉት አይነት ስላልነበር ጥጉን ይዘው ለማገላገል የሚሞክሩት ይሳካላቸው እንደሆን ያያሉ።
ማኪያቶ ካዘዘው እስከ ባሬስታውም፣ ካሸሯና ታሪክ ጸሐፊው ድረስ ሁሉም ተረብሿል። የገላጋይ ያለህ የሚል ጸብ! በዚህ መሐል አስደንጋጭ ነገር ሆነ። የጸቡ ሂደት በከፍተኛ ኡኡታ ተዋጠ፤ አንዱ ሰው ጩቤውን አወጣ… ቤቱ ውስጥ ጩኸት በረከት። ጫጫታው በዛ። ጡረተኛው ያለ የሌለ ኃይላቸውን ተጠቅመው እርሳቸውም ወደ መገላገሉ ለመግባት ወሰኑ። … አሳዛኝ ቅጽበት … አዛውንቱ የጩቤው ሰለባ ሆኑ… የጨመረ ኡኡታ … ኡኡ … ኡኡ … የተጻፈው ሳይታተም ጡረተኛው አንቀላፉ። በታሪክ አዎንታዊ ታሪክ መሥራት በሚከብድበት ውይይት ውስጥ ሊሆን የሚችለው የነባራዊው ሕይወታችን ማሳያው ይህ ነው።
የካፍቴሪያው ደንበኞች አንገታቸውን ደፉ። ይህን አንገት የመድፋት ገጠመኝ ወደ አገራችን እናምጣው። በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ አልፈን የእምቅ አቅም ባለቤት የሆነችው አህጉር አንገት የደፋችበትን ዓመታትም እንመርምር። ጉዟችን ከየት ወዴት እንደሆነ እየመረመርን ከታሪክ መዝገብ ውስጥ ፈልገን ያጣነውን እንቁ እንፈልግ።
የመፍትሄው መንገድ ውስጥ ፍጽምናን እንመርምር። በፍጽምና ውስጥ ራሱን የሚገልጽ አንድም ሰው ካለ ራሱን ይመርምር። እያንዳንዳችን ውስጥ ድካም አለ። እያንዳንዳችን ውስጥ ጥንካሬም አለ። የዛሬ እኛነታችን በብርታትም ሆነ በጥንካሬ የሚገለጽ ከሆነ ትላንትም እንዲያ እንደሆነ እናስብ። የመፍትሄው መንገድ ለራሳችን ከሰጠነው የፍጽምና ካባ ማውለቅ መሆኑን እንረዳ። ካባውን አውልቀን እንደ ግለሰብ፣ እንደ ቤተሰብ፣ እንደ ማህበረሰብ፣ እንደ አገር የሆነውን ስንሆን ከቀልባችን ጋር እርቅ ማውረጃው ዋዜማ ላይ እንደርሳለን። ኃላፊነቱ የማን ነው? ለሚለው ጥያቄ ምላሹ የሁሉም የሚለው ነው። አገር የእኔም ናት ከሚለው ሁሉ ዘንድ ኃላፊነት አለ። ካፍቴሪያው ይዘጋ አይዘጋ የሚለውን ክርክር በትክክለኛው አቅጣጫ በመምራት የሚጀመር ኃላፊነት።
ካፍቴሪያው አይዘጋም!
የምናባችን ታሪክ ወደ ሌላ ገጽ ይውሰደንና ወደ ማጠቃለያችን ያመጣናል። ልጆች አባታቸውን ቀብረው በካፌው እጣፈንታ ላይ እየመከሩ ነው። ገሚሶቹ ይዘጋ ይላሉ፤ “አባታችንን ባሰብን ቁጥር ክፉውን የሚያስታውሰን ነውና ካፌው ይዘጋ እቃውም ይሸጥ” ይላሉ። ሌሎች ደግሞ “የለም ካፌው ይኑር የአባታችን መታሰቢያ አድርገን ለሌሎች ትምህርት የሚሰጥ ይሁን” ይላሉ። ትላንትን ለመሸሽ መሞከር ካፌው ይዘጋ ሲያስብል፤ ትላንትን ለዛሬ በሚበጅ መንገድ መጠቀም አለብን ያሉቱ ደግሞ ካፌው ይኑር ይላሉ። የመሰነባበቻችን ቁልፍ ነጥብም ከአዛውንቱ ልጆች የእርስበርስ ሙግት ውስጥ ይታያል።
እኛ ኢትዮጵያውያን በክፋቱም ሆነ በልማቱ ከሌሎች አገራት የምንለይ አይደለንም። በእኛው ትላንት ውስጥ ልማትም ጥፋትም ሆኗል። ዛሬ የትም እንዳለ በእኛም መካከል አለ። መውጫው መንገድ ትላንትን መመልከት በቻልንበት መነጽር ውስጥ መሆኑን መካድ አንችልም። ውስጥ ለውስጥ ስንፈትለው የኖርነው የትላንት ድር ዛሬ ላይ ወደ መጠላለፍ ወስዶን በደም በጨቀየ መንገድ ውስጥ እንገኛለን።
“ካፍቴሪው ይዘጋና አይዘጋ” የሚለው ጥያቄ መልሱን መፈለግ የግድ መሆኑን አንባቢው ይረዳ። ትላንትን እየሸሸን እንደ አዲስ ቁርሾን ዘርተን እያጨድን እንቀጥል ወይንስ ታሪካችንን ስለ ተሻለ ታሪክ እንጠቀምበት? ምርጫው በእጃችን አለ። ምርጫችንን ከምድር አድርገን ማሳለፍ እንድንችል ወደ ካፌው ተመልሰን ቦታችንን ይዘን እንምከር። ማኪያቶም፣ ቡናም፣ ወተትም ሆነ ሻይ እንዲሁም ለስላሳ እንደምርጫችን አዘን ቁጭ ብለን እንምከር። ዳግም ጸብ ውስጥ ከሚከት ደመሞቃትነት ወጥተን በተረጋጋ መንገድ እንምከር። የውድቀታችንን ልክ እየመረመርን እየመጡ ያሉትን ብዙ ዛሬዎች ውበት እንስጣቸው።
በታሪክ የሚሰራን ታሪክ ፍለጋ በበጎነት መስመር በዘለቅን ቁጥር እጃችን ፍሬ ይዞ መመለሱ አይቀርም። ፍሬው ለሁላችንም ፍሬ ያለው ይሆን ዘንድ ለጊዜው የካፍቴሪያው ጠረጴዞች ሁሉ በአንድ ጉዳይ ላይ ይምከሩ። ንግዱም ሆነ እርሻው፤ ትዳሩም ሆነ የተጣላውን ማስታረቁ መቀመጫ ሲኖር ነውና መቀመጫ አሳጥቶ ሁሉንም ወደ ምሽጉ ያባረረውን ጉዳይ እንምከርበት። ለማንም ብለን ሳይሆን ስለራሳችን ብለን። ቤተክህነቱም ሆነ ቤተመንግሥቱ፤ የአገር ሽማግሌውም ሆነ የወጣት ስብስቡ አብረው ይምከሩ። ካፍቴሪያውን ዘግቶ ከትላንት ከመማር ከመጉደል በትላንት የተከፈለ ዋጋ የንጹሃን ሞትና እንግልት ላይ እየመጡ ያሉ ነገዎች የሰላም ይሁኑ።
ለማንበብም ሆነ ለመጻፍ፣ ለማውራትም ሆነ ለማድመጥ መገናኛ የሆነውን ቤት ወደ ስራ እንመልሰው። ለእከሌ የሚተው ያልሆነ፤ የሁሉም የሆነ። በታሪክ የሚሰራ ታሪክን ፍለጋ። ከህጻን እስከ አዋቂ፣ ከመሃል አገር እስከ ዳርድንበር፣ ከአገር እስከ ባህርማዶ፣ … እናንተ የአገሬ ልጆች በታሪክ የሚሰራ ታሪክን እንፈልግ ዘንድ ጊዜው አሁን ነው! ብሩህ ቀናትን በቅንነት የሚሹ ልቦች ተያይዘው የቆሰለውን ያክሙ፣ የተዘጋውን ይክፈቱ፣ ስለ ነገ መንገዱን ይቀይሱ። በታሪክ የሚሰራ ታሪክ ከደጃችን!
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 27/2014