በፍቅር ኢትዮጵያ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ማህበር ቅጥር ግቢ ውስጥ ልጇን አዝላ በትካዜ የቆመች ሴት ተመለከትኩኝ። በወቅቱ ከማህበሩ ህዝብ ግንኙነት ወይዘሮ የሸዋጌጥ ክብረት ጋር ስለ ማህበሩ ሁኔታ ለመመካከር ነበርና ወደዚያ የሄድኩት የዚህች ሴት አኳኋን ላሰበኩት ጉዳይ ማጥበቂያ ሊሆነኝ እንደሚችል በማሰብ ይህችን የተከፋች እናት ብሶት ለማዳመጥ አጠገቧ ጠጋ አልኩ።
ወይዘሮ አስቴር ጌታነህ ዕድሜዋ በሃያዎቹ መጨረሻ የምትገኝ ሲሆን፤ ከተወለደችበት ከሰሜን ሸዋ አካባቢ ሠርቶ ለማደግ አስባ ነበር ከዓመታት በፊት የወጣችው። አዲስ አበባም እንደደረሰች የሰው ቤት ሠራተኛ በመሆን ለዓመታት ሠርታለች። በሥራ አጋጣሚ ካገኘችው ሰው ጋር ትዳር መሰርታ ኑሯቸውን ከጀመሩ በኋላ የእናትነት ፀጋን ታድላለች። ነገር ግን የወለደቻት ልጅ የአዕምሮ እድገት ውሰንነት ያለባት ሆነች።
በወሊድ ጊዜ ባጋጠማት መታፈን የተነሳ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያላት ልጅ መውለዷን የተነገራት ሲሆን፤ ልጇ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ብቻ ሳይሆን የእንቅስቃሴ ችግርና በእይታዋም ላይ የተወሰነ እክል መኖሩም ጨምሮ ተነገራት። በወቅቱ እንደማንኛዋም እናት ወልዳ የመሳም ጉጉቷ እቅፏ ወስጥ ባለችው የታመመች ልጅ የተነሳ በኀዘን ቢተካም ልጇን ማዳን ተቀዳሚ አጀንዳዋ በማደረግ ጥረት ጀመረች።
አንዴ በህክምና፤ ሌላ ጊዜ በእምነት ቦታ እየተዘዋወረች የበኩር ልጇን ለማዳን ደፋ ቀና የምትለው ይች እናት ባላሰበችው ወቅት ሁለተኛው እርግዝና ይከሰታል። ያኔ ነው እንግዲህ የፈተናው መጀመሪያ በሩን ወለል አድርጎ የከፈተው።
የሁለተኛ ልጇ እርግዘና ጉዳይ እንደተሰማ የባለቤቷ ቤተሰቦች ጤነኛ ልጅ ከማትወለድ ሴት ጋር አብረህ እየኖረክ በማለት ባለቤቷ ጥሏት እንዲሄድ ያደርጉታል። ወትሮም በቋፍ የነበረው ትዳር ደጋፊ ገፋፊ ሲያገኝ ፈረሰ። ባለቤቷ ጥሏት እንደሄደ መኖሪያ አጥታ ስትንከራተት ያገኘቻት ለነፍሷ ያደረች ሴት በለገጣፎ አካባቢ አንድ ክፍል ቤት ሰጥታት ልብስ በማጠብ የዕለት ጉርሷን ለማግኘት መታተር ጀመረች።
ሁለት ሕፃናት ሊያውም ያለረዳት አብልቶ አጠጥቶ አልብሶ ማኖር የህልም ያህል እየራቃት የምትኖረው ወይዘሮ አስቴር፤ በአቅራቢያዋ ባለ አንድ የመንግሥት ትምህርት ቤት የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያላትን ልጇን ጠዋት ወስዳ አስቀምጣ ማታ በመውሰድ እንደ ሁሉም ልጅ እንድትማርላት ጥረት ብታደርግም መምህራኖቹ ልጇን የምታስተምርበት ሌላ ቦታ እንድትፈልግ ከመንገር በስተቀር ይህ ችግር የጋራችን ነው ብለው ሊረዷት እንዳልፈለጉ ትናገራለች።
ወደ ማህበሩም የመጣችሁ በአቅራቢዋ የትምህርት ዕድል ሊጣት የሚችል ሰው እንዲፈለጉላት መሆኑን የምትናገረው ወይዘሮ አስቴር፤ ተፈጥሮ የሰጠቻትን ሰጦታ በችግር ምክንያት እንደ መርገምቷ እንዳትቆጥራት ዕርዳታ እንደምተሻ ትናገራለች። በማህበሩ መመላስ ከጀመረች ሁለት ዓመታትን ማስቆጠሯን የምትናገረው ወይዘሮዋ፤ መጠነኛ ድጋፍ ብታገኝም አሁን ካለችበት ችግር አንፃር በቂ አለመሆኑን ታስረዳለች።
የፍቅር ኢትየዽያ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያላቸው ብሄራዊ ማህበር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወይዘሮ የሸዋጌጥ ክብረት እንደሚሉት፤ ማህበሩ በ1987 ዓ.ም የተመሰረተ ሲሆን፤ ትምህርት ሳያገኙ በተለያዩ ምክንያቶች ቤት ውስጥ የቆዩ ወጣቶች እና አዋቂዎች እራስን የማወቅ የማስተዳደርና የተለዩ ክህሎቶችን የሚያስጨብጡ ስልጠናዎችን ይሰጣል።
ከዚህም በተጨማሪ ህብረተሰብ የአዕምሮ እድገት ወስንነት ምን እንደሆነ አውቆና ተረድቶ ለእነዚህ የህብረተሰብ ክፍሎች የበኩላቸውን እንዲያደረጉ እንደሚሠራ ያስረዳሉ። ወይዘሮ የሸዋጌጥ እንደሚሉት፤ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለበት ልጅ ማለት አንድ ልጅ ያለው ትምህርት የመቀበልና የማስታወስ አቅም፣ የማገናዘብ ፣ ውሳኔ የመወሰን ፣ ችግር የመፍታት ፣ ከሌሎች ጋር ያለው የመግባባት እና ራስን የመርዳት ክህሎት ከዕድሜው ከሚጠበቀው በታች ሲሆን ነው። አንድ ሰው ጤናማ የሆነ የአዕምሮ አቅም አለው የሚባለው የማገናዝብ፣ ነገሮችን የመረዳትና የማስታወስ አቅም IQ=100 ሲሆን የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለባቸው ደግሞ IQ ከ 70 በታች ሲሆን ነው።
እነዚህ ልጆች ከተወለዱ በኋላ የተለመደውን እድገት ደረጃ ጠብቀው መገለባበጥ፣ መቀመጥ፣ መዳህ፣ መሄድ፣ ፖፖ መጠቀም እና መናገር መጀመር ባለባቸው ዕድሜ ካለመጀመራቸውም ባሻገር፤ ነገሮችን የማስታወስ አቅማቸው ዝቅተኛ ሲሆን ፤ የባህሪ ችግር ሲኖር፤ በየዕለቱ የሚያዩት የህይወት እንቅስቃሴ የመረዳት እና የመተግበር ውስንነት ሲኖር ከዚህ ችግር ጋር እንደተወለዱ ለማወቅ ይቻላል። በህክምና ሙሉ በሙሉ መንስኤው ይህ ነው ለማለት ቢከብድም አብዛኛዎቹ እንደ መንስኤ የሚታዩት ብለው ካስቀመጧቸው ውስጥ በዘር ሊከሰት መቻሉ፤ በፅንስ ወቅት እናት አልኮል እና በፅንስ ወቅት ሊወሰዱ የማይገባቸው መድሃኒቶች መውሰድ፣ የምግብ እጥረት እና የተለያዩ ህመሞች በእናት ላይ ከነበሩ፤ በወሊድ ወቅት የኦክስጂን እጥረት መከሰት እና ሊወለድ ከሚገባ ጊዜ ቀድሞ መወለድ፤ ልጅ ከተወለደ በኋላ በመውደቅ ወይም በግጭት የአዕምሮ ጉዳት ሲያጋጥም ፤ ከፍተኛ የሆነ የምግብ እጥረት፣ ሜኒንጃይተስ በተባለ ህመም መጠቃት፣ አዕምሮን ሊጎዱ በሚችሉ ኢንፌክሽኖች መያዝ እና ለጎጅ ንጥረ ነገሮች ተጋላጭነት ሊከሰት ይችላል።
የአዕምሮ እድገት ውስነት እንዳይከሰት በእርግዝና ወቅት አስፈላጊውን የህክምና ክትትል ፣ ምርመራ እና የባለሞያ ምክር በማግኘት ማለትም በእርግዝና ወቅት ምንም ዓይነት የአልኮል መጠጥ እናቶች ባለመውሰድ፣ ተገቢውን ክትባት መውሰድ፣ ተጨማሪ በሀኪም የሚታዘዙ ቫይታሚኖችን በመውሰድ እና ልጆች ከተወለዱ በኋላ ለግጭት እና ጉዳት እንዳይጋለጡ በመጠበቅ ችግሩን መከላከል ይቻላል የሚለውን ነገር ማስተማር የማህበሩ ዋና ዓላማ ነው።
ሌላው እንደነዚህ ዓይነት ሕፃናት ገና በትንሽ ዕድሜያቸው ሲገኙ ከመንግሥት ጋር በመሆን ትምህርት ቤት እንዲገቡ ማድረግ በተለያዩ አከባቢዎች የልዩ ፍላጎት ክፍሎችን በማስከፈት ልጆቹ በትምህርትም ተጠቃሚ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ ይሠራል። ሦስተኛው ልጆቹ በቤት ውስጥ ተዘግተው ቆይተው፤ ወይንም በሌሎች በተለያዩ ምክንያቶች የተነሳ ሳይማሩ ዕድሜያቸው የገፉ ልጆችን በተለይም ከ18 ዓመት በላይ ለሆኑት የተለያዩ የከህሎት ማለትም ገቢያ ወጥቶ የመገበያየት፤ ራስ የማስተዳደር ክህሎት፤ የተለያዩ የእጅ ሙያዎችን ሠርቶ የመሸጥና ሎሎች ከህሎቶችን መስተማር ነው።
አራተኛው ወላጆች ላይ መሥራት ነው። እንደነዚህ ዓይነት ችግር ያላቸው ልጆች በመውለዳቸው ከ85 በመቶ በላይ ተጎጂዎቹ ሴቶች ናቸው የሚሉት ወይዘሮ የሸዋጌጥ፤ ለዚህም ከላይ ያየናት እናት ማሳያ ናት ይላሉ። እንደዚህ ዓይነት ልጅ ሲወለድ ቤተሰብ ይፈረሳል፤ ብዙ ጊዜ ልጆቹን ይዘው የሚቀሩት ሴቶች ናቸው፤ እነዚህ ሴቶቸ ደግሞ ልጅ ስለሆነ ማዳን ላይ ትኩረት አድርገው በየፀበሉ፤ በየ ባአድ አምልኮው መዳኛ ያሉት መንገድ ላይ ሲንከራተቱ የመማርም ሆነ የመሥራት ዕድሜያቸው አልፎ በችግር ላይ የሚያልፉ ማረፊያ የሌላቸው ሴቶችን የስነ ልቦና ደጋፍ፤ የአቅም ማጎልበት ሥራ ማለትም በኢኮኖሚና የመሳሰሉትን ሥራዎቸ ይሠራሉ።
ሌላው በዚህ ችግር ውስጥ ያሉ ልጆች ጉዳታቸው ድርብርብ በመሆኑ የተነሳ በተለይም የእንቅስቃሴ ችግር ያላቸውን ልጆች በፊዚዮቴራፒ የተሻለ መሻሻል እንዲኖራቸው፤ እንደልባቸው እንዲንቀሳቀሱ የማድረግ ሥራን ለመሥራት የሚያስችል የመታሻ አገልግሎት በማህበሩ ይሰጣል። በየትምህርት ቤቱ የፊዚዮቴራፒና የንግግር ቴራፒ አገልግሎት መሰጠቱም ልጆቹ በንግግርም ሆነ በእንቅስቃሴ የተሻሉ እንዲሆኑ እንደሚረዳቸው ይጠቁማሉ።
ሌላው የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያላቸው ልጆች የመረጃ አጥረት አላቸው። ልጆቹ በሚገባቸው በሚያውቁት ቋንቋ በተገቢው መልኩ መረጃ እንዲያገኙ የማድረግ ሥራ በማህበሩ ይሠራል። የስነ ተዋልዶ ጤና፤ ኤች አይቪ ፤አሁን ደግሞ ኮሮና እንዴት መከላከል እንዳለባቸው ከመሳወቅም በላይ ራሳቸውን እንዴት መከላከል እንደሚኖርባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን በሚገባቸው ቋንቋ እንዲረዱ ያደርጋል።
ማህበሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ እንቅስቃሴ የሚያደርግ እንደመሆኑ ከእናቶች ጋር በሚሠራው ሥራ የእነዚህን ልጆች ቤተሰቦች ተጠቃሚ ማደረግ ተችሏል። አዲስ አበባና የተለያዩ ክልሎች የቁጠባ ማህበር በማደራጀት ልጆቻቸውን ይዘው የሚሠሩበት ሁኔታ ይፈጠራል። በአዲስ አበባ ከአካል ጉዳተኛ ሴቶች ጋር በመሆን የመንግሥት መፀዳጃ ቤቶች ላይ ሥራ እንዲሠሩ በማድረግ የሥራ ዕድል ፈጠራ ለሠላሳ እናቶች እንዲመቻች ተደርጓል።
በአጠቃላይ በልጆቻቸው እድገት ውስንነት እናቶች ተጎጂ ሰለሆኑ በስነ ልቦናና በኢኮኖሚም ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ፤ ልጆቹም ወላጆቻቸው ሳይኖሩ ራሳቸውን ማስተዳደር የሚችሉ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ ይሠራል። ምንም እንኳን የማህበሩ አቅም ውስን ከመሆኑና ከችግሩ ስፋት አንፃር በቂ ድጋፍ እየተደረገ ባለመሆኑ በተናጥል ድጋፉ አናሳ እንዲሆን አድርጎታል። ማህበረሰቡ ጉዳዩን ጉዳዬ ማለት ከጀመረ ለአንድ ሰው ሸከም የሆነው የኑሮ ጫና የማይቀልበት ምክንያት አይኖርም።
መከራ በየቤቱ ሞልቶ ደጅ አስኪደፋ ከመጠበቅ ሁሉም የአቅሙን በመተባበር የአዕምሮ እድገት ወስንነት ያላቸው ልጆች የላቸውን እናቶች ሸክም ለማቃለል የአቅማችንን በማገዝ ማህበራዊ ግዴታችንን እንወጣ መልዕክታችን ነው።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ነሐሴ 9/2013